ፕሮፌሰር ፓትሪክ ሎች ኦቴኖ ሉሙምባ/P. L. O. Lumumba /በፓን አፍሪካ አቀንቃኝነታቸው እና አነቃቂ ንግግራቸው የሚታወቁ ምሁር ናቸው። ኬንያዊ ፕሮፌሰር በተለይ ‹‹አፍሪካውያን አንድነታቸውን ማጠናከርና ስለ አህጉሪቱ አንድ ቋንቋ መናገር ካልጀመሩ ዳግም በቅኝ ግዛት መዳፍ መውደቃቸው አይቀርም›› በሚል ከንግግር በተሻገረ አቋማቸው ይታወቃሉ፡፡
ፕሮፌሰሩ ባለፈው ግንቦት ወር አጋማሽ ላይ ‹‹discussion on foreign interference in Africa›› በሚል በተዘጋጀው በአስረኛው የሩዋንዳ ብሄራዊ የፀጥታ ጉባዔ ላይ በመገኘት ስሜት በተሞላበት መልኩ ያስተላለፉት መልእክት እንዲሁም አንድን ጥናት ዋቢ በማድረግ ያነሱት ጥያቄ አግራሞትን ከመጫር አልፎ እንደ አህጉር ግዙፍ ፈተና ውስጥ እንደምንገኝ ያመለከተ ነበር፡፡
ፕሮፌሰሩ በዚሁ መድረክ ላይ እንደጠቆሙትም በርካታ የአፍሪካ መሻቶች፣ እቅዶች እና ግቦች በአፍሪካውያን ዘንድ አይታወቁም፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ስንቶች ስለ አፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣና እና ስለ አፍሪካ 2063 አጀንዳ እንደሚያውቁ መጠየቅ ብቻውን በቂ ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ እንዳሉትም ሁለት በቂ መረጃና እውቀት ያላቸውን ሰዎችን ማግኘት እድለኝነት ነው፡፡
ፕሮፌሰሩ ለአብነት እነዚህን አጀንዳዎች ያንሱ እንጂ እንደ እኔ እምነት በርካታ የአፍሪካ አጀንዳዎች ከጉባዔ ሊሻገሩ አልቻሉም፡፡ ሕዝብም በቂ በሆነ መልኩ አልተረዳቸውም፡፡ ጥቅም ጉዳታቸውን ለመመርመርም እድል አላገኘም፡፡ በተለይም ጥቅማቸውን ተረድቶ ለተፈፃሚነታቸው ለመታገል እድሉን አላገኘም፡፡ በዚህ መልኩ ከሚገለፁ አጀንዳዎች መካከልም የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክርቤትና የአፍሪካ ቋሚ መቀመጫ ጉዳይ አንዱ ነው፡፡
የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤትም እ.ኤ.አ በ1948 የተቋቋመና የዓለምን ወሳኝ ሠላም፣ ፀጥታና የደህንነት ጉዳዮችን የሚከታተል የድርጅቱ ዋነኛ የሥልጣን አካል ነው፡፡ ምክር ቤቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሰላምና ከደህንነት ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ከፍተኛው የድርጅቱ ክንፍ በመሆኑ ማዕቀቦችን ይጥላል፣ የሃይል እርምጃዎችን ያፀድቃል ወይንም ይሽራል፡፡
በተባበሩት መንግሥታት ቻርተር (23) እንደተመላከተው የፀጥታው ምክር ቤቱ 15 አባል ሀገራት አሉት፡፡ ከእነዚህ መካከል አምስቱ ማለትም አሜሪካ፣ ሩሲያ፣ ቻይና፣ እንግሊዝና ፈረንሳይ ድምጽን በድምጽ የመሻር መብት ያላቸው ቋሚ United Nations Security Council ‹‹veto power ›› ያላቸው እና ‹‹መስራች አባላት›› አገራት ናቸው፡፡
ባለፉት ሰባት አስርት ዓመታት ምክር ቤቱን በበጎ መልኩ የሚያነሱት እንዳሉ ሁሉ የዓለም ህዝቦች እጣ ፈንታ በአምስት አገሮች ፍላጐት እንዲወሰን በመፈቀዱ ምክንያት ዓለማችን ይሆናሉ ተብለው የማይገመቱ እልቂቶችንና አሳዛኝ ክስተቶችን እንድታስተናግድ ምክንያት እየሆነ ይገኛል የሚል ትችትም ይሰነዘርበታል።
አንዳንዶች በተለይም ‹‹የRealism theory››ን ዋቢ በማድረግ፣ አምስቱ አገራት በያዙት ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ውሳኔዎች እንዲያልፉ ወይም እንዲወድቁ ድምፅ የሚሰጡት ከዓለም አቀፍ ሕግ በመነሳት ሳይሆን ከራሳቸው መንግሥት ጥቅምና ፍላጎት አንፃር መሆኑን በመጥቀስ በዚህ ውስንነት የድርጅቱን ተዓማኒነትና ገለልተኝነት ጥያቄ ውስጥ ያስገቡታል፡፡
ከቅቡልነት ባሻገር በርካቶች ድርጅቱ የአሳታፊነት ችግር አለበት፣ ለውጥ ያስፈልገዋል፣ ማድረግም አለበትም ይላሉ፡፡ በእርግጥም ምክር ቤቱ ባለፉት ሰባት አስርት ዓመታት ማሻሻያ ያደረገው አንድ ግዜ ብቻ ነው፡፡ እሱም እኤአ በ1965 ቋሚ መቀመጫ የሌላቸው አባል አገራትን ቁጥር በአራት በመጨመር ነው፡፡
ይህን ዋቢ የሚያደርጉ የተለያዩ ምሁራንና አገራትም፣ የተባበሩት መንግሥታት ሲመሰረት የነበረው ነባራዊ ሁኔታ አሁን ካለው ጋር በፍጹም የማይገናኝና የተለየ መሆኑን በተደጋጋሚ ሲያስረዱና ድርጅቱ ለውጥ እንደሚያስፈልገው፣ ከሁሉም በላይ በድምጽን በድምጽ የመሻር መቀመጫ ያላቸው አገራት ቁጥር ከፍ እንዲልና ሲሟገቱ ቆይተዋል፡፡
ባለፉት ዓመታትም ከተለያየ አቅጣጫ የለውጥ ያስፈልጋል፣ የእኛም ድምፅ ሊሰማ ሊከበር ይገባል የሚሉ ድምፆች ይበልጥ ሲያስተጋቡም ተደምጠዋል፡፡ የተለያዩ አገራት ለውጡ ሊመራበት ይገባል የሚሉትን ሃሳብ ከማቅረብ ባለፈ የሪፎርም እቅድ ይዘውም ቀርበዋል፡፡
G4 የተሰኙት ብራዚል ጀርመንና ጃፓን ህንድ የመሳሰሉ አገራት የፀጥታው ምክር ቤት አሁን ባለው አሰራር የብዙሃንን ጥቅም ማስከበር እንደማይቻል በተለያዩ ማስረጃዎች አስደግፈው በማቅረብ፣ አሰራር ላይ የማሻሻያ ለውጥ እንዲደረግ ከሚጎተጉቱ አገራት ተርታ ይጠቀሳሉ፡፡
አፍሪካ በጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ማግኘት አለባት የሚለው ጥያቄና ትግል የረጅም ዓመታት ያስቆጠረ ነው፡፡ ምክር ቤቱ ሲደራጅ አብዛኞቹ የአፍሪካ አገራት በቅኝ ግዛት ስር የነበሩ ሲሆን አሁን ይህ ምስል ተለውጧል፡፡ አፍሪካውያንም ምክር ቤቱ ኢ-ፍትሃዊ ነው በሚል አህጉሪቱ በምክር ቤቱ ቋሚ መቀመጫ ሊኖራት ይገባል የሚል ተደጋጋሚ ሃሳብ ማቅረብ ጀምረዋል፡፡
ከአፍሪካ ውጪ ያሉ ተቋማት አገራትና ምሁራንና አህጉሪቱ ቋሚ መቀመጫ ይገባታል የሚል ጥያቄን ደጋግመው ጠይቀዋል። አፍሪካ ህብረትም አህጉሪቱ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲሰጣት በተደጋጋሚ ጥያቄ አቅርቧል፡፡ በተለይም እኤአ በ2005 መፍትሄ የሚለውን እቅድ Ezulwini Consensus በሚል አስተዋውቋል፡፡
በዚህ እቅድም ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ለዓለም አቀፍ ፖለቲካ ዋነኛ መሳሪያ ሆኖ እንደሚያገለግል ዋቢ በማድረግ የአፍሪካ አገራትም ቋሚ መቀመጫ ከማግኘት ባለፈ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብትን ጨምሮ ተመሳሳይ የሆነ ሥልጣንና ጥቅም ሊሰጣቸው ይገባል ብለው ቀርበዋል፡፡
የተለያዩ የአፍሪካ አገራት መሪዎችም ይህን ጥያቄ በተለያየ ጊዜ አንስተዋል፡፡ የቀድሞው የዚምባብዌ ፕሬዚዳንት ሮበርቶ ሙጋቤ ከጠያቂዎቹ መካከል በቀዳሚነት ስማቸው ይነሳል፡፡ ፕሬዚዳንቱ እኤአ በ2016 አዲስ አበባ ላይ በተካሄደው በ26ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ ላይ ‹‹በየአመቱ መስከረም ወር ላይ የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ስብሰባ ሲደረግ እንሳተፋለን። ይሁንና ያለን ተወካይነት ለይስሙላ ነው። ንግግር አድርጎ ከመመለስ የዘለለ አይደለም፡፡ ይህም ብቻ አይደለም በጠቅላላው ጉባኤ ለመገኘት በርካታ ወጪዎች እናወጣለን። በዚህ አይነት መልኩ ዓመታት አልፈዋል ሌሎች ዓመታትም መጥተዋል። ይህ አሰራር እንዲለወጥ እኛም ያለማቋረጥ ትናንትም፣ ዛሬም ሆነ ነገ እንጠይቃለን፣ የጸጥታ ምክር ቤት ማሻሻያ ይደረግበት፣ አፍሪካም ተወካይ ይኑራት›› ሲሉ ጥያቄአቸውን አቅርበው ነበር፡፡
አፍሪካ ከትናንት እስከ ዛሬ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት የይስሙላ ተሳታፊና በማንኛውም አጀንዳ ላይ የምትሰጠው ድምጽ የዜሮ ድምር ነው፡፡ ምክር ቤቱ የአፍሪካን የፀጥታና ደህንነት፣ ፖለቲካና ኢኮኖሚ በተጠና መልክ በእጅ አዙር ይዘውራል፡፡ ይህም ግልፅ ኒዮ ኮሎኒያሊዝም ምሳሌ ነው፡፡
በተለይ ምክር ቤቱ አፍሪካ በሌለችበት አፍሪካውያን ላይ የሚወስነው ውሳኔ ለብዙዎች የጭን ቁስል ነው። ይህን ተከትሎም በርካቶች አፍሪካ የራሷን ጉዳይ ሌላ ወገን ሲወስንባት ዳር ቆማ መመልከት ማቆም አለባት ይላሉ፡፡ በእርግጥም ምክር ቤቱ አፍሪካውያን በሌሉበት ስለአፍሪካውያን ውይይት ማድረጉና መወሰኑ በኦቶማን ቢስማርክ ዘመን እኤአ በ 1980ዎቹ ‹‹The Scramble for Africa›› አፍሪካን ለመቀራመት ከተካሄደው የበርሊን ኮንፈረንስ ቢመሳሰል እንጂ ልዩነት የለውም፡፡
ምክር ቤት ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ስለ አፍሪካ ያስተላለፋቸው ውሳኔዎችና የተመካከረባቸው ጉዳዮች ሚዛናዊነትና ግልጽነት የጎደለውና የምዕራባውያን ፍላጎት ያማከለና አህጉሪቷን በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና በማህበራዊ ጉዳዮች ጥገኛ ለማድረግ የታለሙ ናቸው። ለዚህ ምሳሌ ሊቢያ ናት፡፡ የአንድ ነጥብ ሦስት ቢሊዮን ሕዝብ መኖሪያ የሆነችው አፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት አለመወከሏ በኃያላን አገራት ተፅዕኖ እንድትወድቅ አድርጓታል፡፡
እንደ ትናንቱ ሁሉ የተባበሩት መንግሥታት አዲስ በሆነ መልኩ የወቅቱን በየዓለም ቁመና ከግምት ባስገባና በሚመጥን አደረጃጀት በተለይም የአፍሪካን ጥቅሞች በሚያስጠብቅ መልኩ መዋቀር የሚኖርበት ትክክለኛው ጊዜም አሁን ነው የሚሉ ድምፆች ከየአቅጣጫው እያስተጋቡ ናቸው፡፡
የተለያዩ ምሁራንና ፀሃፍትም፣ ‹‹አፍሪካ በዓለም አቀፍ አስተዳደራዊ ተቋማት ውስጥ የተሻለ ውክልና ማግኘት ይገባታል፣ በተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ውስጥ አንድ ወይም ሁለት ወንበር ሊኖራት ይገባል። ከቋሚ አባላቱ ውስጥ የአፍሪካን ውክልና አንዱ የማድረግ ጥያቄ እንደውም እንደዘገየ ነው ፣ ሃያላኑ አገራትም ለዚህ ዕቅድ ሙሉና የማያወላዳ ድጋፍ ሊሰጥ ይገባል፤›› እያሉ ናቸው፡፡
የወቅቱ የአፍሪካ መሪዎችም የፀጥታው ምክር ቤት የዓለም ቁመና ከግምት ያስገባ መዋቅራዊ ለውጥ ያስፈልገዋል እያሉ ናቸው፡፡ በአፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ጥበቃ ምክር ቤት ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ ኢ-ፍትሐዊነት ነው ከሚሉት መካከል የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎዛና የሴኔጋሉ አቻቸው ማኪ ሳል ይገኙበታል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የአፍሪካ አገራት በተመድ የፀጥታው ምክር ቤት የተሻለ ውክልና እንዲያገኙ የሚጠይቀውንና ሌሎች አፍሪካውያን መሪዎች እያደረጉት ያለውን ንቅናቄ መቀላቀላቸው የሚታወስ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አፍሪካን በተመለከተ የሚወሰኑ ውሳኔዎች ከአፍሪካ ውክልና ውጭ መወሰን እንደሌለባቸውም በመጠቆም ‹‹1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ህዝብ ያላት አፍሪካ በተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እና ድምፅ ሊኖራት ይገባል ነው›› ያሉት፡፡
በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫን ማግኘት በርካታ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ስፍራና ከበሬታ ከፍ ያደርገዋል። ተደማጭነትና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷን ያገዝፈዋል። ጥቅሟን እንድታስጠብቅ፣ የተለያዩ የሰላም አማራጮችን እንድታቀርብ፣ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም እንድታሰፍን እድል ይሰጣታል፡፡፡
ለአህጉሪቱ በጎ የማይመኙ አገራትን ስውርና ገሃድ ሴራ በቅርበት በመከታተል አሉታዊ ፍላጎትና ውሳኔያቸውን ለመመከት እንዲሁም ለሌሎችም ጥብቅና ለመቆም፣ በሴራ ጥልፍልፎሽ የሚያደርሱ ጉዳቶችን ለመቀነስና ከተቻለም ለማስቆም ፋይዳው የጎላ ነው። የቅኝ ግዛት አስተሳሰቦችን ለመታገል፣ አፍሪካ የራሷን ጉዳይ በራሷ ቆማ በመታገል ተደማጭነት እንዲኖራትና የአፍሪካ ሃሳብ በዓለም ላይ ገዥ ሃሳብ እየሆነ የሚመጣበት እድል ይፈጥራል፡፡
የአፍሪካ ቋሚ መቀመጫ ማግኘት ጥቅም ለአፍሪካውያን ብቻ አይደለም፡፡ ለዓለም አቀፍ ተቋሙም ጭምር ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ መቀመጫው ለአህጉሪቱ ሁለንተናዊ እድገት በተለይም ሰላምና ደህንነት እጅግ ወሳኝ ከመሆኑ ባሻገር ድርጅቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ በበርካቶች ዘንድ የሚሰነዘርበትን የአድሎአዊነት ትችት እንዲቀንስ እንዲሁም የተቋቋመበትን ዓላማ እያሳካ ለመቀጠል የሚያስችለው መሆኑ ነው፡፡
በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ትግሉን ውጤታማ ሊያደርጉት የሚችሉ ምቹ ሁኔታዎችም አሉ፡፡ በተለይም የዓለም አቀፉ የፖለቲካ አሰላለፍ መቀየር የጥያቄውን መልስ የማግኘት ዕድል ከፍ የሚያደርግ ዋነኛ ምክንያት ነው፡፡
አፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲኖራት ማድረግ አዲስና ፍትሐዊ ዓለም መፍጠር በመሆኑ በተለይም ‹‹የአፍሪካን ጉዳይ በአፍሪካ የሚለው ቁልፍ የፍትህ ጥያቄን ለመመለስ፣ ሁሉም የአፍሪካ ህብረት አባል አገራት ጉዳዩን አጀንዳ አድርገው እንቅስቃሴ ውጤት እንዲያመጣ በተቀናጀ መንገድ ሃሳቡን ሊደግፉት ይገባል፡፡
አፍሪካውያን በምክር ቤቱ መቀመጫ ለማግኘት መተባበር እንጂ መሻኮትን ማቆም ይኖርባቸዋል። አፍሪካ ምክር ቤት ቋሚ መቀጫ እንዲኖራት የተጀመረው ትግል ከጉባዔ አጀንዳነት ባለፈ የመላ አፍሪካውያን ጥያቄ እንዲሆን ማድረግ ይገባል። አፍሪካውያንም ድምጻቸውን በጋራ ማሰማት፣ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና በማህበራዊ ጉዳዮቻቸው ዙሪያ ቀጠናዊ ትስስራቸውን ማጠናከር ግድ ይላቸዋል፡፡
ከሁሉ በላይ አፍሪካ በምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲኖረው የተጀመረው እንቅስቃሴ ከጉባኤ አጀንዳነት ተሻግሮ የነጻነት፣ የእኩልነትና የፍትሐዊነት ትግል ሆኖ ሊቃኝ ይገባል፡፡ ይህ ታሪክ የሚቀየርበትና አፍሪካ በምክር ቤቱ ቃሚ መቀመጫ ማግኘት ያለባት ትክክለኛው ጊዜ ነገ ሳይሆን ዛሬ መሆን አለበት፡፡
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ግንቦት 29/2015