የአገራችን የትምህርት ሁኔታ በየዘመኑ የተለያዩ ትችቶችና አንዳንዴም ቅሬታዎችን ሲያስተናግድ አልፏል፡፡ አሁንም ቢሆን ከዚህ ትችል አላመለጠም፡፡ ከዚህ አንጻር አሁን ያለውን የትምህርት ሁኔታ ለቅርብ መረዳት ሲባል በሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፤ ቅድመ -እና ድህረ 1983። ከ1983 ዓ.ም በፊት የነበረው የትምህርት ፖሊሲ ችግር አለበት በሚል ማስተካከያ ተደረገበት፡፡ ሆኖም ለውጥ ያጣል ተብሎ በ1986 ዓ.ም ፀድቆ ወደ ስራ የገባው አዲስ የትምህርትና ስልጠና ፖሊሲም እነሆ “አንድም ቀን” በሚያስብል ደረጃ ከህዝባዊ ውይይት ርእስነት፣ ከፖለቲካዊ ውዝግብ አጀንዳነት ዝቅ ሳይል እዚህ ላይ ደርሶ እምንመለከተውን እየተመለከትን እንገኛለን። በተለያዩ መገናኛ ብዙሀንም “ዩኒቨርሲቲ ብሎ ለመጥራት የሚያስ ቸግሩ “ዩኒቨርሲቲዎች”፣ “ዕውቀት ሳያገኙ ትምህርት ቤት መመላለስ” ተብሎ ሁሉ ሲፃፍ መክረሙ አይዘነጋም።
በተለይ ስለትምህርትና ትምህርት ነክ ጉዳዮች ሲነሳ ሁለመናችንን ከሚቆጣጠሩትና ከፍተኛ የገበያ ዋጋ ያላቸው ቃላት ቢኖሩ “ተደራሸነት፣ ፍትሃዊነት፣ አግባብነት፣ የጥናትና ምርምር ድርቅ፣ የልህቀት ተቋማት እጦት፣ ብቃት እና ጥራት” እና የመሳሰሉትን የሚያክል የለም። ምን ያደርጋል በአሁኑ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጥናት መሰረት ሁሉም ውሀ በልቷቸዋል። (ይህ የመንግሥትን ብቻ የሚመስለን ካለን ተሳስተናል። በፍኖተ ካርታው “አብዛኞቹ ስታንዳርዳቸውን ያልጠበቁ፣ ከጥራት ይልቅ ገንዘብ መሰብሰብ ላይ ያተኮሩ” የተባለላቸውና በቅርቡም እስከ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርት መረጃን እስከ መቸብቸብ የደረሱትን የግል ተቋማትንም ይመለከታል።) በተለይ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ክፍል ተማሪዎች ያለ ፈተና ይለፉ፣ ማትሪክን ወደ አስረኛ፣ የመጀመሪያ ዲግሪ ፕሮግራም ማጠቃለያ ዓመትን ወደ ሶስት፣ “የትምህርት አግባብነትን ለማሻሻል” ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ ተማሪዎች የ70፡30 ቀመር (ማህበራዊ ሳይንስ/ሳይንስና ቴክኖሎጂ) ምኑ ቅጡ።
ለሚቀጥሉት ሰባት ዓመታት ያገለግላል ተብሎ ከታሰበው አዲሱ የትምህርት ፍኖተ ካርታ ተነስቼ ነው ይህን የሰራሁት የሚለው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሰሞኑን ባሰረጨው ፕሬስ ሪሊዝ አማካኝነት በአገሪቱ የሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት (የመንግሥትም የግልም) በአስከፊ ሁኔታ ላይ የሚገኙና አፋጣኝ መፍትሄን የሚሹ መሆናቸውን አንድም ሳያስቀር ለአደባባይ አብቅቷል፤ ሊመሰገን ይገባዋል። ሚኒስቴሩ “በአገራችን ያሉ ሁሉም ከፍተኛ ተቋማት የሚሰጧቸው የትምህርት ፕሮግራሞች ተመሳሳይና ድግግሞሽ የሚታይ ባቸውና አደረጃጀታቸውም ሁሉን አቀፍ (Comprehensive) በመሆኑ ለትምህርት ጥራትና ተገቢነት ሲባል በተልእኮ ትኩረትና በተዋረድ ለመለየት (Differentiation) የሚያስችል የማስፈፀሚያ ስትራተጂና የመለያ መስፈርት” እያዘጋጀ መሆኑን ይገልፃል።
ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን (ዩኒቨርሲ ቲዎችን)፣ የከፍተኛ ትምህርት ስትራተጂክ ማእከል፣ የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ፣ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኤጀንሲ፣ እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኢንስቲቱዩትን በበላይነት የሚመራው ሚኒስቴር እንደሚነግረን ከሆነ የአሁኑ ወቅት የዩኒቨርሲቲዎቻችን (ባጠቃላይ የስርአተ-ትምህርቱ) ይዞታ ብዙም የሚያወላዳ፤ ደረት አስነፍቶ “ምሩቅ/ምሁር” የሚያሰኝ ሳይሆን፤ ይልቁንም ተቋማቱ ፈጥነው ወደ ለውጥ መስመር መግባት፤ የመለየትና መልሶ የማደራጀት ስራውም በአስቸኳይ መጀመር ያለበት መሆኑን ነው መገንዘብ የሚቻለው። “በተግባር ላይ ያለው ስርአተ-ትምህርት የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎችን በበቂ ሁኔታ ለሙያ መስካቸው የማያዘጋጅና ሰፊ የቀመር፣ የቋንቋና ተግባቦት፣ የምክንያታዊነትና አስተው ሎት እንዲሁም ከዘመኑ ቴክኖሎጂዎች ጋር ያልተጣጣመ መሆኑን በመገንዘብ እነዚህን የእውቀት፣ ክህሎት እና ስብእና ክፍተቶች የሚሞሉ ኮርሶች ተካተው ስርአተ-ትምህርቱ እንዲከለስ” እያደረኩ ነው የሚለው ሚኒስቴሩ በእነዚህና ሌሎች በርካታ ጉዳዮች ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር መምከር አስፈላጊ መሆኑን በማመን የምክክር መድረኩን እንዳ ዘጋጀ አስረድቷል።
ባለፈው ሳምንት በዚሁ አምድ ላይ ጠቆም አድርገን ለማለፍ እንደሞከርነው በጊዮን ሆቴል ለሁለት ቀናት (ሚያዝያ 16 እና 17/2011 ዓ.ም) በተካሄደ የምክክር መድረክ ላይ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሚገኙ ምሁራን የተለያዩ ጥናቶች ቀርበዋል። ከቀረቡት ጥናቶችም አንዱና የመጀመሪያው በሀሮማያ ዩኒቨርሲቲው መምህርና ምክትል የአካዳሚክ ዲን ፕሮፌሰር ንጉሴ ደቻሳ “Differentiating The Ethiopian Higher Education System” በሚል ርእስ የቀረበውና ማእከላዊ ጭብጡን “ልየታ/Differentiation” ላይ ያደረገው ነበር። የጥናቱ አቅራቢ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋር ልዩ ቆይታ ያደረጉ ሲሆን በጉዳዩ ላይ ማብራሪያም ሰጥተውናል። እንደ ፕሮፌሰር ንጉሴ አገላለፅ “ልየታ” ወይም “Differentiation” የሚለው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ልየታ ማለት ነው። ለምሳሌ አንዳንድ ተቋማት በመጀመሪያ ዲግሪ፣ አንዳንዶቹ በማስትሬት፣ አንዳንዶቹም በፒኤችዲ ደረጃ ያሰለጥናሉ፤ ያስመርቃሉም።
አንዳንዶቹ መማርና ማስተማር ላይ ሌሎች ደግሞ ምርምር ላይ ትኩረት ሲያደርጉ ይታያል። እነዚህ ብቻም አይደሉም፤ ሌሎች በግሉ ዘርፍና መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶችም የሚተዳደሩ አሉ፤ እነሱን ሁሉ በማካተት የሚያከናውኗቸውን ተግባራት መለየትና እነዚህን በአንድ ላይ ይዞ ማስፋት ማለት ነው “ልየታ” ስንል። ለምሳሌ አሁን በትምህርት ላይ የሚገኘው ተማሪ ቁጥር አንድ ሚሊዮን ነው። ይህ ከህዝባችን ቁጥር አንፃር በጣም ትንሽ ነው። ነገር ግን በዚህ “ልየታ” መሰረት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ወደ አንድ በማምጣት የተማሪውን ቁጥር በእጥፍ ማስፋት ሁሉ ይቻላልና “ልየታ” ይህን ሁሉ ያካትታል። እንደ ፕሮፌሰሩ ማብራሪያ ይህ ዩኒቨርሲ ቲዎቹን ሦስት ዋና ዋና ዘርፎች ከፍሎ እንዲሠሩ ያስችላል ተብሎ የታመነበት “ልየታ” እና በልየታው መሰረት መልሶ የማደራጀት ስራ ሰው ጥቅሙ ብዙ ነው። አሰራሩ ተግባራዊ ሲደረግ ዩኒቨርሲቲዎቹ “በሚሰጡት ደረጃ (የመጀመሪያ፣ ሁለተኛና ሶስተኛ ዲግሪ)፤ በሚሰጡት ትምህርትና በሚያስመርቁበት የጥናት መስክ አይነት ይለያሉ። አሁን በሶስት ዋና ዋና ዘርፎች (ትምህርት፣ ምርምር እና ፖሊቴክኒክ) ስር ያርፋሉ እንበል እንጂ ወደ ፊት በተለያዩ የሙያ ዘርፎችም ይኖሩናል።
በእጅ ሙያ፣ በቢሮ ሙያ ወዘተ የማህበረሰብ ኮሌጆች ሁሉ ይኖሩናል። ግብፅ፣ ቻይና፣ አሜሪካና ሌሎች አገራት እየሰሩ ያሉት በዚህ መንገድ ነው፤ እኛም ወደ እዚህ አሰራር መግባት አለብን። እኛ አገር ያለው አሰራር ከመነሻው ጀምሮ በደንብ ባልተለየ መልኩ ነው፤ ያለው ሁኔታ ዝም ብሎ ማስተማር ነው። ተደጋጋሚነት ሁሉም ጋር አለ። ይህን በማስቀረት እያንዳንዳዱ ዩኒቨርሲቲ የሚሰራበትን ለይቶ በማወቅ ደረጃው (የሚሰጠውን ዲግሪ አይነት) ማብዛት፣ የጥናት መስኩን ማስፋትና በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ ብቁ የሰው ኃይል ማፍራት እንዲችል ማድረግ ነው።” የዩኒቨርሲቲዎችን ቁጥር ማብዛቱ ጥሩ ነገር ሆኑ ብዛት ብቻ ውጤት አያመጣም የሚሉት ፕሮፌሰር ንጉሴ “ልየታን ብንጠቀም የምሩቀንን ብቃት ከፍ ከማድረግ በተጨማሪ የቅበላውን አቅምም እጥፍ ሊያደርግልን ይችላል።
መቶ እና ሁለት መቶ ዩኒቨርሲቲዎችን ስለከፈትን አይደለም ብዛትና ጥራት የሚገኘው፤ ያሉትን በየባህሪያቸው ለይተን ብንመድባቸውና ብንሰራ የበለጠ አገርም ህዝብም፣ ምሩቃን” የሚጠቀሙ መሆኑን ይገልፃሉ። “ይህን አሰራር ተግባራዊ ካደረግን የማህበረሰብ ኮሌጅ (Community College) ሁሉ ይኖረናል።” በማለትም የ”ልየታ”ን ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያስረዳሉ። “የማህበረሰብ ኮሌጅ የአሜሪካ ልምድ ነው። ለምሳሌ አንድ ሰው በሌላ የስራ ዘርፍ የተሰማራ ሊሆን ይችላል፤ ከስራ ውጪ ያለ ሰው ለሆን ይችላል፤ በምርምር ላይ ያለ ሰው ሊሆን ይችላል ወዘተ። እንደዚህ አይነት ሰዎች ልዩ ስልጠና ሲፈልጉ ወደ እነዚህ ኮሌጆች ገብተው ነው የሚፈልጉትን እውቀትና ክህሎት የሚያገኙ። እኛም ወደ ፊት ይህ ሊኖረን ይገባል። ሊኖረን የሚችለው ደግሞ ወደ”ልየታ” ገብተን በሱ መሰረት ዩኒቨርሲቲዎቻችንን ለይተን መደልደል ስንችል ነው።” ያሉት ፕሮፌሰር የአሁኑ አካሄድ እንደማያዋጣንም በደማቁ በማስመር ጭምር ነው።
አጥኚው እንደሚናገሩት ኢትዮጵያ ውስጥ የዩኒቨርሲቲዎቻችን ቁጥር ይብዛ እንጂ አንዱ ካንዱ የሚለይበት ምንም መስፈርትም ሆነ መንገድ የለም። በአብዛኛው አንዱ ያንዱ ግልባጮች ናቸው። ይህ በፍፁም ሊሆን የሚገባውም፤ መደረግ የነበረበትም አልነበረም። ስለዚህ ይህ ስህተት አሁኑኑ ሊታረም፣ ሊስተ ካከልና አገርና ህዝብም ከየዩኒቨርሲቲዎቹ ማግኘት ያለባቸውን ሁሉ ማግኘት አለባቸው። ይህ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን በተ ልእኮ ትኩረትና በተዋረድ መለየትን እና ስርአተትምህርት ክለሳን መሰረት ያደረገው የፕሮፌሰሩ ጥናት በ“ልየታ/Differentiation” ፅንሰሀሳብ ላይ በሚገባ ያተኮረ፣ አሰራሩን ተግባራዊ በማድረግ ውጤታማ የሆኑ በርካታ አገራትን ልምድ የዳሰሰና በቂ ማብራሪያን የሰጠ በመሆኑ የተሳታፊዎችን ቀልብ በመሳብ ሞቅ ያለ ውይይትን ገብዟል።
የከፍተኛ ትምህርት ምርምርና አካዳሚ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል እና የውይይት መድረኩ አስተናባሪ ዶ/ር ኤባ መዥና እንደገለፁልን “ጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው በመሆኑ በዚህ ጉባኤ ላይ 400 ሰው ይጠበቃል። የሚሳተፉትም የእያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ አበላት (ሰባቱም ማለት ነው)፣ የሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ፕሬዚዳንቶች፣ ምክትል ፕሬዚዳንቶችና አካዳሚክ ዲኖች፣ የተመረጡ የግል ዩኒቨርሲቲዎች ፕሬዚዳንቶች እና የቦርድ አባላት፣ ፖሊሲ አውጪዎች፤ እንዲሁም ከሀገር ውስጥና ከውጪ ጥሪ የተደረገላቸው ምሁራን የተገኙ ሲሆን ጥሩ ጥሩ ግብአት ይገኛል ተብሎም ይጠበቃል” ሲሉ አስረድተውናል። እኛም ከጉዳዩ አስቸኳይነትና አሳሳቢነት አኳያ በተገኘው ግብአት መሰረት ቶሎ ወደ ልየታ እና ማደራጀት ስራው ይገባል ብለን ተስፋ እናደርጋለን።
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 28/2011
ግርማ መንግሥቴ