(ክፍል አንድ)
በእኔ ትውልድ ወላጆቻችን በሰፈሩ የሚታወቅ ባለጌ ልጅ ካለ ከእሱ ጋር እንዳንገናኝ እንዳንውል ከማስጠንቀቂያ ጋር እንመከርና እንዘከር ነበር ። አንድ ቀን አብረን ከታየን ማታ ቁንጥጫና ኩርኩም ይጠብቀናል ። ሁለተኛ ከዚህ አሳዳጊ ከበደለው ጋር አይህና ፤ ሁለተኛ እየተባልን ጭናችን አጋም እስኪመስል ይመዘለግ ነበር ። አጥፍተን ከተገኘን ደግሞ ከዚያ ስድ ጋር እየዋልህ ድሮስ እንባላለን ። ከአህያ ጋር የዋለች ላም ፈ* ተምራ ትመጣለች እየተባለ ይተረትብናል ።
በሰፈሩ በትምህርቱ ጎበዝና ለወላጆች የሚታዘዝ ልጅ ካለ ደግሞ የእሱን ሰብዕናና ባህሪ እንድንላበስ አጋጣሚ እየተፈለገ ከእነ ወላጆቹ ስሙ ይነሳል ። ወላጆቻችን ሥነ ልቦናን አስኳላ ገብተው ባያጠኑም የአቻ ለአቻ ግፊት ወይም ተጽዕኖ በአዎንታም ሆነ በአሉታ በልጆች ሰብዕናና አስተዳደግ ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ አበክረውና ጠንቅቀው ያውቃሉ ። ያደግንባት ከተማ ጠባብ ስለነበረች ስለትምህርት ቤት አዋዋላችንም ከአስተማሪዎቻችን በቀላሉ ወሬ ማግኘት ስለሚችሉ ያን ያህል አይቸገሩም ነበር ።
አሁን አሁን ግን ከተሞች በመስፋታቸውና የተማሪዎች ቁጥሩም የዛን ያህል በመጨመሩ የወላጅን ክትትል ከባድ አድርጎታል ። እንደ አዲስ አበባ ባሉ ትላልቅ ከተሞች ደግሞ ይብስ ያዳግታል ። በእንቅርት ላይ እንዲሉ በአናቱ ላይ ማህበራዊ ሚዲያ ተጨምሮበት ልጆችን በሥነ ምግባር ኮትኩቶ ማሳደግ ፈታኝ እየሆነ ነው ። የሚማሩበትን ትምህርት ቤትና ጓደኞቻቸውን መምረጥ ብንችልም ፤ የማህበራዊ ሚዲያ ወይም የቨርቹዋል አለሙን ጓደኞቻቸውን ግን መምረጥም ሆነ መከታተል ይቸግራል ። አሁን አሁን ልጆች ከእኩዮቻቸው ጋር ጭቃ አቡክቶ ቦርቆ ከመጫወት ይልቅ ቴሌቪዥንና እጅ ስልክ ላይ መጣድን ይመርጣሉ።
እኔ በምኖርበት የጋራ መኖሪያ ቤት ቅዳሜና እሁድ ሆነ በአዘቦት ከትምህርት ቤት ሲመለሱ በእረፍታቸው ውጭ ወጥተው ሲጫወቱ አላይም ። ድንገት መብራት ሲጠፋ ግን ቴሌቪዥን ስለሚቋረጥ ፣ ብሮድ ባንዱም ስለማይሰራ ከየቤታቸው መውጣትና ሰፈሩን መቀወጥ ይጀምራሉ ። በዚህ መሃል መብራት ከመጣ ሰፈሩን በጩኸትና በፉጨት ያደበላልቁና ወደየቤታቸው ይመለሱና ሰፈሩ መልሶ ጭር ይላል ። ሩጦና ዘሎ ያላደገ ህጻን አካላዊም አእምሯዊ ብቃቱ ላይ የሚያመጣውን ተጽዕኖ ለአፍታ አስቡት ።
የእጅ ስልክ ምርኮኛ እየሆኑ ነው ። ዘመድ ቤት ሲመጣም ሆነ እናንተ ዘመድ ጥያቄ ስትሔዱ ሁለት ዓመት ያልሞላቸው ህጻናት ሳይቀሩ ጠጋ ብለው የእጅ ስልክን ተቀብለው ከአንድ አንድ ጌም ፍለጋ ነው የሚገቡት ። ሁለት አመት ያልሞላት የእህቴ ልጅ ቤት ስትመጣ ስልኬን ለመቀበል ነው የምትሽቀዳደመው ። መጣጥፎችን በእጅ ስልኬ ስለምጽፍና ብዙ ዶክመንት ስለሚይዝ ታጠፋብኛለች ብዬ ስለምፈራ ስለማልሰጣት ሁል ጊዜ በመጣች ቁጥር ጸብ ነው ። ስታለቅስ ሌላ ስልክ ሰጥተው ያባብሏታል ።
ልጅ ሲያለቅስ በከረሜላ በቼኮላት ሳይሆን የሚደለለው በስልክ ሆኗል ። ይህ የስልክ ፍቅር አብሮ ያድግና ከፍ ሲሉ ስልክ ካልተገዛልን ከወላጅ ጋር ጸብ ነው ። መቼም ወላጅ የሚኖረው ለልጆቹ ነውና እነሱን ለማስደሰት ቢያጣም ተበድሮና ተለቅቶ ገዝቶ መስጠቱ አይቀርም ። ስልኩን ገዝቶ ይስጥ እንጂ አጠቃቀሙ ላይ ቁጥጥር ስለማያደርግ ልጆቹ በጌምና እንደ ቲክቶክ ባሉ የማህበራዊ ሚዲያ ሱስ ይጠመዳሉ ። ለከፉ ሌሎች አደጋዎችም ሊጋለጡ ይችላሉ ። ሱሱ ያድግና ለተለያዩ የአእምሮ ሕመሞች ይዳርጋቸዋል ።
ለጭንቀት ፣ ለድብርት ፣ ራስን ለመጥላትና ራስን ለማጥፋት ይጋለጣሉ ። ዛሬ ልጅን አሳድጎ ለወግ ለማዕረግ ማብቃት ፈታኝ እየሆነ ነው ። ልጆቻችን ከእጃችን እያመለጡን ነው ። ከእድሜያቸው ቀድመው ለተለያዩ እኩይ ተግባራት እየተጋለጡ ነው ። ችግሩ ዓለምአቀፋዊ ነው ። መጠኑ ይለያይ እንጂ ምዕራባውያን በዚህ እየተፈተኑ ነው ። ቢቸግራቸው ማህበራዊ ሚዲያዎች የእድሜ ገደብና የይዘት ክልከላ እንዲያደርጉ ግፊት ቢያደርጉም የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ስላልሆነ ከእነ አካቴው ይታገዱ እስከማለት ደርሰዋል ።
አሜሪካ ቲክቶክን ለማገድ የሄደችበትን እርቀትና በልጆች አእምሮ ላይ ስለደቀነው አደጋ ለመሞነጫጨር እየጎለጎልሁ ሳለ ፤ አሳፍ ሃይሉ የተባሉ ጸሐፊ ስለ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ወይም Artificial Intelligence /AI/፤ “ያለንበት የኤአይ ዘመን”በሚል ርዕስ ፌስቡክ ላይ ያጋሩንን ማለፊያ ጽሑፍ ስለወደድሁት እናንተስ ለምን ይቅርባችሁ ብዬ ላካፍላችሁ ወደድሁ ። ከዚያ ወደ ተነሳሁበት መጣጥፍ እመለሳለሁ ።
“ይሄን ፎቶ የፈጠረው ኤአይ ነው! ተገረምክ?! ማነው ይሄ ኤአይ የተባለ ሰው? ወይ ካሜራ? የማወራው ስለሰው ስም አይደለም! የዘመኑን ቴክኖሎጂ ነው። ኤአይን። ይሄ ኤአይ (AI/Artificial Intelligence) ስለሚሉት የቴክኖሎጂ ጉድ…፣ አስገራሚ የዘመኑ ተአምር ነው የማወራው! ኤአይ በአሁኑ ጊዜ… የማይሠራው ተአምር የለም! የሰውን ልጅ ሜካኒካል ሥራዎች ሁሉ መተካቱ አንሶ… ወደ ፐርሰናላይዝድ ፕሮፌሽኖች ሁሉ ከገባ ቆየ።
ሃኪም ሆኖ ይመረምራል ። ህመምተኛን ያክማል። መድሃኒት ያዛል። ፖሊስ ሆኖ ይቆጣጠራል። አጥፊውን አሳዶ ይይዛል ። ይቀጣል። ፋብሪካዎች ውስጥ ይፈበርካል፣ ይገጣጥማል፣ ቴስት ያደርጋል ፣ ጥራትን ይቆጣጠራል ። ቤቶችን ይገነባል ። ይተክላል። ይለካል ። ያድሳል ፣ ያፀዳል ። ጦርነትን ይዋጋል ። የጦር ጄት ያሽከረክራል ። ታንክ ያነጣጥራል ። ዒላማን ይመታል ። መመታትና አለመመታቱን፣ የደረሰን ጉዳት ይለካል ። የቢዝነስን አዋጪነት ይገመግማል ። ትርፍና ኪሣራን አስቀድሞ ይተነብያል ።
ሠራተኛ ለመቅጠር ተስማሚው ሰው የቱ እንደሆነ በቀላሉ ይጠነቁላል። ባንክ ቤት ያንቀሳቅሳል። አየር መንገዶችንና ባቡር ጣቢያዎችን ያንቀሳቅሳል ያለድካም። 24 ሰዓት ይሠራል። አይደክመውም። አሁን አሁን ሃኪሞችና ሕግ አስከባሪዎች ሥራቸው የኤአይ ሮቦቶች ረዳት መሆን ሆኗል ። ማሽኖቹ ሁሉንም ነገር እያነበቡ፣ እየመረመሩ ይናገራሉ። ይፈርዳሉ። ሌላ ቀርቶ ከሃኪሙ በፊት መሞትህንና አለመሞትህን የሚያረጋግጠው ኤአይ ነው።
ልጅ ወልደህ… ከ1 ሺህ በላይ በሳይንስ ከተረጋገጡ የተለያዩ የጤና እክሎች ነፃ መሆኑንና አለመሆኑን ከእግዜሩ ቀድሞ የሚበይነው የኤአይ አልጎሪዝም ነው። ኤአይ ሥራው ብዙ ነው። ብዙ ሆኗል። ጉድ ነው! የዘመኑ ጉድ ሆኗል አርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ። ታዲያ በአርቱም ዙሪያ… መጀመሪያ በኤአይ ዲዛይኑን ካወጡ በኋላ… ከኤአይ የሚኮርጁ አርቲስቶች እየበዙ መጥተዋል። በኤአይ የሚደገፉ አርቲስቶችማ ተፈቅዶላቸዋል። ማን ከልክሏቸው። በአርት ውስጥ ደግሞ የሰው ልጅ አዕምሮ ሊደረስባቸው አይችሉም የሚባሉ የዲዛይን ዓይነቶችን ይፈጥራል። እንደየጠያቂው ፍላጎት በፍጥነት ሠርቶ ያቀርባል። በቅርቡ አዲስ ለዓለም ህዝብ በነፃ የተለቀቀ “ዳሊ 2”/DALL•E/የተሰኘ የአርቲስቲክ ኢሜጀሪ የኤአይ አልጎሪዝም፣ በጥቂት ሰከንዶች ውስጥ 650 ሚሊዮን ኢሜጆችን (የተለያዩ ምስሎችን) አስሶ… የምትፈልገውን የምስል ዓይነት ፊትህ ከነአማራጩ ገጭ ያደርግልሃል።
ሰባራ ሳንቲም አያስከፍልህም። በነፃ። ከፈለግክም የምትፈልገው ስዕል ወይም ኢሜጅ ምን ዓይነት እንደሆነ በቃላት ትፅፍለታለህ… ከመቅፅበት ሃሳብህን ተቀብሎ ተቀብሎ.. 650 ሚሊዮኑን ካዝናውን አስሶና አዳቅሎ የምትፈልገውን ነገር እፊትህ በሰከንዶች ውስጥ ገጭ ያደርግልሃል።
እና አሁን አንድ አርቲስት ሥራውን ይዞ አደባባይ ሲወጣ፣ የትኛው በኤአይ የተመከረው ሥራ እንደሆነ፣ የትኛውስ ከራሱ ጭንቅላት ያመነጨው እንደሆነ መለየት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በአሁኑ ወቅት ታላላቅ የጥበብ መዘክሮች ሁሉ ሳይወዱ በግድ ይህን የዘመኑን የቴክኖሎጂ ጉግማንጉግ ለመከላከልም ሆነ ለመጠቀም ባለሙያዎችንና ቴክኖሎጂዎቹን ሳይወዱ እየታጠቁት ነው። ትተኸው፣ እንደሌለ ቆጥረኸው መኖር አትችልም። አለዚያ ይወርስሃል። ባጠቃላይ እስከዛሬ በዘመናት ሂደት የነበረውን የሰው ልጅ ያደረጀውን ሰውኛ የሆነ ነገር ሁሉ ኤአይ እንዳልነበር እያደረገው ነው። ወይም እየተዋጠ ነው። ሮቦቱ በሰው አዕምሮ ሥራዎች ውስጥ ረዳት ሆኖ ገብቶ፣ አሁን የሰው አዕምሮ ሮቦቱን እየኮረጀው ነው። ሰውን ከጨዋታ ውጭ እያደረገው ነው።
ከእንግዲህ በኋላ የፒካሶና የካንዲኒስኪን ሥራዎች፣ ወይ የዳቪንቺንና የሚካኤል አንጄሎን ሥራዎች ሳይሆን የምታገኘው.. የታወቀ የኤአይ ሶፍትዌር ያወጣውን አስደማሚ ዲዛይን ብቻ ይሆናል! ኦርጋኒክ አርት በፍለጋ ላይገኝ ነው በቃ! ኤአይ ያልገባበት የሰው ልጅ ውጤት የሚገኘው ምናልባት በማዳጋስካርና በአንጨቆረር እርሻዎች ውስጥ ሊሆን ይችላል። እዚያም ቢሆን ምናልባት የምርጥ ዘሩንና የማዳበሪያውን ደረጃ አስቀድሞ የወሰነው ኤአይ ሊሆን ይችላል። ዩቫል ኖአህ ሃሪሪ ይህ ሁሉ እንዲህ ያደባባይ ምስጢር ከመሆኑ በፊት በትክክል አስተውሎ ተንትኖታል። ተንብዮታል። ሌሎችም። አሁን አሁን ብዙ የባለሙያ ጭንቅላት የሚጠይቁ የነበሩ የሥራ ዘርፎች በአርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ እየተተኩ ነው።
በነገራችን ላይ አንዳንድ የምዕራቡ ዓለም ሀገሮች… ካሁኑ በተወሰነ የሙከራ ደረጃ ጀምረውታል። ሠራተኛን በኢአይ እየተኩ፣ ዜጎቻቸውን UBI (Universal Basic Income) እየከፈሉ ያለሥራ ማኖርን። አውስትራሊያ፣ ካናዳ፣ ዘ ኔዘርላንድስ፣ ኒውዚላንድ፣ ወዘተ እየሞከሩት ነው። ዜጎቻቸውን ቁጭ አድርጎ ለኑሮው በቂ የሆነ ገንዘብ እየደጎሙ ማኖርን። አንዳንዶች ይህን ሽግግር የሰው ልጅ ከደሞዝ ባርነት የሚወጣበት የኤአይ ዘመን ላይ ደረሰን፣ ነፃ ወጣን ይሉታል።
ሌሎች ብዙዎቻችን ደግሞ፣ የሰውን ልጅ ኤአዮች ቅርጥፍ አድርገው የበሉበት የቶማስ ሙር የበጎች ዘመን ዳግመኛ መጣ እያልን ስጋት ገብቶናል። ድሮ በኢንደስትሪያላዜሽን ዘመን ለዘመኑ ዘመናዊ የሆኑ የሱፍ ጨርቅ ፋብሪካዎች የአውሮፓን ምድር ሲያጥለቀልቁ.. ኑሯቸውን በእርሻ የሚገፉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ገበሬዎች ከየማሳቸው ላይ ተፈናቀሉ። እርሻዎች የበግ እርባታና ግጦሾች ሆኑ። አራሾች የከተማ ጭሰኞች ሆኑ! ያኔ ነበር ኋላ ‹‹ሰር›› የሚል የክብር ማዕረግ ‹‹ቅዱስ›› ከሚል የመለኮት ካባ ጋር የተደረበለት ደራሲ ቶማስ ሙር ‹‹በጎች ሰዎችን በሏቸው›› ብሎ የጻፈው። አሁን ደሞ “ኤአዮች ሰዎችን እየበሉ ያሉበት ዘመን” ነው። ያለማጋነን! ከእንግዲህ ፕሮፌሽን አይኖርም። ሥራ አይኖሩም። የማይሠሩ እጆች ይበላሉ። ኤአይ ይሠራል። እኛ ተኝተን እንበላለን። ጊዜ ይተርፈናል። የፈለግነውን ነገር እንፈጥራለን። ወይ ደሞ.. የምንፈጥረው ሲያልቅብን… የተፈጠረውን ሁሉ በሙሉ ጊዜ ተሰማርተን እናወድማለን።
ይህን ፎቶ ተመልከቱት። ኤአይ የፈጠረው ነው። እንግዲህ እንደ ዳሊ-2 የምስል አልጎሪዝም ሁሉ አንድ የዲጂታል አርቲስት… ‹‹እስቲ ሊዮናርዶ ዳቪንቺን ከሞናሊዛ ጋር ቁጭ ብሎ እያወራ.. እና የሞናሊዛ ስዕል ደግሞ ከጀርባቸው ተሰቅሎ የሚታይበት… የቆየ ባር የሚመስል ስዕል አውጣልኝ›› ብሎት ይሆናል ለኢአዩ (ሳስበው)! ከዚያ ኤአዩ ‹‹እኔን ነው?›› ብሎ ከተፍ ያደርግለታል። ‹‹ይሄንን ነው?›› እንዲህ ነው የፈለግከው? ይኸው! .. እና ኤአይ በዚህ መልክ በሰከንዶች የፈበረከውን ፎቶ… በ1504 ዳቪንቺ ከሳላት ሞናሊዛ ጋር የተነሳው ፎቶግራፍ ነው እየተባለ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ የማህበራዊ ሚዲያ ዕድምተኞች እየተቀባበሉት ነው። ካሜራና ምስል የተፈለሰፈው በ1800ዎቹ! ይሄ የዳቪንቺ ፎቶ ተነሳ የሚባለው ካሜራ ከመወለዱ ከ300 ዓመታት በፊት! እና ግን እውነት ስለሚመስል የሶሻል ሚዲያው ህዝብ ያለጥያቄ ተቀብሎ እያጋራው ነው!
አሁን እውነቱንና ውሸቱን ራሱ ለመለየት የሚቸግርበት ጊዜ ስለሆነ… ይሄ ፎቶ ትክክለኛ ፎቶ ነው ወይ? ብለህ ራሱ የምትሰጠው.. ለኤአይ ነው። ጌታ ኤአይ ትክክል አለመሆኑን ይነግርሃል። ካልነገረህ ግን.. ትክክል ነው ማለት ነው። ሙዝየም ገብቶ የባለፊርማው የጥበብ ሥራ ነው ተብሎ ይሰቀላል። አበቃ። ሰው ሃሳብ ትቶ ፣ ኮምፒውተሮችና አርቴፊሻል ኢንተሊጀንሶች፣ ሮቦቶችና አልጎሪዝሞች ደግሞ እያሰቡ ያለንበት ዘመን ነው። ማሰብን ለሌላ በመስጠታችን፣ ሕይወት እየቀለልን ነው። ማሰብ ሰውን ከሮቦት የሚለየው ነገር የሚሆንበት ጊዜ ሩቅ አይመስለኝም። ያውጣን አንድዬ ነው የሚባለው? ወይስ እንኳን አደረሰን! ግልግል?! አላውቅም! ኤአይ ግን እንዲህ ሆኗል።
በነገራችን ላይ ይሄን ፅሑፌን ራሱ ለማህበረሰብ ህሊና ይቃረናል፣ አይቃረንም ብሎ የሚወስነው ኤአይ ነው። ኤአይ ካልፈቀደ ይሄ ፅሑፌ ራሱ ለዕይታ አይበቃም። (ኤአይ ይወቅልኝ እንግዲህ! አንድዬን አላስቸግረውም!) .. እና ባዕድ አምልኮ ማለት ከዚህ በላይ ምን ትርጉም አለው? ከእነዚህስ ምልክቶች በላይ የ8ኛው ሺህን መጠጋት የሚያበስር ሌላ ጠቋሚ ማስረጃ ከየት ይገኝ?… ። “
ወደ ተነሳሁበት መጣጥፍ ስመለስ በፋሪድ ዘካሪያ የዋሽንግተን ፖስት መጣጥፍ እነሳለሁ ። “ የሁለት ሴት ልጆች አባት ስለሆንሁ ግማሹ ልቤ ቲክቶክ ቢታገድ ይለኛል ። በሚያስፈራ ሁኔታ ሱስ አስያዥ ስለሆነ ። በአሜሪካ 150 ሚሊዮን ሰዎች የቲክቶክ ተጠቃሚዎች ሲሆኑ ፤ ከሶስቱ ተጠቃሚዎች ሁለቱ ነፍስ ያላወቁ ብላቴናዎች ወይም ልጆች ናቸው ።
ልጆች ለቲክቶክ ሱስና ለአእምሮ በሽታዎች ማለትም ለጭንቀት ፣ ለድባቴ ፣ ራስን ለማጥፋት ለሚገፋፋ ስሜት እየተዳረጉ ነው ። አሜሪካውያንን ጨምሮ በመላው ዓለም የሚገኙ የሥነ አእምሮ ሊቃውንትና ፖለቲከኞች ከቲክቶክ ጋር በተያያዘም ሆነ ስለተቀረው ማህበራዊ ሚዲያ ልጓም ለቆ ቼ ፈረሴ ይቁም ። ሳይቃጠል በቅጠልን እየለፈፉ ነው ። በቀጣይ መጣጥፌ ሰፋ አድርጌ እመለስበታለሁ ።
የዛ ሰው ይበለን ! ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 1/2015