መንደርደሪያችን፤
ለዚህ ጽሑፍ በዋና ርዕስነት የተመረጠው ነባር ብሂል የሚብራራው፡- “እንኳንስ እናቴ ሞታ እንዲያውም አልቅስ አልቅስ ይለኛል” በሚል ጥንታዊ አቻ አባባል ነው። ከዕለት ወደ ዕለት ግራ እያጋቡንና እየተወሳሰቡ የሚያስተክዙንና የሚያስቆዝሙን መራር ሀገራዊ የውስጥ አበሳዎቻችን ያነሱን ይመስል ሌሎች ውጫዊ ጫናዎች ሲጨመሩብን እንደምን ስሜታችንን፣ አካላችንንና መንፈሳችንን እያጎበጡ እንደሚያስነክሱን ደግመን ደጋግመን መወትወታችን አይዘነጋም።
መልካቸውንና ባሕርያቸውን እየለዋወጡ ስሜታችንን፣ ኑሯችንንና ውሏችንን ቤትኛ በማድረግ ሥር የሰደዱትን “ብሔራዊ” ችግሮቻችንንና መከራዎቻችንን ስናስብ ትዝ የሚለን፤ “መከራው ያላለቀለት በሬ፤ ከሞተም በኋላ ቢሆን ቆዳው ለነጋሪት ይጠፈራል” የሚለው የአንጋፎች አባባል ነው።
የፈተናዎቻችን ዓይነቶች በአንድ አካባቢና ሁኔታ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ፤ “ጉድ! ጉድ! ምን ያንተ ብቻ ጉድ! እየው የእኔንም ጉድ” የምንባባልባቸው የጋራ ሕመሞቻችንና የግል ተሞክሮዎቻችን እንደ ሻህላ እያመነዠኩን ዕለት በዕለት እያመነመኑን እንዳሉ የሚካድ አይደለም። ደግመን ደጋግመን በዚህ ነፃ ዓምድ ላይ የሚጠቃቀሱትን ሀገራዊ ቁስሎቻችንን ተመልከቱልን፣ አንብቡልን፣ ስሙልን ማለታችን “ከዝምታ፡- መፍትሔ እናፋልግ በውትወታ” ለሚለው የአበው ምክር ዋጋ የሰጠን መስሎን ነው።
የዛሬ አኗኗራችንና ቅጥ ያጣው ውሎ አምሽቷችን ቀድሞ የገባው ነፍሰ ሔሩ ባለቅኔያችን ጸጋዬ ገብረ መድኅን ልክ የዛሬ ሃምሳ አምስት ዓመት “እሳት ወይ አበባ” በሚል ርዕስ በጻፈው ግጥም ውስጥ (የግጥም መድበሉ ርዕስም ይሄው ነው) የተጠቀመባቸው ጥቂት ስንኞች ጉምጉምታችንን ጮክ አድርገው የሚያስተጋቡ ስለመሰለን እነሆ ነቅሰን ለማውጣት ግድ ብሎናል።
የግጥሙን ማዕከላዊ ጭብጥ በተመለከተ በዚህ ጽሐፍ ለመነካካት ብንሞክር በዝርዝር ሊታዩ የሚገቡት ጉዳዮች እንዳይጨነግፉብን ስለምንሰጋ ወደፊት ዘርዘር ባለ ሂሳዊ ግምገማ ተመልሰንበት “በንስር ዐይን” ብንቃኘው የተሻለ ስለሚሆን በችኮላ ያለመነካካቱ መልካም መስሎ ታይቶናል።
“እንጂ…እኛማ ተረግመን፣
መቸ መነጋገሪያ አለን?
የእርግማን ቢሆን ነው አዎን፤ እንጂ ከየት መጣ አመሉ፣
ላንዲት አፍታ ሳንጠቀም፣ በደስታ ጎሕ በፀበሉ፣
በብርሃኑ በፀዳሉ።
ለአሉ ቧልታ ለስም ብቻ፣ ለይስሙላ መደለሉ፣
የተደሰትን ማስመሰሉ፤ ለማስመሰል መታለሉ፤
በፍቅራችን መዋሸቱ፤ በነፍሳችን መዶለቱ፣
በፍቅራችን ግፍ መዋሉ፤ እርግማን እንጂ ትርጉሙ፣
ሌላ ምን ሊባል ነው ስሙ?”
እርግጥ ነው ለአብዛኞቹ የሀገራችን “ብሔራዊ” እንቆቅልሾች “ምን አውቅልህ/ሽ” ባይ “የልብ አውቃ” መላሽ ስላጣን በነጋ በጠባ “ሀገር ስጡን” እየተባባልን መጠያየቁን የባሕል ያህል ተቀብለን “በአሜንታ” ካጸደቅን ሰንብቷል። እስከ መቼ? እንጃ!
የተቃርኖ ወግ፣
የሀገሪቱ ብዙኃን መገናኛ ሰሞኑን ጎላ አድርገው ከዘገቧቸው ዜናዎችና በስፋት የተሠሩት ዘገባዎች ይፋ ያደረጉልን አንዱ ጉዳይ “የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ አልቀረበልንም” የሚለውን የአርሶ አደሮቻችንን ብሶት ነው። ይህ የአርሶ አደሮቻችን ጥያቄ ቀለል ተደርጎ እንደቀረበው ሳይሆን ጥያቄያቸውን ያቀረቡበት የተስፋ መቁረጥ ስሜትና ድምጸታቸው ከሺህ ቃላት የበለጠ ገላጭ ነበር።
በተለይም በአንድ ክልል የሚኖሩ አርሶ አደር አባት የማዳበሪያ ችግራቸውን የገለጹበት የብሶት ንግግር ውስጥን ሰርስሮ መግባት ብቻ ሳይሆን ስሜታዊ የሚያደርግ ጭምር ነበር። “እስቲ መልካችንን ተመልከቱት። የሰው መልክ ይመስላል? ምናለ በአግባቡ አርሰን ይህ መልካችን እንኳን እንዲወዛ መንግሥት ቢደግፈንና ቢረዳን።
ለእኛ ለአርሶ አደሮች የተመደበላችሁ ኮታ አልመጣም እየተባለ ገበያዎቻችን መካከል ግን ማዳበሪያ በሲኒ ሲቸረቸር እያየን ነው። ለሽያጭ የቀረበው ማዳበሪያ ከየት መጣ…” የሰነዘሩት ጥልቅ ሃሳብ ስሜትን የሚያነዝር መሆኑን ብቻ በማስታወስ ማለፉ ይሻል ይመስለናል።
የሀገሪቱ የጀርባ አጥንት የሚባለውና ከ80% በላይ የሚሆኑ ዜጎች “ኋላ ቀር ሞፈር እየጎተቱ” ነፍሳችን እንዳይወጣ እየመገቡንና የኢኮኖሚው ዋነኛ ምንጭ ነው የሚባለው የግብርና ዘርፍ ለምን ጉስቁልና እንደበዛበት ማሰቡ ልብን ያታክታል። እንዴት ለሺህ ዓመታት “በሬ ሆይ! በሬ ሆይ!” እየተባለ የአስተራረስ ባሕላችን እንደተከበረ እንዲኖር ፈቀድንለት?
ከማዳበሪያው እጥረት ጎን ለጎን በአስርና በአስራ አምስት ዓመታት እያዘነጋ ዞሮ የሚመጣው ድርቅ፣ የአንበጣ ወረርሽኝና ረሃብ “የዚሁ ገበሬ የመርገምት ዕጣ ፈንታ” እንደሆነ ዘመናት መቆጠሩስ እንደ ሀገር አይቆጠቁጠንም። እኛ በእኛው ቋንቋ የገለጽነው “ብሔራዊ እፍረታችን” በባዕዳኑ ሪፖርት ሲደጋገም የኖረው በሚከተለው ዓይነት አገላለጽ ነው።
“Most of the people in Ethiopia lack coping mechanisms designed to help them face famine induced by drought. They have inadequate knowledge regarding contingency planning… Based on this basic fact 68.7 percent of the population of Ethiopia (80,000,000 people in 2020) multidimensional poor while an additional 18.4 percent is classified as vulnerable to multidimensional poverty.” “ከሰደበኝ መልሶ የነገረኝ ገደለኝ” እንዲሉ አበው፤ በርህራሄ እጃቸውን የሚዘረጉልን ሀገራትና ተቋማት የሚሉንን ሁሉ ደግመን ብናስታውስ ራሳችንን ሙልጭ አድርገን ከመስደብ ሰለማይተናነስ፤ እንዲሁ “በሆድ ይፍጀው” ፈሊጥ ማለፉ ይበጃል።
ከሀገራችን የግብርና ዘርፍ ጋር ተያይዘው የሚጠቀሱት የውስጥና የውጭ “ብሔራዊ ፈተናዎቻችን” መልካቸውም ይሁን ዓይነታቸው የተዥጎረጎረ ብቻ ሳይሆን የረቀቀም ጭምር ነው።
ለምሳሌ፡- “እንደ ረሃብ ቀን ሰብል እየተቆነጠረ ከካዝና በሚወጣ ገንዘብ ማዳበሪያ የሚገዛበት የውጭ ምንዛሪ” በተፈላጊው ጉዳይ ላይ ውሎ የግብርና ግብዓቶች ሀገር ውስጥ ገብተው ከገበሬው ቀዬ ከደረሱ በኋላ በፈጣን ሁኔታ ተቀነባብሮ የሚፈጸመው ሌብነት በእጅጉ የፊልም ያህል በሚደንቅ ሴራ የተወሳሰበ ነው። ይህንን የሌብነት ዘዴ ገበሬው ራሱ እንዲናገር ቢበረታታ ይሻላል። ሆዳቸው ከሕሊናቸው የገዘፈ ሹመኞች ለገበሬው የመጣውን ማዳበሪያና ኬሚካል ለነጋዴ እያሸጋገሩ እንደሚቸበችቡ አርሶ አደሮቹን የሚሰማቸው ጠፋ እንጂ በቂ መረጃ መስጠት ይችላሉ።
የድፍረታቸው ድፍረት አርሶ አደሩ “የማዳበሪያ ያለህ!” እያለ በሚጮኽበት በራሱ ቀዬ በሚቆሙ ገበያዎች ላይ ለእርሻ ግብዓት የሚያገለግሉ የአፈር ማዳበሪያና የተባይ መከላከያ መድኃኒቶች በሺህ እጥፍ ዋጋ ወጥቶላቸው ሲቸበቸቡ ማየት የተለመደ እንደሆነ ብሶተኞቹ በአደባባይ የሚመሰክሩት ነው።
ይኼው የፈረደበት አርሶ አደር በግብዓት እጥረት እርሻው ሲመክንበትና አዝመራው ሲነጥፍበት እጁን ለእርዳታ መዘርጋቱ የተለመደ ነው። ዓለም አቀፍ የተራድዖ ድርጅቶችና መንግሥታትም ይህንን እንደ ብርቱ ባሕልና ወግ የተጣባን ችግር እንዲቀረፍ ሲረዱን የኖሩት “ደግሞ ኢትዮጵያ ተራበች!” እያሉ በመነጫነጭ እንጂ የወርቅ ሜዳሊያ በአንገቱ ላይ እንደሚጠለቅለት አሸናፊ አትሌት እያጨበጨቡልንና እያሞገሱን አይደለም።
እርስ በእርስ በግጭቶች ስንፋለምና አርሶ አደሩ ሲጎዳ ለእርዳታ እጅ መዘርጋት፣ ድርቅና ረሃብ ሲጠናወተን “ስለ ነፍስ ብሎ መማጠን”፣ አንበጣና ተምች ሲበረታብን “ድረሱልን!” እያልን እሪ ስንል “በሆዳቸው እያጉተመተሙም ቢሆን” የሕዝባችንን ነፍስ ላዳኑልን ሰብዓውያን ለእስካሁኑ በጎነታቸው ምሥጋናችንን ካልተጠየፉ “ለሰጭም እግዜር ይስጠው” ብለን ብንመርቃቸው ክፋት አይኖረውም።
ሰሞኑን እየሰማን ያለው አሳዛኝ መርዶ ግን ማስደንገጥ ብቻ ሳይሆን ምን ያህል “ብሔራዊ ክብራችንን” ዝቅ የሚያደርግ እንደሆነ መገመቱ አይከብድም። “ስም አይጠሬ” አንዳንድ ሀገራትና ተቋማት “ለኢትዮጵያ የምንሰጠው የእርዳታ እህል በሕገ ወጥ መንገድ እየተዘረፈና ለገበያም እየቀረበ መሆኑን ስላረጋገጥን ለጊዜው ምንም ዓይነት እርዳታ አንሰጥም” እስከ ማለት ደርሰዋል። ውሳኔያቸውን በምሥጢር ሹክ ቢሉን ባልከፋ ነበር። እጅግ የሚያሳዝነው ዜናውን ለመላው የዓለም ማኅበረሰብ ለማድረስ መፍጠናቸው ነው።
“ልብ ያለው ልብ ይበል!” የሚለው የቀዳሚ ዘመን ብሂል መታወስ ካለበት ሊታወስ የሚገባው በዚህ ወቅት ነው። ለምነንም፣ የለመኑትን ተሰራረቁ ተብለንም እንደምን ስማችን በድርብ ክስ ይጥፋ? “አለብሰን ብናርስ፤ በአረም መመለሳችን ስለማይቀር” ይህንን ጉዳይ ንቀንም ይሁን አፍረን ዝም ልንል የሚገባ አይመስለንም።
ይህም ሲባል “ጡንቻቸውን አሳይተው አንረዳችሁም”
ካሉን መንግሥታትና ተቋማት ጋር እንካ ሰላንትያ እንግጠም ማለት ሳይሆን እፍረታችንን ለማደስ በራሳችን ላይ ኮስተር ያለ እርምጃ መውሰድ የሚገባን ይመስለናል። “የልመና እንጀራ ምንግዜም ከልመና አያወጣም” እንዲሉ መፍትሔው በራሳችን ላይ መጨከን ብቻ ነው። እንዴት? የመፍትሔውን መላ ምሑራንና ገዢዎቻችን ቀድመው ቢነግሩን የተሻለ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ እኛ “ተገዢ ዜጎችም” ሃሳባችን ቢደመጥ ክፋት ያለው አይመስለንም።
ለምሳሌ፡- የእርሻውን ዘርፍ ከማሳ እስከ ጉርሻ ከተተበተበት ውስብስብ ችግሮች ማላቀቅ። የሀገርን ውጪያዊ መልክ ከሚያደምቁ ወጭዎች ይልቅ ለመሠረታዊ የእርሻ ግብዓቶች ቅድሚያ መስጠት። ተፈላጊው ማዳበሪያም ሆነ ሌሎች ግብዓቶች ከአርሶ አደሩ እጅና አፍ የሚነጥቁትን “የኅሊና ድኩማን” በአግባቡ መቅጣትና ቅጣቱንም ያለምንም ይሉኝታ ለሕዝብ ግልጥ አድርጎ “እኔን ያየህ ተማር” እንዲሉ ማድረግ።
መከራው ወደ ልጆቻችን እንዳይሸጋገር መንግሥት እየተጋበት ላለው የተፈጥሮ አጠባበቅ ፕሮግራሞች ውጤታማነት “ቢርበንም ሆነ ቢጠማንም” ችለንና ጠንክረን ተባብረን አካባቢያችንን በመታደግ “ነፍሳችንን ማዳን። ” ሁሉንም ነገር ለመንግሥት ጥላቻ መግለጫነት ማዋል እስከ ዛሬ አልረባንም ወደፊትም ሊጠቅመን የሚችል አይደለም።
መንግሥት ግዴታውን ካልተወጣ ሊገሰጽና ሊወቀስ ግድ ነው። ነገር ግን ሁሉንም የመንግሥት እቅዶች ጥላሸት እየቀቡ መቃወምና መተቸት “የሚነቀፈውን ብቻ ሳይሆን፤ የተቺውን ማንነትም የሚገልጽ” መሆኑን ልብ ማለት ይገባል። መቼም ሳር ቅጠሉ ሁሉ ፖለቲካ የሆነበት ሀገር እንደ ኢትዮጵያ ሌላ ሀገር ይኑር አይኑር ለማወቅ ያዳግት ይመስለናል።
“ወንዞች ይገደቡ ይዋሉ ለልማት፤ በከንቱ ፈሰዋል ለብዙ ሺህ ዓመታት” የሚለው የደርግ ዜማ እውነታነት ስላለው ጠንክሮ ተፋሰሶቻችንን ሥራ ላይ ማዋል። “ይሄ ጉዳይ መች ይጠፋናል፤ እስከ ዛሬስ እየሠራንበት አይደለም ወይ!” የሚሉ የመንግሥት ሹመኞች እንደሚኖሩ አንጠራጠርም። አልፎም ተርፎም በምንሰጠው “አስተያየቶች” የሚዘባበቱም ሆነ ላለማንበብ ዐይናቸውን የሚጨፍኑ የፖለቲካው ጋሻ ጀግሬዎችና ሹመኞች እንደማይጠፉ እንገምታለን።
ይህ ጉዳይ ከተነሳ አይቀር ደፈር ብለን አምቀን ያቆየነውን ስሜታችንን ይፋ እንግለጠውና ለመሆኑ የመንግሥት ዋና ዋና ሹመኞች የሕዝቡ ሃሳብ የሚስተናገዱባቸውን ጋዜጦች ሥራዬ ብለው ያነቡ ይሆን? እነርሱ እንኳን ባይሞላላቸው በዙሪያቸው ያሉትን የበታች ሠራተኞቻቸውን “የጋዜጦችን አጢራራ” ማለዳ ማለዳ እንዲያቀርቡላቸው ያዟቸው ይሆን? መልስ ለመጠበቅ ሳይሆን እንደ ማስታወሻ ማቅረባችን እንደሆን ልብ ይባልልን።
አንዳንድ የተራድዖ ድርጅቶች “እርዳታ እስከማቆም የደረሱት” ምናልባት መንግሥት ስንዴ ወደ ውጭ መላክ መጀመሩ ስላልተመቻቸው ይሆን? ወይስ ያቆሙበት ምክንያት በርግጡ አሳማኝ ስለሆነ? እንደ እውነቱ ከሆነ የቀረበብን ክስ “ሀገራዊ ገጽታችንን ያጎድፋል ብለን በመስጋት” ብቻ ሙሉ ለሙሉ ምክንያታቸው ሐሰት ነው ብሎ መቃወሙም አግባብ ስላልሆነ መንግሥት የራሱን ጓዳና ጎድጓዳ ቢፈትሽ አይከፋም።
ይህ ሀገራዊ ተቃርኖ እልባት አግኝቶ እንዲፈታ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ብቻ ሳይሆን ጾምና ፀሎት የታከለበት የእምነት ቤተሰቦችን ትጋት የሚጠይቅ ጭምር ሳይሆን ይቀራል? “እርግማን ካለብን” መፍትሔው ለሥራ እየተጉ ሕሊናን ከእድፈት፣ እምነትን በፈጣሪ ላይ መጣሉ ዋጋ ስላለው መሆኑን ልብ ይሏል። ሰላም ለሕዝባችን ለዜጎችም መልካም ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 3/2015