የሰውን ልጅ የመደሰት፣ የማኩረፍ፣ የማዘን፣ የመከፋት፣ የመጠራጠር ወዘተ. ስሜቶች ለመረዳት ፊትን መመልከት ብቻ ይበቃል። “የልብን ምሥጢር ከፊት ላይ ማንበብ ይቻላል” የሚለው ብሂል ተዘውትሮ መነገሩም ይህንንው ሃሳብ ለማጽናት ይመስላል። ከተትረፈረፈ ግብዣ ይልቅ ለእንግዳ ክብሩ “ከፍትፍቱ ፊቱ” እንዲሉ “የፊት ፈገግታ” ምን ያህል ተመራጭ እንደሆነም ማከል ይቻላል።
“ፊቱን አዙሮ ሄደ” ሲባል ተከፍቶና ተቀይሞ ተመለሰ ማለት እንደሆነ ለቋንቋው ተናጋሪ እንግዳ አባባል አይሆንም። “ፊቱን አጠየመ፣ ፊቱን አጠቆረ” – ተከፋ፣ “ፊቱን አጠመመ” – የሚያስጸይፍ ነገር ስላየ ዘወር አለ፣ “ፊቱን ያዘ” – አፈረ፣ “ፊቱ ተፍለቀለቀ” – ከመጠን በላይ ተደሰተ፣ “ፊት አሳየ” – አቀረበ፤ ወደደ፣ “ኮሶ ፊት” – ኮስታራ፤ የጨፈገገው፣ “ፊተ ሰልካካ” – ቆንጆ፣ “ፊቱ ተኮፈሰ” – አኮረፈ፣ ተዶረረ ወዘተ. የመሳሰሉት ፈሊጣዊ አነጋገሮች “ፊት” ምን ያህል በርካታ መልእክቶች እንደተዋቀሩበት የሚያረጋግጡ ናቸው።
“ፊት” በውክልና የሚቆመው ለሰብዓዊ ፍጡር ብቻ ሳይሆን “የሰማዩ ፊት ጠቁሯል” እየተባለም “ለዶፍ ዝናብ” ጠቋሚነት አገልግሎት ላይ ይውላል። “ደስ ያለው ልብ ፊትን ያበራል” (ምሳሌ 15፡3) የሚለው የጠቢቡ አገላለጸም ትርጉሙ ላቅ ያለ ነው። “ፊት አውራሪ (ፊታውራሪ)” የሚለው ወታደራዊ ማዕረግም ከበድ ያለ ሥልጣን የተወከለበት ነው።
ብዙ ሰዎች (በተለይም ከተሜ ቀመሶቹ) ማለዳ ወደ መደበኛ የሥራ ገበታቸው ከመሰማራታቸው አስቀድሞ በመስታወት ፊት ቆመው “በፊታቸው” ውክልና ራስን ማስገምገም የተለመደ የዕለት ተዕለት ክስተት ነው። “የፊት እድፍ በመስታወት፤ የኃጢያት እድፍ በክህነት” የሚለው ንስሃንና ይቅር መባልን የሚያበረታታው “ሃይማኖት ነክ” ብሂልም በክርስትና አማንያን ዘንድ ትርጉሙ ላቅ ያለ ነው።
ልብ ብለን ብናስተውል እያንዳንዱ ዘመን በራሱ ፊት ላይ የሚነበብ ታሪክ አለው። አንዳንዱ ዘመን በፈካ ፊቱ ላይ ልቡናውና አእምሮው የፈካ ትውልድ አስተናግዶ ያልፋል፡፡ ይህን መሰሉ ትውልድ የዘመንን ወንዝ የሚሻገረው ለራሱ ኖሮ ብቻ ሳይሆን ለተከታዩ ትውልድም ደማቅ አሻራ በማኖር ነው። አንዳንድ ዘመን ደግሞ እንደተጨፈገገ ተከስቶ ጠልሽቶ ሲያሸልብ በታሪካችን ውስጥ ደጋግመን የምናነበው እውነታ ነው። የዘመን ፊት የሚገመገመው በዕለት ኑሮ ብቻ ሳይሆን በታሪክ ብያኔ ጭምር ነው የሚባለውም ስለዚሁ ሳይሆን ይቀራል።
ደግሞም አለ አንዳንድ ዘመን ፊቱ እንደተሸፈነ መጥቶ “ምን ተሠራበት” ተብሎ ቢጠየቅ “ምንም” እየተባለ የሚመሽበት። ሆደ ባሻ ዘመንም አለ “እምባው” እንጂ ሣቁ ሳይሰማ የሚያልፍ። ነፍሰ ሔሩ መምህራችን ደበበ ሰይፉ ይህንን መሰሉን “አሻራ ቢስ” በራሪ ዘመን የመሰለው በሚከተሉት ጥቂት ስንኞች ወካይነት ነው። ነበርን እያስታወሱ ዛሬን መገምገም ያለና የሚኖር የሰው ልጆች ሁሉ ጠባይና ባህርይ ስለሆነ ስለምን ተብሎ አይጠየቅም።
ጊዜ በረርክ በረርክ፣
ጊዜ በረርክ በረርክ፣
ግና ምን አተረፍክ፣
ግና ምን አጎደልክ?
ሞትን አላሸነፍክ፣
ሕይወትን አልገደልክ።
በእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ ዛሬም ድረስ ነግሠው ያሉት እኛ ሹሩቤያሙ የቀዳሚ ዘመናቱ ታላቅ መሪ እንደተናገሩት አስመስሎ የጻፈልን የተወዳጁ ባለቅኔችንን ጥቂት ግጥሞች እንደ መንደርደሪያ በመዋስ የዘመናችንን የፊት እድፍ “በመስታወት ፊት በሚደረግ የአፍታ ቆይታ” ያህል በፍጥነት ጠቅሰን እንለፍ።
“ያለፈ ጥረታችንን፣ ሳስታምመው ትዝ ሲለኝ፣
ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው እሚቆጨኝ።
ታዲያ እንግዲህ አንቺ ኢትዮጵያ፣ እኛስ ልጆችሽ ምንድነን፣
አመንኩሽ ማለት የማንችል ፍቅራችን የሚያስነውረን።
ዕዳችን የሚያፎክረን፣
ግፋችን የሚያስከብረን፣
ቅንነትየሚያሳፍረን ቂማችን የሚያስደስተን፣
እኮ ምንድን ነን? ምንድን ነን?
አሜክላ የሚያብብብን፣
ፍግ የሚለመልምብን።
ከአረም ጋር ያፈራን ጊንጦች፣ ከእንክርዳድ ያልተለየን ዘር፣
ግርዱ ከምርቱ ተማጥቆ፣ ከቶ ያልተበራየን መከር፣
ምንድን ነን? እኮ ምንድነን?
እንደ እውነቱ ከሆነ ገጣሚያኑ ብቻ ሳይሆኑ እኛ ራሳችን የራሳችንን ዘመን ኑሮ ወደ ግጥም ብንለውጠው በመጻኢው ትውልድ የሚጠቀስ ፈለግ ትተን ለማለፍ አይቸግርም።
የዘመናችን የፊት እድፍ፤
ዛሬ የደረስንበት የጊዜያችን የፊት እድፍ በዛሬ ጀንበር የተደፈደፈብን ብቻ ሳይሆን ከትናንት ታሪካችን የወረስነው ጭቅቅት ጭምር ነው። ገፈቱ እያንገሸገሸን ያለውና በኢትዮጵያችን ላይ የተላከከው የዛሬው ወሰክ (ቆሻሻ) መሰረቱን ጠለቅ ብለን እንፈትሽ ብንል የምንደርሰው የትናንቱ ዘመን ጥሎብን ባለፈው የከፋ ማዲያት ላይ ሊሆን ይችላል።
እየገፈገፍን ያለነው ሁለንተናዊው የዛሬ ብሔራዊ ዕዳችን የትናንቱ ዘመን ታቅፎና ፈልፍሎ ያሸጋገረልን ውላጅ እንጂ ዛሬ ላይ እያጨድን ያለነው የመከራችን አዝመራ ያፈራውን ምርት ብቻ አይደለም። ልባሙና ስደተኛው ገጣሚያችን ክፍሌ አቦቸር (ሻለቃ) “የትናንቱን ዘመን የፊት እድፍ ተግተንና ጨክነን” ይሉኝታ ሳይቆጣጠረን አብሰን ብናልፍ ኖሮ የዛሬው መከራችን ይቀልልን እንደነበር የተቀኘው እንዲህ በማለት ነበር።
“ሀ” ሲባል “ሀ” ቢባል፤ ጅምሩ ቀድሞ ቢዳሰስ፣
ቀድሞ! ቀድሞ ቢቀነጠስ፣
መፈልፈያው ቢደፈን፤ ሥሩ ማለዳ ቢበጠስ፣
የውስጥ ውስጡ የላይ ላዩ፣
ቃርሚያው በወጉ ቢነሳ፣
ባልኖረ ባልነበረ ነበር፤ የዛሬው ክምር አበሳ!
ይኼው ዛሬም እንዲሁ፣
ለቆየ ችግር “እርሾ” ሆኖ፣
እንደ “ጲላጦስ” አንጡኝ የሚል፣
የውስጡን በውስጡ ይዞ፣ ሲታዘን
ቀድሞ የሚስል፣
የችግሩ “ችግር” ይህ ነው።
ሽምቅታው ነው የገደለን፣
የሣመን ነው የነከሰን፤ የሣቀ ነው የገደለን።
ከላይ ማጣቀሻና የማዋዣ ስንኞችን የተዋስና ቸውን ባለቅኔዎቻችንን አመስግነን ዛሬያችንን ወደ መፈተሸ እናዝግም።
እናስ ምን ይሁን? ከዜጎች የሚጠበቀውስ ምንድን ነው?
እርግጥ ነው ሀገሬን ያበለዛት የዛሬው ዘመን የፊት እድፍ በዓይነቱም ይሁን በመልኩ ውስብስብና ለመፍትሔውም አስቸጋሪ ሆኖብናል። ብዙ ዜጎች በስክነትና በማስተዋል የዘመኑን የፊት እድፍ በመደጋገፍ ለማጠብ ከመትጋት ይልቅ ይበልጥ ለከፉ ችግሮች ምክንያት ለመሆን ርብርብ ሲደረግ ይስተዋላል።
በችግሩ ላይ ዘምቶ ዘመኑንና ራስን ከእድፍ ከመጠበቅ ይልቅ የትናንትን ቆሻሻ “ከታሪክ ኮሲ” ላይ እየለቀሙ ካልኖሩበት ትውልድ ጋር ግብግብ በመፍጠር ይዋጣልን ብሎ መፎከር የተለመደ ክስተት ሆኗል። የትናንት ዘመን እድፍ በዛሬ ማጽጃ ሊነጻ የሚችለው በመነጋገርና በመግባባት እንጂ ነፍጥ ወልውሎ “ይዋጣልን” እያሉ መፎከሩ እንኳን ለዛሬው ትውልድ ቀርቶ ለትናንቶቹም “ዱር አደሮች” የበጀ እንዳልሆነ መረዳት አይከብድም።
በመጯጯኽና “በለው! ቁረጠው! ፍለጠው!” እየተባባልን በማሕበራዊ ሚዲያ ደን ውስጥ ተሸሽጎ መፋለሙ “በቡሃ ላይ ቆረቆር” ከማከል ውጭ ምንም ፋይዳ አይኖረውም። የብሔራዊ ችግራችን ሁነኛ መፍትሔ የትናንትን ችግር ከዛሬ ችግር ጋር እያጋቡ የከፋ ችግር እንዲፈለፈል ከማድረግ ውጭ ከቶ ምን የረባ ውጤትስ ሊገኝ ይችላል?
በሀገር ላይ የተደፈደፈው የዘመን ውርስ እድፍ ሊታጠብ የሚችለው በጠረጴዛ ዙሪያ የውይይትና የምክክር ወንበር ስቦ አድምጠኝ እኔም ላድምጥህ ሲባል ብቻ ነው። በሙሉ አቅሙ ሊንቀሳቀስ እየተሟሟቀና “ጉልበቴ በርታ! በርታ!” እያለ ባለው የብሔራዊ አካታች የምክክር ኮሚሽን ላይ ይህ ጸሐፊ ትልቅ ተስፋ አሳድሯል። ኮሚሽኑ የሀገራችንን ፊት
ያጠየሙና ያቆሸሹ የውርስ ችግሮችና አዲስ በቀል እድፎችን ለማስወገድ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለበትም ይረዳል።
የሀገሪቱ ችግሮች እንደ ንብርብር አለቶች ሲደራረቡ የመጡ ድድር እድፎች መሆናቸውን ቀድመን ካልተረዳን በስተቀር መፍትሔውን በቀላሉ ማግኘት ሊያዳግተን ይችል ይመስለናል።
ለምሳሌ፡- የዘር ማንዘር ቆጠራ ደዌ የተቆራኘንና የተጠናወተን በየትኛው ዘመንና ትውልድ ነበር? ያ “ተወቃሽ ትውልድ” ስለምን ነበር ለልክፍቱ ሊጋለጥ የቻለው? ይህ አንዱ የምክከር ኮሚሽኑ የእድፍ ማራገፊያ ርእስ ሊሆን ይችላል።
እንቀጥል፡- ስንት መከራ የተጫናት ሀገር በቋንቋ እንካ ሰላንትያ አታካራ ውስጥ ስለምን ልትዘፍቅ ቻለች? ከዚህ ላለመግባባት ካግባባን ክፉ እድፍ እንዴት መላቀቅ እንችላለን? ይኼኛው ችግራችንም በኮሚሽኑ ቅድሚያ ተሰጥቶት ቢስተናገድ እንጠላም።
እንሠልስ፡- “ይኑርልን ለክብራችን” እያልን የምንዘምርለት የሀገሪቱ ሕገ መንግሥት ዋነኛ የፊት እድፎች በየትኞቹ አናቅጽ ላይ የሚገኙት ናቸው? እናስ እድፎቹ እንዲወገዱና “የሕጎቹ አውራ” እንዲጸዳ መወያየት ያለብን እንዴትና በምን አኳኋን ነው? ሌላው ልንወያይበት የሚገባ መሰረታዊ ጉዳይ ይመስለናል።
በሀገሬ ፊት ላይ የተደፈደፈውን የዛሬውን ብሔራዊ እድፍ በአጭር ቋንቋ እንግለጸው ካልን በደል የውበት ማበልጸጊያ ሜክአፕ ይሆን ይመስል የትናንትን ቂም በሌላ በደል በመኳል ለማሸነፍ መትጋታችን ያመጣቸው መዘዞች እንዴት ሊወገዱ ይችላሉ? ሌላው የጋራ አጀንዳችን ቢሆን አንጠላም። ሊሆንም ግድ ይላል።
ጸሐፊ ተብዬዎች ምሬትን እያስተጋቡ እሪታ ካበዙ፣ ጥበብ በብሶት ተጸንሳ ብሶት ብቻ የምትወልድ ከሆነ፣ ምሁራን እየተንገፈገፉ መፍትሔውን ሳይሆን በእድፉ ጉዳዮች ላይ ብቻ እያላዘንን እንድንጮህ “ጃስ!” በማለት የሚያስደነብሩን ከሆነ፣ የፍትሕ ሥርዓቱ ኮምጥጦ የሚያኮመጥጠን ከሆነ፣ ፖለቲካው ቃዥቶ የሚያሯሩጠን ከሆነ፣ ሃይማኖቶቻችን ስክነትን ከመስበክ ይልቅ ወዮታ የሚበዛባቸው ከሆነ የሀገር እድፍ ተስፋን ያጨለም ካልሆነ በስተቀር ሌላ ምንም ትሩፋት አይኖረውም።
ይህ ጸሐፊ የዛሬ ሠላሳ ስምንት ዓመት ይህንን አንጋፋ ጋዜጣ የተቀላቀለው “ሀ – በጽጌሬዳ ብእር” በሚል ርእስ በተጻፈ ሥነ ጽሑፋዊ ሂስ ነበር። ያ ዘመን እንኳንስ ስለ ጽጌሬዳ ሊጻፍ ቀርቶ ምድርና ሰማዩን የሞላው የጦርነት ዜና፣ የወጣቶች አፈሳና ዘርፈ ብዙ መከራ ፋታ የሚሰጥ አልነበረም። ጸሐፊው ለዚያ ክፉ ዘመን ተመጣጣኝ የብእር ምት ከመስጠት ይልቅ ተስፋ ማሳየቱ የተሻለ መስሎ ስለታየው እነሆ በእሾህ ለተከበበች ሀገር “ተስፋ አለሽ” ብሎ ማጽናናቱን በመምረጥ የድርሻውን ለመወጣት ሞክሯ።
ዛሬም በዘመናት የንብርብሮሽ የሀገራችን ፊት በእድፍ ገርጥቶና ቅስሟ ተሰብሮ አንገት የደፋች ቢመስልም በርግጥም ተስፋ አላት። የውጭ ወደረኞቿ ስም በማጥፋት ቢዘባበቱባትም፣ የውስጥ ችግሮቻችን የተወሳሰቡ ቢመስሉም ለበጎነት ከበረታንና ተስፋችንን የማንጥል ከሆነ ያለ ምንም ጥርጥር ነጋችን የተዋበ፣ የደደረው እድፍም ለቆ የሀገሬ የፊት ማዲያት መፈወሱ አይቀርም።
ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 10/2015