በሀገራችን በነጻ ገበያ ስም ስድ የተለቀቀው የግብይት ስርዓት ዛሬ ለምንገኝበት ከፍተኛ የዋጋ ግሽበትና የኑሮ ውድነት ዳርጎናል። የዋጋ ግሽበት አለማቀፍ መነሻና በፍላጎትና አቅርቦት አለመጣጣም የሚከሰት ቢሆንም የሀገራችን የዋጋ ግሽበትና የኑሮ ውድነት ግን ከተቀረው ዓለም የተለየ ነው የሚል ዕምነት አለኝ። ይህ ኢትዮጵያዊ የሆነ የኑሮ ውድነት፤ ኢትዮጵያዊ የሆነ ጣልቃ ገብነትና መፍትሔ ይሻል። ወደ ፊት በጥናት ሊታጀብና ሊረጋገጥ ቢችልም ገበያውን በቅርበት እንደሚከታተል የሸማቾች ተቆርቋሪ ፤ በሀገራችን እየተስተዋለ ያለው የዋጋ ግሽበትና እሱን ተከትሎ አልቀመስ ያለውና ሕዝብን ክፉኛ እያማረረ ያለው የኑሮ ውድነት ዋና መነሻ ግን በነጻ ገበያ ስም ወይም ነጻ ገበያን ተገን አድርጎ ስድ የተለቀቀው የግብይት ስርዓት ነው ማለት ይቻላል።
በአናቱ የገበያ አሻጥርና ስግብግብ ደላላ ተጨምሮበት ገበያው ለያዥ ለገናዥ አስቸግሯል። መንግስት አቅም በፈቀደ መጠን ለማረጋጋት የሚያደርገውን ጥረት ተፈላጊውን ለውጥ እንዳያመጣ አድርጎታል። ሰሞኑን ይህን መጣጥፍ እያጠናቀርሁ እያለ እስከ ግንቦት 25 ምሽት ድረስ 45 ብር እየተሸጠ የነበር ኪሎ ሽንኩርት ጾም መያዣ ሲቃረብ ማለትም በበነጋው ግንቦት 26 በአንድ ቀን በአንድ ጊዜ 20 ብር ጨምሮ 65 ብር ገባ። በዚህ አያያዙ በተከታይ ቀናትም ይብስ ሊወደድና ሊጨምር ይችላል። ይህን የታዘበ ሸማች ትላንት 45 ብር የነበረ ምን ተፈጠረና ነው በአንድ ቀን 20 ብር የጨመረው ብሎ ቢጠይቅ ነጻ ገበያ ነው ከፈለግህ ግዛ ካልፈለግህ ተወው የሚል መልስ ሊሰጠው ይገባል።
በዚህ ምላሽ ያዘነው ሸማች ወረዳ ወይም ክፍለ ከተማ ሄዶ ቢያመለክት በሚያሳዝን ሁኔታ እኛ በነጻ ገበያው ጣልቃ መግባት አንችልም የሚል ቅስም ሰባሪ ምላሽ ሊሰጠው ይችላል። በነገራችን ላይ የአዳም ስሚዟ እንግሊዝም ሆነች የነጻ ገበያ አቀንቃኟ አሜሪካ ባለስልጣናት እንኳ እንደኛዎቹ ሹማምንት ለነጻ ገበያ ጥብቅና አይቆሙም። በእነዚህ ሀገራት እንኳ ነጻ ገበያ ነው ብሎ እንዳሻው ዋጋ የሚጨምር፣ እጥፍ ስንጥቅ ላትርፍ የሚል የለም። የትርፍ ሕዳጉ ባልተጻፈው የፍላጎትና የአቅርቦት ሚዛን አማካኝነት ከአምስት ወይም ከሰባት እስከ 20 በመቶ የሚጫወት ነው።
እንደኛ አንዳንድ ስግብግብ ነጋዴ ከመርካቶ ያመጣውን ሸቀጥ ፒያሳ ላይ በእጥፍ ወይም በእጥፍ እጥፍ ልሽጥ አይልም። የትርፍ ሕዳግ ባልተጻፈ ሕግ በሻጩና በሸማቹ ስምምነት የተወሰነውና። የእኛው ግን ከዓለም ሁሉ የተለየ ነው። የተደጎመን ምርት እንዲሁም በፍራንኮ ቫሉታ የገባን ሸቀጥ ሳይቀር ነጋዴው በመደበቅ፣ ገበያን በማሻጠርና በግብይት ሒደቱ ደላላን በማስገባት የጣሰውን ነጻ ገበያ፤ መንግስት የግብይት ሒደቱን ስርዓት አሲዝልን ሲባል ነጻ ገበያ ነው ጣልቃ አልገባም ይላል።
የንግዱ ማህበረሰብ እንዳሻው እየጣሰው ላለ ነጻ ገበያ መንግስት ጠበቃና ቃፊር ሊሆን ይፈልጋል። ሲያሻው ደግሞ ድንገት ዘው ብሎ ድፍርስርሱን ያወጣና መልሶ ትቶ ይወጣል። የሀገራችን ነጻ ገበያ ለገላጋይ ያስቸገረ፤ በውስብስብ ችግር የተተበተበ ነው የሚባለው ለዚህ ነው። ለሕግ የበላይነት በጀ የማይል ነው። በጥናት ላይ የተመሰረተ ጥልቅ እይታና መፍትሔ ይሻል።
በ”The Ethiopian Economiat View” ድረ ገጻቸው ቢዝነስ፣ ኢኮኖሚክስና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በመጻፍ ፤ ማህበራዊ ሚዲያውን በተለይ ፌስቡክን ለበጎ አላማ በማዋል የሚታወቁት የኢኮኖሚክስ ባለሙያው አቶ ዋሲሁን በላይ ፤ እንደ ኢትዮጵያ ከሞላ ጎደል Progressive Capitalism (ማለትም በመንግስት ፤ የግል ሴክተሩ እና የምርምር ተቋማት በመቀናጀት ስትራቴጂክ የሆነ አቅም በመፍጠር አቅርቦት እና ፍላጎትን ማቀራረብ ላይ ያነጣጠረ) ስርዓት ለመተግበር በምትሞክር ሀገር ውስጥ ነጻ ገበያ ስለሆነ ማሰገደድ አንችልም የሚሉ መግለጫዎች፤ ነጻ ገበያ በመሆኑ መብታችን ነው ተባልን የሚሉ ሸማቾች እና ነጻ ገበያ በመሆኑ ዋጋ ተማኝ ነን የሚሉ አምራቾች/ሻጮች ፤ መስማት በጣም እንግዳ ነገር ነው ይላሉ፡፡
ነጻ ገበያ ማለት በጥቂት የመንግስት ጣልቃ ገብነት ወይም ያለ መንግስት ጣልቃ ገብነት ገበያውን አቅርቦት እና ፍላጎትን ተከትሎ እንዲመራ መፍቀድ ማለት ነው (ነጻ ገበያ የዋጋ ጉዳይ ብቻ አይደለም)፡፡ ነጻ ገበያ የኢኮኖሚ ዋና ተዋናይ የሆኑት ሸማቾች እና አምራቾች/ሻጮች ሌላው ተዋናይ መንግስት ተቀንሶ ገበያው ላይ የመወሰን መብት እንዲወስዱ የተሰጠ የውክልና አካሄድ ነው፡፡ በዜጎች መካከል ያለው የሀብት ክፍፍል ሲዛነፍም ሆነ ፍታዊነትን ለመጠበቅ ሲባል ገበያን ለብዙሃን ምቹነት ሲባል በመንግስት መጎብኘቱ አይቀርም ።
ምክንያቱም ነጻ ገበያን ይዞ ብቅ ካለው አዳም ስሚዝ (1723-1790) ጀምሮ ላለፉት 250 ዓመታት ነጻ ገበያ በወረቀት እንጂ በተግባር አሟልቶ መተግበር የቻለ አንድም ሀገር የለም፡፡ በዓለም የኢኮኖሚ ታሪክ ውስጥ ነጻ ገበያ ስርዓት ምናባዊ ነው ተብሎ የሚተችበት ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መተግበር አለመቻሉ ነው፡፡ ምክንያቱም መንግስታት በጥቂቱም ቢሆን ገበያውን ማየት አለመቻላቸው የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ጣልቃ መግባታቸው ወደው ሳይሆን ተገደው ነው።
ሀገራት በተለይ ፖለቲከኞች ነጻ ገበያ ላይ ገደብ ለማስቀመጥ የሚደፍሩበት መሰረታዊ ምክንያት የሚመነጨው ለፖለቲካል ኢኮኖሚው ደህንነት ፤ ፍታዊነትን ለመጠበቅ እና የሕዝብ የጋራ መጠቀሚያ ሀብቶችን ለመፍጠር ሲባል ነው፡፡ ገበያ ቸል በተባለ ቁጥር የጥቁር ገበያ መፈርጠም ፤ የብቸኛ አምራች እና አቅራቢነት/ሞኖፓል/ ባህሪ መፈጠር እንዲሁም ወደ ኢኮኖሚው ስርዓት መግባትን ከባድ የማድረግ ልምምድ ስለሚፈጠር ነው ሲሉ ያብራራሉ አቶ ዋሲሁን፡፡
ለነጻ ገበያ የቀረበ የኢኮኖሚ ስርዓት አመክንዬ ያላቸው ሀገራት ነጻ ገበያን የግለሰቦችን ሀብት የመፍጠር ነጻነት እና የግለሰቦችን መብት ማክበር ድረስ ነው የሚተገብሩት ምክንያቱም ነጻ ገበያ የመንግስት ቁጥጥር ብቻ ሳይሆን የመንግስት ድጎማንም ማስቀረት አለበት ስለሚል ነው፡፡ በአይነትም ሆነ በፖሊሲ ባልተደጎመ አርሶ አደር በተመጣጣኝ ዋጋ እና በገፍ ሰብል ወደ ገበያ ለማቅረብ ላደጉም ሀገራት ቀላል አይደለም፡፡
ስለ ካፒታሊዝም በተለይ የነፃ ገበያ አቀንቃኞች የማይነግሩን 23 ቁልፍ ጉዳዮች! በሚለው ድንቅ መጽሃፉ ፕሮፌሰር ሃ ጁን ቻንግ እንደሚለው በእውነት ነፃ ገበያ የሚባል ነገር የለም There is Really No Such Thing as a Free Market ወይም ብዙ ኢኮኖሚስቶች እንደሚስማሙት No Pure Free Market Economies Actually Exist, and All Markets Are in Some Ways Constrained):: ይህ ከኢትዮጰያ እስከ አሜሪካ ገበያ ያለ ሃቅ ነው፡፡
አስታውሱ የነጻ ገበያ መስፈርቶች በሙሉ ተተገበሩ ማለት መንግስት የገበያ ቁጥጥር ብቻ ሳይሆን ድጎማንም ማስቀረት አለበት ማለት ነው፡፡ በተለያየ መልኩ በድጎማ ስርዓት ውስጥ የማያልፍ አምራች እና ሻጭ ለማግኘት ከባድ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- በሚደጎም ነዳጅ ፤ በሚደጎም ውሃ፤ በሚደጎም መብራት፤ በሚደጎም የሕዝብ መገልገያ እየተጠቀሙ የሚያመርቱ አምራቾች ሸማቾችን መግፋት መብታቸው ሊሆን አይችልም፡፡ ነጻ ገበያ ነው ከፈለክ ግዛ ካልፈለህ ትተህ ሂድ፤ ከፈለኩ እሸጣለሁ ካልፈለኩ አልሸጥም፤ በገዛ ንብረቴ ዋጋ መወሰን እችላለሁ፤ ወዘተ ማለት ነጻ ገበያ ማለት አይደለም፡፡ ህግን ማስከበር ባለመቻል የሚመጡትም ሆነ በህግ ያለመገዛት አዝማሚያዎች ሁሉ የነጻ ገበያነት መገለጫ አይደሉም ሲሉ አጽንኦት ይሰጣሉ።
አቶ ዋሲሁን እንዳሉት ቁጥጥር የማይደረግበትና መንግስት ጣልቃ የማይገባበት ልቅ ነጻ ገበያ ብሎ ነገር በዓለም ላይ የለም። አዎ ሙሉ በሙሉ ነጻ ገበያ ብሎ ነገር የለም። ሁሉም ኢኮኖሚ ቁጥጥርና መንግስታዊ ጣልቃ ገብነት ይደረግበታል። በነጻ ገበያ አቀንቃኝነት በምትታወቀው አሜሪካ እንኳ ብቸኛ አምራች እና አቅራቢነትን ወይም የገበያ ሞኖፓልን፣ የሸማቾችን መብት ለማስከበር፣ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከልና የስራ ቦታ ደህንነትን ለማረጋገጥ ነጻ ገበያው በሕግና በደንብ ልጓም ይደረግበታል። ስለሆነም በየደረጃው ያለ የመንግስት አካል በነጻ ገበያ ስም ስድ የተለቀቀውን ገበያ ሀይ ሊለው ይገባል። እንዲህ ሲባል ነጻ ገበያው ለመንግስት ብቻ የተተው ነው ማለት አይደለም።
ከመንግስት ጣልቃ ገብነት በተጨማሪ ሸማቾች፣ ማህበራዊ ልማድ፣ ባህላዊ እሴቶችና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የነጻ ገበያውን ጤናማነት የመከታተል ኃላፊነት አለበት። እንደ አለመታደል ሆኖ በተለያዩ ምክንያቶች ለዘመናት ያኗኗሩን በጎ እሴቶቻችን ተሸርሽረው አንተ ትብስ አንቺ ትብሽ መባባሉን ችላ እያልነው እየተጨካከን ነው። አንዳንዱ ነጋዴማ ኢትዮጵያዊነቱን እንድንጠራጠረ ሁሉ አድርጎን ነበር። በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅት ሕዝብና ሀገር በሞትና በሕይወት መሐል እየተንጠራወዙ አጋጣሚውን ተጠቅሞ በአንድ ጀምበር ለመክበር የፊት መሸፈኛ ማስክን የሳንትሳይዘርን ዋጋ እንዴት እንዳናረው የምናስታውሰው ነው።
በሀገሪቱ በተከሰተው የኑሮ ውድነት ሸማቹ ምኑን ከምን እንደሚያደርገው ግራ በተጋባበትና በተቸገረበት አንዳንድ አከራዮች ለዛውም የከተማ አስተዳደሩ ኪራይ ላይ ጭማሪ እንዳይደረግ በደነገገበት ወቅት ከ4000 እስከ 5000 ብር ይከራይ የነበረን ባለአንድ መኝታ 10ሺህና 11ሺህ አስገብተውታል። ይህ የመተዛዘንና የመደጋገፍ ባህላችን ተሸርሽሮ ተሸርሸሮ የት እንደደረሰ ጥሩ አብነት ሲሆን መጨካከናችን በዚህ ከቀጠለ መጭው ጊዜ ከባድ ስለሚሆን ቁጭ ብሎ በጥሞና መነጋገርና እየጠፉ ያሉ መልካም እሴቶችንና ልማዶችን ለመታደግ ርብርብ ማድረግ ይገባል። እስከዚያው በማህበራዊ እሴቶቻችንና የመደጋገፍ ባህላችን መሸርሸር እየተፈጠረ ያለውን ክፍተት መንግስት የመሸፈን ድርብ ኃላፊነት አለበት።
ለመሆኑ ነጻ ገበያ ምን ማለት ነው ? የሸቀጦችና የአገልግሎቶች ዋጋ ያለማንም ጣልቃ ገብነት በፍላጎትና በአቅርቦት እንዲወሰን የማድረግ ኢኮኖሚያዊ ስርዓት ነው። በነጻ ገበያ ስርዓት ግለሰቦችና የንግድ ድርጅቶች ያለማንም ጣልቃ ገብነት በነጻነት ማምረት፣ መግዛትና መሸጥ ይችላሉ። በነገራችን ላይ የነጻ ገበያ ቀደምት አባቶች እነ አዳም ስሚዝ፣ ዴቪድ ሪካርዶ፣ ፍሬደሪክ ሀዬክ፣ ሚልተን ፍሬድማንና ሌሎች የነጻ ገበያን ጽንሰ ሀሳብ ያመጡት ውድድርና ፈጠራን በማበረታታት ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ፤ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትንና ውጤታማነትን ለማሳካትና የግለሰቦችን ኢኮኖሚያዊ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ እንጂ ነጋዴውና ደላላው እንዳሻው ገበያውን እንዲያምሰው ወይም ኮሽ ባለ ቁጥር መንግስት ጣልቃ እንዲገባ አይደለም።
አልያም ነጻ ገበያ ነው በሚል ገበያውን ስድ መልቀቅም አይደለም። የነጻ ገበያ ተቺዎች ደግሞ ነጻ ገበያ የሀብት ልዩነትን፣ ብዝበዛን፣ የገበያ ሞኖፓልንና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ የጎንዮሽ ችግሮችን ያነሳሳሉ። ሌሎች ደግሞ ነጻ ገበያ ሁልጊዜ ለሸማቹ ጥሩ ነገር ይዞ ስለማይመጣ መንግስት የሸማቹን መብትና ጥቅም ለማስከበር በተመረጠና በተጠና አግባብ ጣልቃ ሊገባ ይገባል ሲሉ ያሳስባሉ። የገበያ ውድድሩም ጤናማ እንዲሆን ጭምር መንግስት ጣልቃ የመግባት ሕጋዊ መብትና ግዴታ አለበት።
እውነት ለመናገር ከወረዳ እስከ ፌደራል ያሉ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች “ነጻ ገበያ” በሚል ነጋዴው ዋጋ እንዳሻው ሲተምን፤ የነጻ ገበያ አባትና ቃፊር ነን በሚሉ ምዕራባውያንም ሆነ በሌሎች ሀገራት ባልተለመደ አግባብ የትርፍ ምጣኔው ዕጥፍ፣ የዕጥፍ ዕጥፍና ከዚያ በላይ ሆኖ ዜጋው ሲራቆት “ነጻ ገበያ” ስለሆነ ጣልቃ አልገባም ብለው እጃቸውን አጣጥፈው ሲቀመጡ ስመለከት አዝናለሁ። ነጋዴውም በአቋራጭ ለመበልጸግና በአንድ ምሽት ለመክበር ያለ በቂ ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ዋጋ ዕለት ዕለት ሲቆልል ለምን ሲባል ደረቱን ነፍቶ “ነጻ ገበያ” ነው መብቴ ነው ፤ ከፈለግህ ግዛ ካልፈለግህ ተወው ሲል መሀል ገብቶ የሚጠይቅ አካል እምብዛም መሆኑ ዛሬ ለምንገኝበት ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት/ሀይፐር ኢንፍሌሽን/ እና ዜጋውን ላማረረ የኑሮ ውድነት ዳርጎናል።
በዚህ የተነሳም “ነጻ ገበያ ዋጋው ስንት ነው!?”ለማለት ተገድጃለሁ። ዛሬ በነጻ ገበያ ስም ያለ ምንም ኢኮኖሚያዊ ምክንያት መሰረታዊ ሸቀጦች ፤ የምግብ እህሎችና ጥራጥሬዎች በሰዓታትና በቀናት ልዩነት እየናሩና አልቀመስ እያሉ ሕዝብ ለምሬትና ለቅሬታ እየተዳረገ ይገኛል። በአንድም በሌላ በኩል ይህ የኑሮ ውድነት ለብልሹ አሰራርና ለሙስና በር እየከፈተና ሌብነት፣ ንጥቂያና ዘረፋ እየተንሰራፋ ይገኛል። በዚሁ ከቀጠለ ደግሞ የሰላምና የደህንነት ስጋት ወደ መሆን መዳሁ አይቀርም። ታዲያ በነጻ ገበያ ስም ስርዓት አልባ የሆነውን ግብይት ለማስተካከል ከዚህ በላይ ምን እስኪመጣ ድረስ ነው እግራችንን የምንጎትተው!? እጃችንን አጣጥፈን የምንጠብቀው ፤ በነገራችን ላይ መንግስትንም አመድ አፋሽ እያደረገው፤ በሕዝብና በመንግስት ላይም ልዩነትን እየጎነቆለ ስለሆነ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት ዛሬ ነገ ሳይባል ዘላቂና የማያዳግም መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል።
ሻሎም ለሀገራችን ኢትዮጵያ !
አሜን X ፫።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 27/2015