ጥራት ያለው ትምህርት ጥራት ያለው ሀገርና ማህበረሰብ ብሎም ትውልድ የሚገነባበት የልህቀት ማዕከል መሆኑ እሙን ነው፡፡ ዓለም ከትላንት ወደ ዛሬ በሚያስገርም የለውጥ ርምጃ ላይ የቆመችው እውቀት በሚሉት ሀያል መንኮራኩር ላይ ተፈናጣ ነው፡፡
ደቡብ አፍሪካዊው የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ይህን የትምህርትና የለውጥ ቁርኝት አስመልክቶ “ትምህርት ዓለምን ለመቀየር የምንችልበት እጅግ ዋናው ኃይላችን ነው” ብለው ነበር፡፡ ዓለም ላይ የታዩ የስልጣኔ ወጋገኖችን ያለ እውቀት ማሰብ ፈጽሞ የማይቻል ነው፡፡
ዓለምን ያለ እውቀት ብናስባት ብዙ ርቀቶችን ወደኋላ መሄድ ያሻናል፡፡ ስልጣኔና ዘመናዊነት ባልተስፋፉበት በዛ ጥንት ዘመን ዓለም በጥበቧ ሰልጥና የአሁኑን አይነት ልዕልና አልነበራትም፡፡ ዓለምን የቀየራት የእውቀት ኃይል፣ የማስተዋል ርምጃ ነው፡፡ አሁን ላይ የምንገረምባቸውን ቴክኖሎጂዎች እያየን ያለነው ሰው እውቀትን የኃይል ምንጭ አድርጎ ነው፡፡
ዓለም ከዛሬ በተሻለ የለውጥና የተሐድሶ ርምጃ ወደ ነገ እንደምታዘግም ለሁላችንም ግልጽ እውነታ ቢሆንም፤ ይህ ሁለንተናዊ ለውጥ እንዴት መጣ? ከየት መጣ? ብለን ስንጠይቅ መጀመሪያ የምናገኘው ጥራት ያለው የትምህርት ስርዓትን ነው፡፡ ጥራት ያለው የትምህርት ስርዓት ሀገርን ከኋላ ቀርነት የሚታደግ፣ በእውቀትና በክሂሎት፣ በምክንያትም የተገነባ መፍትሄ መር ስርዓት ነው፡፡
በዚህ ብቻ አያበቃም፣ በሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚና የፖለቲካ የበላይነት ብናጠና መለኪያው እውቀትና ጥራት ያለው የትምህርት ተደራሽነት እንደሆነ እንደርስበታለን፡፡ በግልጽ ቋንቋ ለመናገር ጥራት ያለው ትምህርት ጥራት ያለው ሀገርና ማህበረሰብ፤ ትውልድም የሚፈጥር የልዕልና ምንጭ ነው።
የእውቀት ኃይል የማይገባበት ስፍራ የለም። እንደ ህልመኛ ሀገር ለመቀየር የተነሳ ማህበረሰብ መጀመሪያ ሊለማመደው የሚገባው የእውቀትን ኃይል ነው። ከእውቀትም ጥራት ያለውን እውቀት ነው፡፡ ጥራት ባለው የመማር ማስተማር ስርዓት ያልተራመደ ማህበረሰብ የሚፈለገውን ለውጥ ሊያመጣ አይችልም፡፡
እንደ ሀገር ብዙ ቦታ ላይ ጸንቶ መራመድ አቅቶን የምንፈገመገመው ዘመኑን ባልዋጀ የትምህርት ስርዓታችን ነው፡፡ እንደ ሀገር ጥራት በሌለው የትምህርት ስርዓት ብዙ ዋጋ ከፍለናል፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ አሁንም በዛ አስተሳሰብ ውስጥ መሆናችን ነው፡፡
ጥራት የመልካም ለውጥ መለኪያ ነው፡፡ ጥራት የሚሉት የለውጥ መስፈርት በሌለበት ሁኔታ እንደ ሀገርም ሆነ እንደ ግለሰብ ማደግ የማይታሰብ ነው፡፡ በዚህ እውነታ ላይ ተንጠራርተን የሀገራችንን የትምህርት ስርዓት ብንፈትሽ እልፍ ጉድለቶችን እናገኛለን፡፡ የሀገራችን የትምህርት ስርዓት በአንድ አይነት አረዳድ፣ በአንድ አይነት እሳቤ ከትላንት ወደ ዛሬ የመጣ ወደ ነገም ሊሄድ እየተንደረደረ ያለ ነው፡፡
ሁሉም ነገር ዛሬ ላይ እንዲያበቃ መንግስት እንደመንግስት፣ ኃላፊነት የሚሰማውም የድርሻውን እንዲወጣ ድምጽ የምንሆንበት ወቅት ላይ ነን፡፡ በትምህርት ስርዓታችን ሳንታደስ የሀገራችንን የድህነት ቀንበር ቀና ማድረግ አንችልም፡፡
የድህነት ቀንበራችን እንዲለዝብ ችግር ፈጣሪዎችን ሳይሆን፣ ተምረው ስራ የሚጠብቁን ሳይሆን፣ ተምረው ከሀገር ላይ የሚሰርቁን ሳይሆን፣ ተምረው በእውቀታቸው ሀገር የሚጎዱትን ሳይሆን . . . ለሀገር ችግር መፍትሄ የሚሆኑ፣ የተማሩ ዜጎችን ማፍራት ይጠበቅብናል፡፡
እስከ ዛሬ ያፈራነው የሰው ኃይል በሚፈለገው መልኩ ችግር ፈቺ አልነበረም፡፡ እንዳውም በተቃራኒው ተምረው ሀገር የሚጎዱ በርካታ የቀለም ቀንዶችን ለመታዘብ ችለናል። ይሄን አሀዝ እንደ አጠቃላይ ማየት ብንችል ትላንትም ሆነ ዛሬ ሀገራችን እየተጎዳች ያለችው በአብዛኛው ተማርን በሚሉ ሰዎች እንደሆነ እንደርስበታለን፡፡
ይህን ዘመን ያፈጀ እውነታ የሚሽር የትምህርት ስርዓት ያስፈልገናል፡፡ ተምረን ሀገር እየጎዳን፣ ተምረን ችግር ፈጣሪ እየሆንን የምናሻግራት ኢትዮጵያ የለችም። ትምህርት ትህትና እንደሆነ፣ እውቀት ማለት ያወቁትንና የተረዱትን ወደ ተግባር ቀይሮ ሀገርና ሕዝብን መጥቀም እንደሆነ እስኪገባን ድረስ በተሐድሶ ጎዳና ላይ ሳንዝል መራመድ አለብን፡፡
ይህ ብቻ አይደለም እውቀት ማለት በምክንያትና በሚዛናዊነት ውስጥ መቆም፣ የፍትህና የነጻነት መገኛም እንደሆነ ቢገባን ተነጋግረን ባለመግባባት፣ ተምረን ባለመለወጥ በሀገርና ሕዝብ ላይ እያደረስን ያለነውን ስቃይ መቀነስ እንችል ነበር፡፡ ጥራት በሌለው ትምህርት፣ ጥራት በሌለው እውቀት ዛሬ ላይ መፍትሄ አልባ ችግሮችን አብዝተናል፡፡
ወንዝ በማያሻግር መርህ፣ ሩቅ በማይወስድ ስርዓት ትውልዱን አደጋ ውስጥ ሀገርን ስጋት ውስጥ ከትተናል። ይህ ሁሉ ውጥንቅጡ የወጣ ሀገራዊ ስጋት በትምህርት ስርዓታችን በኩል የተዋወቅነው የጋራ ገመናችን ነው። የጋራ ገመና ደግሞ በጋራ እውቀት፣ በጋራ ትጋት የሚጠራ የአብሮነት መንፈስ ነው፡፡
እንደ ሀገር የትምህርት ስርዓታችን ሁላችንንም ጎድቶናል፡፡ ለይቶ የጎዳው የማህበረሰብ ክፍል የለም፡፡ ለውጥ እየናፈቀን ለውጥ ያጣነው፣ ሰላም እየፈለግን ሰላም የናፈቀን እውቀታችን ከመፍትሄ ይልቅ ችግር ፈጣሪነት ላይ ስለበረታ ነው፡፡ አንድነት አጥተን በመለያየት የቆምነው፣ በብሔርና በጎሳ ተቧድነን ኢትዮጵያዊነትን የሻርነው አንድ የሚያደርግ የወንድማማችነት እውቀት ስላጣን ነው፡፡
እንደ ብሔራዊ አርማ ድህነትና ኋላቀርነት መገለጫችን ሆነው የከረሙት፣ ድህነት ሲታሰብ ምስራቅ አፍሪካ የሚታወሰው ለለውጥ የሚሆን ጥራት ያለው ትምህርትን ተደራሽ ስላላደረግን ነው፡፡ በዚሁ ከቀጠልን ከዛሬ የባሰ ብሔራዊ ስጋትን ነው የምናስተናግደው። ችግሮቻችን ከዛሬ ወደ ነገ እንዳይሄዱ የእድገትና የብልጽግና ቁልፍ የሆነውን የትምህርት ስርዓታችንን መቀየር ዋናው ጉዳይ ይሆናል፡፡
የትምህርት ጽንሰ ሀሳብ ሀገር መስራት፣ ለማህበረሰብ ችግር ፈቺ መሆን ነው፡፡ የእውቀት መነሻ በበጎነትና በቅንነት ሳይማር ያስተማረን ማህበረሰብ ማገልገል ነው፡፡ በኛ በኩል ያለውን እውነታ አንባቢ ሊመልሰው የሚችለው ይመስለኛል፡፡
ኢትዮጵያ በማንና እንዴት ባለው መንገድ ለአደጋ ተጋላጭ እየሆነች እንደሆነ ብንመረምር ስርዓት በሳቱ፣ ግን ደግሞ “አወቅን” በሚሉ ግለሰቦችና ቡድኖች እንደሆነ ሁላችንንም የሚያግባባ እውነታ ነው ብዬ አምናለሁ። አሁን የጀመርነው የእድገትና የለውጥ ትግላችን ፍሬ እንዲያፈራ የትምህርት ስርዓቱ ጠንካራ ሆኖ ስር መስደድ አለበት፡፡
የትምህርት ስርዓታችን ተገቢና አስፈላጊ በሆነ መልኩ ስር ባልሰደደበት ሁኔታ የሚመጣ በረከትና ጸጋ የለም። እንደ ሀገር የተጎሳቆልነው እንክርዳድ ዘርተን ስንዴ በመጠበቃችን ነው፡፡ ትምህርት እውቀት እንዲሆን፣ እውቀት ደግሞ ልማትና ስልጣኔ እንዲያመጣ ነገ ላይ ዋርካ ሆኖ ብዙዎችን የሚያስጠልል የእውቀት ዛፍ መትከል አለብን፡፡
ትላንት ላይ የተተከሉ ዛፎቻችን ያላስጠለሉን ከአረምነት ባለፈ ዋርካ መሆን ስላልቻሉ ነው፡፡ አሁን እንደ ሀገር የሚያስፈልገን የእውቀት ዋርካ፣ የሰላም ጥላ ነው፡፡ በዚህ መሰረት ላይ ቆመን ወደ ነገ ካላሻቀብን ትግላችን ምንም ነው፡፡ በእውቀት የተዘራ፣ በማስተዋል የበቀለ፣ አድጎና ጸድቆ ለብዙዎች ጥላ የሚሆን በዋርካ የተመሰለ ትውልድ ሀገራችን ትሻለች፡፡
ሁላችንንም የሚያግባባ አንድ እውነት ቢኖር ሀገራችን በሁሉም ረገድ የጥራት ችግር ያለባት መሆኑ ነው፡፡ ፖለቲካውን ብንፈትሽ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ጓዳውን ብንበረብር የስጋት ማዕከል ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ እነዚህ ሁሉ እንከኖች ደግሞ የትላንት የትምህርት ስርዓታችንን ታከው ነፍስ የዘሩ ናቸው፡፡
እንደ ሀገር የጠራ ፖለቲካ፣ የጠራ ኢኮኖሚና በምክንያት የሚያምን ማህበራዊ መዋቅር ለማቆም መጀመሪያ መሰረት መጣል ይጠበቅብናል፤ የእውቀት መሰረት፡፡ መሰረታችን እውቀት ካልሆነ ከማሰብ የዘለለ የድርጊት አቅም አናገኝም፡፡
ለማሰብ ለማሰብ እማ እኮ ድሮም የትምህርት ስርዓታችን ጥሩ እንዳልነበር ስናወራ፣ ስንጽፍ፣ ስንመካከር ነበር፡፡ ግን ለትግበራ የሚሆን የድርጊት አቅም አልነበረንም፡፡ አሁንም ከመናገር ወጥተን ወደ ተግባር ካልገባን ሁለንተናዊ ስጋት ከመሆን ባለፈ መጪው ትውልድ እንዲሁ እያነሳ እየጣለው እንዲሄድ መንገድ ነው የምንቀድለት፡፡ ኢትዮጵያን የሚጎዳ፣ ትውልድ የሚያመክን የትኛውም ስርዓት እዚህ ጋ መቆም አለበት፡፡ በእኛው መቅረት አለበት።
ሁላችንም ዝም ባልንበት ሰሞን፣ ሰምተን እንዳልሰማን፣ አይተን እንዳላየን በሆንበት ማግስት የትምህርት ሚኒስቴር ቀዳዳ ቀዶልናል፡፡ በዛ ቀዳዳ በማጮለቅ የትምህርት ስርዓታችንን ማደስ ግዴታችን ይሆናል፡፡ ከትምህርት ሚኒስቴር የሰማናቸው ሰሞነኛ መግለጫዎች በመማር ማስተማሩ ላይ ምን ያክል የጥራት አደጋ እንደተጋረጠበት የሚጠቁም ናቸው፡፡
እኚህ የጥራት ግድፈቶች ትውልዱን ተምሮ እንዳልተማረ፣ ሰልጥኖ እንዳልሰለጠነ፣ አውቆ እንዳላወቀ በማድረግ በሀገር ላይ የራሳቸውን መጥፎ አሻራ አሳርፈዋል፡፡ በጥናት ከተረጋገጡት የትምህርት ሚኒስቴር መግለጫዎች በመነሳት “መጪውን ጊዜ እንዴት ባለው ሁናቴ ብንቃኝው ለሀገራችን ስኬታማ ይሆናል?” ብለን መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡
የተደቀኑብን ፖለቲካዊም ሆኑ ኢኮኖሚያዊ፣ ብሎም ማህበራዊ ተግዳሮቶች የትምህርት ስርዓቱ ሲስተካከል አብረው የሚስተካከሉ ናቸው፡፡ በሰላሙ፣ በልማቱ፣ በእርስ በርስ መስተጋብሩ የሚስተዋሉት ክፍተቶች ከትምህርት ጥራት መጓደል የመጡ እንደሆኑ መገመት አይከብድም፡፡
የትምህርትን አላማ በሚመለከት ማርቲን ሉተር ኪንግ “የእውነተኛ ትምህርት አላማ እውቀትና ስብዕና የተጣመሩበት ነው” የሚል አባባል አለው። ከዚህ ግለሰባዊ ምልከታ ብንነሳ እንኳን በሀገራችን አሁናዊ የመማር ማስተማር ስርዓት ላይ ብዙ ሀሳቦችን ማንሳት እንችላለን፡፡
እውቀት መልካም ስብዕና ነው፡፡ ተምረን እና አውቀን የመልካም ስብዕና ባለቤቶች ካልሆንን፣ ወይ እኛ አሊያም ደግሞ ትምህርቱ ችግር አለበት ማለት ነው። የምንማረው የራሳችንን ባዶነት ሞልተን ወደ ሌሎች እንድንመለከት ነው፡፡ የምንማረው የሀገራችንን የልማት፣ የእድገት፣ የዲሞክራሲ፣ የሰላም፣ የአስተዳደር እንዲሁም ሌሎች ጥያቄዎችን ለመመለስ ነው፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ የእውቁን ሳይንቲስት የአልበርት አንስታይንን ድንቅ አባባል ጠቅሼ ማለፍ ግድ ይለኛል። ሳይንቲስቱ የትምህርትን አላማ ሲገልጽ “ትምህርት እውነትን መማር ብቻ አይደለም፤ አእምሮን እንዲያስብ ማሰልጠን እንጂ” ነበር ያለው፡፡
በትምህርት ቤት ውሏችን ተምረን የመልካም ባህሪ ባለቤቶች ካልሆንን፣ በእውቀታችን መፍትሄ ተኮር እሳቤን ካልተለማመድን ጊዜአችንን እንዳባከንነው ነው የሚቆጠረው፡፡ ወይም ሳይንቲስቱ እንዳለው እውነትን ከማወቅ ባለፈ አእምሮ እንዲያስብ እድል አልሰጠነውም ማለት ነው፡፡
አእምሮ እንዲያስብ እድል ካላገኘ የምንማረው ትምህርት ለውጥ አላመጣልንም ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ ትውልድ ቀረጻ እየተኬደበት ያለው የመማር ማስተማር የትግበራ አቅጣጫ አመርቂ እንዳይደለ መረዳት ይቻላል፡፡ የእውቀት የመጀመሪያው ጫፍ አእምሮን በበጎ መግራት ነው፡፡
በበጎ ያልተገራ አእምሮ እዛም እዚህም እንደምናያቸው ተምረው ሀገር እንደሚያስጨንቁ ባንዳዎች እና እራስ ወዳዶች ለመሆን የተዘጋጀ ነው፡፡ ሀገራችን በሰለጠነ ትውልድ፣ በበቃ ባለሙያ ለመቀየር የአቅጣጫ ለውጥ ያስፈልጋታል፡፡ የእስካሁኑ አቅጣጫችን የምንፈልገውን ለውጥ ካላመጣልን ትንሽ ዞር ብሎ በሌላ አቅጣጫ ማየት፣ ወደ ሌላ መማተር ያዋጣናል፡፡
ጥራት ባለው ትምህርት ጥራት ያላት ሀገራችንን እስካልፈጠርን ድረስ ከእህህ አንድንም፡፡ ትልቁ ተስፋችን ያለው በጠራና በተገራ ስርዓትና መርህ፣ አቅጣጫና ትግበራ ላይ የተመሰረተ የትምህርት ፖሊሲ ሲኖረን ነው። ከሰማነውና ካየነው ተምረን መጪውን ጊዜ የተሻለ ለማድረግ በተሻለ ሀሳብ ጥራት ተኮር የእውቀት ንቅናቄ ግድ ይለናል፡፡
በሀገር ግንባታ ላይ ቀዳሚው ነገር የትምህርት ጥራት ነው፡፡ ከችግሮቻችን ወጥተን በታደሰ ማንነት ለመቆም በትምህርት ስርዓታችን ላይ ተጨባጭ የአቅጣጫ ለውጥ ማድረግ ፤ ከዚህ የሚመነጭ ትውልዱ ተምሮ ችግር ፈቺ እንዲሆን የሚያበቃና የሚያነቃ የንቅናቄ መርህ እውን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ግንቦት 25/2015