እንደ አንድ ሀገር ወዳድ ወጣት ለሁላችንም የሚጠቅምና የሚበጅ አንድ ሀገራዊ መፈክር ይዤ መጥቻለሁ። ‹ከጦርነት በፊት ሰላም› የሚል መፈክር። ዓለም በብዙ አይነት አስተሳሰብ ውስጥ ናት። እንደ ሰላም ባሉ ጽንሰ ሀሳቦች ላይ ግን አንድ አይነት አቋም ነው ያላት።
ከትላንት እስከዛሬ በሰላም ጉዳይ ላይ የዓለም አቋም ተቀይሮ አያውቅም። ሰላም በመነጋገር፣ በመመካከር እንዲሁም ደግሞ በውይይት የሚመጣ ነገር እንደሆነ የጋራ አቋም አላት። እንደ መልክና ቁመታችን፣ እንደ ውፍረትና ቅጥነታችን የተለያየ ሀሳቦችን የምናራምድ ነን። እኚህ ሁሉ ሀሳቦቻችን ከሌላው ሀሳብ ጋር የሚታረቁት ደግሞ በምክክርና በውይይት ብቻ ነው።
እንደ ፖለቲከኛ ስናየው ደግሞ ይሄ የሀሳብ ልዩነት ገኖ ሲወጣ እናየዋለን። ገኖ መውጣቱ ብቻ ሳይሆን በሀገርና ሕዝብ ላይ የራሱን ጫና የሚፈጥርም ነው። ሰው እንደ ተፈጥሮው ልዩ ሀሳብ እንዳለው ከተረዳን ሀሳቡን ለማክበር አንቸገርም። ችግር የሆነብን ግን የኔ ሀሳብ ካልሆነ፣ እኔ ያልኩት ካልሆነ የሚለው እኔነትንና ራስ ወዳድነትን የተሸከመ፣ የሌሎችን ሀሳብ ያላማከለ ሀሳባችን ነው። በዚህም ምክንያት ብዙ ጊዜ ሀሳቦቻችንን ማሸነፍ አቅቶን፣ ለእርቅና ለተግባባቶ ጊዜ አጥተን ብዙ ነገር ሆነናል።
ከጦርነት በፊት ሰላም የሚለው መፈክሬ ዘመኑን የዋጀ ሁላችንም የምናምንበት አዲስ አስተሳሰብ ነው። ጥቂት ስልጡን ሀገራት እየተራመዱበት ያለው እሳቤ ስለመሆኑ አልጠራጠርም። ከጦርነት በፊት ሰላምና ከጦርነት በኋላ ሰላም የተለያዩ ናቸው። እስከዛሬ ከጦርነት በኋላ ሰላምን ስንፈልግ፣ አንድነትን ስንመኝ ኖረናል አሁን ግን ሰላማችንንም ሆነ አንድነታችንን ከጦርነት በፊት መጀመር አለብን።
ከጦርነት በፊት የተጀመረ ሰላምና አንድነት፣ እርቅና ምክክር ሀገርን ያስቀደመ፣ ልማትና ብልጽግናን የተቀበለ ሁሉን ያቀፈ በጎ አስተሳሰብ ነው። ከጦርነት በፊት የተጀመረ ፍቅርና ይቅርታ በማሸነፍ የታጀበ፣ ለሀገር ክብር፣ ለወገን ደጀን የሆነ ነው። ከጦርነት በኋላ ሰላም ግን ከዚህ በተቃራኒ ብዙ ነገራችንን ካሳጣንና ከነጠቀን በኋላ የሚሆን ነው።
እስኪ አስቡት የሰሜኑ ጦርነት በፍቅርና በወንድማማችነት ቀርቶ ቢሆን ኖሮ፣ በመከራ ያለፉት እነዛ ሁለት የጦርነት አመታት በእርቅና በምክክር፣ በውይይትና በስምምነት አልፈው ቢሆን? እስኪ አስቡት እነዛ ሁሉ ሞትና የአካል ጉዳቶች፣ መፈናቅሎችና ጉስቁልናዎች በወንድማማችነት ተሸንፈው ቢሆን? ትርፋችንን..ክብራችንን.አስባችሁታል? ከጦርነት በፊት ሰላም ማለት። ከጦርነት በፊት ፍቅርና ይቅርታ፣ አንድነትና ወንድማማችነት ያልኳችሁ ይሄንን ነው።
እንደ ሀገር እንደ ዜጋ ከምንም በላይ ደግሞ እንደ ፖለቲከኛ ሳንሞትና ሳንጎሳቆል ተነጋግሮ መግባባትን መለማመድ አለብን። በውይይት፣ በንግግር እንዴት ሰላም እንደሚመጣ መማር ይኖርብናል። ትንንሽ ነገሮች ዋጋ ሲያስከፍሉን ሳይ ይከፋኛል። ለኢትዮጵያዊነት የማይመጥን ምናምንቴ ሀሳቦች ለመለያየት ሲዳርጉን ሆድ ይብሰኛል።
ባጣነው ልክ ለማግኘት፣ በከሰርነው ልክ ለማትረፍ ከጦርነት በፊት ወዳለው መንፈስ መመለስ ይኖርብናል። በሰላምና ተግባቦት፣ በእርቅና ምክክር፣ በውይይትና ስምምነት ሀገራችንን ካልታደግናት በምንም አንታደጋትም። ያለፍንበት መንገድ ሊያስተምረን ይገባል። ምን አጥተን ምን እንዳለን፣ ምን ጎሎን ምን እንደሞላን እናስተውል። ተነጋግሮ ከመግባባት፣ ተግባብቶ ሰላም ከመፍጠር በቀር ሁሉም ያለን ሕዝቦች ነን።
እኚህ ብዙ ነገሮች እንዲጠቀሙንና ዋጋ እንዲያወጡልን በሰላምና በፍቅር፣ በአንድነትና በመተቃቀፍ ሊከበቡ ይገባል። ዛሬ ላይ ትንሽ ያላቸው ሀገራት እየበለጡን ነው። እኛ ያለን የሌላቸው፣ ከእኛ በብዙ ያነሰ ነገር ያላቸው ሀገራት እየቀደሙን ነው..ለምን ካልን እነሱ በሰላምና በመነጋገር ጥቂቱን ነገር አብዝተውታል። እኛ በሰላም እጦት፣ ተነጋግሮ ባለመግባባት ብዙውን ነገራችንን ዋጋ አሳጥተነዋል። ልዩነታችን ይሄ ነው..ሰላም በሌለበት ሁኔታ ውስጥ የሚጠቅም ምንም የለም። ያለን ነገር እንዲጠቅመን ወደ ሰላም እንመለስ። ወደ ሰላም እንይ። ከጦርነት በፊት ወዳለው አዲስ አስተሳሰብ እንማትር።
ከሰሞኑ በኢቢኤስ ቴሌቪዥን ላይ እንግዳ ሆኜ ቀርቤ ነበር። መጽሀፌ ላይ ከከተብኳቸው ሀሳቦች አንዱን አንስተው እንዲህ ሲሉ ጠየቁኝ ‹አእምሮ እውነትን ሲጸንስ ልብ ሀገርን ይወልዳል› ብለሃል ምን ማለት ነው ሲሉ። እኔም እንዲህ ስል መለስኩ.. ልብ ሀገርን ለመውለድ አእምሮ ሀገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ሊያውቅ ይገባል። አእምሮ ሀገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ እንዲያውቅ ከዘረኝነትና ከብሔር አስተሳሰብ የጸዳ ማንነት ያሻዋል።
ስለብሔርና ስለዘር በሚያስብ አእምሮ ውስጥ ሀገር የለችም። ሀገር ያለችው ሰላምና ፍቅርን በሚጠይቅ አእምሮ ውስጥ ነው። ስለማይረቡ ነገሮች እያሰብን የሚረቡንን ነገሮች አናገኝም። ስለማይጠቅሙን ነገሮች እያሰብን የሚጠቅሙንን ነገሮች አንደርስባቸውም። በአእምሯችን ምናምንቴ እያሰብን በልባችን በኩል ሀገራችንን መፍጠር አንችልም። ስለጥላቻ እያሰብን ሰላም ማምጣት አንችልም ስል መለስኩ።
ከፍቅርና ከሰላም የቀደመ ምንም ነገር እንዳይኖረን አድርገን ራሳችንንና ሀገራችንን እንፍጠር። በልባችን በኩል ሀገራችን እንድትወለድ ለሀገራችን የሚመች አእምሮን እናዳብር። ስለ ሰላምና ሰላም ስለሆኑ ነገሮች ብቻ እናስብ። ዓለም ላይ ያሉ ሀገራት ሁሉ በዜጎቻቸው አስተሳሰብ ልክ የተፈጠሩ ናቸው።
የአሁኗ ኢትዮጵያ በእኔና በእናንተ አስተሳሰብና ድርጊት የተፈጠረች ናት። ለሁለት አመታት ጦርነት ውስጥ ነበርን፣ ስለብሔርና ዘረኝነት ስናቀነቅን ኖረናል፣ ምክክርና ውይይትን ተጸይፈን በአልሸነፍ ባይነት ውስጥ ነበርን፣ ብቸኛው የሰላም መገኛ ጦርነት እንደሆነ አምነን ተቀምጠን ነበር። እኚህ ሁሉ አስተሳሰቦቻችን የአሁኗን ኢትዮጵያ ፈጥረዋታል። መጪዋ ሀገራችን በሀሳብና በሰላም እንደተፈጠሩ ሌሎች የዓለም ሀገራት በስልጣኔና በብልጽግና ወደፊት እንድትገሰግስ ስለሰላም ብቻ ልናስብ ይገባል።
ተሰርቶ ያለቀ ሀገር፣ ተሰርቶ ያለቀ ትውልድ የለም። ሀገር ቀን በቀን ነው የምትሰራው። ትውልድ ቀን በቀን ነው የሚቀረጸው። ሀሳቦቻችን ሁሉ ወደሰላም የሚወስዱንና ሰላም አምጪ ሊሆኑ ይገባል። ከብዙ ሞት በኋላ፣ ከብዙ እልቂት በኋላ ፖለቲከኞች ይታረቃሉ። ከብዙ ውድመት በኋላ፣ ከብዙ ክስረት በኋላ ሰላም ይመጣል።
ይሄ እውቀት አይጠይቅም። ይሄ መቼም በማንም መሆን የሚችል ነገር ነው። እውቀት የሚጠይቀውና አስተዋይ ሊያስብለን የሚችለው ከመሞታችን በፊት የሚያኖረንን ሰላም፣ ከመጎሳቆላችን በፊት የሚያበረታንን ፍቅር፣ ከመለያየታችን በፊት አንድ የሚያደርገንን ሰላም የእኛ ስናደርግ ነው። እዚህ ነገር ላይ ስንበረታ አንታይም። ታሪኮቻችን ሁሉ ከጦርነት በኋላ እርቅን፣ ከብዙ ሞቶች በኋላ መተቃቀፍን የሚያሳዩ ናቸው።
ሳንሞት ሞትን የሚገል ሰላም ያስፈልገናል። ጥላቻን፣ መለያየትን የሚያጠፋ አንድነት ግድ ይለናል። የሄድንባቸውን የመከራና የጦርነት ጊዜያቶች ላለመድገም ዋስትና የሚሆኑ ስራ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። ሁሉንም አይነት መስዋዕትነት ከፍለን ኢትዮጵያ ሀገራችን በአስተማማኝ ሰላም ውስጥ፣ በአስተማማኝ አንድነት ውስጥ፣ በአስተማማኝ ወንድማማችነት ውስጥ የምትሆንበትን ሰላም መፍጠር አለብን።
ይሄ ሰላም፣ ይሄ አንድነት፣ ይሄ ወንድማማችነት፣ ይሄ መተማመን በመካከላችን ካልተፈጠረ ዘመን ጠብቀው፣ የምርጫ ጊዜ ጠብቀው የሚመጡ አንዳንድ ነውጦች አይጠፉም። በምንም ነገር የማይላላ የሰላምና የእርቅ መሰረቶችን መገንባት አሁን ካለነው ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። ከጦርነት በኋላ ሳይሆን ከጦርነት በፊት ስላለው ሰላምና ተግባቦት፣ እርቅና ምክክር እውነትና ቁርጠኝነት ሊኖረን ይገባል። ሞተንና ገለን፣ ተጋፍተንና ተለያይተን የምናገኘው ሰላም ምን አይነት እንደሆነ እናውቀዋለን። አሁን የሚቀረን ሳንሞትና ሳንገል፣ ሳንጋፋና ሳንለያይ ለሰላም መቀመጥ ነው።
ችግር የሆነብን ከስቃዮቻችን በፊት ችግሮቻችንን ለመፍታት ለውይይት አለመቀመጣችን ነው። ብዙ ነገሮቻችን ከተበላሹ በኋላ ለምክክር የምንቀመጥ ነን። ይሄ አስተሳሰብና ይሄ የሕይወት ልምድ ነው ዛሬ ላይ ሀገራችንን ኋላ ያስቀራት። ይሄ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ነው ዛሬ ላይ ከድጡ ወደ ማጡ እያስገባን ያለው።
ፖለቲከኞቻችንም ሆነ ፖለቲካችን መፈተሸ አለበት። እየሄድን ያለው መንገድ ከጦርነት በኋላ ሰላም የሚል ከሆነ ቆም ብለን ማሰብ አለብን። የሚበጀን ከጦርነት በፊት ሰላም፣ ከጦርነት በፊት እርቅ፣ ከጦርነት በፊት አንድነት ነው። ቀጣይ ኢትዮጵያን የመፍጠርና የማሻገር ህልማችን ከዚህ ከችግሮቻችን በፊት ለሰላም መቀመጥ ከሚለው ጽንሰ ሀሳብ ቢጀምር እላለሁ። ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኽ የሚባለው ብሂል ከእንግዲህ መቆም አለበት።
ኢትዮጵያ ሀገራችን ለዚህ ዘመን በማይመጥኑ አስተሳሰቦች መጓዟ ሊያበቃ ይገባል። አንድ ነገር ካልጠቀመንና ካልቀየረን እንድቀይረው የስነ ልቦና ባለሙያዎች ይመክራሉ። አንድ ነገር የምንፈልገውን ሰላምም ሆነ ሌላ ነገር ካልሰጠን አቅጣጫችንን ቀይረን ሌሎች ነገሮችን መሞከር እንዳለብን የዘርፉ ባለሙያዎች ይመክሩናል። ከጦርነት በኋላ ሰላም ጠቅሞን አያውቅም። ከችግሮቻችንና ከመከራዎቻችን በፊት እርቅና መተቃቀፍ አሻግረውን አያውቅም። ለእንግዲሁ ከጥፋቶቻችን በመማር ከችግሮቻችን በፊት እንዴት ሰላም ማምጣት እንዳለብን በመምከር ስልጣኔአችንን መጀመር አለብን።
ከሞትን በኋላ፣ ብዙ ነገሮቻችንን ካጣን በኋላ የምንጮኽው መጮህ የምንለፋው ልፋት ዋጋ የለውም። አንድ ነገር ከመሆኑና ዋጋ ከማስከፈሉ በፊት እንዴት መቆጣጠር እንዳለብን ማወቁ ነው ህልሞቻችንን ወደመሆን የሚያመጣቸው። ሊለውጠንና ሊቀይረን በሚችል ሃሳብና ሙግት ላይ እንጂ ሊያከስረንና ዝቅ ሊያደርገን በሚችል ሀሳብና ሙግት ላይ ጊዜያችንን ማጥፋት አይኖርብንም። እንዲህ አይነቱ አካሄድ ኢትዮጵያን ለጠላት አሳልፎ ከመስጠት ጋር አንድ ነው።
ዛሬም ትናንሽ አሉባልታና ሰላም ለማደፍረስ የማይበቁ ትናንሽ ሀሳቦችን እየነዙ ወደነበርንበት የጦርነት ሜዳ ሊመልሱን የሚፈልጉ አንዳንድ ኃይሎች ከዚህም ከዛም አሉ። ዳግመኛ ወደ ጦርነት እንዳንሄድ፣ ዳግመኛ ወደ መለያየት እንዳንሳብ የጥልን ግድግዳ የሚያፈርስ የፍቅር ምኩራብ መገንባት አለብን። ዳግመኛ ጦር እንዳናነሳ፣ ዳግመኛ እንዳንገፋፋ በመካከላችን ፍቅር የነሱንን ቁርሾዎቻችንን ተነጋግረን መፈታት አለብን።
እኔ በግሌ ከጦርነቱ በፊትም ሆነ በኋላ ብዙ ነገር ታዝቤአለሁ። አሁን እንኳን የሰሞኑን የሰላም መውረድ ተከትሎ አንዳንድ መቀመጫቸውን ውጭ ሀገር ያደረጉ፣ የኢትዮጵያን ሰላም የማይፈልጉ፣ ሁሌ ስንባላና ስንጋደል እንድንኖር የሚፈልጉ ግለሰቦች በሰላማችን ላይ ውሃ ለመቸለስ አሉባልታ ሲነዙ እየተደመጠ ነው።
መንግስት ከሕወሓት ጋር በገባው አስር ነጥብ ባለው ቅድመ ሁኔታ ላይ ተንተርሰው የማይሆን ነገር በመናገር ያገኘነውን ሰላም ለማጠልሸት የሚሞክሩ ድምጾች እየተሰሙ ነው። እኚህ ድምጾች የነበሩ ድምጾች ናቸው.. በነዚህ ድምጾች ላይ ተረማምደን ነው ሰላማችንን የመለስነው። በነዚህ ድምጾች ላይ ተረማምደን ነው ኢትዮጵያ እንድታሸንፍ ያደረግነው። ወደኋላ ማየትም ሆነ መመለስ የማይታሰብ ነው።
በብዙ ጸሎትና ምኞት የመጣ ሰላማችንን መጠበቅና ማስቀጠል ከመንግስት ብቻ፣ ከተፎካካሪ ፓርቲ ብቻ፣ ከአፍሪካ ህብረት ብቻ የሚጠበቅ ሳይሆን ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ታላቅ የቤት ስራ ነው። አእምሯችንን ከዘረኝነት አጽድተን፣ በሀሳባችንና በተግባራችን ኢትዮጵያ የምትፈልጋቸው ሆነን ከሰላም ጋር፣ ከእርቅ ጋር፣ ከአንድነት ጋር ወደፊት መሄድ ቀሪ ተግባራችን ሊሆን ይገባል። ከላይ ባስነበብኳችሁና ይዤው በመጣሁት ‹ከጦርነት በፊት ሰላም› በሚል አዲስ መፈክር ጦርነት የሌለባትን፣ ሞትና ስደት የሌለባትን፣ መለያየትና መገፋፋት የሌለባትን ኢትዮጵያ እንፍጠር ።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ሰኔ 12 ቀን 2015 ዓ.ም