አንዲት አገር ምርታማነቷ የሚገለጸው በተለያየ ዘርፍ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ የተለያዩ ቴክኖሎጂን በመጠቀም በግብርናው ዘርፍ የተሻለ በማምረት ውጤታማ ልትሆን የምትችል አገር እንዳለች ሁሉ በኢንዱስትሪው ዘርፍ ደግሞ ብዛትና ጥራት ያለው ምርት በማምረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተደራሽነቷን የምታሰፋ አገር ልትኖር ትችላለች።
ከምርታማነት አኳያ ሲታይ ደግሞ በተለይም የኢንዱስትሪ መስፋፋት ጠቀሜታው ዘርፈ ብዙ ነው። አንዲት አገር የትኛውንም የምርት አይነት በጥራትና በብዛት ማምረት የሚያስችላትን አቅም ስታዳብር የዜጎቿን ጥያቄ ለመመለስ አትቸገርም፡ የኢንዱስትሪ መስፋፋትም በመጀመሪያ ከተሞች በተገባቸው ልክ የማደግና የመስፋፋት እድል እንዲኖራቸው ከማድረጉም ሌላ የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር ይፈታል።
እንደሚታወቀው በአሁኑ ወቅት አገራችንን እየፈተናት ያለው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ችግር እንደመሆኑ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ተገዝተው ወደአገር የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ በማምረት ይወጣ የነበረውን ወጪ ማዳን ይቻላል። በአገራችን እየተመረተ ያለው የግብርና ምርትን ከኢንዱስትሪው ጋር በማስተሳሰርም ሁነኛ ግብዓት እንዲያገኝ ስለሚያደርግ አርሶ አደሩንም ተጠቃሚ በማድረጉ በኩል አይነተኛ ሚና እንዳለው የሚታወቅ ነው።
ይህን በአግባቡ የተረዳው መንግሥትም ከዓመት በፊት ‹‹ኢትዮጵያ ታምርት›› በሚል መሪ ሐሳብ ያስጀመረው ንቅናቄ ከኢንዱስትሪው ዘርፍ ሊገኝ የሚችለውን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ለመቋደስ የሚያስችል እንደሆነ እሙን ነው። በቅርቡም ንቅናቄው የተጀመረበትን የመጀመሪያ ዓመት ምክንያት በማድረግ በሚሊኒየም አዳራሽ አንድ መርሐ ግብር መካሔዱም ይታወቃል።
እርግጥ ነው ኢትዮጵያ ልታሳካ ከያዘችው የብልጽግና እቅድ አኳያ ሲታይ የ‹‹ኢትዮጵያ›› ታምርት ንቅናቄ የጀርባ አጥንት ነው። የዚህ የንቅናቄው ዓላማም በኢንዱስትሪው ዘርፍ ያለውን ችግር ለመፍታት እና ምርታማነትን ማሳደግ ነው። ይህ በራሱ በጎ ሐሳብ ሲሆን፣ ለተፈጻሚነቱ ግን ቅድመ ሁኔታዎች መኖራቸው የማይዘነጋ ጉዳይ ነው።
ስለዚህ ኢትዮጵያ ኢንዱስትሪዎቿ በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ አስተማማኝ የግብዓት አቅርቦትን ይሻሉ። በዚህ በኩልም በአገራችን እየተደረገ ያለ ጥረት የሚያበረታታ ነው። በተለይም በግብርናው ዘርፍ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተጣለ ያለ መሠረት ላይ ሁሉም የየበኩሉን ሊያበረክት ግድ ነው። በአንድ ዓይነት የአመራረት ሥርዓት ላይ የሙጥኝ ብለን የኢትዮጵያን ብልጽግናን ለማረጋገጥ አይቻልም። ግብርናን ዘመናዊ በሆነ ቴክኖሎጂ በመደገፍ ሁለትና ሦስት እርምጃ ወደፊት ማስፈንጠር ይቻላል። ይህ እድል ያለው በእጃችን ነው። እውነት ለመናገር ደግሞ አገራችን የውሃም ሆነ የመሬት ችግር የለባትም። የዚህ መኖር ‹‹ኢትዮጵያ ታምርት›› ለሚለው ንቅናቄ ያው አስተዋፅዖ ላቅ ያለ ነው።
ከዚህ ጎን ለጎን የተፈጥሮ ሀብቱን ብቻ ስለተቸርን የሚመጣ ተዓምር የለምና በሰለጠነ የሰው ኃይል የተሻልን ሆነን መገኘት የግድ ነው። ይህ ደግሞ ተነሳሽነትን እንጂ የተለየ ወይም በሌላ አገር ሄዶ መሰልጠንን የግድ አይልም። ዋናው ነገር አገርን በማሳደጉ ረገድ በሚደረገው ርብርብ ውስጥ ራስን ተሳታፊ በማድረግ የሚጠበቅብንን አስተዋፅዖ ለማበርከት መዘጋጀት ነው።
ይህ በእርግጥ ቅንጅታዊ የሆነ አሠራርን ይፈልጋል። አንዱ በግብርናው ዘርፍ ሌላው ደግሞ በኢንዱስትሪው ዘርፍ መሳተፍ ሲችል (ማዕድንም ሌላው ሀብታችን መሆኑ ሳይዘነጋ) የሰመረ ውጤት ማስመስገብ ይቻላል። ለሁለቱም ዘርፎች ስኬታማነት የኃይልም ሆነ የብድር አቅርቦቱ ተፈላጊ በመሆናቸው በዚህ ረገድ ያለው እንቅስቃሴም ለ‹‹ኢትዮጵያ ታምርት›› ንቅናቄ ዋናዎቹ መሆናቸው እሙን ነው።
ኢትዮጵያ በዜጎቿ ቀና ቅንጅት እንዲሁም ባሏት ኢንዱስትሪዎች በሙሉ አቅሟ ማምረት ትጀምር እንጂ በቀጣናው ያሉ አገራትም ሆኑ በአህጉሩ ያሉ አገሮች ብሎም ከአህጉራችን ውጪ ያለው የገበያ እድል በርካታ ነው። ብዙ ሩቅ መሄድ ሳያስፈልግ ከሩቅ ምሥራቅ ወደ አህጉራችን በገፍ የሚገባ ምርትን መተካት ለመቻል መሥራት በራሱ አንዱ በቅርብ ያለ የገበያ ዕድል መሆን የሚችል ነው።
ኢትዮጵያ በደንብ ስታመርት ዋናውና አሁናዊ አንገብጋቢ ጉዳይ የሆነው የሥራ አጥነት ጥያቄን በአግባቡ መመለስ ይቻላል። ኢኮኖሚዋም የሚያንሰራራ ከመሆኑም ባሻገር በብዙ ደጅ ጥናት የሚገኘውን የውጭ ምንዛሪን ለማግኘት ዋና በር መሆን ይችላል። ስናመርት የሥራ እድልን መፍጠር ብቻ ሳይሆን የሥራ ባሕልንም ጭምር እያዳበርን መሄድ ያስችለናል። ይህ ብቻ አይደለም፤ የአገራችን ሕዝብም የአኗኗር ዘይቤው ይቀየራል።
ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነቷ ከዓመት ዓመት እየተሻሻለ ሲመጣ ግብ አድርጋ የያዘችው እቅድ ስኬታማ መሆን ይችላል። በቀጣዮቹ ዘጠኝ እና አስር ዓመታት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪው አገራዊ የምርት ድርሻው ከስድስት ነጥብ ዘጠኝ በመቶ ወደ 17 ነጥብ 2 በመቶ ወደተቀመጠው ግብ መድረሱም አይቀሬ ይሆናል።
ይሁንና ለማምረት አገር ሰላም መሆን አለበት። ይህ ዋና ቁልፍ ጉዳይ ነው። በጥራት እና በብዛት አምርቶና ተወዳዳሪ ሆኖ መገኘት ብቻ የችግር ሁሉ መፍቻ ቁልፍ ሊሆን እንደማይችል ሊታወቅ ይገባል። በጥራትም ሆነ በብዛት የተመረተን ምርት ወደ ዓለም ገበያ ለማድረስም የቀጣናችን ብሎም የአህጉራችን እና የዓለማችን ሰላም መሆን ፋይዳው ወሰን የለውም። ምክንያት ቢባል ለአምራች ኢንዱስትሪው ሰላም ዋና ቁልፍ ጉዳይ ነው።
ሰላም መሠረታዊ ጉዳይ ነው ለማለቴ ሌላው ማሳያ የማምረቻ ኢንዱስትሪ ዕድገት ሊረጋገጥ የሚችለው ከኢንቨስትመንት መስፋፋት ጋር ተያይዞ በመሆኑ ነው። እንደሚታወቀው ኢንቨስትመንትን መሳብ የሚቻለው የመጀመሪያ የሰላም መረጋገጥ እንደሆነ ግልጽ ነው። ሌላው ደግሞ ሌሎች ለኢንቨስትመንት አስፈላጊ የሆኑ ምቹ ሁኔታዎች ናቸው።
ሐቁን ለመናገር በአንዲት አገር ሰላም ታጣ ማለት የጥይት ድምጽ እየተሰማ ነው ማለት ብቻ እንዳልሆነ የሚታወቅ ነው። ሰላም የለም ለማለት ከሚያስደፍረው መካከል አንዱ ለሌላው ጀርባ ሲሰጥም ጭምር እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባል። ሰላም ከእርስ በእርስ ሰላማዊ ግንኙነት የሚጀምር እና አንዱ ለሌላው ቀና ማሰብ ሲችል የጭምር ነው። ሰላም የራስን ዙሪያ ያለማስደፈር ብቻ ሳይሆን ለጎረቤትም ጭምር መሟገት ሲቻል ነው።
ስለዚህም ‹‹ኢትዮጵያ ታምርት›› ንቅናቄ የበለጠ ጎልብቶ በእርግጥም ኢትዮጵያ በኢኮኖሚዋ እንድታንሰራራም እንድትበለጽግም ወሳኙ ሰላምም ጭምር ነው። ስለሆነም ሰላም ለኢትዮጵያችን፣ ሰላም ለቀጣናችን፣ ሰላም ለአህጉራችን እና ለዓለማችን መሆኑ የግድ ነው። የኢትዮጵያ በሙሉ አቅም ማምረት ደግሞ ለምርታማነት፣ ለልማት ብሎም ለድህነት ቅነሳ ላቅ ያለ አስተዋፅዖ አለውና ከዚህ ምርታማነት ለመቋደስ ሰላም ይብዛልን!!!
ወጋሶ
አዲስ ዘመን ሰኔ 4 ቀን 2015 ዓ.ም