በአገራችን ቡና ለኢኮኖሚው ባለው የገዘፈ አስተዋጽኦ አረንጓዴው ወርቅ በመባል ይታወቃል። የቻይናው ፕሬዚዳንት ሺን ዥንፒንግ የአካባቢ ጥበቃ ማለትም የችግኝ ተከላን ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችንና ከአየር ንብረት ጥበቃ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ተግባራት “አረንጓዴ ወርቅ ናቸው !” ሲሉ ያሞካሿቸዋል። በሰብዓዊነትና በተፈጥሮ ሕብርነት ላይ በመከረ “የ2023 ኤርሀይ መድረክ” ላይ ተፈጥሮና ልማት ሳይጠፋፉ መሳ ለመሳ ስምም ሆነው መሔድ እንደሚችሉ ተመልክቷል ።
ሥነ ምህዳርና ሲቪላይዜሽን እጅና ጓንት ሊሆኑ እንደሚችሉ ከቻይናዋ ዳሊ ቤይ ክፍለ አገሯ ኤርሀይ በላይ ማሳያ የለም ይላል ሰሞኑን ለንባብ የበቃውና ከቻይና መንግሥት ልሳኖች አንዱ የሆነው “ቤጂንግ ሪቪው” መጽሔት በርዕሰ አንቀጹ ። ይች ደሴት ሲቪላይዜሽንንና ሥነ ምህዳርን እርቅ አውርደው በአንድነት መኖር ለመቻላቸው ጥሩ አብነት ናት። በግሌ የአካባቢ ጥበቃ ስራ ለሰው ልጅም ሆነ ለምንኖርባት ፕላኔት ህልውና ወሳኝ ስለሆነ በአልማዝም ሆነ በወርቅ አይለካም ብዬ አምናለሁ። ከየትኛውም የከበረ ማዕድን በላይ ነው ። ሰሞነኛው የቻይና መድረክ ከአገራችን ሁለተኛ ዙር የአረንጓዴ ዐሻራ ጋር ስለተገጣጠመ አነሳሁት እንጂ በዓለማችን የዘንድሮውን ጨምሮ ከ31 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል አገራችንን መወዳደር ቀርቶ አጠገቧ የሚደርስ አገር የለም።
በአገራችን የዘንድሮን የአረንጓዴ ዐሻራ ተከላ ስናገባድድ ፣ ኢትዮጵያ በ31 ቢሊዮን ችግኞች ትለብሳለች። ኑ ! ይህንን ታሪክ አብረን እንሥራ ! ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ጥሪ አስተላልፈዋል። “ዛሬ ነገን እንትከል !” ይህ ዛሬ ለምንጀምረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር የሁለተኛው ምእራፍ ጅማሮ መሪ ሃሳብ ነው፡፡ 25 ቢሊዮን ችግኞችን የተከልንበት የመጀመሪያ ምእራፍ ተሳክቷል። በሁለተኛው ዙር ደግሞ ኢትዮጵያ 25 ቢሊዮን ችግኞችን ትተክላለች። አረንጓዴ ዐሻራ ለትውልድ የሚተርፍ ቅርስ ነው።
የአየር ንብረት ለውጥን እና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም የወጠንነው አገር በቀል አካሄዳችን ነው። የሥራ ዕድል ለመፍጠር አንዱ መንገዳችን ነው። እንዲሁም ለምግብ የሚውሉ ዕጽዋትን በመትከል የምግብ ዋስትናችንን የምናረጋግጥበት ሌላው ስልት ነው ይላሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ። እውነት ለመናገር የአረንጓዴ ዐሻራ ከየትኛውም አገራዊ ሜጋ ፕሮጀክት ይበልጥብኛል። አገርንና ኢትዮጵያውያንን ይዞ የሚነሳ ርዕይ ነው።
በመንግሥታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ፕሮግራም (ዩኤንኢፒ)አገራችን ኢትዮጵያን ለአየር ንብረት ለውጥ ክፉኛ ከተጋለጡ 10 አገራት አንዷ መሆኗን ይገልጣል። መልሶ ኢትዮጵያውያን ግን የአየር ንብረት ለውጥን ከማያባብሱ ዜጎች ተርታ ይሰለፋሉ ይለናል። ኢትዮጵያውያን በአማካኝ ወደ ከባቢ አየር የሚለቁት ግሪንሀውስ ጋዝ 1.3 ሜትሪክ ቶን ወይም 1300 ኪግ ሲሆን በአንጻሩ የአሜሪካውያን 20ሺህ ኪግ ፤ ኩየታውያን ደግሞ 60ሺህ ኪግ ግሪንሀውስ ጋዝ ወደ ከባቢ አየር ነው።
የቻይናና የሕንድማ አይነሳ ። ይህ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ለከባቢ አየር ሙቀት መጨመር እዚህ ግባ የሚባል ድርሻ የሌላቸው አገራት የበለጸጉ አገራት ከኢንዱስትሪ አብዮት ጀምሮ ወደ ከባቢ አየር በለቀቁት ከፍተኛ መጠን ያለው ግሪንሀውስ ጋዝ በተፈጠረ የአየር ንብረት ለውጥና የከባቢ አየር ሙቀት የተነሳ ለተደጋጋሚ የዝናብ ዕጥረት ፣ ለድርቅና ርሃብ ተዳርገዋል ።
አገራችን ከ1966 ዓ.ም ጀምሮ በየአስር ዓመቱ ይጎበኛት የነበረው ድርቅ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በየዓመቱ የሚከሰት ሆኗል። ዘንድሮ እንኳ በቦረና፣ በሶማሌና በደቡብ ክልል የተከሰተው ድርቅ በእንስሳትና በአርብቶ አደሩ ላይ ያስከተለውን ከፍተኛ ጉዳት አይተናል። በመንግሥት ርብርብ ድርቁ በሰዎች ላይ የከፋ ጉዳት ባያስከትልም የህልውናቸው መሠረት የሆኑ እንስሳቱ ላይ ግን የከፋ ጉዳት አድርሷል። መጠኑ ቢለያይም እንደ 1966ቱ ፣ 77ቱና 87 ሰዎች በርሃብ እንደ ቅጠል አልረገፉም።
የሕዝብ ቁጥር ዕድገቱን የሚመጥን ምርት ባለመመረቱ ፤ በፍላጎትና በአቅርቦት መካከል ያለው ሰፊ ክፍተት ባለመጥበቡ ፤ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ሕወሓት በከፈተው ጦርነትና እዚህም እዚያም በተከሰቱ ቀውሶች ፤ በኮቪድ 19ኝና ራሽያ ዩክሬንን በመውረሯ በተፈጠረ የዋጋ ግሽበቱና የኑሮ ውድነቱ የተነሳ በከተሞች ሳይቀር ኑሮው አልቀመስ ብሏል ።
አገራችን ዛሬ ለምትገኝበት ውስብስብ ችግር በርካታ ምክንያቶችን መደርደር ቢቻልም ዋነኛዎቹ ግን ሁለት ናቸው ። እነሱም አበክረን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አለመገንባታችን ፤ የተፈጥሮ ሀብታችንና የሰው ኃይላችንን በአግባቡ አቀናጅተንና አልምተን አለመጠቀማችን ናቸው ። ሰፊ ለም መሬት ፣ ዓመቱን ሙሉ የሚፈሱ ወንዞች ፣ የከርሰ ምድር ውሃ ፣ ዝናብና ወደ 117 ሚሊዮን ከሚገመተው ሕዝብ 70 በመቶው ወጣት ስለሆነ ከምግብ ዋስትና አልፈን የተትረፈረፈ ምርት አምርተን ኢንዱስትሪውን ፣ የአገልግሎት ዘርፉንና የውጭ ንግዱን ይዘን መነሳት እየቻልን ዛሬም እርዳታን የምንቀላውጥ መሆናችን አንገት ያስደፋል።
ከለውጡ ወዲህ ግን ችግኝ ተከላውን ከግብርና ልማቱ ፣ ከአካባቢ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ጋር መሳ ለመሳ በማስኬድ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያልተጠበቀ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ ችለናል ። በ2025 ዓ.ም ደግሞ የግሪንሀውስ ጋዝ ልቀቷን ወደ ዜሮ ለማውረድ ግብ ተጥሎ እየተሰራ ነው። ባለፉት አራት ዓመታት 25 ቢሊዮን ችግኞችን የተከለች ሲሆን የኤሌክትሪክ ፍላጎቷንም ከታዳሽ ኃይል ማለትም ከግድብና ከንፋስ እያገኘች ሲሆን በቀጣይም ከእንፋሎት ለማመንጨትም እየሰራች ትገኛለች።
አገራችን በታሪኳ ከፈጸመቻቸው፤ እየፈጸመቻቸው ካሉ ግዙፋን ፕሮጀክቶች ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጨምሮ አንድ ላይ ቢደመሩ የ “ አረንጓዴ ዐሻራን” ያህል ክብደት አልሰጣቸውም ፡፡ የህዳሴውም ሆነ የሌሎች ታላላቅ ግድቦች ህልውና እንዲሁ 80 በመቶ አገሬው ኑሮ የተመሰረተበት ግብርና እጣ ፈንታ የሚወሰነው ዛሬ በትጋት በምንከውነው የአካባቢ ወይም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ነውና ፡፡ በቀደሙት ሶስት ዓመታት ከ18 ቢሊዮን በላይ አገር በቀል ችግኞችን ለዛውም ከሞላ ጎደል ሥነ ምህዳርን ታሳቢ ያደረጉ በመላው የአገሪቱ ክፍሎች መትከል ተችሏል። ከተተከሉ ችግኞች መካከል እንደ አቡካዶ፣ ማንጎ፣ አፕል፣ ፓፓየ፣ ሙዝ እንዲሁም ቡና የመሳሰሉት ይገኙበታል። በአራቱም ዙር ከ90 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ በችግኝ ተከላው ተሳትፏል።
ከፍ ብዬ ለመግለጽ እንደሞከርሁት ችግኝ መትከል የአየር ንብረት ለውጥን ፣ የዓለም ሙቀት መጨመርን ወይም የአካባቢ ጥበቃ ችግሮቻችን ለመፍታት የማይተካ ሚና አለው። ድህነትን ፣ የምግብ ዋስትና ጉድለትን ፣ የምርታማነት ተግዳሮትን ፣ ድርቅን፣ ርሃብን ፣ የዝናብ መቆራረጥንና መቅረት ፣ የውሃ እጥረትን ፣ የኑሮ ውድነትን ፣ በፈጣን የሕዝብ ቁጥር እድገትና በምርት አቅርቦት መካከል ያለውን ክፍተትት፣ ሥራ አጥነት ፣ ከገጠር ወደ ከተማ የሚደረግ ፍልሰትን ፣ የጸጥታና የደህንነት ችግርን ፣ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን ሽግግር በማሳለጥ እና ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማለም መስፈንጠሪያ በመሆን ያገለግላል። ለዚህ ነው ችግኝ ተከላን የችግሮቻችን ሁሉ መፍቻ ማስተር ኪይ ነው የምለው፡፡
በየዓመቱ በአገራችን ከ92ሺህ ሔክታር መሬት በላይ ደን ይመነጠራል። ይጨፈጨፋል። በዚህ የተነሳ የደን ሽፋናችን ከ50 ዓመታት በፊት ከ35 በመቶ ከነበረበት ደረጃ ወደ ሶስት በመቶ አሽቆልቁሎ ነበር። ለዝናብ እጥረት ፣ ለድርቅና ለከባቢ አየር ሙቀት ተዳረግን። በየዓመቱ ምርታችን ከ10 በመቶ በላይ መቀነስ ጀመረ ። በየዓመቱ ከ35 እስከ 40 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይቀንሳል። ሆኖም ባለፉት አራት ዓመታትም ሆነ ከዚያ በፊት በተከናወኑ የችግኝ ተከላና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የደን ሸፋኑን ወደ 17 በመቶ ማገገሙ ይበል የሚያሰኝ ነው።
የበጋ ስንዴ ፣ የኩታ ገጠም ግብርናን ፣ በተወሰነ ደረጃ ሥነ ምህዳርን ታሳቢ ያደረገ የቴክኖሎጂና የሜካናይዜሽን እገዛ ፣ የከርሰና የገጸ ውሃን አሟጦ የመጠቀም ፣ ፍራፍሬና አትክልት ላይ ለመስራት ፣ በተለይ ከአለፈው ዓመት ጀምሮ የከተማ ግብርና ትኩረት ማግኘቱ ፤ በአርብቶ አደሩ የሚገኙ ጦም ያደሩ ሰፋፊ መሬቶችን በመስኖ ለማልማት አበረታች ጥረትና ርብርብ መደረጉ እና ከውጭ የሚገባውን ስንዴ ማስቀረት መቻሉ የአተያይ ለውጥ በማምጣቱ ተስፋ ያስቆረጠን ግን ደግሞ ብቸኛ ሊባል በሚችለው ግብርና ከምግብ ዋስትና ባሻገር ተስፋችንን እንድናድስ አድርጎናል፡፡ ለዚህ ነው ተስፋ ሰጪ ጅምር እውቅና መስጠት የሚያስፈልገው፡፡
ችግሮቻችንን ሁሉ ፈታተን ፣ በታትነንና አገላብጠን ብንመረምራቸው አብዛኛዎቹ ከአንድ ቅርጫት የሚገኙ ናቸው ፡፡ የተፈጥሮ ሀብታችንን በአግባቡ ካለመንከባከብ ፣ ካለመጠበቅና ካለማልማት ቅርጫት። የዓለም ሙቀት መጨመርን ተከትሎ በመጣ የአየር ንብረት ለውጥ የተነሳ የተፈጥሮ ሀብታችን እየተጎሳቆለ በመምጣቱ ማለትም መሬታችን የተራቆተ ፣ ዝናባችን የአጠረና የተቆራረጠ በመሆኑ የከርሰና የገጸ ምድር ውሃችን በመመናመኑ ግብርናው ውጤታማ ሊሆን አልቻለም ፡፡
በዚህ የተነሳ በግብርና ላይ የተመሰረተው የዜጋው ሕይወት ፤ የአገሪቱ ልማት ችግር ላይ ወድቋል ፡፡ ይህ የሀብት ውስንነትን ፈጥሯል ፡፡ በዚህ የተነሳ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮች ከዓመት ዓመት እየተባባሱ መጡ፡፡ እነዚህን ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ደግሞ የተፈጥሮ ሀብታችን እንዲያገግም ሌት ተቀን መሰራት አለበት፡፡ መሬት ማገገም ፣ ውሃ መያዝ አለባት፡፡ ይህ ደግሞ እውን ሊሆን የሚችለው ችግኝ በመትከልና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን በስፋት በማከናወን ነው፡፡ “አረንጓዴ ዐሻራ” የበሽታውን ምልክት ከማከም ይልቅ መነሻውን በማያዳግም ሁኔታ የመፈወስ አቅም እንዳለው በማመን ነው፤ “አረንጓዴ ዐሻራ !” የእንቆቅልሾቻችን ሁሉ መፍቻ ቁልፍ (ማስተር ኪይ) የምለው ፡፡
ለዚህም ነው 31 ቢሊዮን ችግኞችን መትከል ከቁጥርና ከአኃዝ በላይ በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅ፣ የበርሃማነት መስፋፋት ፣ የአፈር መከላት ፣ የዝናብ ዕጥረትና መቆራረጥ ፣ የገጸና የከርሰ ምድር ውሃ መቀነስን በመከላከል ፤ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ከተመጽዋችነት የመላቀቅ የማሪያም መንገዳችን፤ ሉዓላዊነታችን ሙሉኡ ማድረጊያችን፤ የአገሪቱ ሁለንተናዊ ብልጽግና ማርሽ መቀየሪያ ፤ አስተማማኝ ሰላም ማስፈኛችን ፤ እውነተኛ አንድነትና እርቅ ማረጋገጫችን ፤ ወዘተረፈ ስለሆነ አረንጓዴ ዐሻራ ከአኃዝ በላይ ከመሆኑ ባሻገር ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉትም እንደ አገርና ሕዝብ ብቸኛ መዳኛችን ነው።
የአራት ዓመቱ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብርን መጠናቀቅ አስመልክቶ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ያስተላለፉት መልዕክትም የአረንጓዴ ዐሻራው 25 ቢሊዮን ችግኝ ተተክሏል ከሚለው የአኃዝ ዜና በላይ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው ።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የአራት ዓመቱ የአረንጓዴ ዐሻራ ዘመቻ መጠናቀቅን አስመልክተው ባለፈው ዓመት ባወጡት መግለጫ በአረንጓዴ ዐሻራ ሥራዎች ከችግኝ ማፍላት እስከ እንክብካቤው 25 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን መሳተፋቸውን ፤ በኢትዮጵያ ሲካሄድ የቆየው የአረንጓዴ ዐሻራ ዘመቻ በአገሪቱ አረንጓዴ ባህልን በመፍጠር ስኬታማ መሆኑን መግለጻቸውን የኢትዮጵያ ፕሬስ ኤጀንሲ ዘገባ ያወሳል።
ኢትዮጵያ የከተሞቿን የአረንጓዴ ሽፋን ለማሳደግ የአረንጓዴ ዐሻራ ዘመቻን መጀመሯን ፤ ለአራት ዓመት በቆየው ዘመቻ 20 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ወጥና ብትነሳም ፤ ዜጎቿ 25 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል ካስቀመጡት ግብ በላይ ፈጽመዋል ። የአረንጓዴ ዐሻራ ዘመቻው ሲጀመር 40 ሺህ ብቻ የነበሩት የችግኝ ማፍያዎች አሁን ላይ ወደ 121 ሺህ ማደጋቸውንና በዓመት ሰባት ነጥብ ስድስት ቢሊዮን ችግኝ የማፍላት አቅም ላይ መደረሱን ፤ አረንጓዴ ባህልን ከመፍጠር ባለፈ ዘመቻው ለ767 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ያበረከተውን ኢኮኖሚያዊ አስተዋፅኦም ማንሳታቸውን የኤጀንሲው ዘገባ ያመለክታል ።
ከዚህ ባለፈ ለችግኝ ተከላ የሚያስፈልጉ ቦታዎችን በመምረጡ እና ለተከላ በማዘጋጀቱ ረገድም የታየው ውጤት አበረታች መሆኑን ፤ በመላው አገሪቱ የሚገኙ ከተሞች አሁን ላይ የአረንጓዴ ስፍራ አስፈላጊነትን ተረድተው ቦታ እያዘጋጁ መሆኑ ለተፈጠረው አረንጓዴ ባህል ማሳያ ነው ። የአረንጓዴ ዐሻራ ባህል ለቀጣዩ ትውልድም የሚቆይ መሆኑን ፤ በዚህ ስኬት ውስጥ የፖለቲካ ፍላጎት እና ቁርጠኝነት ቁልፍ ሚና መጫወቱን ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብሩ በርካቶች መሳተፋቸውን ፤ አሁንም ብዙ ሥራ የሚጠበቅብን ቢሆንም ንቅናቄው በአገሪቱ ፍሬ እንዳፈራ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል ።
ያለፉትን ጥቂት ሳምንታት ብቻ በዓለም ዙሪያ የተስተዋሉት የጎርፍ አደጋ ፣ የደን ቃጠሎ ፣ ኃይለኛ ማዕበል እና ያልተለመደ ሙቀትን የመሰሉ ሁኔታዎች ለአየር ንብረት ለውጥ ዓይነተኛ ማሳያዎች መሆናቸውን፤ የአፍሪካ ቀንድ ያስተናገደው ድርቅ የዚሁ የአየር ንብረት ለውጥ ውጤት መሆኑን ፤ በኢትዮጵያም የአየር ንብረት ለውጥ የውሃ ምንጮችን ማድረቁን በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎችም የድርቅ አደጋን ማስከተሉን ፤ አሁን ላይ ዓለም እየተሰቃየ ያለበትን ይህን ችግር ለመፍታት ከስብሰባዎች ያለፈ ተግባራዊ መፍትሄ መውሰድ ያስፈልጋል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ማሳሰባቸውን ኤጀንሲው ዘግቧል ።
አገሪቱ የታዳሽ ኃይል በሆኑት የውሃ ፣ ንፋስ ፣ ፀሐይ እና የእንፋሎት የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች ላይ የምታውለው መዋዕለ ንዋይ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በበኩሏ እየተወጣች የምትገኘው ኃላፊነት መሆኑን ፤አሁንም ብዙ ሥራ ቢጠበቅም በአገሪቱ አረንጓዴ ባህልን በመፍጠሩ ረገድ ዘመቻው እንደተሳካ፤ አፍሪካ ብሎም ዓለም ተፅዕኖው እየከፋ የመጣውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል ልክ እንደ ኢትዮጵያ ተግባራዊ የአረንጓዴ ዐሻራን በመፍትሄነት ሊጠቀሙ እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መልዕክት አስተላልፈዋል ።
አረንጓዴ ዐሻራ የሕዳሴያችን ዋልታና ማገር ነው !
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሐሙስ ሰኔ 8 ቀን 2015 ዓ.ም