“መማር ያስከብራል አገርን ያኮራል ” የሚል መፈክር መሳይ አባባል የትምህርት በሁሉም የሕይወት ዘርፍ አስፈላጊነት ብቻ ሳይሆን ለአገርም ምን ያህል ፋይዳ እንዳለው ያመላክታል:: ትምህርት ለግል አዕምሮአዊ ዕድገት እጅጉን አስፈላጊ ነው። በዚህ ዘመን ስኬት ያለ ትምህርት ፈጽሞ ሊታሰብ አይችልም ። ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ አገር በትምህርት ውስጥ የሚያልፉ ዜጎች በጨመሩ ቁጥር ምክንያታዊ ትውልድን እያፈራች ዕድገትና ልማቷን የማፋጠን ዕድሏ እየጨመረ ይሄዳል:: ምክንያቱም በእውቀት የተገነቡ ዜጎቿ ችግሯን የሚሸሹ፣ ሲከፋም ችግር የሚፈጥሩባት ሳይሆን በቅርብ ሆነው መፍትሔ የሚሰጡና የችግርን መፍቻ ቁልፍ የታጠቁ ይሆናሉ::
ከዚሁ እውነታ ጋር በሚናበብ መልኩ፤ ኢትዮጵያዊው ደራሲ ሲሳይ ንጉሡ በ1978 ዓ.ም ባሳተመው ሰመመን ልቦለድ መጽሃፍ ላይ ትምህርት ለሁሉ ነገር መሠረት መሆኑን ፤ «…በሕይወት ላይ ትምህርት ያላስተካከለው ለውጥ ምን አለ? የዘመኑ እኛነታችን ራሱ የትምህርት ውጤት ነው:: የትምህርት መስክ ጠቦ መታየት የለበትም:: እያንዳንዷ የሕይወት እንቅስቃሴ የምትበለጽገውና የምታድገው በትምህርት ነው!» ሲል ይገልጸዋል። ይህ የደራሲው ምልከታ፤ የትምህርት ዘርፍን አድማሳዊነት ያስረዳናል። በዚህ ደረጃም አስፈላጊ ለሆነው የትምህርት ዘርፍ ተገቢውን ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል።
ከዚህም የተነሳም አገራት ለትምህርት ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ባላቸው አቅም ሁሉ በዘርፉ ውጤታማ ለመሆን ይንቀሳቀሳሉ። በሚያገኙት ውጤት መጠንም አሁናዊ ዕድገታቸው ሆነ ቀጣይ እጣ ፈንታቸው ይወሰናል። በኢትዮጵያም ቢሆን የቀደሙት አባቶቻችን ለሚወዳት አገራቸው ትልቅነት ትምህርት የሚኖረውን አስተዋጽኦ በመረዳት ለትምህርት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተው ለመስራት ጥረዋል።
በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዳግማዊ ምኒልክ የንግስና ዘመን እንደተጀመረ ታሪክ ይናገራል። ከዚህ ጊዜ አንስቶ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከጀመሩት ዳግማዊ ምኒልክ ጀምሮ በትውልድ ቅብብሎሽ አገርን በእውቀት መሰረት ላይ ለማቆም የተቻላቸውን ያህል ሠርተዋል ፤ ብዙ ዋጋም ከፍለዋል።
በተለይም በአገሪቱ ዘመናዊ ትምህርት መስፋፋትን ተከትሎ፤በማህበረሰቡ ውስጥ ስለ ትምህርት የነበረው አስተሳሰብ ከመቀየር ጀምሮ፤ ትውልድን በተሻለ የትምህርት መሰረት ላይ አንጾ ለማውጣት እንደ አገር ሰፊ ስራዎች ተሰርተዋል። የትምህርት መሰረተ ልማቶችን ከማስፋፋት ጀምሮ፤ ጥራት ያለው ትምህርት በመስጠት፤ አገር እንደ አገር የምታድግበትን፣ ዜጎችም የተሻለ ሕይወት የሚመሩበትን አገራዊ አውድ ለመፍጠር ረጅም ርቀት መጓዝ ተችሏል።
ይሁን እንጂ በአገራችን በትምህርት ዘርፍ የሚጠበቀውን ያህል ስኬት እንዳልተመዘገበበት፤ በብዙ ፈተናዎችና ተግዳሮቶች ተተብትቦ እንዳለ በርካታ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል:: ለአብነትም ያህል የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ትምህርት ሚኒስቴር ግንቦት 14 ቀን 2015 ዓ.ም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የ9 ወራት የአፈፃፀም ሪፖርት “ልብን ዝቅ፤ ደምን ከፍ ” የሚያደርግ መረጃን ይፋ አድርጓል።
በኢትዮጵያ ካሉ 47 ሺህ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ ላይ ያሉት 4 ትምህርት ቤቶች ብቻ ናቸው:: የደረጃ ምደባውን ካገኙት ትምህርት ቤቶች መካከል 99 በመቶ የሚሆኑት ከደረጃ በታች መሆናቸው የተረጋገጡ ሲሆን፤ ከደረጃ በታች የሆኑት ትምህርት ቤቶች የዳስ ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ በግብአት (በመሰረተ ልማትና በሰው ሀይል) ፣ በመማር ማስተማር ሂደትና ውጤት በኩል የሚጠበቅባቸውን ያላሟሉ ናቸው” ይላል። ይህ የሚኒስቴሩ ሪፖርት የትምህርት ዘርፍ ጥልቅ ጨለማ ውስጥ የሚገኝ ስለመሆኑ ያሳየናል።
በእውነቱ ከሆነ በአገራችን በተለይ ከባለፉት ሦስት አስርት ዓመታት ወዲህ የትምህርት ተደራሽነት ላይ ከፍተኛ ስራ ተሰርቷል። የትምህርት ተደራሽነት ማደጉን ሳይረሳ፣ በቂ የትምህርት መሣሪያ፣ አስተማሪና የትምህርት አሰጣጥን በማቅረብና መፍጠር ረገድ የተሰራው ስራ ዝቅተኛ ነው:: ወይም ስራው ፍሬያማ አልሆነም። ይህም መንግስት በትምህርት ዘርፍ የሰራውን በጎ ስራ በዜሮ የሚያባዛ ነው።
በተለይ ደግሞ በአገራችን ከተጀመረ ዘመናትን ያስቆጠረው ዘመናዊ ትምህርት ዛሬም ድረስ በዳስና ዛፍ ጥላ ስር እየተሰጠ መሆኑ መንግስትን አመዳፋሽ ያደርገዋል። በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የሚገኙ ብዙ ሺ ትምህርት ቤቶች ከዳስና ከዛፍ ጥላ ስር አልወጡም። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተማሪዎች በዳስና ዛፍ ጥላ ስር ሆነው ትምህርታቸውን ይከታተላሉ። የትምህርት ዘርፍ በአገራችን ይህን ገጽ የተላበሰ መሆን ያስደነግጣል፤ አንገት ይሰብራል!
በእርግጥም መንግስት ባለፉት አምስት ዓመታት ይህን ጥቁር ታሪክ ለመቀየር እቅድ በማውጣት የተለያዩ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል። በአገር አቀፍ ደረጃ ተመዝነው ከደረጃ በታች የሆኑ ትምህርት ቤቶችን እንዲሁም የዳስ ትምህርት ቤቶችን ሙሉ በሙሉ በማሻሻል እስከ 2020 ዓ.ም ድረስ ደረጃቸውን የጠበቁ ለማድረግ ወደ ስራ መግባቱን አውቃለሁ። ይሁን እንጂ ከአምስት ዓመት በፊት የተጀመረው የትምህርት ቤቶችን ደረጃ እንዲሻሻሉ የማድረግ ስራ ውጤታማ በሆነ መልኩ እየሄደ ስለመሆኑ ያጠራጥራል።
ለዚህ ማሳያ የሚሆነው፣ በ2011 ዓ.ም ከ21 ሺህ በላይ ለሆኑት የደረጃ ምደባ ተሰጥቶ 90 በመቶ የሚሆኑት ከደረጃ በታች መሆናቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል። በ2015 ዓ.ም በኢትዮጵያ ካሉ 47 ሺህ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ ላይ ያሉት 4 ትምህርት ቤቶች ብቻ ሲሆኑ፤ ይህም ከ99 ነጥብ 9 በመቶ የሚሆኑት ከደረጃ በታች ሆነዋል። በግልጽ መረዳት እንደሚቻለው ትምህርት ቤቶቹን እስከ 2020 ዓ.ም ድረስ ደረጃቸውን የጠበቁ የማድረግ እቅድ እውን መሆን አለመቻሉን (መክሸፉን ) ነው። በተጨማሪም በፌዴራልና በክልል ደረጃ የዳስ ትምህርት ቤቶችን ደረጃ የማሻሻል ስራ አለመሰራቱን አመላካች ይሆናል።
በ21ኛው ክፍለ ዘመን ከዳስና ከዛፍ ስር ትምህርት ቤቶች ያልተላቀቀውን ዘመናዊው ትምህርት ከገጠመው ውስብስብ ችግር ለማውጣት ትልቅ ስራ መስራት ያስፈልጋል። በዋናነት መንግስት ደረጃቸውን የጠበቁ ትምህርት ቤቶች እንዲሆኑ በጀት መድቦ የማሻሻያ ስራ ሊሰራ ይገባል። በተለይ ደግሞ ቀደም ሲል የዳስ ትምህርት ቤቶችን ሙሉ በሙሉ ለማሻሻልና ደረጃቸውን የጠበቁ ለማድረግ የተጀመረውን ስራ ከልሶ በተሻለ መልኩ ትኩረት ሰጥቶ መስራት ይኖርበታል።
እዚህ ጋር በመንግስት አቅምና በጀት ብቻ ጉድለቶቹን ማሟላት አዳጋች እንደሚሆን መረዳት አይከብድም። ስለዚህ የመንግስት ጥረት ውጤታማ የሚሆነው የሁሉም ባለድርሻዎች ተሳትፎ ሲታከልበት በመሆኑ፤ ህብረተሰቡ የበኩሉን ኃላፊነት ሊወጣ ይገባል:: በህብረተሰቡ በራሱ ወጪ ተጨማሪ ትምህርት ቤቶች በመገንባት ስራ ላይ ተሳትፎ ማድረግ፤ “የችግሩ ባለቤት መንግስት፤ መፍትሄ አብቃዩም መንግስት ነው» የሚለውን እሳቤ በመተው በስራው ላይ በንቃት ሊሳተፍ ይገባዋል። በዚህ መልኩ፣ “ከዳስ ያልወጣውን” የኢትዮጵያ ዘመናዊ ትምህርትን በተባበረ ክንድ ከችግሩ ማላቀቅ ያስፈልጋል።
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ግንቦት 27 ቀን 2015 ዓ.ም