መነሻ ሃሳብ፤
ይህ ጸሐፊ በተለየ ሁኔታ የንባብ ቅድሚያ የሚሰጠው ለግለሶቦች ግለ ታሪክና የሀገርን ታሪክ ለተሸከሙ መጻሕፍት ነው። “የታላላቅ አርዓያ ሰብ ግለሰቦች የሕይወት ውጣ ውረድ የተሰነደባቸው መጻሕፍት ተዝቆ በማያልቅ የማዕድን ሀብት ክምችት ይመሰላሉ” የሚለውን የጠቢባን ምክር ጸሐፊው በሚገባ ያምንበታል።
በየመደርደሪያችን ላይ የተሰደሩት መጻሕፍት እውቀትን፣ ጥበብን፣ በጎነትን፣ የክፋትን አጸያፊነት፣ የመንፈሳዊ ሕይወትን ትሩፋቶች፣ የልቦለድና የግጥሞች “ማርና ወተት” የሚፈልቅባቸው በረከቶች ናቸው። በመጻሕፍት ሕይወታችን ይታነጻል። ተስፋችን ይለመልማል። መንፈሳችን ይነቃቃል። አብሮነታችን ይጠናከራል። ታሪኮቻችን ይተረካሉ። ባሕሎቻችን፣ ቋንቋዎቻችንና ወጎቻችን ይደምቃሉ። ስለዚህም “ከንባብ ትሩፋት አንጉደል” የጸሐፊው ትሑት ምክር ነው።
ሰሞኑን ለስንተኛ ጊዜ እንደሆነ እርግጠኛ ባልሆንም በ2003 ዓ.ም ታትሞ ለንባብ የበቃውን የፊታውራሪ አመዴ ለማን “የሕይወት ታሪኬን” መጽሐፍ እንዳነብ ስሜቴ ጠንከር ያለ ግፊት አደረገብኝ። መጽሐፉ ኅዳር 16 ቀን 2004 ዓ.ም በግዮን ሆቴል በተመረቀበት ዕለት ታዳሚ ሆኜ በመገኘቴ ብቻ ሳይሆን በዚያው ዕለት መጽሐፉን አንብቤ ማጠናቀቄን የግሌ ዜና መዋዕል መመዝገቢያ ማስታወሻዬ አረጋግጦልኛል።
ለተደጋጋሚ ጊዜያትም የመጽሐፉን አንዳንድ የተመረጡ ክፍሎች “በውርድ ንባብ” መዝለቄንና መከለሴን በተለያዩ ቀለማት ያሰመርኩባቸው ገጾች መስክረውልኛል። የዚህ ዓምድ ተከታታይ ቤተሰቦች መጽሐፉን ፈልገው ቢያነቡ በእጅጉ ይጠቀማሉ።
አመዴ ምን አሉ?
ባለታሪኩ ክቡር ፊታውራሪ አመዴ ለማ የሕይወትን ውጣ ውረድ ተቋቁመው በንግዱ ዘርፍ ተሳክቶላቸው አንቱ ለመባል የበቁ፣ የንግድ ሥራ ማኅበርና ምክር ቤት በማቋቋም የተመሰገኑ፣ የሕዝብ እንደራሴ (ከ1950 ዓ.ም ጀምሮ)፣ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል፣ የአክሱም ሐውልት አስመላሽ ብሔራዊ ኮሚቴ አባል፣ የውሃ ዋና ፌዴሬሽን መሥራችና ሊቀመንበር፣ ሀገራቸውንና የወከላቸውን ተቋምና ሕዝብ በታማኝነትና በውጤት ያገለገሉ፣ እስከ መጨረሻው ህልፈት ሕይወታቸው ድረስም የሀገር ሽማግሌ በመሆን “ክብርን ተጎናጽፈውና ሕዝባቸውንና ሀገራቸውን አክብረው የኖሩ” የተግባር ምሳሌና አንደበተ ርትዑ አባት ነበሩ።
ይህን ጽሐፍ ለመጻፍ ምክንያት የሆነኝንና ለርዕስነት የተዋስኩትን አባባል በተመለከተ በግለ ታሪካቸው ገጽ 204 የተመዘገበውን ድንቅ ትዝታ እንደሚከተለው እጠቅሳለሁ። “ይህቺ የምንኖርባት መሬት ለመላው የሰው ልጆች የምትበቃ መሆኑን ጦርነት የሚጭሩ አምባገነኖች ሊረዱትና ሊገነዘቡ ይገባል።
የመንግሥታት መሪዎች በሞቀ ቤተ መንግሥታቸው ውስጥ እየተንደላቀቁ ደሃውን ወታደርና ምንም የማያውቀውን ንፁሕ ዜጋ እንደ ማገዶ እንጨት በጦርነት እሳት ውስጥ እየማገዱ ለጥፋትና ለውድመት ምክንያት ከሚሆኑ የጠብን መንገድ አስወግደው የሰላምና የእርቅን መንገድ ቢከተሉ ሀገሮቻቸው ምን ያህል በልማት በበለጸጉ ነበር” ብለው ከተንደረደሩ በኋላ የሚከተለውን ሀገራዊ ታሪክ እንዲህ በማለት ለማሳያነት ያስታውሳሉ።
“ንጉሥ ሚካኤል የወሎ ንጉሥ በነበሩበት ዘመን አንድ ጥጋበኛ ሽፍታ ከእኔ በላይ ማን በማለት በንጉሡ ሥልጣን ላይ አቅራራና ሸፈተባቸው። በዚህ ጊዜ ንጉሡ መኳንንቶቻቸውን ሰበሰቡና ምን ትመክሩኛላችሁ? በማለት ጠየቋቸው። ሁሉም በየተራ እየተነሱ ሽፍታው ተይዞ ይገረፍ፣ ይሰቀል፣ እንደዚህና እንደዚያ ይፈጸምበት እያሉ የበኩላቸውን ጭካኔ የተሞላበት ፍርድ ሰጡ። በዚህን ጊዜ ንጉሡ የሁሉንም አስተያየት አዳመጡና በቁጣ እንዲህ መለሱላቸው።”
“አዬ! አሁን ይሄ ከእናንተ የሚጠበቅ ምክር ነው? ሌላው ቀርቶ አሁን ይሄ ሽፍታ ጨለማ ለብሶ አዳራሼን ቢያቃጥለው የንጉሥ ሚካኤል አዳራሽ የተቃጠለ ዕለት ነው የተወለድኩት እያለ ሕዝብ የዕድሜ መቁጠሪያ እንዲያደርገኝ ነው? ይልቅስ ሽፍታውን አምጡትና አስታርቁኝ። አሉና ከዚያ ሽፍታ ጋር እርቀ ሰላም አወረዱ ይባላል። ይህ ታላቅ ታጋሽነትንና ብልህነትን ያመለክታል።”
ጥበብ የተሞላበት ታጋሽነት ምን ያህል ከስሜታዊነት እንደሚታደግ አንባቢው ከዚህ ታሪክ ብዙ ሊማር ይችላል። የአብዛኞቹ የሀገራችን ዜጎች የትውልድ ዘመን ከነገሮች ግጥምጥሞሽና ከሁኔታዎች ክስተት፣ ከታሪካዊ ኩነቶችና አጋጣሚዎች ጋር እንደሚያያዝ ይታወቃል።
ለአብነት የምንጠቅሰው በዚሁ መጽሐፍ ውስጥ የተጠቀሰውን አንድ ታሪካዊ ክስተት ነው። በአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት የኢጣሊያ መንግሥት ለሀገራችን የሰጠውን የሁለት ሚሊዮን ሊሬ ብድር አስታኮ ሉዓላዊነታችንን ለመዳፈር ማድባቱን ንጉሡ ይደርሱበታል። በመሆኑም ምኒልክ ተንኮሉን ቀደም ብለው ስለተረዱ ገንዘቡን ቶሎ ከፍሎ ለመገላገል አንዱ ውሳኔ ላይ ይደርሳሉ። በውሳኔው መሠረትም እያንዳንዱ ሰው ባለው የቀንድና የጋማ ከብት ብዛት ለጭራ (በአንድ የቤት እንስሳ ቁጥር ማለት ነው) ገንዘብ እንዲያዋጣ ተደርጎ ብድሩ ይመለሳል።
ያ የጭራ ብር እንዲያዋጣ የተደረገበት ዘመን የጊዜ መቁጠሪያ ሆኖ “በጭራ ብር ጊዜ ተወለድኩ። የጭራ ብር ጊዜ የአምስት አመት ልጅ ነበርኩ” እየተባለ ይነገር ነበር። የወሎ ንጉሥ ሚካኤል “ከደመኛቸው ሽፍታ ጋር አስታርቁኝ” በማለት ሹመኞቻቸውን የተማጸኑት ይህንን መሰል ታሪክ ከዜጎች ዕድሜ ጋር እየተጎዳኘ ስማቸው ከትውልድ ትውልድ እንዳይተላለፍ በመስጋት ነበር። “የማንነትን የክብር ዋጋ ላለማቅለል” መሆኑን ልብ ይሏል።
የቅርብ ዘመናት መሰል ታሪኮች፤
ከሠላሳ እስከ ስልሳ የዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ዜጎች የልደታቸውን ጊዜ በተመለከተ ከላይ የተጠቀሰውን መሰል ታሪክ ከወላጆቻቸው ይሰሙ እንደነበር ይህ ጸሐፊ ከወዳጆቹ አንደበት ደጋግሞ አድምጧል። “እናቴ እንደነገረችኝ በታኅሳስ ግርግር ጊዜ ሁለት ዓመቴ ነበር። የተወለድኩት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከሥልጣን ሊወገዱ ሁለት ሳምንት ሲቀራቸው ነው።
መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ሀገር ጥለው ሲሰደዱ እናቴ ታናሽ እህቴን አርግዛ አምስት ወር አልፏት ነበር። ወያኔ አዲስ አበባን በተቆጣጠረበትና የሸጎሌ የጦር መሣሪያ ዴፖ የፈነዳ እለት የመጀመሪያ ልጃችንን ልትወልድ ባለቤቴ ጳውሎስ ሆስፒታል ገብታ ነበር ወዘተ.” የሚሉ የዕድሜ ቀመር ትዝታዎችን ለዚህ ጸሐፊ ያጋሩት የቅርብ ወዳጆቹ ነበሩ።
በመሠረቱ ታሪካዊ ሁኔታዎችን መነሻ በማድረግም ሆነ የተለየ አጋጣሚን በማስታወስ ወላጆችም ሆኑ ልጆች “የተወለድኩት እንዲህ ዓይነት ክስተት በሀገር ውስጥ በተመፈጸመበት ወቅት ነው” ማለት መብታቸው ስለሆነ “ትክክል ወይንም ስህተት” ነው በመባባል መሟገት አይቻል ይሆናል። ይህንን በማድረጋቸውም እንደ ችግር ተቆጥሮ ለፍርድ ይቅረቡ ማለት እንዳይደለ ግልጽ ሊሆን ይገባል።
“እናስ ምን ይሁን? ማንም ሰው ከፈለገው ሁኔታ ጋር አዛምዶ የልጁን እድሜ ቢያስታውስ ስህተቱም ሆነ ክፋቱ ምኑ ላይ ነው?” በማለት አንባቢው ተገርሞም ይሁን ግራ ተጋብቶ ቢጠይቅ አግባብ ብቻም ሳይሆን መብቱም ጭምር ነው። ችግር የሚሆነው ራስ ሚካኤል አሉ እንደተባለው በአሉታዊ ይዘታቸው የሚጠቀሱ ታሪካዊም ሆኑ አጋጣሚያዊ ችግሮች ሲታወሱ አብረው የሚጎተቱ ብዙ ቅርንጫፎች መኖራቸውን አለማሰቡ ላይ ነው።
በሀገርና በሕዝብ ላይ የሚደርሱ ችግሮችን በሰላም ንግግርና ምክክር መፍታት እየተቻለና “አንተም ተው አንቺም ተይ” ሊባሉ የሚችሉ ፈተናዎችን ተግባብቶ ማብረድ እየተቻለ “በይዋጣልን ጀብድ ወይንም ልኩን አሳየዋለሁ በሚል እብሪት” ሀገር መከራ ላይ ወድቃ ያልተጠበቀ ውጤት ይፈጠርና “የልደት ጊዜ ማስታወሻ” እየተደረገ ለትውልድ መተላለፍ ሲጀምር ያን ጊዜ “ሙት ወቃሽነት” የሀገር ዋና ታሪክ ሆኖ ሥርዓቶችና የሥርዓቱ ዘዋሪዎች ቢያልፉም እንኳን “አጽማቸው ግን አርፎ ላይተኛ” ይችል ይሆናል።
ሃሳቡን ግልጽ እንዲያደርጉልን ከላይ የጠቀስ ናቸውን የቅርብ ዘመን ታሪኮች እንደገና ተመልሰን እንፈትሻቸው። ከግለሰቦች ዕድሜ ጋር የ1953ቱ “የታኅሳስ ግርግር” ሲታወስ አብሮ ሥርዓተ መንግሥቱም መታወሱ አይቀርም። ለምሳሌ፡- “የተወለድኩበት ዘመን የምትለው/ይው የታኅሳስ ግርግር ምን ክስተት የተፈጸመበት ነበር?” ብሎ ማብራሪያ ለሚጠይቅ አድማጭ፤ ዕድሜውን ከግርግሩ ክስተት ጋር አቆራኝቶ የተናገረው ግለሰብ መፈንቅለ መንግሥት የተፈጸመባቸውን ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን እና አማጽያኑን ጄኔራል መንግሥቱንና ወንድማቸውን ግርማሜ ንዋይን ማስታወስ የግድ ይሆናል። አንድም በጭካኔያቸው፣ አለያም በጀብደኝነታቸው።
ስለዚህም “መንግሥቱና ገርማሜ በጭካኔና በጅምላ የረሸኗቸው የንጉሡ ጎምቱ ሹማምንት ግፍ ለኋለኛው የዘመነ ደርግ መንግሥት የቀይና የነጭ ሽብሮች ፍጅት በር ከፋች ሆኖ አገልግሏል” ተብሎ መጠቀሱ ስለማይቀር የመፈንቅለ መንግሥቱ ጠንሳሽና ፈጻሚዎች ስም የሚታወሰው በበጎ ተግባር ሳይሆን
በእርግማን ታጅቦ ሊሆን ይችላል። ንጉሡ በአመጸኞቹ ላይ የፈጸሙት የስቅላት ቅጣትና ሌሎች የበቀል እርምጃዎችም ቢሆኑ በምንም መመዘኛ በመልካም ምሳሌነት ተጠቅሰው የሚሞካሹ ላይሆኑ ይችላሉ።
ስለዚህም ነው ታሪካቸው የሚታወሰው ግለሰቦችና መሪዎች እንኳን የአስተዳደራቸው ትሩፋት ሊወደስ ቀርቶ “አጽማቸውም ቢሆን በሰላም ማረፍ አይችልም” ለማለት ድፍረት ያገኘነው። “ምን ነበረበት ያ ደም አፋሳሽ ድርጊት ባይፈጸም ኖሮ? ይሁን እንኳን ቢባል ችግሩ ራሱ በመለስተኛ እርምት ቢታለፍ ኖሮ ሀገሪቱ በደም አበላ ባልተጠመቀች ነበር።” እየተባለም በቁጭት መንዘርዘር ባልተቻለ ነበር። የወያኔንም ሆነ ሌሎች ከልደት ዘመን ጋር የሚታወሱ መዘከሪያዎችን በዚሁ አግባብ በመፈተሽ ከንጉሥ ሚካኤል አባባል ጋር እያዛመዱ መመልከት ይቻላል።
ነጋችን «የሕዝብ ዕድሜ መቁጠሪያ» እንዳይሆን እንጠንቀቅ፤
ዛሬ በሀገር ደረጃ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የሚፈጸሙ ክስተቶች በነገው ትውልድ ታሪክ ሆነው መጠቀሳቸው አይቀርም። ምናልባትም ልክ እኛ የተወለድንበትን ዘመን ስንናገር እንደምንጠቅሰው ሁሉ ነጋችንን የሚረከቡ ልጆቻችንም ከዛሬ አርባና ሃምሳ ዓመታት በኋላ የትውልድ ዘመናቸውን ሲጠየቁ “የተወለድኩት በወያኔና በመንግሥት መካከል ውጊያ በተደረገበት ዓመት ነበር። የተወለድኩትም በጦርነቱ ምክንያት ከአካባቢያችን ተፈናቅለን ወላጆቼ መጠለያ ውስጥ በነበሩበት ወቅት ነው።” ብሎ ቢነገር ምን ይጠቅማል።
በዚያ ወቅት የሚያስተዳድረው ማን ነበር? ለምንስ ወደ ጦርነት መግባት አስፈለገ? በሰላም ተወያይቶ ችግሮችን መፍታት አይቻልም ነበርን? ከጦርነቱስ ወላጆቻችሁ ምን ትርፍ አገኙ? ወዘተ.” እየተባበሉ ልጆቻችን እርስ በራስ ቢጠያየቁ ወይንም ባእዳን ሲጠይቋቸው ይህንን መራራ ወቅት እያስታወሱ ቢኮንኑ ሟቹ አጽማችን በፍጹም እርፎ ሊተኛ አይችልም። “ስም ከመቃብር ማዶ ይሻገራል” የሚባለውም ስለዚሁ ነው።
እናስ ስለምን ዘመናችን በክፉ ድርጊቶቻችን የሕዝብና የልጆቻችን የዕድሜ ማስታወሻ እንዲሆን እንፈቅዳለን? አስተዋዩ ንጉሥ ሚካኤል የጠየቁትን ጥያቄ በእኛ ዐውድ ቃኝተን ወደ ቀልባችን ተመልሰን ወቅትና ጊዜያችንን መፈተሹ አግባብ እንደሆነ ይሰማናል። “አንዳንዴ ‹እኩይ› የሚል ቅጽል ስም ከምንሰጣቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ጋር በሆደ ሰፊነት በመነጋገር ለሀገርና ለሕዝብ በሚበጅ የጋራ ስምምነት ችግሮች ተፈትተው ወደ ሰላም መመለስ ሲቻል፤ የሚያደርሱት የጥፋት ድርጊት እንደ በጎ ታሪክ እየተቆጠረ ስለምን “የተወለድነው ይህንንና ያንን የመሰለ ክፉ ድርጊት በተፈጸመበት ዓመትና ወር ነው” እየተባለ የሕዝብ ዕድሜ መቁጠሪያ እንዲሆን እንፈቅዳለን? አምጡና አስታርቁን” በማለትም እርቀ ሰላም እንዳይወርድ በር እየዘጋን ስለምን ወኔ ይከዳናል? “ታጋሽነት ብልህነት ነው።” አሉ ንጉሥ ሚካኤል።
እነሆ በፊታውራሪ አመዴ ለማ ግለ ታሪክ ውስጥ የተካተተው የንጉሥ ሚካኤል አስደናቂ ምስክርነት እስካሁን ለተነጋገርንበት ሃሳብ መልካም መነሻ ሆኖን ቆዝመንበታል። እናስ ምን እርምጃ እንውሰድ? “ከታሪክ መሰዊያ ላይ አመዱን ሳይሆን ፍሙን እንጫር” የማሳረጊያ መልእክታችን ነው። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 19/2015