ነገረ ልብ፤ የመነሻ ወግ፤
“የሀገር ስፋትና ጥበት የሚወሰነው በሰው ልጆች የልብ መጠን ነው” የሚሉት አባባል “በሥልጡኖቹ ሀገራት” ዘንድ ተደጋግሞ የሚነገር ብሂል ነው:: በእኛውም ሀገር ቢሆን “ልብ ከሀገር ይሰፋል” የሚለው አባባል በትንሽ በትልቁ አፍ ሲነገር የኖረ ዘመን ጠገብ ምሳሌያዊ አነጋገር እንደሆነ ማን ይስታል::
በአማርኛ ቋንቋ “ልብን” ማዕከላዊ ጭብጥ በማድረግ የተዋቀሩ እጅግ በርካታ ፈሊጣዊና ምሣሌያዊ አነጋገሮች መኖራቸውን ይህ ጸሐፊ ያረጋገጠው የተለያዩ መጻሕፍትን በማመሳከር ነው:: “ልበ ባሕር፣ ልበ ቅን፣ ልበ ደንዳና፣ ልበ ብርቱ፣ ልበ ደፋር፣ ልበ ገር፣ ልበ ጠናና ወዘተ.” የሚሏቸውን ዓይነት ፈሊጦችን በአማርኛ ቋንቋ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የሀገራችን ቋንቋዎች ውስጥ በስፋት ለማግኘት አይከብድም::
ከምሳሌያዊ አነጋገሮች መካከልም፡- “ልብ ያለው ሀገሩ ሰማይ ነው፣ ልብና ነፋስ ከሁሉ ያደርሳል፣ ልብ ሲያውቅ ገንፎ ያንቅ፣ ልብ ዳኛ ዐይን እረኛ፣ ልበ ሰፊ ነገር አሳላፊ፣ ልቡ ነጭ ያቦካል” የሚሏቸውን ዓይነት አባባሎችንም ማስታወስ ይቻላል:: ስለዚህ “ልብ” ስንል በአማካይ 320 ግራም የምትመዝነውን፣ 96,560 ኪሎ ሜትሮች ርዝመት ባላቸው የደም ሥሮቻችን ውስጥ በየደቂቃው 30 ሊትር ደም ሲዘዋወር እየተቀበለችና እየላከች (በደም ቅዳና ደም መልስ ቧንቧዎች አማካይነት) በዋነኛነት የምትመራውንና የምትቆጣጠረውን ጭብጥ የማትሞላውን ሚጢጢዬ የሰውነት ክፍላችንን ማለታችን አይደለም::
“ልብ”፡- በፈሊጣዊና በምሣሌያዊ ንግግሮች ውስጥ በውክልና የሚቆመው አስተሳሰባችንን፣ ራዕያችንን፣ በጎ ፈቃዳችንን፣ ምኞታችንን፣ የማመዛዘን አቅማችንንና ችሎታችንን በጥቅሉ ለሰብዕናችን አስኳል የሆኑ ሰብዓዊ ንጥረ ማንነታችንን ለማመልከትና ለመግለጽ ነው:: ቀደም ሲል ለማሳያነት የጠቅስናቸውን ፈሊጣዊ አነጋገሮች እንደገና መለስ ብለን የተሸከሙትን ትርጉም በግርድፉም ቢሆን ለማብራራት እንሞክር::
“ልበ ሰፊ” ወይንም “ልበ ባሕር” የምንለው ቻይነትንና ታጋሽነትን ለመግለጽ ነው:: “ልበ ቅን” ስንል ትሁት ወይንም ደግ የሚሉትን ባህርያት ለመወከል ሲሆን “ልበ ደንዳና” ግትር ችኮ፣ መንቻካ የሚባሉትን ዓይነት ባህርያት ለማመልከት ነው:: “ልበ ብርቱ” ጠንካራ ባህርይ የተላበሰ የሚል ፍች ይሰጠናል:: “ልበ ገር” የቀናነትና የየዋህነት ሰብእና መገለጫ ነው:: “ልበ ጠናና” ክፋትን እንጂ ደግ ደጉን የማያስብ የሚል ትርጉም ይሰጠናል::
ምሣሌያዊ አነጋገሮቻችንም እንዲሁ “ልብን” በተመለከተ የሚሰጡት ትርጉም ከሌጣ ፍቺያቸው እጅግ የራቁና የጠለቁ እንደሆነ ማሳየት ይችላል:: “ልብ ያለው ሀገሩ ሰማይ ነው” የሚለው ምሳሌያዊ አነጋገር የተሸከመው መልእክት “ቆራጥ ሰው የፈለገውን ለማድረግ የሚገድበው ነገር የለም” የሚል ነው:: ባእዳኑ “The sky is the limit” ከሚሉት አነጋገር ጋር ይቀራረብ ይመስለናል:: “You can achieve anything if you really want it” በማለት እንደሚጀግኑት መሆኑን ያስታውሷል::
“ልብ” ግለሰባዊ ፍላጎትን፣ መሻትን፣ ፅናትን፣ ርህራሄንና አርቆ ማሰብን፣ ግትርነትን፣ እምቢተኛነትን፣ አትንኩኝ ባይነትን ወዘተ. በአሉታዊና በአወንታዊ ትርጉሞች የሚገለጹበት መሆኑን ደግመን አስምረን እናልፋለን:: በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥም እንዲሁ “ልብ” ከአንድ ሺህ ጊዜ በላይ መጠቀሱን የሃይማኖቱ የጥናት ሰነዶች ያረጋግጡልናል:: ለአብነት ያህልም “እኛ ግን የክርስቶስ ልብ አለን” (1ኛ ቆሮንቶስ 2፡16) የሚለውን አንድ አገላለጽ ብቻ ማስታወስ ይቻላል::
ክፍሉ የሚናገረው ስለ ሥጋ ልብ ሳይሆን “ክርስቶስን እስከ መስቀል ሞት ድረስ ያደረሰው የሰው ልጆች ፍቅር በእኛም ውስጥ ሊገለጽ ይገባል፣ ርህራሄ መለያችንና መታወቂያችን ሊሆን ይገባል፣ ዕለት በዕለት የበደሉንን ይቅር ለማለት፣ እኛም ሌሎችን ከመበደል እንድንርቅ፣ ለራስ ብቻ ከመኖር ይልቅ ለሌሎች ደስታ ምክንያት መሆን እንደሚገባን” የሚያሳስብና የሚያስተምር ክፍል ነው:: “ፈርዖን ልቡን አደነደነ” የሚለው አሉታዊ ይዘት ያለው አባባልም እንዲሁ በስሜትና በድርጊት መጨከንን የሚያሳይ ነው::
ስለ “ልብ” ይህንን ያህል ካልን ዘንድ ወደ ዋናው የመነሻ ጉዳያችን አቅንተን ወቅታዊና ሀገራዊ ውሎ አምሽቷችንን ከወዲያም ከወዲህም እየጠቃቀስን እንደተለመደው ዋናውን የጽሑፍ ርዕሳችንን ተንተርሰን ከራስ ጋር ሙግቱንና ውይይቱን እንቀጥላለን::
እራሴን አሞኝ እያያችሁ፣
ለምን ሰከረ ትላላችሁ::
ለእኔ ማን ሰጠኝ ጠጅ፣
ነገር አዞረኝ እንጂ::
እንዳሉት ቀዳሚው በገና ደርዳሪ እኛም ጆሯችንን ጭው እያደረጉ ፋታ የነሱንንና እንደ ሰካራም አካላችንንም ሃሳባችንንም እያንገዳገዱ በቁዘማ የሚያወዛውዙንን ሀገራዊ ገመናዎቻችንን እየጠቃቀስን ጥቂት በመተንፈስ የስሜት ወላፈናችንን እናቀዝቅዝ::
“ልብ ያለው ልብ ያድርግ”
ዓለማችን ከደረሰችበት የዕውቀት ዘርፎች መካከል በተለየ ሁኔታ ከፍተኛ ተግዳሮትና ፈተናዎች እየተጋፈጡ ካሉት ዲሲፕሊኖች መካከል ሁለቱ የታሪክና የጂኦግራፊ ትምህርቶች ናቸው:: እነዚህ ሁለት የጥናት መስኮች ተረጋግተው በየመስካቸው ላይ የተለመደ ግልጋሎታቸውን በመስጠት ለሰው ልጆች የዕውቀት ምንጭ እንዳይሆኑ የማደፍረስ ሥራውን ተግቶ እየሠራ ያለው ደግሞ ፖለቲካ ይሉት ክፉ በጥባጭ መሆኑን የመስኩ ምሁራን በበርካታ የጥናት ውጤቶች አረጋግጠዋል::
“የራሷ እያረረባት” አሰኝቶ እንዳያስተርትብን እንጂ፤ በ1917 የጥቅምት አብዮት በቦልሼቪኮች ሶሻሊስታዊ ርዕዮተ ዓለም ፈርጥማ የተወለደችው የቀድሞዋ ታላቋ ሶቪዬት ኅብረት የዛሬዋ ሩሲያ ከ1922 እስከ 1990 በሥሯ አቅፋ የያዘቻቸው ግዛቶቿ ነፋስ እንደገባው ገለባ ብትንትን ብለው ሊከፋፈሉ ስለምን ቻሉ? ብለን እንጠይቅ::
የፖለቲካቸው መርዝና የገዢዎቿ የልብ ድንዳኔ ነፋስ ዘርተው አውሎ ነፋስ ስላሳጨዳቸውም አይደል? ዛሬም ድረስ ሳንጃ ከመሞሻለቅ እንዳያርፉ ያደረጋቸውስ ይኼው የፖለቲካ ጦስና ጥንቡሳት አይደለምን? ለዚህ አባባላችን ማሳያ የሚሆነው በዚህ ሰዓት አፈሙዙን ከፍቶ ፍጥረት እያጨደ ያለውን የዩክሬንና የሩሲያን ጦርነት ማስታወስ ይቻላል:: ፖለቲካው በታሪካቸውና በጂኦግራፊያቸው ማንነታቸው መሃል ተሰንቅሮ በመግባት የፈጠረው ስንጥቅ መቼ ክፍተቱ ሞልቶ እንደሚገጥም ለጊዜ ጊዜ ሰጥቶ በትዕግሥት መጠበቁ ይበጃል:: የቀድሞዋን ዩጎዝላቪያ፣ የቅርብ አሳረኛ ጎረቤታችንን ሱዳንን ወዘተ. እየጠቃቀስን ብንዘረዝር ብዙ ማለት ስለሚቻል እዚሁ ላይ መግታቱ ይበጃል::
“እኛም በሀገራችን ሰላም ፍሪዳችን”፤
የምሳሌያዊ አነጋገሩ ፍቺ በሌሎች ላይ መጠቆም ብቻ ሳይሆን እኛንም ሰላም እንደ ፍሪዳ አስጎምጅቶናል፣ የሰላም እጦቱም ከእህል በከፋ ሁኔታ ርሃብተኛ አድርጎናል ማለት ነው:: እንዴታውን ለማብራራት ጥቂት ሀገራዊ ምሳሌዎችን መነሻ በማድረግ ለመንደርደር እንሞክር:: ወያኔ በለኮሰው ጦርነት ምክንያት ከማዕከላዊ መንግሥት ጋር የተፈጸመው ደም የመቃባት ጦርነት ለመቶ ሺህዎች ሞት ምክንያት ሊሆን ችሏል:: የብዙዎች ግምት ወደ ሚሊዮን ይቃረባል:: ሺህ ምንተ ሺህ ወገኖችም ተፈናቅለው ለመንከራተት ተዳርገዋል:: በትሪሊዮን የሚቆጠር የሀገር ንብረት እንዲወድምና በቀላሉ ሊፈወስ የማይችል የሥነ ልቦና ቀውሱም ከሚገመተው በላይ ነው::
በዚህ ጦርነት ምክንያት ኢትዮጵያ እያለቀሰችና እየደማች እንድትኖር የተፈረደባትና ቁስሏም ሙሉ ለሙሉ ለማገገም ዓመታት ይፈጃል እየተባለ በባዕዳን መንግሥታት ሳይቀር ነጋ ጠባ የሚተነበየው በምን ምክንያት ነው? መልሱ ቀላልም ግልጽም ነው – የፖለቲካው ብልሽት ውጤት እንደሆነ ማንም አይክድም:: በዚህም ይሁን በዚያ ፖለቲካው በዋነኛነት የተጠቀመበት ዘዴ ክልላዊ ታሪክ፣ ጂኦግራፊንና ቋንቋን እንደ ምክንያት በመጠቀም “የራስ በራስ አስተዳደር” የሚል ሽፋን ተከናንቦና በግለሰቦች የሥልጣን ጥያቄ ተጠምቆ እንደሆነ ከልጅ እስከ አዋቂ የሚያውቀው ሐቅ ነው::
ባለፉት ዓመታት ሀገር ተሸማቃ አንገቷን ከደፋችባቸው አሳፋሪ ምክንያቶች መካከል አንዱንና በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ ላይ ሃሳባችንን የገለጽንበትን አንድ ጉዳይ ማስታወሱ አግባብ ይመስለናል:: ዛሬ ችግሩ እንዴት እየተቀረፈ መረጃ ባናሰባስብም ከተወሱኑ ዓመታት በፊት በበርካታ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማቶቻችን ውስጥ የታሪክ ትምህርት ክፍሎች ተዘግተው እንደነበረ የምናስታውሰው ነው::
የጂኦግራፊው የትምህርት ክፍልም እንዲሁ የሚመዘገቡ ተማሪዎች እስከ ማጣት ደርሶ ብዙ ዩኒቨርሲቲዎች ሁለትና ሦስት ልጆችን ይዘው ሲተክዙ መክረማቸው አይዘነጋም:: ለዚህ አሸማቃቂ ክስተት ሰበበ ምክንያቱ ምን ነበር? አሁንም መልሱ ግራ የሚያጋባ አይደለም – የፖለቲካው ጡንቻ በርትቶ ጉልበቱን በሁለቱ ዲስፕሊኖች ላይ ስላሳየ ነበር:: እንዴታውንና ለምኑን መዘርዘሩ ለቀባሪ የማርዳት ያህል ስለሚቀልብን ብናልፈው ይበጃል::
በዛሬይቱ ጀንበርም ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን ልባችንን እጅግ ከማጥበባችን የተነሳ ሀገራችን በልባችን ልክ ጠባ ክፉኛ እስከ መደንገጥ የደረስንበት ወቅት ነው:: ጥበቷም እጅጉን ስላሳሰበን የገጣሚውን ስንኞች ተውሰን እንደ ብሔራዊ መዝሙር እስከ ማንጎራጎር ደርሰናል::
ሀገር ድንኳን ትሁን ጠቅልዬ የማዝላት፣
ስረጋ ተክዬ ስገፋ እንድነቅላት::
“ሀገራችን ጠባለች” የሚለውን መነሻ ሃሳብ አስፋፍቶ ማብራራቱ ተገቢ ይመስለናል:: ቀደም ሲል ለመጥቀስ እንደተሞከረው ፖለቲካችን በታሪክና በጂኦግራፊ የዕውቀት ዘርፍ ላይ ሰልጥኖ እንዳስገበራቸው ለማስረጃነት የሚቀርቡ ብዙ ማሳያዎች እንደሚኖሩ ከዚህ ጸሐፊ በተሻለ አንባቢያን የሚረዱት ይመስለናል::
በጋራ ታሪክና እሴቶች ላይ ለመግባባት ከተሳነን ዓመታት ነጉደዋል:: ስለምን ቢሉ የፖለቲካ ባህላችን የተበረዘና “በገዢዎች ‹የእኔ ብቻ ልክ› ትምክህት የተቃኘ” ስለመሆኑ ያግባባን ይመስለናል:: የሀገራዊ ድንበራችንና ወሰናችን ጉዳይም ከውስጥ ብቻ ሳይሆን ከውጭ ኃይላትም ፈተና በዝቶበት ድንጋጤ ላይ ከወደቅን እንዲሁ ብዙ መስቀል ተተኩሷል:: ለዚህስ ምክንያቱ ምንድን ነው ብንል ብንጠይቅ አሁንም መልሳችን “ግራ የተጋባው ፖለቲካችን” ግራ ስላጋባን ነው የሚል ይሆናል::
ከዚህ ሁሉ የከፋው ግን ዜጎች እንደ ልብ መንቀሳቀስ ተስኗቸው በየአካባቢያቸው ተገድበው ለመኖር መገደዳቸው ነው:: እንደ ቀዳሚ ዘመናት ወደ አንድ የሀገሪቱ ክልል ለመንቀሳቀስ የሚጠየቀው መረጃና የሚሰጠው ትንታኔ እንዲህ በቀላሉ “አካባቢው ሰላም ነው” ተብሎ ብቻ የሚታለፍ አይደለም:: የሞት ፍርሃቱ፣ የመታፈን ስጋቱ፣ የመሰናክሉ አበዛዝና በየኬላዎቹ ላይ የሚፈጸመው የግፍ ዓይነት በእጅጉ ያስደነግጣል:: በአጭሩ ለማለት የሚቻለው ልባችንን አጥብበን ኬላዎቻችንና መንገዶቻችን በፍርሃት ውስጥ ስለወደቁ ግፈኞች እንደፈለጋቸው እየፋነኑበት የወንጀል ድርጊቶች በሽበሽ ስለሆኑ እንቅስቃሴዎቻችንን ለመገደብ ተገደናል:: እንቅስቃሴዎቻችን ተገደቡ ማለት ደግሞ ልባችንም ሀገራችንም ተያይዘው ጠበቡ ማለት ነው::
ልባችን ስለጠበበ ኑሯችንና ኢኮኖሚያችንም አብሮ ተጨማዷል:: ልባችን ስለጠበበ የፖለቲካችን ጡንቻ አብጦና ደድሮ ዲሞክራሲን በእግሩ ሥር በማንበርከክ ተስፋችንን አምክኖታል:: ልባችን ስለጠበበ ሃይማኖት አቅሙንና ሥልጣኑን ተነጥቆ መራቆቱን ማስተዋል ከጀመርን ሰነባብተናል:: በጸሐፊው እምነት ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ዛሬ “የልብ ጠጋኝ ወይንም ፈዋሽ” የልብ አውቃ ባለመድኃኒቶች የሚያስፈልጉን ጊዜ ይመስላል::
እከሌ ከእከሌ ሳንባባል ቀጣዩ የሀገራችን ዕጣ ፈንታ ከእጃችን ሳይወጣ “ምን ነክቶን ነው?” በመባባል እርስ በእርስ ለመጠያየቅና ለመሟገት ሀሞታችንን አምርረን ለመጨከን ትክክለኛው ጊዜ አሁን ይመስለናል:: በጋራ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ተቀራርበን፣ የተኳረፍንም ብንኖር በልብ ስፋት ይቅር ተባብለን፣ ተጨካክነንም ከሆነ የኮመጠጠውን ስሜታችንን አስክነን፣ ልበ ጡልነት (ወፈፌነት) ቀልባችንን ነስቶን ከሆነም ረጋ ብለን ለመደማመጥ በተጫነን አዚም ላይ ልንሰለጥንበት ይገባል? በጋራ ሞትን ከምንጠራ መሰንበት ስለሚበጅ::
ተስፋችን ከዕለት ወደ ዕለት እየጠወለገና እየወየበ ሲሄድ እየተመለከትን እንደምን በቁም እንቅልፍ ማንጎላጀጁ ሊመቸን ቻለ? ተስፋው የተሟጠጠበት ነብየ እግዚአብሔር ኢዮኤል ቢቸግረው ሳይሆን አይቀርም፤ “ከተምች የቀረውን አንበጣ በላው፣ ከአንበጣ የቀረውን ደጎብያ በላው፣ ከደጎብያ የቀረውን ኩብኩባ በላው” በማለት በተስፋ ሞታቸው ላይ ቅኔ የተቀኘው::
የሚገርመው ደግሞ ይህንኑ ሙጣጭና እንቃሪ ያልቀረለትን ታሪካቸውን የገለጸው እንዲህ በማለት ነበር፡- “ይህ በዘመናችሁ ወይስ በአባቶቻችሁ ዘመን ሆኖ ነበርን?” ብሎ ከጠየቀ በኋላ የለገሳቸው ምክረ ሃሳብ እንዲህ የሚል ነበር:: “ይህንን ለልጆቻችሁ ንገሩ፤ ልጆቻችሁም ለልጆቻቸው፣ ልጆቻቸውም ለኋለኛው ትውልድ ይንገሩ” በእውነቱ ይህን መሰሉ የጨፈገገ ተስፋ ምን ትምህርት ሊሰጥ ከትውልድ ትውልድ እንዲተላለፍ ተፈለገ? ምክንያቱን ነብዩ ስላልገለጸልን እናልፈዋለን::
ሀገሬ ሆይ የምንጠይቅሽን ጥያቄ ሳትሸፋፍኚ መልሽልን:: “በእኛ ዘመን ልባችንን ከማጥበባችን የተነሳ ሀገራችንንም ሸብሽበን አጥብበን ነበር” ብለን ለመጭው ትወልድ የታሪክ ማስታወሻ ብናኖር ምን ይረባሻል? “በኖርንበት ዘመን ሞት ብርቃችን አልነበረም፣ መፈናቀልም እንዲሁ፣ ቋንቋችን እንደ ባቢሎን ‹ግንበኞች› ተደበላልቆ መግባባት ስለተሳነን እርስ በእርሳችን ላይ የመከራ ዶፍ ለማዝነብ ተጨካክነን ነበር፣ በልተን የኖርነው በተዓምር ነው፣ ዕድሜያችንን የፈጀነው የተስፋ አየራችን ከብዶብን ለመተንፈስ እንኳን ተቸግረንና ግራ ተጋብተን ነው” ብለን ለትውልድ ፈርጀ ብዙ መርዶ ሰንደን ብናስተላልፍስ ፋይዳው እንኳን ቢቀር መፃኢው ትውልድ አይፈርድብሽም? አይፈርድብንም? ኢትዮጵያ ሆይ! ደግመን እንማጸንሻለን፡- “ልባችንን ከቂም በቀል፣ ቃላችንን ከበደል፣ እጃችንን ከመገዳደል እንድንጠብቅ ተቆጭን፤ ምከሪን፤ ገስጪን ወይንም ቅጭትን::” ምክራችን ይህ ነው:: ሰላም ለሕዝባችን ለዜጎችም በጎ ፈቃድ::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 26/2015