ሀገር በመሪና በተመሪ አስተሳሰብ ውስጥ ናት። መሪ ወደ ሥልጣን ሲመጣ በተመሪ ተመርጦ ነው። ይሄ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ሀገርና ሕዝብን መሰረት ያደረገ ነው። የትኛውም መንግሥት ከሚመራው ማህበረሰብ ጉያ የወጣ ነው። የትኛውም ፓርቲ ከሕዝብ መሀል፣ ሕዝብ ለማገልገብ፣ በሕዝብ የተደገፈ ነው። ይህ ማለት መሪዎች የሕዝቡን ባህል፣ ወግና ሥርዓት ያውቁታል ማለት ነው። ይህ ማለት የሕዝቡን ሙላት፣ ጉድለትና ሥነልቦና ተረድተውታል ማለት ነው። ይህ ማለት የሕዝቡን ጥያቄ፣ ሕዝብ ምን ፈልጎ እንዳጣ ያውቃሉ ማለት ነው።
ይህ የመሪና የተመሪ ትውውቅ መንግሥት ጥሩ ሀገርና ጥሩ ማህበረሰብ እንዲገነባ እድል ሲሰጠው ሕዝብ ደግሞ በሚመራው መንግሥት እንዲተማመን ያደርገዋል። ይህ መንግሥት የሕዝብን ጥያቄ ለመመለስ መንገድ ይከፍትለታል። እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ እኛ የመጣንባቸው የፖለቲካ መንገዶች ከነዚህ የተለዩ ናቸው። በራስ ወዳድነት እርሾ ቦክተው የተጋገሩ ፤ራስን እና ራስን ብቻ ማዕከል ያደረጉ ናቸው።
ይህንን እውነታ ለመቀየር ዛሬ ላይ እውነትና ፍትህን መሰረት ያደረገ፣ ለሕዝብ ጥያቄ የተጋ ፖለቲካ ያስፈልገናል ። ይህ ሲሆን ብቻ ነው የማይናወጥ ሰላም ልናመጣ የምንችለው። ይህ ሲሆን ብቻ ነው ጦርነትን ሽረን በጠረጴዛ ዙሪያ መግባባት የምንችለው። ይህ ሲሆን ብቻ ነው የመሪና የተመሪ ግንኙነት ትርጉም የሚያገኘው። ከታሪኳ ጋር፣ ከባህልና ሥርዓቷ ጋር፣ ከማንነቷ ጋር፣ ከስብዕናዋ ጋር ልክክ ያለ ፖለቲካና ፖለቲከኛ እንዲመጣ ፖለቲካችንን ከራስ ወዳድነት ልናጠራው ይገባል። በራስ ወዳድነት የተገነባ ፖለቲካ አይደለም ለሕዝብ ለራስ እንኳን ከአንድ ጊዜ በላይ ክብር አይሰጥም። ጦርነትን ከመውለድ ባለፈ ለሰላም የሚሆን ማህጸን የለውም። ፖለቲካችን ሰላምን እንዲፀንስ፣ ፍቅርን እንዲወልድ አገልጋይነትን ልናስተምረው ይገባል።
ከጦርነት አስተሳሰብ ለመውጣት ፖለቲካችን ሕዝብ ተኮር ሊሆን ይገባል። ሕዝብ ተኮር ፖለቲካ ሕዝብ ይጠቅማል እንጂ ሕዝብ አይጎዳም። ለሕዝብ ይሰጣል እንጂ ከሕዝብ አይወስድም። ሕዝብ ያገለግላል እንጂ በሕዝብ አይገለገልም። አንዳንድ ፖለቲከኞቻችን ዛሬ ሳይቀር የሕዝብን ጥያቄ ወደ ኋላ ብለው በጉዳቱ ለማትረፍ የሚሞክሩ ናቸው። ሰላም ባጣንባቸው ዓመታት እንኳን የሰላም አማራጮችን በመዝጋት ትርፋቸውን የሚያሰሉ ናቸው። ፖለቲካና የተባሉበትን ትልቁን ትርጓሜ ረስተው ሀገርና ሕዝብን የሚጎዳ ድርጊት ሲከውኑ በአደባባይ ይታያሉ።
እኛ ኢትዮጵያውያን እንደ አገር ያጣነው ብዙ ነገሮች አሉ። ማንም ቀምቶን፣ ማንም ወስዶብን ሳይሆን ራሳችን ከራሳችን የደበቅነው ነው። እንዴት አንድ ትልቅ ሕዝብ የራሱን ከራሱ ይወስዳል? እንዴት ክብሩን በነውር የሚቀይር ማንነት ያለው የትውልድ አረም ያፈራል ?። ተነጋግረን ያልተግባባንባቸው እና ወደጦርነት የገባንባቸው ጉዳዮቻችን ክብራችንን በነውር የቀይርንባቸው ናቸው። ከሰላም ውጪ አገር ክብር የላትም።
መሪነት ምንድነው? የተመሪነት ሚናውስ ምንድነው? በአንድ አገር ላይ እንደ መሪና ተመሪ ስንኖር የሚጠበቅብንን ሃላፊነት ማወቁ ጥቅም አለው። ስለመሪነት የተነገሩም ሆነ የተጻፉ መፃህፍቶች ጥሩ መሪ ማለት ጥሩ ሃሳብ ያለው፣ ለሰላም አማራጮች በሩን የሚከፍት፣ ከምንም በፊት የሕዝቡን ደህንነት የሚጠብቅ እንደሆነ ይነገራል። ወደ ተመሪነት ስንመጣ ደግሞ መንግሥት ሲያጠፋ የሚጠይቅ፣ ጥሩ ሲሰራ የሚያሞግስ፤ ባጠቃላይ በአገሪቱ ጉዳይ ላይ ማንኛውንም የመንግሥት እንቅስቃሴ የሚቆጣጠር እንደሆነ ይገለጻል። ከእነዚህ ሁለት የመሪና ተመሪ ጽንሰ ሃሳቦች ተነስተን ስለ ሀገራችን አሁናዊ ሁኔታ ብዙ ነገር ማውራት እንችላለን።
በአገራችን ፖለቲካዊም ሆነ ማህበራዊ እንቅስቃሴ ላይ ሕዝብ በንቃት ሲሳተፍ አይታይም። ማንኛውንም ውሳኔ ከመንግሥት ወደ ሕዝብ የሚተላለፍ ነው። ከሕዝብ ወደ መንግሥት የሚተላለፉ ፖለቲካዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ጉዳይ የለም። በአገራችን ክፍተት የፈጠረው ይሄ የመንግሥት ብቻ ውሳኔ ሰጪነት ነው። ሰላምን፣ ልማትና ብልጽግናን ለማምጣት መንግሥት ብቻውን ሚና የለውም። ከሕዝብ ወደ መንግሥት የሚተላለፍ ውሳኔ ሰጪነት ያስፈልገናል። በዓለም ታሪክ ሕዝብ ያልተሳተፈበት ፖለቲካም ሆነ ልማት የለም። አገር የሕዝብና የመንግሥት፣ የፖለቲካና የፖለቲከኞች ውህደት ናት።
በዚህ ሁሉ ውስጥ ገንኖ የሚወጣ አንድ ሃይል ያለ ሲሆን፣ እሱም የሕዝብ ሃይል ነው። የሕዝብ ሃይል ገኖ ባልወጣበት ሁኔታ የሚወሰኑ ማናቸውም አይነት ውሳኔዎች ትርጉም አይኖራቸውም። ምናልባትም ለሰላም መደፍረስ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ። ዓላማችን ሰላም ከሆነ፣ ዓላማችን እድገት ከሆነ ለሕዝብ ሃሳብ ቅድሚያ መስጠት ይኖርብናል። ዓላማችን አንድነት ከሆነ፣ ዓላማችን ብሄራዊ መግባባት ከሆነ ለሕዝብ ጥያቄ መልስ ማዘጋጀት ግድ ይለናል። ልክ አሁን ላይ ብሄራዊ ምክክር ብለን ለእርቅና ለአገራዊ ተግባቦት እንቅስቃሴ እንደጀመርንው ሁሉ ስለሰላምም ሆነ ስለሌሎች አገራዊ ጉዳዮች ከመንግሥት እኩል የሕዝቦች ውሳኔ ሰጪነት ያስፈልጋል።
በእኛና በሰለጠኑት አገራት መካከል የተፈጠረው የፖለቲካም ሆነ የኢኮኖሚ ልዩነት በዚህ ትንሽ በሚመስል የሕዝብና የመንግሥት የተሳሳተ አካሄድ የመጣ እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ። አገራችን ላይ ለተፈጠረው ጦርነት፣ ለተፈጠረው ጥላቻ፣ ለተፈጠረው ዘር ተኮር እሳቤ ይህ ፖለቲካዊ አረዳድ ተጠያቂ ነው ። ከሰላም ውጪ ሕዝብ ልዕልና የለውም። ከሰላም ውጪ ለትውልድ የምናስቀምጥለት አደራ የለም። የሕዝብና የመንግሥት መስተጋብር በእውነትና በፍትህ ቢመራ ያለጥርጥር አገራችን ላይ ለውጥ ይመጣል። ሕዝብ መንግሥትን ቢያውቀው፣ መንግሥትም ሕዝቡን ቢረዳ አሁን ላይ ያጣናቸው ነገሮች ሁሉ የእኛ እንደሆኑ የሚቆዩበት እድል ሰፊ ነው።
ለውጥና ሥልጣኔ በሚጠይቁና መልስ በሚሰጡ ሞጋቾች መካከል ያለ ነው። እኛ እኮ ያጣነው ነገር የለም። ያሉንን ነገሮች በአግባቡ መጠቀም ነው ያቃተን። በነገራችን ላይ አንድ የምታውቁትን እውነት ላስታውሳችሁ በዓለም የአገራት ታሪክ ውስጥ በተፈጥሮ ሀብት፣ በሰው ሃይል፣ በአየር ንብረት፣ በጉርብትና፣ በተመቻቸ ማህበራዊ መስተጋብር የሚገዳደረን የለም። ለልማት የሚሆኑ፣ ለእድገትና ለሥልጣኔ መንገድ የሚከፍቱ ብዙ ነገሮች አሉን። ሰላምን ሊያመጡ የሚችሉ የጋራ እሴቶችን የታደልን ሕዝቦች ነን። ግን ምን ያደርጋል እየተጠቀምንባቸው አይደለም። የሌሉንን ውስን ነገሮች እየቆጠርን ወደ ጦርነትና፣ ወደ መለያየት የምንሄድ ነን።
ኢትዮጵያን ለመለወጥ፣ ሕዝባችንን ከድህነት ለማውጣት እጃችን ላይ ያሉት እንቁዎቻችን በቂ ናቸው። ወዳለን ነገር እንያ፤ ከሚያጣላን ይልቅ የሚያፋቅሩን ብዙ ናቸው። ከሚለያዩን ይልቅ የሚያቀራርቡን እልፍ ናቸው። ማንም የሌለውን በረከቶቻችንን እንቁጠር። ኢትዮጵያዊነት መልኩን ያገኘው በአንድ ብሄር፣ በአንድ ማንነት የበላይነት ሳይሆን ከሰማንያ በላይ ብሄር ብሄረሰቦች ተደምረው ነው። መደመር ነው የሚሻለን። መደመር መብዛት ነው … አንድ መሆን ነው። የመቀነስ ስሌት ውስጥ ገብተን ዜሮ ከመሆን ባለፈ ዋጋ የለንም።
የብሄር ፖለቲካ አገርን ዜሮ ከማድረግ ባለፈ ጥቅም የለውም። የራስ ወዳድነት ፖለቲካ ሕዝብን ከድጡ ወደ ማጡ ከመስደድ ባለፈ ርባና የለውም። ጽንፍ ስንይዝ በዜሮ እየተባዛን ነው። ወደ ጦርነት ስንገባ በዜሮ እየተባዛን ነው። ጎራ ስንፈጥር ሀገራችንን እያራቆትን ነው። የሕዝብን ጥያቄ ለፖለቲካ ጥቅም ስናውለው በዜሮ እየተባዛን ነው። ከዜሮ አስተሳሰብ እንውጣ። በስመጥር አገር ውስጥ የዜሮ አስተሳሰብ ወንዝ አያሻግርም። አገራችን ስመጥር ናት። ለስሟ የሚመጥን የሰላም ሃሳብ፣ የሰላም ፖለቲካ ያስፈልጋታል። ለክብሯ የሚመጥን ክብር ያለው፤ ስለክብር የሚያውቅ ፖለቲከኛ ያስፈልጋታል።
በአንድነት ሃሳብ ከመንግሥት ወደ ሕዝብ፣ ከሕዝብ ወደ መንግሥት የተዘረጋ የእውነትና የፍትህ ድልድይ እንገባ። በሰላም ሃሳብ ከዛሬ ወደ ነገ፣ ከነገም ወደ ራቀው ነገ ተነገ ወዲያ … የሚወስድ የትውልድ መረማመጃ ምንጣፍ እናንጥፍ። በጥላቻ ከተገነቡ ድልድዮቻችን ሰባራ ናቸው። በመለያየት ከተነጠፉ ምንጣፎቻችን አዳፋ ናቸው። አይደለም ለትውልድ ለእኛ እንኳን የማይሆኑ መናኛ ነው የሚሆኑት። ያለፈ ታሪካችን አንድ አይነት ነው። በተለይ ከአጼው ሥርዓት መባቻ ወዲህ ያለው ፖለቲከና ፖለቲከኛ ማሸነፍን የተለማመደው ገሎ በመሞት ነው። አንደኛነትን የተቀዳጀው በሃይልና በጉልበት ነው። ዛሬም በዛ አስተሳሰብ ስር ነን። የኢትዮጵያን የድህነት ሚስጢር ለማወቅ፣ የሰላም እጦቷን ለመረዳት ወዴትም መሄድ ያለፈ ታካችንን በአግባቡ ለመረዳት ፈቃደኛ መሆን ብቻ በቂ ነው።
ኋላ ቀር ያደረጉን ሰላምን በጦርነት ለማምጣት የሄድንባቸው መንገዶች ናቸው። ዓለም ከበጎ ነገራችን እኩል በጦርነት እያወቀችን ነው። ብዙ ታሪኮቻችን፣ ብዙ ጀግንነቶቻችን ከጦርነት አውድ ላይ የሚመዘዙ ናቸው። አሁን ጊዜው የማሸነፍና የመሸነፍ ሳይሆን ለአንድ ሀገር በጋራ የምንለፋበት ነው። ድህነትን አሸንፈን፣ ከጦርነት ወደ መነጋገር ተመልሰን ጀግና የምንሆንበት እንጂ ገለንና ሞተን ጀግና የምንባልበት አይደለም። አሁን ግዜው መንግሥት ሕዝብን በማገልገል፣ ሕዝብም ከመንግሥት ጎን በመቆም በጦርነትና በድህነት፣ በኋላቀርነትና በብሄር እሳቤ ያጎነበሰችን አገር ቀና ማድረግ ነው።
ሕዝብን ያማከለ ፖለቲካን በመገንባት ለሀገራችን ውለታ እንዋል። መሪና ተመሪ የተሳሰሩበት የአንድ ሳንቲም አንድ አይነት ገጽ የሆኑ አገርና ሕዝብን እንስራ። ፍቅርን በመስበክ፣ ሰላምን በመናገር ለትውልዱ ቤዛ እንሁን። “ከወደ የት ናችሁ?” ስንባል ከኢትዮጵያ፤ ማናችሁ ላለን ኢትዮጵያዊ የሚል የጋራ ድምጽን እንለማመድ። የማያድፉ … የማይሰበሩ ከዚህ እስከዛ የተዘረጉ የሰላም ድልድዮችን እንገንባ። በኢትዮጵያዊነት የደመቁ ማንም የሚረማመድባቸውን የሰላም ምንጣፎች እናንጥፍ። ቸር እንሰንብት!!!
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵያ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 28 ቀን 2015 ዓ.ም