ጊዜው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር 1952 ነው። በዚህ ዘመን ከቅኝ ግዛት ያልተላቀቁ የአፍሪካ አገራት በርካቶች ነበሩ። በወቅቱ ነፃነታቸውን ካገኙት መካከል ደግሞ ስምንት አገራት ብቻ በጣት ይቆጠራሉ። እነሱም ከነፃነታቸው ማግስት በወጉ ባልደረቀው የገዢዎቻቸው አሻራ በተጽዕኖ ቆይተዋል።
እነዚህ አገራት የራሳቸውን ነፃነት ካገኙ ወዲህ በይሁንታ አልተቀመጡም። የመጀመሪያ ጉባኤቸውን በጋና አክራ አካሂደው በጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ መክረዋል። ከአገራቱ መካከል ኢትዮጵያ ይሏት አገር ደግሞ ከሁሉም ትለያለች። ይህች አገር የቅኝ ግዛት ታሪክ የላትም። ሊደፍሯት የመጡ ወራሪዎችን አንበርክካ የድል ቀናቶቿን በኩራት ታከብራለች።
በወቅቱ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የተወከለችው ኢትዮጵያ ስላደረገችው ታላቅ አስተዋጽኦ ክብርና እውቅና ተችሯታል። የጉባኤው ዋና ዓላማ የሌሎች አፍሪካ አገራትን ነፃነት ዕውን ማድረግ ላይ ያተኮረ ነበር። ለዚህ አብይ ጉዳይም ኢትዮጵያ ታላቅ ኃላፊነት ተጥሎባታል።
ከመጀመሪያው የአክራ ጉባኤ በኋላ የፓን አፍሪካኒዝም ዓላማዎችን ዳር ማድረስ ግብ ያደረጉ በርካታ ተግባራት ተካሂደዋል። ለዚህ ታላቅ እንቅስቃሴ የመሪነት ድርሻ የተሰጣት አገራችን በ1960 ሁለተኛውን ጉባኤ በአዲስ አበባ ማካሄድ ችላለች።
የኢትዮጵያው መሪ ንጉሠነገሥት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የአፍሪካ አገራትን ነፃነት ለማረጋገጥ ቀዳሚውን ድርሻ ተወጥተዋል። ድርጅቱ በጥንካሬ እንዲመሠረትም የመጀመሪያውን ጡብ አኑረዋል። ይህ እውነታም ኢትዮጵያን ከቀዳሚዎቹ ተርታ አሰልፎ ከፊተኞቹ ረድፍ ያቆማታል።
ከሁሉም አፍሪካ አገራት በተሻለ የነፃነት አየር የምትተነፍሰው ኢትዮጵያ ለአፍሪካ የነፃነት አርበኞች ተገቢውን ድጋፍና ከለላ ስትሰጥ ቆይታለች። እንደአውሮፓውያኑ ዘመን ከ1960ዎቹ በኋላ ነፃ በወጡ አፍሪካ አገራት መካከል የተፈጠረውን ቅራኔ ለመፍታት የኢትዮጵያ ድርሻ በእጅጉ የላቀ ነበር።
በ1961 የጋናው መሪ ክዋሜ ኑክሩማ የአፍሪካ አገራት ፈጥነው በፌዴሬሽን ይዋቀሩ ዘንድ ሀሳብ አቀረቡ ። ይህ ውጥናቸው ዳብሮም እንደሀሳብ የአፍሪካ አንድነት የተባለ ስብስብ እንዲጸነስ ምክንያት ሆነ። የኑክሩማንን ሀሳብ ዕውን ለማድረግ ጊኒ ማሊና ጋና፣ አልጄሪያና ሞሮኮ በጋማል ናስር ከምትመራው ግብጽ ጋር በመሆን የካዛብላንካን ቡድን መሠረቱ።
በሌላ ወገን እንደ ሴኔጋል ናይጄሪያና ላይቤሪያን ጨምሮ በርከት ያሉ አገራት ያሉበት የሞኖሮቢያ ቡድን ሌላ ሀሳብ ይዞ ተነሳ። ይህ ቡድን ‹‹በአፍሪካ አንድነትን መፍጠር የሚቻለው በመፍጠን ሳይሆን ቀስ በቀስ በሂደት ሊሆን ይገባል›› የሚል ዕምነት ነበረው። ከዚሁ ጋር ተያይዞም ለኢኮኖሚያዊ ውህደቱ ቅድሚያ የመስጠት ሀሳብ ማራመድን ዓላማው አድርጓል።
በዘመኑ ‹‹የካዛብላንካና የሞኖሮቢያ ቡድን›› በሚል የተፈጠረው ክፍፍል በአህጉሪቱ የአንድነት መሠረት ላይ ክፉ ጥላውን አጥልቷል። ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታም አደጋው የጎላ ነበር። በወቅቱ ኢትዮጵያ በርካታ አገራት የተካተቱበትን የሞኖሮቢያ ቡድን የላከላትን የስብሰባ ጥሪ አክብራ ተቀበለች።
ለሞኖሮቢያው ቡድን ስብሰባ ሌጎስ የተገኙት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የአገራቸውን አቋም በግልጽ አሳወቁ። ንጉሡ ኢትዮጵያ ለማንኛውም ቡድን እንደማትወግንና ከየትኛውም ስብስብ ገለልተኛ መሆኗን በገሀድ ተናገሩ። ከዚሁ ጎን ለጎንም አገራችን ቀጣዩ የቡድን ስብሰባ በአዲስአበባ ላይ እንዲካሄድ በማሳመን ቅስቀሳ አደረገች።
በዘመኑ ከሁሉም አገራት ጋር መልካም መግባባት የነበራት ኢትዮጵያ ተሰሚነቷ የላቀ ነበርና የአስታራቂነት ሚናዋ ለውጤት አብቅቷታል። ሁለቱ ቡድኖች ልዩነታቸውን አስወግደው በአፍሪካዊነታቸው ለምስረታ እንዲተጉ ጠንካራ መሠረት ጥላለች።
ከዚህ ታላቅ ውጤት ማግስት ግንቦት 25 ቀን 1963 ዓ.ም በቁጥር ሰላሳ ሁለት የሚሆኑ ነፃ የአፍሪካ አገራት በአዲስአበባ ተገናኝተው መከሩ። የአፍሪካ አንድነትን ምስረታ አስመልክቶ አገራቱ የየራሳቸውን የቡድን አቋም የሚያንጸባርቅ ረቂቅ ቻርተር ይዘው ቀረቡ። ኢትዮጵያ በወቅቱ ገለልተኛ በመሆን የሁለቱንም ወገን ያማከለ ረቂቅ የመመስረቻ ቻርተርን አቀረበች። ቻርተሩም በጉባኤተኛው ሙሉ ድምጽ ጸድቆ ተቀባይነትን አገኘ።
ይህ አጋጣሚም ለአፍሪካ ህብረት ምስረታ ምክንያት ሆኖ በታሪክ ተመዘገበ። ኢትዮጵያም በወቅቱ ለአፍሪካ ህብረት ምስረታና ለህብረቱ መቀመጫነት ትክክለኛዋ አገር መሆኗ ታመነበት። በጊዜው የኢትዮጵያው ንጉሥ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ፣ የጋናው መሪ ክዋሜ ኑክሩማ፣ የግብጹ ጋማል አብዱል ናስር፣ የታንዛንያው ጁሊየስ ኔሬሬ፣ የጊኒው አህመድ ሴኮ ቱሬ፣ አስተዋጽኦ በእጅጉ የላቀ ነበር።
በእነዚህ የአፍሪካ አባቶች ጥረት አንድነቱ ተጠናክሮ የአፍሪካውያን ትስስር ጥብቅ መሠረትን መገንባት ተችሏል። አዲስአበባ ከአፍሪካ ህብረት ምስረታ ጀምሮ የአፍሪካ መዲናነቷን አስመስክራ እስካዘሬ ዘልቃለች። የአፍሪካውያንን ታላቅ ኃላፊነት በብቃት የምትወጣው አገራችን ለዓመታት በዘለቀው ትጋቷ ለህብረቱ ጸንቶ መቆም ድርሻዋ የላቀ ሆኖ ቆይቷል።
የአፍሪካ ህብረት እንደ አውሮፓውያኑ ዘመን አቆጣጠር በ2002 በደቡብ አፍሪካ ‹‹ደርባን›› በነበረው ጉባኤ ወደ አፍሪካ አንድነት ለመቀየር ችሏል። ህብረቱ ስያሜውን ከመቀየሩ አስቀድሞ መቀመጫነቱ ከአዲስ አበባ ይነሳ ዘንድ ጥቂት የሚባሉ አገራት ሲወተውቱ ቆይተዋል። ይህ ዓይነቱ ያልሰመረ እንቅስቃሴ ግን ረጅም መንገድ አልተጓዘም።
ኢትዮጵያ በነበራት የተለያዩ የመንግሥት ለውጦች ሳይቀር የአህጉሪቱን ጉዳይ ፈጽሞ አልረሳችም። በየዘመናቱ የተለዋወጡ መሪዎቿ ጭምር የአፍሪካንና የአፍሪካውያንን ህልውና ለማስጠበቅ ሲታገሉ ቆይተዋል። ይህ አይረሴ እውነታ አገሪቱ ለአፍሪካ ነፃነት የከፈለችውን ታላቅ ዋጋ ሚዛን አስድፍቶ በከፍታ አጉልቶታል።
የኢትዮጵያን መልካም ስም በማይሹ ምዕራባውያን መሪነትና በአንዳንድ ግለሰቦች ተንኮል ሲተበተብ የቆየው መረብ የታቀደውን ውጤት አላስገኘም። የአፍሪካን መዲናነት ከአዲስ አበባ የመንቀል ተልዕኮ በኢትዮጵያ መሪዎችና በእውነተኞቹ የአፍሪካ አገራት አጋርነት ሳይሳካ ቀርቷል።
ዛሬም ስለኢትዮጵያ መልካም ሥምና ዝና ዕንቅልፍ የሌላቸው አካላት በየሰበቡ ጉዳዩን አጀንዳ የማድረግ አባዜው አለቀቃቸውም። አሁንም የኢትዮጵያን ታላቅ ነትና ውለታ ፈጽሞ የማይዘነጉ አፍሪካውያን ግን ይህን ዓላማቸውን በጽኑ ይታገሉታል። ኢትዮጵያን ድምጽና አጋር አድርገውም ለአህጉራቸው ሰላምና አንድነት በጽኑ ይተጋሉ።
እነሆ! የአፍሪካ ህብረት ከተመሠረተ ዘንድሮ ስልሳኛ ዓመቱን ይይዛል። ቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በሚል ምስረታውን ያጸናው ይህ ህብረት ላለፉት ስልሳ ዓመታት በስኬትና ፈተናዎች መሀል ተረማምዷል። በርካታ ችግሮችን በመፍትሄ ደርሶም ላልተፈቱ የአህጉሪቱ ቋጠሮዎች ለዓመታት ሲተጋ ቆይቷል።
ህብረቱ ላለፉት ስልሳ ዓመታት በነበረው ጉዞ መንገዱ አልጋ በአልጋ አልነበረም። በምዕራባውያን ረጃጅም እጆችና ዓይን ያወጣ ጣልቃገብነት ሲፈተን ቆይቷል። እስከዛሬ በተካሄዱ የእርስበርስ ጦርነቶች፣ በሚፈጠሩ ግጭቶችና በሌሎችም አብይ ጉዳዮች የባለቤትነት ሚናው የጎላ ነበር።
ህብረቱ ዘንድሮ ስልሳኛ ዓመቱን የሚያከብረው በተመሠረተበት ኢትዮጵያ የአፍሪካ መዲና በሆነችው አዲስአበባ ከተማ ይሆናል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰሞኑን እንዳስታወቀው በዓሉ ከግንቦት 17 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ለአንድ ዓመት በድምቀት ይከበራል።
ሚኒስቴር መስሪያቤቱ በሰጠው መግለጫ እንዳረጋገጠው የአፍሪካ ህብረት ሰልሳኛ ዓመት የሚከበረው የአዲስ አበባን የዲፕሎማሲ ማዕከልነት በሚያጸና መልኩ ነው። አገራችን የአፍሪካ ህብረት መሥራችና ጽኑ መሠረት ናት። በዓሉ የስልሳ ዓመታት ጉዞን ከመዳሰስ ባለፈ የመዲናዋን የዲፕሎማሲያዊ ማዕከልነት ለማጉላት ድርሻው የጎላ ይሆናል።
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እንዳለው በኢትዮጵያ ያለውን ወቅታዊ ችግር አሳበው የህብረቱን መቀመጫ ከአዲስአበባ ለማንሳት የሚተጉ አገራት ዛሬም ድረስ አልቦዘኑም።
የህብረቱ ስልሳኛ ዓመት ሲከበር ግን መዲናዋ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷ ጸንቶ የዓለም አቀፍ ተቋማት ደህንነት በተሻለ ሁኔታ በሚረጋገጥበት ደረጃ ይሆናል። ዛሬም ኢትዮጵያ በጠንካራው የአፍሪካ ዲፕሎማሲ መንገድ የምታደርገውን ብርቱ ጉዞ ያለድካም ትቀጥላለች። ይህ እውነታ ለህብረቱ ምስረታና ጸንቶ መቆም ታሪካዊ አሻራው ደማቅ ነውና።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን ግንቦት 18/2015