(የመጨረሻ ክፍል )
በክፍል አንድ መጣጥፌ ልጆች እንዴት የተንቀሳቃሽ ስልክ ወይም የሞባይል፣ የጌም፣ የማኅበራዊ ሚዲያና የቴሌቪዥን ምርኮኛ እንደሆኑ፤ ወላጆች ልጆቻቸውን ለማሳደግ እንዴት እየተቸገሩ እንደሆነ፤ እግረመንገድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት Artificial Intelligence/AI/ይዞት እየመጣ ያለውን ትንግርት በጥቂቱ ያነሳሳሁ ሲሆን በዛሬው ጹሑፌ ደግሞ ልጆችን ለሱስና ለአዕምሮ ሕመም እየዳረገ ስላለው የማኅበራዊ ሚዲያ በተለይ ስለቲክቶክ አነሳሳለሁ። በአሜሪካው ነጩ ቤተ መንግሥት የሕዝብ ጤና ተጠሪው ወይም ሰርጀን ጄነራል ዶ/ር ቪቬክ ሙርዚ የልጆችንና የወጣቶችን የማኅበራዊ ሚዲያ ሱስ የወቅቱ የሕዝብ የጤና ቀውስ ይሉታል ።
በኮቪድ ወረርሽኝ እንኳ ወጥተው ምክርም ሆነ ማስጠንቀቂያ ሰጥተው የማያውቁት ዶ/ር ቪቬክ በአደባባይ ወጥተው፤ “እንደ ኢንስታግራምና ቲክቶክ ባሉ ማኅበራዊ ሚዲያዎች የተነሳ የልጆቻችን የአዕምሮ ጤና ጉዳይ በብርቱ ያሳስበኛል።” ሲሉ ለመንግሥታቸውም ሆነ ለአሜሪካውያን የማንቂያ ደወሉን አሰምተዋል። ነግ በእኔ ነውና ነገሩ በዚህ አጋጣሚ ልጆቻችንን ከዚህ አደገኛ የቲክቶክ በአጠቃላይ የማኅበራዊ ሚዲያና የጌም ሱስና ወረርሽኝ ለመታደግና ለመከላከል ምን እየተሠራ፣ እየታሰበና እየታቀደ ነው ስል የሚመለከታቸውን አካላት መቀስቀስ እፈልጋለሁ። በይደር ወዳቆየሁት የቲክቶክ ጉዳይ ስመለስ ፦
ፋሪድ ዘካሪያ በ”ዋሽንግተን ፖስት”ጋዜጣ ፣ “Why banning TikTok won’t do any good” ወይም “ቲክቶክን ማገድ ለምን ፋይዳ ቢስ ይሆናል” በሚል ርዕስ ባስነበበን የግል አስተያየቱ፤ ሰለ ቲክቶክ ባሰብሁ ቁጥር ይበልጥ ያስፈራኛል የሚለው ፋሪድ ዘካሪያ በአንድ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ለተከታታይ ሁለት እሁዶች በዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣም ሆነ በCNN/GPS ጽፎ አያውቅም። ባልተለመደና ተከታዮቹን ባስገረመ ሁኔታ ሰለ ቲክቶክ ግን ጻፈ። ይህ የቻይናው መተግበሪያ አሜሪካንን እንዴት እንዳሳሰባትና እረፍት እንደነሳት ጥሩ ማሳያ ነው። ፋሪድ፣ ባለፈው ሳምንት የቲክቶክን መታገድ ተቃውሜ ሞግቼ ነበር ይለንና። ከተለያዩ ሰዎች ጋር ባደረግሁት ውይይት የተገነዘብሁት ነገር ቢኖር፤ የአሜሪካውያን ዋና ስጋት ቲክቶክ የቻይናዊ ንብረት መሆኑ ሳይሆን ከየትኛውም ማኅበራዊ ሚዲያ በላይ አደገኛ ሱስ አስያዥ መሆኑ ነው። ይህ ደግሞ ሁላችንን እያሳሰብ ያለጉዳይ ስለሆነ ሳንዘገይ አንድ ነገር ማድረግ አለብን።
አሜሪካውያን በ2022 ዓም ከሁሉም የማኅበራዊ ሚዲያ መተግበሪያዎች በአንደኛ ደረጃነት ቲክቶክን አውርደዋል። ሁለት ሦስተኛ የሚሆኑ የአሜሪካ ብላቴናዎች ወይም ታዳጊ ልጆች ቲክቶክን ይጠቀማሉ። ከስድስቱ አንዱ ደግሞ በቲክቶክ ሱስ ተለክፈዋል። ከ2018 እስከ 2021 በተደረገ ጥናት የቲክቶክ ተጠቃሚዎች አኃዝ በ67 በመቶ ሲተኮስ፤ የፌስቡክና የዩቲውብ ተጠቃሚዎች በ10 በመቶ ብቻ ነው ከፍ ማለት የቻለው። ቲክቶክ ምን የተለየ ነገር ቢያደርግ ነው አዳሜን እንዲህ በሱስ የሚያብከነክነው ሲል ፋሪድ ይጠይቅና መልሶ ለነገሩ ማንም አያውቅም ይለናል። በርሊን በሚገኘው ማክስ ፕላንክ ተቋም ተመራማሪ ሊቅ የሆኑት ፊሊፕ ሎሬንዝ የሚያሳዝነው ስለ ቲክቶክም ሆነ ሊያስከትል ስለሚችለው መዘዝ ብዙ የምናውቀው ነገር የለም ይሉናል። ፋሪድ ዘካሪያ ስለቲክቶክ ያለን ግንዛቤ ዝቅተኛ የሆነው ምን አልባት ማኅበራዊ ሚዲያውን ዘግይቶ ስለተቀላቀለና የተጠቃሚ ማጥመጃ ስልቱ ወይም አልጎሪዝም እጅግ የተራቀቀ ስለሆነ ይሆን ሲል ይመረምራል ።
ሌሎች ማኅበራዊ ሚዲያዎች ጓደኛህ የወደደውን ወይም ያጋራውን ተንቀሳቃሽ ምስል፣ ፎቶና መልዕክት ሲያደርሱ፤ ቲክቶክ ግን ፍላጎትህንና የምትወደውን ነገር እየገመተ አጫጭር ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ወይም ቪዲዎችን በአናት በአናቱ ያዥጎደጉድልሀል። አንዱ ያስወደደው ነገር ይህ ነው። በርካታ የሥነ ልቦና ጠበብት ቲክቶክን የሰው አዕምሮ ምግብ፣ አደንዛዥ እጽና ወሲብ ሲፈልግ ከሚያመነጨው ከዶፓሚን ወይም dopamine ንጥረ ነገር ጋር ያነጻጽሩታል። ሌላው ከሰዎች ጋር የሚያገናኘን፣ የሚያቀራርበንና ቤተሰብ የሚያደርገን ነገር ስናገኝ ደስተኛ መሆናችን ለእነ ቲክቶክ ሱስ አጋልጦናል የሚሉም አልታጡም ።
ማኅበራዊ ሚዲያ ምን ያህል አዕምሮአችንን እየተቆጣጠረው እንደ ሆነ ለመረዳት የሥነ ልቦና ሊቁን ስኪነር ንድፈ ሀሳብ ማንሳት ተገቢ ነው። “operant conditioning” በሚለው በዚህ ግኝቱ ሰዎች ጥሩ ሲሠሩ የምትሸልማቸው ከሆነ ያን ጥሩ ሥራ ደጋግመው ያከናውኑታል። ማኅበራዊ ሚዲያው በእሱ መመዘኛ ጥሩ ተሳታፊ የሆኑ ተከታዮችን ገንዘብን ጨምሮ በላይክ፣ በሼርና በኮሜንት ያበረታታል። የሚዲያው ተጠቃሚ ዩቲውበር ከሆነ ባገኘው ሰብስክሪፕሽን፣ ቪውና ላይክ መጠን ስለሚከፈለው ዩቲውበሩ የተሻለ ክፍያ እንዲያመጣለት ይጥራል ።
አንድ ዩቲውብር ቀድሞ የሚመለከተው ትላንት የጫነው ቪዲዮ ምን ያህል ሰብስክሪፕሽን፣ ቪውና ላይክ እንዳገኘና የተሰጠውን አስተያየት ነው። የቲክቶክ፣ የፌስ ቡክ፣ የቲዊተር፣ የኢንስታግራም፣ የቴሌግራምና የሌሎች ማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎችን ይሄን ነው በየዕለቱና ሰዓቱ የሚያደርጉት። ብዙ ጊዜያቸውን እያጠፉበት በሄዱ ቁጥር ሱስ እየሆነባቸው ይሄዳል። እንስሳትን ሰርከስን ጨምሮ ለተለያየ ዓላማ የሚያሰለጥኑ ባለሙያዎች የሚጠቀሙት የስኪነርን ስልት ነው። የሚሰለጥነው ውሻ የታዘዘውን ሳያዛንፍ ሲፈጽም አጥንት ሲሰጠው እንደሚበረታታው ሁሉ ማኅበራዊ ሚዲያውም እነ ላይክንና ቪውን እንደ ዶፓሚን በመጠቀም በሱስ ያጠምዳል ።
በማኅበራዊ ሚዲያ ሐያሲነቱ የሚታወቁትና በኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ጆናታን ሄይት ከማኅበራዊ ሚዲያ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የአዕምሮ ሕሙማን ብላቴናዎች ቁጥር በከፍተኛ ቁጥር እየጨመረ ነው ይሉናል። ከ2012 ዓም ወዲህ ከዓመት ዓመት በአዕምሮ ሕመም የሚሰቃዩ ሕጻናት ቁጥር በአስፈሪ ሁኔታ እየጨመረ ነው። የስሜት መዋዠቅ፣ በጭንቀት፣ በድብርትና ራስን በማጥፋት ሙከራ የተነሳ ሆስፒታል የሚገቡ ልጆች ቁጥር በአሳሳቢ ሁኔታ እያደገ ነው ።
በተለይ ሴት ልጆች ከወንዶች በባሰ በማኅበራዊ ሚዲያ የተነሳ ለተስፋ መቁረጥ፣ ለጭንቀትና ራስን ለማጥፋት በሚዳርግ የአዕምሮ ሕመም እየተሰቃዩ ነው ይሉናል ጆናታን። በ2010ዎቹ ልጆች የእጅ ስልካቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ በታጨቁ ዘመናይ ስማርት ስልኮች መተካት የጀመሩበት ክፉ ዘመን ነው። በ2009 ዓ.ም ፌስቡክ “Like”ን ቲዊተር ደግሞ “retweet”ን በማስተዋወቅ በአጥንት እንደሚደለለው ሠልጣኝ ውሻ ሰዎችን በተለይ ልጆችን ማጃጃል ጀመሩ። ፌስቡክ በ2012 ዓም ኢንስታግራምን ሲጠቀልል ልጅ እግር ተጠቃሚዎችን በብዛት የሚያጠምድበት ተጨማሪ መረብ አገኘ።
ጆናታን ሔይት የልጆች ማኅበራዊ ሚዲያን የመጠቀም መብት ከ13 ወደ 16 ከፍ ሊል ይገባል ሲሉ፤ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤቱም 16 ዓመት የሚል ረቂቅ ይዞ ብቅ ብሏል። ማኅበራዊ ሚዲያው ሙሉ በሙሉ የሰው ሠራሽ አስተውሎትን መጠቀም ሲጀምር ደግሞ ልጅ አዋቂ ሳይል አዳሜን የሱሱ ምርኮኛ ያደርጋል ሲሉ ጆናታን ፍርሀታቸውን አበክሮ ይገልጻሉ። በሳንዲያጎ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ልቦና ፕሮፌሰር የሆኑት ጄን ትዌንጌ ሰሞኑን በተወዳጁ የTIME መጽሔት ላይ እንደገለጹት።
የአሜሪካ የበሽታ መቆጣጠር ማዕከልን ወይም CDCን ጠቅሰው እንዳስታወቁት በ2021 ዓም ከሦስት አንድ የ2ኛ ደረጃ ሴት ተማሪ ራስን ስለማጥፋት ታስባለች። ከ2011 ጋር ሲነጻጸር ደግሞ ራስን የማጥፋት ሀሳቧ በ60 በመቶ አሻቅቧል። በርካታ ልጃገረዶች ደስተኛ እንዳልሆኑና ተስፋ ቢስነት እንደሚሰማቸው የተለያዩ ጥናቶች እያስታወቁ ነው። ከ2012 ዓም ወዲህ የአዕምሮ ሕሙማን ብላቴናዎች ቁጥር እያሻቀበ ነው። ከ2010 እስከ 2019 በድብርት የሚሰቃዩ ልጆች ቁጥር በእጥፍ አድጓል። ከድባቴ ጋር የተያያዙ እንደ ራስን መጉዳት፣ ራስን የማጥፋት ሙከራና ሌሎች የአዕምሮ በሽታዎች ከወንዶች ይልቅ በልጃገረዶች ዘንድ ይከፋሉ።
ከ2009 እስከ 2015 ዓም ራስን በመጉዳት በድንገተኛ አደጋ ሆስፒታል ከገቡት መካከል እድሜያቸው ከ10 እስከ 14 የሆኑ ሴት ልጆች ብዛት በሦስት እጥፍ ተመንድጓል። ይሁንና ይላሉ ፕሮፌሰር ጄን በአሜሪካ የብላቴና አዕምሮ ሕሙማን ቁጥር በአሳሳቢ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን እኔና ባልደረቦቼ ስናስጠነቅቅ ቁጥራቸው ቀላል ያልሆነ የሙያ አቻዎቻችን ይሳለቁብን ነበር ብለው ያስታውሱናል። ዛሬ ስናናንቀውና ስንክደው የኖርነው በሽታ ዋጋ እያስከፈለን ነው። ላለፉት አምስት ዓመታት የአዕምሮ ሕሙማን ልጆች ቁጥር የጤና ቀውስ ሆኗል። ፕሮፌሰር ለመሆኑ የአዕምሮ ሕሙማን ቁጥር ከዓመት ዓመት ለምን እየጨመረ መጣ ብለው ይጠይቃሉ። በ2009 ዓም ይላሉ ፕሮፌሰር አንዲት ብላቴና አብዛኛውን ጊዜዋን የምታሳልፈው ከጓደኞቿ ጋር በመጫወትና የተወሰነ ጊዜዋን ደግሞ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ነበር።
በ2016 ዓም ነገርዬው የተገላቢጦሽ ሆነ። ማኅበራዊ ሚዲያ መጠቀም ግዴታ መሰለ። 90 በመቶ የሚሆኑ ሴት ልጆች በየቀኑ ማኅበራዊ ሚዲያ መጠቀም ጀመሩ። ከጓደኞቻቸውና ከአብሮ አደጎቻቸው ጋር ወጥቶ መጫወት በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል። ይህ ደግሞ ለአዕምሮ ጤና አደገኛ ነው። ከጓደኛና ከአብሮ አደግ ጋር በአካል ተገናኝቶ መጫወት ቀረና ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ተጥዶ መዋል የሕይወት ዘይቤ ሆነ ይላሉ ፕሮፌሰር ጄን። ይህ ደግሞ አደጋ ይዞ ይመጣል። ሴት ልጆችን ለወሲብ ብዝበዛ፣ ከአካል ክፍሎች ጋር ለተያያዘ ነውር ፣ ለስድብና ለማሸማቀቅ አጋለጠ።
ይሄን ተከትሎ የአዕምሮ ሕሙማን እንደ እንጉዳይ ፈሉ። በሳንዲያጎ ዩኒቨርሲቲ የስነ ልቦና ፕሮፌሰር የሆኑት ጄን ትዌንጌ፤ ወላጆች ሆይ ልጆቻችሁ 16 ዓመት እስኪሞላቸው ወይም ከዚያ በላይ እስኪሆናቸው ከማኅበራዊ ሚዲያ አርቋቸው። ካልተቻለ ደግሞ በሚመለከቱት ነገር ላይ የቅርብ ክትትልና ቁጥጥር አድርጉ። ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የሚያጠፉትን ጊዜ ወስኑ ሲሉ ይመክራሉ ።
ይህን አሳሳቢ ችግር ለወላጆች ብቻ በመተው መፍትሔ ማምጣት አይቻልም። ማኅበራዊ ሚዲያዎች የልጆችን ማኅበራዊ ሚዲያ የመጠቀሚያ የዕድሜ ጣራ ከፍ ሊያደርጉ ይገባል። መንግሥትም ይህን የሚወስን ሕግ ሊያወጣ ይገባል ይላሉ ፕሮፌሰር። አሁን አሁን ዴሞክራቶችም ሆኑ ሪፐብሊካኖች የችግሩን ስፋትና ጥልቀት የተረዱ ይመስላል። የልጆችን ማኅበራዊ ሚዲያ የመጠቀሚያ ዕድሜ ወደ 16 የሚያሳድግና ማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ ደግሞ ዕድሜን የሚያጣራ አሠራር እንዲያስቀምጥ የሚያስገድድ፤ እንዲሁም ልጆች ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ተጥደው እንዲውሉ የሚያግባቡና የሚያባብሉ ስልቶችን እንዳይጠቀሙ የሚያስገድድ ሕግ ረቅቆ ለሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ቀርቧል ይሉናል ፕሮፌሰር።
ባይቴዳንስ የተባለ የቻይና ኩባንያ ንብረት የሆነው ቲክቶክ የተጠቃሚዎቼን የግል መረጃ ለቻይና መንግሥት አልሰጥም እያለ ቢምል ቢገዘትም ሰሚ ያገኘ አይመስልም። ከአፍጋኒስታን እስከ አሜሪካ፣ አውሮፓ ኅብረት፣ ካናዳ፣ አውስትራሊያ፣ ወዘተረፈ ድረስ በመንግሥት ተቋማት የታገደ ሲሆን አሜሪካ ደግሞ ሙሉ በሙሉ ለማገድ ሕግ አርቅቃ ለማጸደቅ ላይ ታች እያለች ነው።
የቲክቶክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሾው ቼው በበኩላቸው የቻይና መንግሥት የማንንም የግል መረጃ ጠይቆን የማያውቅ ቢሆንም የአሜሪካውያን መረጃችን በአስተማማኙ የኦራክል ክላውድ ቋት ነው የሚከማቸው። ቻይና ቲክቶክን ተጠቅማ ጸረ አሜሪካዊ የሆነ ፕሮፖጋንዳ ልትነዛ ትችላለች ስለሚባለውም ዋና ሥራ አስፈጻሚው ሲመልሱ 60 በመቶ የሚሆኑት የቲክቶክ ባለቤቶች እኮ ቻይናዊ አይደሉም ይላሉ ።
መረጃን ሆን ብሎ ማዛባትም ሆነ ፕሮፖጋንዳ ቲክቶክ ላይ ቦታ የለውም ሲሉ ቼው ይገልጻሉ። አሜሪካ በተደጋጋሚ ቲክቶክን ለመግዛት ስላቀረበችው ጥያቄ ዋና ሥራ አስፈጻሚው ሲመልሱ ቲክቶክ አይሸጥም አይለወጥም ሲሉ እቅጩን መልሰዋል። ቲክቶክ ከ15 እስከ 60 ሰከንድ የሚወስዱ አጫጭር ቪዲዮዎችን ማጋሪያ የማኅበራዊ ትስስር መድረክ ሲሆን በመላው ዓለም ሁለት ቢሊዮን ጊዜ ወርዷል ብሎኛል በሰው ሠራሽ አስተውሎት ታግዞ መረጃ የሚያፋልገውና እንደ ሰው የሚያወጋው ChatGPT ።
ሻሎም ! አሜን ።
አዲስ ዘመን ሰኔ 4 ቀን 2015 ዓ.ም