ሞጋቹን እንዘክር፤
“ደግ አይበረክትም” ይለናል ጥንታዊው ብሂላችን:: አንዳንዶች ይህ አባባል “ተስፋን በእግር ብረት የሚያስር የጨለምተኝነት መገለጫ ነው” ብለው ይቃወማሉ:: መከራከሪያ ሃሳባቸውም “ጽድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም፤ ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም” የሚለው ዕድሜ ጠገብ ሕዝባዊ ግጥም ነው:: የሁለቱም ጎራ ተሟጋቾች እምነታቸውንም ሆነ መርሃቸውን እየጠቀሱ “በእንካ ሰላንትያ” ቢፋለሙ መብታቸው ነው:: “በዘመነ ነፃነት ስለምን እንዲህ አሰብክ ወይንም አሰብሽ እንደማይባል ‹ላይኖርበት ኑሩበት›” እየተባለ የሚሰበከልን “የጠፍ ርዕዮተ ዓለም ማማለያው ዲሞክራሲ” አጥብቆ ይመክረናል::
በዚህ ጸሐፊ አመለካከት “ደግ ያለመበርከቱን” ከሚያረጋግጡ ስፍር ቁጥር ከሌላቸው ማስረጃዎች መካከል የዋናው ርዕሳችን የ“እስኪ ተጠየቁ” ባለመብት የነፍሰ ሔሩ ባለቅኔ የዮሐንስ አድማሱ(1929-1967 ዓ.ም) ዜና መዋዕል በሚገባ ያረጋግጥልናል:: “የደግ ሰው ሌማቱ አይከደንም” እንዲሉ አበው::
ዮሐንስ አድማሱን ያስታወስነው በግለ ታሪኩና በሥራዎቹ ላይ ጥልቅ ሂሳዊ ትንተና ለመስጠት በማሰብ ሳይሆን የጽሑፋችንን ዋና ርዕስ ከእርሱ ሥራዎች መካክል መርጠን መዋሳችንን ለመዘከርና በጥቂቱም ቢሆን ስለ “እስኪ ተጠየቁ” ግጥሙ ዋና መልእክት አጭር ማስታወሻ ለማኖር ነው:: የባለቅኔው የምድር ጉዞ በ1967 ዓ.ም በ37 ዓመቱ የተጠናቀቀው በይፋ ባልተገለጸና ባልተብራራ ምክንያት ነበር:: ይህንን መጥቀሳችን እስከ ዛሬ ቢኖር ኖሮ ምን ያህል የሥነ ጽሐፍ ምርት ማምረት ይችል እንደነበር ምኞታችንን በቁጭት ለመግለጽ ነው::
“ሞት እንኳን ጨክኖ ወስዶ ከሚያስቀረው፣
ምናለ ደጋጉን ዳግመኛ ቢፈጥረው::
የሚመለስ ቢሆን እንደ ሞተ ባይቀር፣
ያሰኛል አንዳንዱ ዳግመኛ ቢፈጠር:: ”
እንዳለው ድምጻዊ “ሞትን በደርሶ መለስ እንደማናሸንፈው” እያወቅንም ቢሆን መመኘቱ አንድም ለአክብሮት፣ አንድም ለትውስታ መቀስቀሻ ስለሚረዳ “ቢሆን ኖሮ” ማለቱ ክፋት የለውም::
በእጅጉ የሳሳንለት ተዘካሪው ባለቅኔ “ያ ትውልድ” እየተባለ በሚጠቀሰው ዘመን የኖረና እንደ ተወርዋሪ ኮከብ ብልጭ ብለው ከከሰሙት አፍቃሬ ለውጥ ትንታግ ምሁራን መካከል አንዱ ነበር:: ባለቅኔው ወደፊት ከስመው ስለሚጠፉት ዘመነ አቻዎቹ ቀደም ብሎ ታይቶት ነው መሰል “ተወርዋሪ ኮከብ” በሚል ርዕስ የጻፈው ዘለግ ያለው ግጥሙ አርቆ አሳቢነቱን በግልጽ የሚያሳይ ነው:: ጥቂት ስንኞችን እንጥቀስ::
ተወርዋሪ ኮከብ የደረሰው ቦታ የጨለመ ምድር፣
አይታይም ነበር::
ጨለማ አካል ገዝቶ፤
ይዳሰስ ነበረ በየቦታው ገብቶ::
ተወርዋሪ ኮከብ በራሱ ነበልባል በራሱ ነዲድ ተቃጥሎ የጠፋ፣
ተወርዋሪ ኮከብ በምናውቀው ሰማይ ነበረ በይፋ::
ሲቃጠል ያየነው ዛሬ ትናንትና ነገ ሥልስትና ሲደጋገም ወትሮ፣
ድንቁርና ለሞት ዕውቀት ለፍርሃት የትቢያ ቀጠሮ፣
ሰው ዓሣን አስካሪ ብርብራ ነው ኑሮ::
“ያ ትውልድ” ምንም እንኳን የራሱ የሆኑ ግዙፍ የስሜታዊነት ህፀፆችና ብርቱ የሀገርና የወገን ፍቅር ጥንካሬዎች እንደነበሩት መካድ ባይቻልም ሰፋ አድርጎ ዘመኑንና ትውልዱን ለመፈተሸ መነሻችን ስለማይፈቅድልን አስታውሰን የምናልፈው የጥቅሻ ያህል ነው::
“እስኪ ተጠየቁ…” አንድም አራትም፤
“እስኪ ወይንም እስቲ” የመለመንና የመማለድ፣ የማባበልና የማቆላመጥ፣ አነጋገር ነው:: እስኪ/እስቲ ንገረኝ፣ ንገሪኝ እንዲሉ:: አንድን ድርጊት ፈጽም፣ አትፈጽም፣ አድርግ አታድርግ የሚሉ ትዕዛዞች የሚተላለፉበትም ነው:: እነዚህ ሁለት ድንጋጌዎች የተወሰዱት በቋንቋችን ከተዘጋጁ ሁለት መዛግብት ቃላት ውስጥ ነው::
ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ በ1990 ዓ.ም በታተመው የግጥም መድበሉ ውስጥ “እስኪ ተጠየቁ (1954)፣ እስኪ ያጫውተን (1957)፣ እስኪ እንነጋገር (1958)፣ እስኪ ሰው እንሁን (?)” በሚሉ አርእስት አማካይነት የተማጥኖ ያህል ያስተላለፋቸው መልእክቶች ይዘት ምንድን ነበሩ? ትንታኔው ብዙ ቢሆንም በአጭሩ የአራቱን ግጥሞች ጭምቅ ሃሳብ ሊወክሉልን ይችላሉ ያልናቸውን ጥቂት ስንኞች “ከእስኪ እንነጋገር” ግጥም እንጠቅሳለን::
እስኪ እንነጋገር ብዙ ነገር አለ፣
ጭምት እንደረጋው እንደ ጨፌው ውኃ፣
ሆኗል መንፈሳችን ከውስጡ በስብሶ፣
ቁሟል ቀጥ ብሎ አምሮ እንደ ምሰሶ፤
ከውስጡ ቦክቡኮ ቁንቁን ቆርጥሞት፣
መንፈሳችን ቁሞ ይመስላል ያማረ የቆመ በእውነት::
እስቲ እንነጋገር፤ አለ ብዙ ነገር::
“እስኪ እንነጋገር” ግጥምን ከሦስቱ “እስኪ…ዎች” የሚለየው፤ የዶ/ር ፈቃደን አዘዘን አገላለጽ እንዋስና፤ “ለሕያዋን የሚናገረው በሙታን በኩል” መሆኑ ነው:: “በሞቱት ሰበብና በሞቱት አድራሻ መልዕክቱን የሚልክ፣ ሙግትና ሂስ የሚገጥም፣ በሕይወት አለን ከሚሉት ጋር ነው:: …በግጥሙ ውስጥ ከሀገር መሪዎች እስከ ሴተኛ አዳሪዎች አበሳ ያሉ ቁምነገሮች ተወስተዋል:: ”
በግጥሙ ውስጥ ሙታንን ለመጠየቅ የደፈረውና መልስ እንዲሰጡት የተማጸናቸው በርካታ ሕያዋን የማሕበረሰብ ክፍሎች የእምነት መምህራን፣ ባለሥልጣኖች፣ ገበሬዎች፣ ተማሪዎች፣ ሕጻን ሽማግሌ፣ ሠርቶ አደርና አርሶ አደር፣ ቆንጆና ጎበዝ፣ ‹ጢሰኛና ገባር› ወዘተ. ዓይነታቸው የትየለሌ የሆኑት ቋሚ ተጠያቂዎች የልቡን ሊያደርሱለት ስላልቻሉ ነው:: ከህያዋን በተጨማሪም በሕገ ተፈጥሮ የሚተዳደሩትን እንስሳትን በየነገዳቸው እያሰሰ ተመሳሳይ ጥያቄ ቢጠይቀቸውም መልስ ሊሰጡት ያለመቻላቸውን በሀዘን ያስታውሳል:: መቼም የጥበብን ሰው “በምን ቋንቋ ተናግሮ እንዴት ቢጠይቃቸው ነው?” ተብሎ ስለማይጠየቅ ሃሳቡን በአሜንታ መቀበሉ ግድ ይላል:: ቀድሞውንስ ቢሆን፤
“…መቼስ ባለቅኔን ይፈታተኑታል፣
እንዳሻው ሊናገር ሥልጣን ተሰጥቶታል::
ሁሉንም አጣፍጦ ሊያሰማን አፍ አለው፣
ሲያማ ሰውን ቀርቶ፤ እግዜሩም አይተርፈው:: ”
በማለት አቶ መንግሥቱ ለማ በየግጥም ጉባዔ መጽሐፋው ውስጥ ማረጋገጫውን ሰጥተውን የለ:: (የማከብረው መምህሬን ዶ/ር ፈቃድ አዘዘ አመሰግናለሁ::)
ገጣሚው የማሕበረሰቡ “ወካይ ሙታን” “እቅጩን” መልስ እንዲሰጡት የሚማጸነውና አጥብቆ የሚጠይቃቸው “በመቃብር ዓለም የእኛን የመሰለ ዝንጉርጉር የሕይወት ውጣ ውረድ አለ ወይ? ግፈኞችና ጨቋኞች ያስተዳድሯችኋል ወይ? በአስተዳደር ዘይቤያቸውስ ሙታንን ያስጨንቃሉ ወይ? በዳይና ተበዳይ፣ ገፊና ተገፊ፣ እብሪተኛና ጉልበተኛ ወዘተ. እነዚህ ሁሉ በመቃብር ግዛት ውስጥ በርግጡ እንደ ሕያዋን ሥርዓተ መንግሥት አዛዥና ናዛዥ አላቸው ወይ?…” በማለት ነው:: ከግጥሙ መካከል ጥቂት ስንኞች እንጥቀስ::
የመቃብር ዓለም ያ የሞት ግዛት፣
ፖለቲካ ኃይሉ ያገሩ ሥርዓት፣
ብርሃን ነው ጨለማ ያገዛዙ ልኩ፣
ስልቱ የበራለት፣ ስልቱ የጠፋበት ማይታወቅ መልኩ::
የሀብቱስ መጠኑ እድገቱ ልማቱ፣
እንዲያው ተቀብሯል ወይ ሆኖ ለጥቂቱ፣
ግፍና ጭቆና መከራ ስቃይ፣
ይበዛል ወይ እጅግ ከሰው በሰው ላይ::
ትግል የበዛበት ጸብና ክርክር ያሳብ ጦርነት፣
እየናረ ሚሄድ ከሮ ዕለት በለት፣
ይኸ አለ ወይ ከቶ እንዲህ ዓይነት ኅብር፣
ፍጡርን የሚቀጭ እድሜ ሚያሳጥር::
ገጣሚው ለምስክርነት የጠራቸውን ሙታን ለመሞገት ያነሳሳው ዋና ሃሳብ የገሃዱ “ፍትሕ አልባ” ውጥንቅጡ ዓለም ግራ ስላጋባው ብቻ ሳይሆን እያንዳንዱ የሰው ልጅ ተራው ደርሶ የራሱን የሞት ዋንጫ ተጎንጭቶ ወደማይቀርበት አፈር ሲገባ “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” እንዲል መጽሐፉ፤ አርፈው የተኙትን ሙታን እንዳይረብሽና የህያዋንን “የተበላሸ የግፍ ልምምድ” በመቃብር ዓለም እንዳያስፋፋ ምክር ሰጥቶ ለማዘጋጀት ጭምር ይመስላል:: ድንቅ ምልከታ::
እኛም “እስኪ እንጠያየቅ!”፣ “እስኪ እንነጋገር”
ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ “እስኪ ተጠየቁ” እና ሌሎቹንም ግጥሞች ከደረሰ ስድስት አሠርት ዓመታት ተቆጥረዋል፣ አንዳንዶችም ወደዚሁ ዕድሜ እየተጠጉ ነው:: በህልፈተ ሕይወት ከተለየንም ወደ ግማሽ ክፍለ ዘመን ተቃርቧል:: ይህ የቀለም ቀንድ ብርቱ የማሕበረሰብ ኃያሲ ዛሬ ከመቃብር ተነስቶ እንደተለመደው እርሱ የሰነበተበትን የሙታን ዓለምና የእኛን የዛሬ ኑሮ ቢያስተውል ምን ብሎ ይቀኝብን ይሆን? ብለን ብናስብ “የማይሆን ምኞት” ተደርጎ ሊታሰብ አይገባም::
ነፍሰ ሔሩ ባለቅኔ የዛሬውን ብሔራዊ ግራ መጋባታችንን፣ ለመገዳደል መቻኮላችንን፣ ከማረሻ ይልቅ ጠብመንጃ ጨብጠን “ውረድ እንውረድ” እየተባባልን ማቅራራታችንን፣ ሃይማኖትና ባህል ዋጋቸው ረክሶ የማቴሪያል ቁስ የኅሊናችን አስገባሪ መሆኑን አፈር አራግዶ ተነስቶ ቢያስተውለን ምን ይል ይሆን?
ቋንቋ ከመግባቢያነቱ ልቆ የመታኮሻ ምሽግ መሆኑን፣ ዘርና ብሔር የእኩልነትና የክብር መገለጫ መሆኑ ቀርቶ መናናቂያና መዘባበቻ መሆኑን፣ እኛ ምስኪን ዜጎች በኑሮ ሙቀጫ ውስጥ ታጭቀን በኢኮኖሚው ዘነዘና እንደ በርበሬ እየተደለዝን ጸሎታችን፣ ዱዓችንና ጾማችን ሁሉ “ከዕለት እንጀራ ስጠን” ያለማለፉን ሲረዳስ ምን ብሎ ያጽናናን ይሆን?
እንባችን ክረምት ከበጋ ወንዞቻችንን አስንቆ ሲንዠቀዠቅ ቢያስተውል ብዕሩና አንደበቱ ወደ ውጭና ወደ ውስጥ እንባቸውን እያፈሰሱ በግላጭ እዬዬአቸውን በግላጭ፤ እህህአቸውን በለሆሳስ እንደሚያቀልጡ ለመገመት አይከብድም:: ወይንም የሚከተለውን ግጥሙን ደግሞ ያነብልን ነበር::
ይዘለቃል ወይ ከቶ በንዲህ ዓይነት ስልት፣
ወጋግራውን ሁሉ ምሰሶውን ሁሉ ቁንቁን ጨርሶት::
እንዲህ እንደሆነ ቤቱ በውነት…
ማገሩ ሁሉ አልቆ ቤቱ ሆኖ አፈር፤
ግድግዳ ብቻዋን ቤት አትሆንም ሰልታ፣
በግድ የለሽ ሥራ አለማገር ቀርታ::
ወደፊትም ደግሞ ታስቡ እንደሆነ ትልቅ የቤት ሥራ፣
ግድግዳና ጣሪያው እንዲያምር በተራ፣
አለማገር ሆኖ እንዳይፈርስ አደራ::
ሌላ አማራጭ፤ ገጣሚውን ለጊዜው ከሙታን መቀስቀሳችንን እናቆይና እስቲ እኛው ራሳችን ተደፋፍረን እርስ በእርስ እንመካከር፣ እንነጋገር፣ እንጨዋወት እናም “እስኪ ሰው ሆነን እንደ ሰው በእርጋታ እንወያይ:: ለመሆኑ ሰይፋችንን በየቤታችንና በየጥሻችን እየሳልን አንዳችን በአንዳችን ላይ ማድባቱ ምን በጀን? ምንስ አተረፍንበት? ራሳችንን እንጠይቅ::
ተገዳድለን የተቀባበርንባቸው ታሪኮቻችን ምን ፈየዱልን? ሴራ በመጎንጎን መጠላለፋችን ምን ደስታ ፈጠረልን? የሀገር እምባ ዝናብ ሆኖ ላያለመልመን መሻኮቱ የት ወስዶ ወዴት ያደርሰናል? የልባችን ድንዳኔ እንደ አለት ቢጠጠር የማደሪያችንን መሠረት ስለማናጸናበት “ይዋጣልን!” እየተባባልን ጡንቻችንን ማደለቡ ለማን እንደጠቀመ ነው ለኢትዮጵያ ልጆች ይጠቅማል ብለን እርስ በእርስ የምንሻኮተው:: ልባችን እንደከበደብን ገጣሚው የግጥሙን ሃሳብ በቋጨበት ሁለት ስንኝ ሃሳባችንን እንደምድም::
ጥያቄዬ መቸም በእጅጉ ነበር፣
እንዳይሰለቻችሁ በዚሁ ይጠር::
ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 30/2015