የሰው ልጆች የአኗኗር ዘይቤ ከዘመኑ ጋር እየተለዋወጠ አሁን ያለንበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ አሁን ያለንበት ዘመነ ቴክኖሎጂ ደግሞ ከዓለም ጫፍ እስከ ጫፍ ያለው የሰው ልጆች የአኗኗር ዘይቤ በፍጥነት እየተቀያየረ መምጣቱን የሚያሳይ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በምክንያትነት የሚነሳው የሰው ልጆች ፍላጎት እያደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ የቴክኖሎጂ ማደግና መራቀቅ አብሮ ይነሳል፡፡ ቴክኖሎጂ በዓለም ላይ ያሉ በሰዎችን በበይነመረብ (በኢንተርኔት) አማካኝነት በማስተሳሰር የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸውን መረጃ ሳይቀር እንዲለዋወጡና ግንኙነታቸው እንዲጠናከር እያደረገ እንደሚገኝ መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡
ቴክኖሎጂ የሰው ልጆች የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር የዕለት ተዕለት ሕይወትን ቀላልና ምቹ የሚያደርጉ ጊዜን፣ ጉልበትንና ወጪን የሚቆጠቡ አሠራሮች በመዘርጋት የተሻለ የአኗኗር ዘይቤ እንዲኖር እያደረገ ይገኛል። ለዚህም ነው እያንዳንዱ የዓለምን እንቅስቃሴ እየተቆጣጠረ ካለው ከኢንተርኔት ግንኙነት ውጭ መሆኑ የማይታሰብ ፤ ከዓለም በስተጀርባ እንደመቅረት የሚቆጠረው፡፡
በዚህ ዘመነ ቴክኖሎጂ የሰው ልጆች ተግባቦት፣ ግብይትና የሥራ እንቅስቃሴ እንዲሁም የዕለተ ተዕለት እንቅስቃሴ ቴክኖሎጂን መሠረት በማድረግ የሚከወን ከመሆኑ ባሻገር ከዚህ ውጭ መሆን ለዓለም አቀፍ ጉዳዮች ባይተዋር እንደመሆን ያስቆጥራል፡፡ የዓለም ሀገራት በተለይ በለጸጉ የሚባሉት የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴያቸውን ወደ ዲጅታል ቴክኖሎጂ ያሸጋገሩ ሀገራት የዜጎቻቸውን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ በሙሉ ያለ ኢንተርኔት የማይታሰብ ደረጃ ላይ አድርሰውታል፡፡
ዲጅታል ቴክኖሎጂ መተግበር በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ በኢኮኖሚ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ሀገራት ኢኮኖሚያዊ አቅማቸው እንዲጎለብት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው መረጃ ያመለክታሉ፡፡ ታዳጊ ሀገራት ደግሞ በቴክኖሎጂ ላቀ ያለ ደረጃ ላይ የደረሱ የዓለም ሀገራት ዱካ በመከተል ራሳቸውን ለማብቃትና ተወዳዳሪ ለመሆን ፍጥነታቸውን በመጨመር ጉዞአቸውን በማፍጠን እሽቅድምድሙ ላይ ባይደርሱም የየራሳቸውን አቅም ባገናዘበ መልኩ ዓለምን ለመቀላቀል የሚያስችላቸው ሂደት አሃዱ ብለው ጀምረዋል፡፡
ይህም ሆኖ ግን በዚህ ዘመን ለሰው ልጆች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ በእጅጉ አስፈላጊ የሆነው በይነመረብ (ኢንተርኔት) በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚፈለገው መጠን ተደራሽ እንዳልሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ። በአዲስ አበባ በተካሄደው 17ኛው ዓለም አቀፍ የበይነ መረብ ጉባኤ ላይ እንደተጠቆመው፤ በዓለም 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን፤ በአፍሪካ ደግሞ 871 ሚሊዮን ሕዝብ ከኢንተርኔት ግንኙነት ውጭ በመሆኑ የዓለማችን ግማሽ ያህሉን ሕዝብ ያካትታል ማለት ነው።
በኢትዮጵያም የበይነ መረብ ተደራሽነት ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻሎችን እያሳየ መሆኑን ነው በዚሁ ጉባኤ ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ያስታወቁት። በኢትዮጵያ ያለው የበይነ መረብ ተጠቃሚዎች ቁጥር ከአምስት ዓመት በፊት ከነበረበት 19 ሚሊዮን በአሁኑ ወቅት ከ30 ሚሊዮን በላይ መድረሱንም መናገራቸው የሚታወስ ነው።
ኢትዮጵያም የዲጅታል ጉዞ እውን ለማድረግ ትልቅ አቅም እንዲፈጥርና የዲጅታሉን ዓለም ለመቀላቀል የምታደርገውን ጥረት አጠናክራ ቀጥላለች፡፡ በዚህም የዲጅታል ኢኮኖሚን ለመገንባት የምታደርገው ጥረት የተሳካ ለማድረግ የሚያስችላትን ዲጅታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ በ2025 ቀርጻ እና አፅድቃ ወደ ሥራ ገብታለች። ዲጂታል ኢትዮጵያ የዲጂታል እድሎችን በመጠቀም ፈጠራ የታከለበትና በእውቀት ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያስችል ነው፡፡
ኢትዮጵያ እየተገበረች ያለችውን ዲጅታላይዜሽን ለማስፋፋት ተቋማት ከማዘመን ጀምሮ አሠራሮችን ወደ ዲጅታል እንዲቀየሩ በማድረግ፣ ግብይቶቻችንም በዲጅታል ዘዴ እንዲፈጸም እስከ ማድረግ የደረሰ ጉዞ ላይም ናት፡፡ ይህም በቅርቡ በተለያዩ ደረጃዎች ተፈጻሚ እየሆነም ይታያል።
ለዚህም ከግንቦት ወር ጀምሮ በመላው ሀገሪቱ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ የተደረገውን ኤሌክትሮኒክስ የክፍያ ሥርዓት እየተፈጸመ ያለው የነዳጅ ግብይት መመልከት ይቻላል፡፡ ኢትዮጵያ ነዳጅ ወደ ሀገር ለማስገባት የምታወጣው ከፍተኛ ውጪን ስንመለከት አምና ከኤክስፖርት ካገኘችው 4 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር 4 ቢሊዮን ዶላር ያህሉን ለዚሁ ግብይት መዋሉን የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን መረጃ ያመላክታል፡፡ ይህ በከፍተኛ ወጪ የምታስገባው ነዳጅ ደግሞ ለተፈለገው አገልግሎት ሳይውል በሕገወጥ መንገድ ከሀገር ውጪ እንዲወጣ ይደረጋል፡፡ ነዳጅ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ለማድረግ አሁን ላይ የተዘረጋው ዲጅታል የክፍያ ሥርዓት ግን ሕገ ወጥነትን ሙሉ በሙሉ ባያስቀረውም ሕገወጥ አሠራሮች መስመር በማስያዝ ችግሮቹን ሊቀንስ የሚችል እንደሆነ ታምኖበታል፡፡
ልክ እንደነዳጅ ሁሉ ሌሎች ዘርፎች ላይ በዲጅታል ቴክኖሎጂ የታገዝ አሠራርን ተግባራዊ ማድረግ ለሕገወጥና ብልሹ አሠራር ክፍት የሆኑ መንገዶችን በመዝጋት ሕገወጥነት ማጥፋት እንኳን ባይቻልም መቀነስ የሚያስችል ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሚሆነው ዲጅታል ኢትዮጵያ ለመገንባት የሚደረገው ሂደት በማገዝ ኢትዮጵያ የጀመረችን የዲጅታል መንገድ እውን ለማድረግ የምታደርገው ጥረት አጠናክሮ ማስቀጠል ሲቻል ነው፡፡
ለተግባራዊነቱም በእውቀት የዳበረና በመረጃ የበለጸገ ማህበረሰብን መፍጠር የሚጠይቅ ሲሆን አሠራሮቹን ተቀብለው ተግባር ላይ ሊያወሉ የሚችሉ በመረጃ የበለጸገና በእውቀት የታገዙ የማህበረሰብ ክፍሎችን መፍጠር አዳዲስ አሠራሮችና ዘዴዎችን (ሲስተሞች) ሲዘረጉ በፍጥነት ተቀብሎ ተግባራዊ ለማድረግ አያስቸግርም፡፡
ከነበረው አሠራር ወጣያለ አዳዲስ አሠራሮች ተግባራዊ ሲደረጉ ህብረተሰቡ ቴክኖሎጂዎች በደንብ አውቋቸው እንዲጠቀምባቸውና እንዲገለገልባቸው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ አሁን ላይ እንዲተገበሩ የሚፈልጉት አሠራሮች ሆኑ ሲስተሞች የህብረተሰቡን ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪ እንዲሁም እንግልት የሚያስቀሩ ቢሆኑም ግንዛቤን በማስፋት ህብረተሰቡ መጀመሪያ በቴክኖሎጂ ላይ እምነት እንዲያሳድር ማድረግ ይጠይቃል፡፡ ቴክኖሎጂ ከሚሰጠው ጠቀሜታ ባሻገር ህብረተሰቡ በራሱ ተጠቅሞበት እንዲለማመደውና ለውጡን እንዲያውቅ መሰራት አለበት፡፡
አሁን እየታየ ባለው ሁኔታ አዳዲስ አሠራሮች ተግባራዊ ሲደረጉ ህብረተሰቡ በፍጥነት ወደ ተግባር ለመግባትና ለመለማመድ ሲከብደው ይታያል። በተለመደው አሠራር እንዲሄድ የመፈለግ ሁኔታ ይስተዋላል፡፡ ይህንን አመለካካት ለመቀየር እና ችግሩን ለመቅረፍ የግንዛቤ ማስጨበጫዎችን እስከታችኛው የህብረተሰብ ክፍል ድረስ መስራት ደግሞ እጅግ አስፈላጊ የሚሆነው ለዚህ ነው፡፡
በከተሞች አካባቢ የሚኖረው የህብረተሰብ ክፍል ከአኗኗር ዘይቤ አንጻር አዳዲስ አሠራሮችን በፍጥነት የመቀበልና በግንዛቤ ረገድም የተሻለ ሆኖ ቢገኝም በተቀረው የአገሪቱ አካባቢ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎች ተመሳሳይ አረዳድ ይኖራቸው ዘንድ ብዙ ሥራዎች መስራት አለባቸው፡፡
ስለሆነም ዲጅታል ኢትዮጵያ እውን ማድረግ ለመንግሥት ብቻ የሚተው ሳይሆን እያንዳንዱ ሰው ለለውጥ እራሱን ዝግጁ በማድረግ ከአዳዲስ አሠራርና ቴክኖሎጂዎች ጋር በመላመድ ብሎም ዓለም ወደ ተራቀቀ ቴክኖሎጂ እየተሸጋገረ መሆኑን በመገንዘብ ሀገራችን የምታደርገው ሩጫ እንዲፋጠን ሁላችንንም የራሳችንን ኃላፊነት መወጣት አለብን ባይ ነኝ፡፡ ቸር እንሰንብት፡፡
ትንሳኤ አበራ
አዲስ ዘመን ግንቦት 25/2015