በየትኛውም ስፖርት ውጤታማ ለመሆን የግል ብቃት (የቡድን አንድነት) ወሳኝ መሆኑ አያጠያይቅም:: ለዚህ መነሻ የሚሆኑት ግን ስፖርተኛው ያለው ተሰጥኦ፣ ተክለ ሰውነቱ፣ ለስፖርቱ ምቹ የሆነ የቦታ አቀማመጥ፣ የአየር ሁኔታ፣ የአኗኗር ዘይቤ፣… የመሳሰሉት ናቸው:: በአንጻሩ ዘመናዊው ዓለም እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች ሳይሟሉ በሳይንሳዊ ስልጠና እና በቴክኖሎጂ እገዛ ተወዳዳሪና ውጤታማ የሆኑ ስፖርተኞችን ለማፍራት በቅተዋል::
ባለንበት ዘመን የትኛውም ጉዳይ ለማከናወን የሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር ውጤቶችን ምርኩዝ ማድረግ የተለመደ ነው፤ ስፖርትም የዚሁ አካል ነውና ሳይንስና ቴክኖሎጂን የተደገፈ ዘርፍ ለመሆን በቅቷል:: በእርግጥ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት አሁንም ድረስ ባህላዊ የአሰለጣጠንና የብቃት ማሳደጊያ መንገድን በመጠቀም ነው ስፖተኞች ለውድድር የሚቀርቡት::
ኦሎምፒክን ጨምሮ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች የሀገርን ስም እያስጠሩ ያሉ የዘመኑ አትሌቶችም እንደ ቀድሞዎቹ ሁሉ የተፈጥሮ ጸጋ በሆኑት ጋራና ሸንተረር በመሮጥ ነው ለውጤታማነት የሚጥሩት:: ያደጉት ሀገራት አትሌቶች ደግሞ በቴክኖሎጂ ታግዘው በቤተሙከራ እና በጂምናዚየሞች ውስጥ በሚያደርጓቸው ልምምዶች አትሌቶች ብርቱ ተፎ ካካሪ ይሆናሉ::
ስፖርትን በሳይንሳዊ መንገድ መምራት በተለይ ከሁለት አስርት ዓመታት ወዲህ እየተለመደ ብቻም ሳይሆን በመላው ዓለም እየጎለበተ የመጣ ተሞክሮ ነው:: በዚህም የስፖርተኞችን አቅም ከማጎልበት ባለፈ አካላዊ ሁኔታቸውን በመቆጣጠር በምን መልኩ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ በሳይንሳዊ ስሌት ይቀምራሉ::
በእርግጥ ዘመን አመጣሹን ይህንን መንገድ መከተል የስፖርተኞችን አቅም በእጥፍ ከማሳደግ ባለፈ፤ በውድድርና ልምምድ ወቅት የሚፈጠሩ ጉዳቶችን በመቀነስ እንዲሁም ከጉዳት በቶሎ እንዲያገግሙ በማድረግ ረገድም እጅግ ከፍተኛ ጠቀሜታን ያስገኘ ነው::
በብዙዎች ተቃውሞ ይቅረብበት እንጂ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በስፖርት ትጥቆችና ቁሳቁሶች ላይ በመጠቀም ከዚህ ቀደም የሰው ልጅ ያልደረሰበት የብቃት ጥግ ለመመልከት የሚደረገው ጥረትም የዚሁ አካል ነው:: ውድድሮችን አስቀድሞ መተንበይ፣ ቁጥራዊ ትንታኔ መስጠት፣ የውድድሮችን ውበት ይቀንሳል የሚል ስጋት ቢያሳድርም ጨዋታዎችን በቴክኖሎጂ ውጤቶች መምራት፣… ከበርካቶች ጥቂቶቹ ናቸው::
እየረቀቀ በመጣው በዚህ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘመን ተፎካካሪ ለመሆን ወቅቱን መዋጀት የግድ ይላል:: ሳይንስ ከስፖርተኞች ብቃት ጋር ብቻ በተያያዙ ጉዳዮች ተግባራዊ የሚደረግ ብቻም አይደለም:: ይልቁንም ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲና አሰራሮችን ለመቅረጽ፣ ስፖርቱ የሚመራበት አቅጣጫና ዕቅድ ለማዘጋጀት፣
ሀገሪቷ ውጤታማ ልትሆን የምትችልባቸውን ስፖርቶች ለመለየት፣ የስፖርት ተቋማት አደረጃጀትና አስተዳደርን ለማዋቀር፣ የስፖርት ወጪ እና ገቢ በኢኮኖሚው ላይ የሚኖረው አስተዋጽኦ ለማወቅ፣ የስፖርት ባለሙያዎች(ዳኞች፣ አሰልጣኞች፣…) ለማዘመን፣ የውጤታማነት ግምገማ፣ … ከፍተኛ ሚና አለው::
የዘፈቀደ እና ልማዳዊ አሰራሮችን ሙጥኝ ማለት ደግሞ በስፖርት የሚገኙትን የሀገር መልካም ገጽታ ግንባታ፣ የኢኮኖሚ ድጎማ፣ በአካልና በአእምሮ ብቁ የሆነ ትውልድ መፍጠር፣… የመሳሰሉ ጥቅሞችንም ያሰጣል::
በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ስፖርት በሳይንስ እንዲመራ ከማድረግ አኳያ አልተሰራም ማለት ይቀላል:: ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚያፈሯቸው የስፖርት ሳይንስ ምሁራንም በተለያዩ ተቋማት ተቀጥረው ከመስራት ባለፈ በጥናትና ምርምር ታግዘው ሀገሪቷ ልትመራበት በሚገባት የስፖርት አቅጣጫ ላይ ምክረ ሃሳብ ሲሰጡ አይስተዋልም::
ከታዳጊ እስከ ታዋቂ ስፖርተኞች ያለው ስልጠናም ቢሆን አሁንም ድረስ አስቀድሞ ስፖርተኛ በነበሩና በልማድ በሚመሩ አሰልጣኞች ቁጥጥር ስር ያለ ነው:: ሀገርን የሚወክሉ ብሔራዊ ቡድኖችም ከጥቂቶቹ በቀር በስነምግብ፣ ስነልቦና፣ በአካል ብቃት፣ በህክምና እና ማሳጅ፣ በውድድር ተንታኝ፣… ባለሙያዎች ሳይሟሉ ነው የውድድር መድረክ ላይ የሚገኙት::
በሌሎች ሀገራት ከህጻናት አንስቶ በስፖርት ስልጠና የሚያልፉ የትኞቹም አትሌቶች መነሻ እና ግብ አላቸው፤ ከግባቸው የሚደርሱትም በዚሁ መንገድ ተጉዘው ነው:: እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂን ቸል ያሉ ሀገራት ደግሞ በአትሌቶች የግል ብቃት እና እድል ብቻ ድልን እያስመዘገቡ ዘመናትን ማስቆጠር እጣ ፋንታቸው ይሆናል::
ሀገሪቷ የምትታወቅበትን አትሌቲክስ ብናነሳ እንኳን ቀድሞ የምትታወቅባቸው ርቀቶች አሁን ተፎካካሪዎች የተበራከቱባቸው ሆነዋል:: ተፎካካሪ ለመሆን የበቁትም በሳይንሳዊ ስልጠና እንዲሁም ብቃትን በሚያጎለብቱ የስፖርት ትጥቆች ታግዘው ነው:: ስለዚህም ሌሎች ርቀቶችን ማማተር አሊያም በእነዚሁ ርቀቶች አሳማኝ የሆነ ብቃት ይዞ ከመገኘት ውጭ አማራጭ የለም::
በመሆኑም ኢትዮጵያም የአትሌቶች አመጋገብ፣ የስልጠና ሁኔታ፣ በውድድሩ ውጤታማ ስለሚሆኑባቸው ዘዴዎች፣ ስለ ተፎካካሪዎቻቸው አቋም፣ ድህረ ውድድር ግምገማ፣ የእረፍት ጊዜ ማሳለፊያ መንገዶች፣ ከጉዳት የሚያገግሙበት መንገድ፣ በድጋሚ ወደ ውድድር እንዴት ሊመለሱ ይችላሉ፣… የሚለውን ሁሉ በሳይንሳዊ መንገድ ሊመራ ይገባል::
ለዚህም ኃላፊነት የሚወስድና ትኩረቱንም በዚህ ላይ በማድረግ ከመልካም ገጽታ ባለፈ በስፖርት ረብጣ ገንዘብ የሚገላበጡባትን ኢትዮጵያን መገንባት ዓላማው ያደረገ ተቋም ያስፈልጋል:: በእርግጥ የኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ ከተሰጡት ኃላፊነቶች መካከል አንዱ ሳይንሳዊ የስፖርት ጥናትና ምርምር ማካሄድ ነው::
በዚህም ባለፉት ዓመታት ጥቂት የማይባሉ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን በቅርቡ ባካሄደው ሀገር አቀፍ የስፖርት ጥናትና ምርምር ጉባኤ ላይ አስታውቋል:: ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በመሆን የስፖርት ሳይንስ ባለሙያዎች ለሚሰሯቸው ጥናቶችና የምርምር ውጤቶችም እውቅናን ይሰጣል::
ይሁንና አሁንም ድረስ ከመደርደሪያ ወርደው ወደ ተግባር መቀየር ባልቻሉት የጥናት ውጤቶች ምክንያት የኢትዮጵያ ስፖርት ከችግር ሊላቀቅ አልቻለም:: ተቋሙ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ራሱን በባለሙያና በቁሳቁስ እንዳጠናከረ ቢገልጽም፤ የስፖርት ማህበራት፣ የማሰልጠኛ ተቋማት ቀርበው ባሉባቸው ችግሮችና ክፍተቶች ላይ ምክረ ሃሳብ የመጠየቅ ልምዳቸው ግን እጅግ አናሳ ነው ::
በሳይንሳዊ መንገድ የሚመራ፣ በጥናትና ምርምር ላይ የተመሰረተ፣ ውጤታማነትን ግቡ ያደረገ፣ አካሄዱን በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ ያደረገ፣ ሀገርን በገቢ የመደገፍ ትልም ያለው፣ … ስፖርተኛ፣ የስፖርት ባለሙያ፣ ብሔራዊ ቡድን፣ የስፖርት ማሰልጠኛ ተቋም፣ … ለመፍጠር ትኩረት ማድረግ ተገቢ ነው:: ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እንዲሁም የስፖርት ሳይንስ ምሁራንም ለውጥ የሚያመጡ፣ ከመደርደሪያ ወርደው ተግባር ላይ የሚውሉ እንዲሁም የኢትዮጵያን ስፖርት በእርግጥም ማሳደግ የሚችሉ ጥናትና ምርምሮች ላይ መትጋት አለባቸው::
ስፖርቱን በበላይነት እየመራ የሚገኘው የኢፌዴሪ ባህልና ስፖርት ሚኒስትር ደግሞ ለሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር ቅድሚያ በመስጠት እንዲሁም ሳይንሳዊ ግኝቶችን ወደ ተግባር በመለወጥ ረገድ አርዓያ መሆን ይገባዋል::
ብርሃን ፈይሳ
አዲስ ዘመን ግንቦት 30/2015