ለኢትዮጵያ መልካም ስምና ገጽታ ጉድፍ እየሆኑባት ከሚገኙ እንከኖች መካከል አንዱ ልመና ነው፡፡ ልመና መደበኛ ስራ እስከሚመስል ድረስ በርካታ ዜጎች እጃቸውን ለልመና ሲዘረጉ ይስተዋላሉ፡፡ የልመና ተግባር በብዙዎቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚታይ ድርጊት ቢሆንም በከተሞች፣ በተለይም በአዲስ አበባ፣ ስር የሰደደ ችግር ሆኗል፡፡ ሀገሪቱን ያጋጠሟት ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ደግሞ ችግሩን እንዲባባስ አድርገውታል፡፡
የችግሩን አስከፊነት የተረዱ ወገኖች ልመና ከዚህም የበለጠ እንዳይስፋፋ ጥረቶችን ሲያደርጉ ቆይተዋል፤ እያደረጉም ይገኛሉ፡፡ እነዚህ አካላት ልመናን ለማስቆም የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራት ከመፈጸም በተጨማሪ በልመና ሕይወት ላይ ተሰማርተው የሚገኙ ዜጎችን ከጐዳና በማንሳት ወደ ቤተሰብ እና ወደ ማገገሚያ ማዕከላት በማስገባት የሥነ ልቦና ድጋፍና የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን ሰጥተው ግለሰቦቹ ወደ መደበኛ ሕይወትና አምራችነት እንዲመለሱ የተለያዩ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡
ይህም ሆኖ የችግሩ ስፋትና አሳሳቢነት በየጊዜው እየጨመረ በመምጣቱ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ተጨማሪ ጥረቶችን መጠየቁ አስገዳጅ ሆኗል። ‹‹የኢትዮጵያ ልጆች እርስ በእርስ መተጋገዝ የበጎ አድራጎት ማኅበር›› የተሰኘው ምግባረ ሰናይ ተቋም ልመና በሕግ እንዲታገድ የሚያደርገው ትግልም ልመናን የመግታትና በዘላቂነት የማስወገድ ጥረት አካል ነው፡፡ ማኅበሩ በመጋቢት 2014 ዓ.ም ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሲቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ህጋዊ ፈቃድ ያገኘ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅትም ከአምስት ሺ100 በላይ አባላት አሉት፡፡
የዜጎችን ሀብት በማቀናጀትና በማንቀሳቀስ በድህነት ውስጥ ያሉ ወገኖች ወደ ልመና እንዳይወጡ ባሉበት ቦታ በቋሚነት የሚታገዙበትን አማራጭ በመፈለግ ፍትሀዊ፣ ተደራሽና የተቀናጀ የእርስ በእርስ መተጋገዝ ባህል ማሳደግን አልሞ የተቋቋመው ይህ ማኅበር፣ ልመና በሕግ የተከለከለ ተግባር ሆኖ የማየት ራዕይ አለው፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚገኙ አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያን፣ አቅመ ደካሞች፣ ወላጅ አልባ ህፃናትና በማህበራዊ ቀውስ ውስጥ ያሉ ሴቶችና ወጣቶች ማኅበሩ ትኩረት የሚያደርግባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ናቸው።
ማኅበሩ እነዚህን የማኅበረሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ለማድረግ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል ሀገር አቀፍ የግንዛቤና ንቅናቄ መድረኮችን በየደረጃው በመፍጠር ዜጎች እርስ በእርስ የሚተጋገዙበት መደበኛ አሠራር ያለው ማህበራዊ ፈንድ በአንድ ቋት ማዘጋጀት፤ ሰዎች ከአካባቢያቸው ሳይርቁ የመልሶ መቋቋሚያ፣ ማገገሚያ የቋሚና ጊዜያዊ ምገባ እና የክህሎት ማስተማሪያ ማዕከላት ጣቢያዎችን በማቋቋም ጥቅም ላይ ማዋል የሚሉት ይገኙበታል፡፡
መስራት የሚችሉ እናቶች ህፃናት ልጆቻቸውን የሚያስቀምጡበት ቦታ በማጣት ለችግር እንዳይጋለጡ የህፃናት ማቆያ ቦታ ማዘጋጀት፤ የስራና ክህሎት መፍጠሪያ በማዘጋጀት ስራ መስራት ለሚችሉ አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞችና በከፋ የድህነት ችግር ውስጥ ላሉ ወገኖች ስልጠናና የመስሪያ ቁሳቁስ በመስጠት የስራ እድሎችን መፍጠር እንዲሁም እናቶችን እንደ ባልትናና እደጥበባት ባሉ የስራ መስኮች ተጠቃሚ ማድረግ የሚሉትም ሌሎች ተግባራቶቹ ናቸው፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ልጆች እርስ በእርስ መተጋገዝ የበጎ አድራጎት ማኅበር›› ፕሬዝደንት አቶ ነፃነት ጣሰው፣ ማኅበሩ በ2014 ዓ.ም ሲመሰረት ልመናን የሚከለክል ሕግ እንዲወጣ አስተዋፅዖ ለማድረግ እንደሆነ ይናገራል። አቶ ነፃነት እንደሚለው፣ ማኅበሩ የተመሰረተበት ዋና ዓላማ የጎዳና ላይ ልመናን በሕግ በታገዘ አሰራር በማስቀረት፣ ኅብረተሰቡ የእርስ በእርስ የመረዳዳት እሴቱን ተጠቅሞ በሚያከናውናቸው ተግባራት፣ የተቸገሩና በልመና ላይ የተሰማሩ ዜጎች ዘላቂ ተጠቃሚ እንዲሆኑና ልመናን የሚጸየፍ ማኅበረሰብ ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ነው፡፡
ድርጅቱ በይፋ ከመመስረቱ በፊት በኢትዮጵያ በ10 ከተሞች ስለልመና ሁኔታ ጥናት ለማድረግ ሞክሯል። በየከተሞቹ ያለው የልመና ሁኔታ/ደረጃ፣ የችግሩ መንስኤዎች እና በልመና ሕይወት ላይ የሚገኙ ሰዎች ቀጣይ እጣ ፈንታ በጥናቱ የተዳሰሱ ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ወደ ኢትዮጵያ ገብተው የሚንቀሳቀሱ በርካታ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ቢኖሩም የልመና ተግባር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፋ የመሄዱ ምክንያት እንዲሁም ድርጅቶቹ ለሀገሪቱ ያስገኙት ጥቅም ምን እንደሆነም በጥናቱ ለመዳሰስ ተሞክሯል፡፡
የጥናቱ ግኝቶች እንደሚያመለክቱት፣ ተቸግረው የሚለምኑ ሰዎች ቁጥር ዝቅተኛ (34% ብቻ) ነው። ልመናን እንደ ስራ ቆጥረው በድርጊቱ ላይ የተሰማሩና በደላሎች አማካኝነት ወደ ልመና የገቡ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡ የልመና ተግባር መስፋፋት ከድህነት ብቻ ሳይሆን ከአመለካከት ችግር ጋር የተያያዘም ነው፡፡ ከጎዳና ልመና ተነስተው ወደ መደበኛ ሕይወት እንዲመለሱ የተደረጉ ሰዎች በድጋሚ ወደ ልመና ተመልሰው ታይተዋል፡፡ ልመና ከፍተኛ ማኅበረ-ኢኮኖሚያዊ ቀውስ እየፈጠረ ሲሆን፣ ተግባሩ፣ የወንጀለኞች መደበቂያ እየሆነ እንደሚገኝም ጥናቱ አሳይቷል፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ 30 የማገገሚያ ማዕከላት እንዲገነቡም በጥናቱ ምክረ ሃሳቦች ላይ ተጠቁሟል፡፡
ማኅበሩ በተለያዩ ከተሞች ያካሄደውን የመነሻ ጥናትና ምክረ ሃሳቦቹን በተደራጀ መልኩ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ፣ ለሁሉም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች፣ ለሃይማኖት ተቋማት፣ ለመገናኛ ብዙኃን እና ለሲቪክ ማኅበራት አቅርቧል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔም ጉዳዩን ወደ ምክር ቤቱ የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርተውት ማኅበሩ ከቋሚ ኮሚቴው ጋር ውይይት አድርጓል፡፡ በውይይቱም ምክር ቤቱ እና ማኅበሩ በጉዳዩ ላይ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል፡፡
ቋሚ ኮሚቴው ከዚህ ቀደም ያልታዩ ጉዳዮች በማኅበሩ ጥናት መካተታቸውን በአድናቆት መግለጹን ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡ ማኅበሩ የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በማካተት የጎዳና ላይ ልመና በሕግ እንዲከለከል በአፅንዖት መምከሩን ጠቅሰው፣ ቋሚ ኮሚቴውም ምክረ ሃሳቡን በአወንታዊነት እንደሚቀበለው ማሳወቁን ፕሬዚዳንቱ ገልጿል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ልጆች እርስ በእርስ መተጋገዝ የበጎ አድራጎት ማኅበር›› ልመናን በዘላቂነት ለማስቀረት የጎዳና ላይ ልመና በሕግ እንዲከለከል ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ በፅኑ ያምናል ያለው ፕሬዚዳንቱ፣ ከዚህ በተጨማሪም የማኅበራዊ ጥበቃ ፈንድ መቋቋም ለችግሩ ዘላቂ ምላሽ ለመስጠት የሚደረገውን ጥረት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያግዘው የማኅበሩ እምነት መሆኑን ተናግሯል፡፡
አቶ ነፃነት እንደሚለው፣ የሕግ ማዕቀፍ ከሌለ በስተቀር የጎዳና ልመናን ማስቀረት አይቻልም፡፡ ከሌሎች ሀገራት ተሞክሮ በመውሰድ ኢትዮጵያውያንም የማኅበራዊ ኃላፊነት ክፍያ በመክፈል የተቸገሩ ዜጎች ለልመና እንዳይዳረጉ ማድረግ ይገባል፡፡ ‹‹ልመና በዚህ ደረጃ የተስፋፋው ጉዳዩ ትኩረት ስላልተሰጠው እንጂ በድህነትና በማጣት ብቻ አይደለም፡፡ በደላሎች አማካኝነት ልመናን የተቀላቀሉ ሰዎች መኖራቸው ይህን ያሳያል፡፡
የማኅበራዊ ጥበቃ ፈንድ ማቋቋም ልመናን ለማስቀረት ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ማኅበሩ ባካሄደው የጥናት ምክረ ሃሳብ ላይ ተመላክቷል። እያንዳንዱ ግብር ከፋይ ኢትዮጵያዊ የማኅበራዊ ኃላፊነት ክፍያ መክፈል አለበት›› በማለት ሕጋዊ ማዕቀፍ የማበጀትና የማኅበራዊ ጠበቃ ፈንድ የማቋቋም ተግባራት ልመናን በዘላቂነት ለማስቀረት ዓይነተኛ መፍትሄዎች ስለመሆናቸው ያስረዳል፡፡
እንደ ነፃነት ገለፃ፣ ማኅበሩ የሚታገልለት ከልመና የተፋታ ዘላቂ የመተጋገዝ ባህል ሲያድግ ዘላቂ ውጤት የሚያስገኝ መረዳዳትን እውን ለማድረግ የሚያስችል መደበኛ መድረክና አሰራር ይፈጥራል፡፡ ፍትሐዊ ንግድ፣ የስራ ዕድል፣ የመጠለያና ምገባ አቅርቦት መስጠትና መቀበል የሚያስችል እንዲሁም ማህበራዊ ኃላፊነት ተግባራዊ የሚደረግበት አሰራርና አስተዳደር ይኖራል። ማህበራዊ ኃላፊነትን የሚወጡ ተቋማትና ባለ ድርሻ አካላት እየበዙ ሲመጡ የበርካታ ዜጎችን ሕይወት ለመታደግና ለመቀየር ዕድል ይፈጥራል፡፡ ባለድርሻ አካላትና ዜጎች የበለጠ የገንዘብ፣ የጊዜ፣ የዕውቀት፣ የጉልበት አበርክቶ ለመስጠትና ማህበራዊ ኃላፊነትን ለመወጣት በቅንጅትና በተደራጀ መንገድ ለመስራት ይነቃቃሉ፡፡
ማኅበሩ ‹‹አምስት ዳቦ ለአንድ ቤተሰብ›› የሚል መርሃ ግብር አለው፡፡ ይህ መርሃ ግብር የተቸገሩ ወገኖች እጅግ አስፈላጊና አጣዳፊ ፍላጎት የሆነውን ምግብ እንዲያገኙ ለማስቻል እንጂ በዚህ መልኩ እንዲቀጥል የሚፈለግ ተግባር አይደለም፡፡ የማኅበሩ ዓላማ የተቸገሩ ወገኖች በዘላቂነት የሚቋቋሙበት አሰራር እንዲፈጠር ማድረግ ነው፡፡ የማኅበሩ ‹‹አምስት ዳቦ ለአንድ ቤተሰብ›› መርሃ ግብር በአሁኑ ጊዜ 75 ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ ሲሆን፣ ምግብ ለማግኘት አቅም የሌላቸው ዜጎች ምግብ እንዲያገኙ እገዛ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ የተቸገሩ ዜጎች ምግብ እንዲያገኙ ከሚያከናውነው ተግባር በተጨማሪ ከድጋፍ አድራጊ አካላት ጋር በመተባበር የአቅመ ደካሞች ቤት እንዲታደስም አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ለሚያከናውናቸው ተግባራት የሚያስፈልገውን ገንዘብ የሚያገኘው አባላት ከሚከፍሉት ክፍያ (መዋጮ) ነው፡፡ ማኅበሩ ከየትኛውም የውጭ ድርጅት ገንዘብ አይቀበልም፡፡
የተቋሙ ትኩረት እርዳታ በመስጠት ላይ ሳይሆን የችግሮችን መሰረታዊ መንስዔዎች በመለየትና መፍትሄዎችን በማመልከት ላይ ነው፡፡ ማኅበሩ በእስካሁን እንቅስቃሴው ልመና በሕግ ይታገድ የሚለው ጉዳይ የመንግሥትና የኅብረተሰቡ አጀንዳ እንዲሆን ማድረግ ችሏል፡፡ ማኅበሩ የማኅበራዊ ጥበቃ ፈንድ አዋጅ ሕጋዊ መሰረት እንዲኖረው ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
ማኅበሩ የጎዳና ላይ ልመናን የሚከለክል ሕግ እንዲወጣ የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን ለዚህ ተግባር ስኬትም ከመንግሥት፣ ከኅብረተሰቡ እና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እንደሚሰራ የማኅበሩ ፕሬዝደንት አቶ ነፃነት ይገልጻል፡፡ ‹‹ልመና በሕግ እንዲከለከል የምናደርገው ጥረት ከተሳካ በኋላ የአቅም ግንባታ ስራዎች ላይ አተኩረን እንሰራለን። ትምህርት ቤቶችንና የስልጠና ማዕከላትን የማቋቋም እና የስራ ፈጠራ ባህልን የማሳደግ ተግባራት ላይ እናተኩራለን›› በማለት የማኅበሩ ቀጣይ እቅዶች በአቅም ግንባታ ተግባራት ላይ የሚያተኩሩ እንደሚሆኑ ተናግሯል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ማኅበሩ ከመንግሥት ጋር በመተባበር በስራ አጥነት ችግር መንስዔዎችና መፍትሄዎች ላይ ያተኮረ ጥናት የማድረግ እቅድም አለው። የስራ አጥነት ችግር መነሻ ምክንያቶች፣ የኅብረተሰቡ የስራ ባህል እና የችግሩ መፍትሄዎች በጥናቱ ትኩረት የሚደረግባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ይሆናሉ፡፡
አቶ ነፃነት የጎዳና ላይ ልመናን በዘላቂነት ለማስቀረት ከኅብረተሰቡና ከመንግሥት ስለሚጠበቀው ኃላፊነት ሲናገር፣ ‹‹ሕብረተሰቡ ጎዳና ላይ ለሚለምኑ ወገኖች እጁን መዘርጋት የለበትም፡፡ መንግሥት በበኩሉ የጎዳና ላይ ልመናን የሚከለክል ሕግ ማውጣትና የተቸገሩ ወገኖች በዘላቂነት ተጠቃሚ መሆን የሚችሉበት የማኅበራዊ ጥበቃ ፈንድ እንዲቋቋም ማድረግ አለበት›› ይላል፡፡ ማኅበሩ የጎዳና ላይ ልመና በሕግ እንዲከለከል የሚጠይቅና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚቀርብ የ50ሺ ዜጎች የፊርማ ዘመቻ (Petition) በቅርቡ እንደሚጀምርም ጠቁሟል፡፡
አንተነህ ቸሬ
አዲስ ዘመን ግንቦት 25/2015