የዓባይ ወንዝ 86 በመቶ ምንጭ በሆነችው ኢትዮጵያ፤ 65 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ኤሌክትሪክ ተደራሽ አይደለም:: ሁለት ሶስተኛው አገሪቱ ተማሪዎችም በመብራት እጦት ጭለማ ይፈትናቸዋል::በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሴቶች ውሃ ለመቅዳትና የማብሰያ ማገዶ እንጨት ለመልቀም በየቀኑ ብዙ ኪሎ ሜትሮችን ለመጓዝ ይገደዳሉ::
ጅምር አዳጊ ኢኮኖሚዋም የኃይል ፍላጎቷን በየአመቱ በ20 በመቶ ከፍ እንዲል አድርጎታል:: በህዝብ ብዛቷ ከአፍሪካ ሁለተኛ እንደመሆኗም ከድህነት አረንቋ ለመውጣት ጊዜ ማባከን እንደሌለባት የትኛውም አካል በቀላሉ መረዳት ይችላል::
የህዳሴ ግድብ ግንባታ እውን መሆን ደግሞ የአገሪቱን የኃይል ፍላጎት ምላሽ በመስጠት የዜጎችን የዓመታት ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጥያቄ ከመመለስ ባሻገር፤ የተሳሰቡን አገራት የጋራ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ ቀጠናዊ ብሎም አህጉራዊ ትሩፋቱ ጉልህ ነው::
ዓባይ የኢትዮጵያ ተፈጥሮአዊ ሃብት ነው::የዓብይ ግድብም በኢትዮጵያውን አቅም የሚገነባ ታሪካዊ ግድብ ነው::አትዮጵያም ከግንባታ ጅማሮው አንስቶ ላለፉት አስር አመታት ግድቡ በየትኛውም የተፋሰሱ አገራት ላይ ጉዳት እንደማያደርስ ለዓለም አቀፉ ህብረተሰብ ስትገልፅ ቆይታለች::
የግድቡን የግንባታ ሂደት አስመልክቶ ከግብፅና ከሱዳን የሚነሳውን ስጋት በመገንዘብ መተማመንን ለመፍጠር በራሷ አነሳሽነት ዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን መጋበዟን፣የሶስቱ አገራት ብሔራዊ የቴክኒክ አማካሪ ምክር ቤት ብሎም ገለልተኛ የጥናት ባለሙያዎች ኮሚቴ እንዲመሠረት ማድረጓም የሚታወስ ነው::
አገራቱ ያልተግባቡባቸውን የቴክኒክ ጉዳዮች በሳይንሳዊ መንገድ ለመፍታት እንዲቻላቸው በርን ክፍት ከማድረግ ጀምሮ፤ ግድቡን በተመለከተ የሚመክሩበትንና የሚተባበሩበትን የሚችሉበት የመርሆ ስምምነት ማዕቀፍ በሦስቱም ይሁንታ እንዲፀድቅ አድርጋለች።
ይሁን እንጂ የግብጽ እና የሱዳን በተለይም የካይሮ ሰዎች የግድቡን ግንባታ ለማጨናገፍ የተለያዩ እኩይ ተግባራት ሲከውኑ ቆይተዋል፤ ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ጫና ለመፍጠር ያላደረጉት ጥረት የለም::በተለይ የግድቡን የውሃ ሙሌት በተመለከተ በሚያራምዱት አቋም ከማስገረም አልፎ ሲያስተዛዝብ ቆይታል::
በናይል ወንዝ ላይ 5 በመቶ እንኳን አበርክቶ የሌላት ግብፅ በምስራቅም በምዕራብም የዚሁ ወንዝ ብቸኛ አለቃ ነኝ በማለት በሌሎች የናይል ተፋሰስ ሀገራት ላይ የምትሰነዝረው ዛቻ እና ማስፈራሪያ ጊዜን እየጠበቀ መስተጋባቱ የተለመደ ሆኗል::
ሆኖም ኢትዮጵያ የግብፅ ሽለላና ቀረርቶ ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት በግዛቷ ውስጥ በሚገኘው ዓባይ ላይ የዓባይን ግድብ ግንባታ ጀምራ ከመገባደጃው አድርሳዋለች::ይህ የኢትዮጵያ ጉዞ አልዋጥልህ ያለው እና የግብፅ አፍ እንደሆነ የሚታወቀው የዓረብ ሊግም የካይሮ ሰዎች በማንአለብኝነት የሚሰጡትን ሃሳብ በመግለጫ ጭምር በመደገፍ ጉዳዩን ዓረባዊ ለማድረግ ሲጥር ቆይቷል:: እየጣረም ይገኛል::
የዓረብ ሀገራት የጋራ ጥምረት የሆነው የዓረብ ሊግ ሰሞኑን በሳዑዲ ዓረቢያ ጅዳ ባካሄደው የአባል ሀገራቱ የመሪዎች ጉባኤው በርካታ ውሳኔዎችን ያሳለፈ ሲሆን፤ የዓባይ ግድብ ጉዳይም ከእነዚሁ መካከል ነበር::
ቀደም ባሉት የሊጉ ስብሰባዎች የአቋም መግለጫዎች ውስጥ በአፅንኦት ይደጋገም የነበረው “ኢትዮጵያ አስገዳጅ ስምምነት መፈረም አለባት” እና “የግብፅ የውሃ አቅርቦት ጉዳይ የአረብ ሊግ ሀገራት የፀጥታ ስጋት ጉዳይ ነው” የሚል ነበር:: ሊጉ በዚህ ሳምንት መጨረሻ ከጅዳ ሆኖ በወጣው ፅሁፍ እና ስለ ዓባይ ግድብ ይፋ ባደረገው የአቋም መግለጫው ደግሞ ስለ ግብፅ እና የሱዳን የውሃ ዋስትና ጉዳይ አንስቷል::
ሊጉ በመግለጫውም ‹‹የግብፅና ሱዳን የውሃ ዋስትና የአረብ ሊግ ሀገራትም የውሃ ደህንነት ዋና አካል ነው::በዓባይ ውሃ ለመጠቀም ያላቸውን መብት የሚነካ ማንኛውንም እርምጃ ውድቅ እናደርጋለን›› ብሏል::
ከዚህ በተጨማሪ በዓባይ ግድብ ዙሪያ የፀጥታው ምክር ቤት እአአ በመስከረም 15 ቀን 2021 ለሰጠው መግለጫ ምላሽ የሰጡበት አቋም ነው። በዚህም የፀጥታ ምክር ቤቱ ኢትዮጵያን፣ ሱዳንን እና ግብፅን በተመለከተ ያቀረበውን ጥሪ በደስታ እንቀበለዋለን። ብሏል::
ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በፈረመቻቸው ሰነዶች መሰረት ወደፊትም ቀጣይነት ባለው መልኩ ድርድሮች መቀጠል አለባቸው:: እያጋጠሙ ያሉ መደነቃቀፎችም አሳሳቢ ናቸው።” ብሏል።
“ኢትዮጵያም በቅን ልቦና የመደራደርን አስፈላጊነት ከግምት በማስገባት በግድቡ የውሃ ሙሌትና የስራ ትግበራ ውስጥ የሶስቱን ሀገራትና የግብፅና ሱዳንን ጥቅም ባስጠበቀ መልኩ ፍትሃዊ፣ሚዛናዊና ህጋዊ የሆነ አሳሪ ስምምነት ላይ ለመድረስ ቁርጠኛ እንድትሆን፤ በተጨማሪም ሶስቱ ሀገራት እአአ በ2015 የፈረሙትን ስምምነት ያከበረ አካሄድ በግድቡ ሙሌት ገቢራዊ መሆን አለበት” ሲል ሊጉ በመግለጫው አካቶ አቅርቧል።
ኢትዮጵያም ሊጉ በዓባይ ግድብ ላይ ያሳለፈው የውሳኔ ሃሳብ የመሰለ መግለጫን እንደማትቀበለው አስታውቃለች::የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ፣በቅርቡ የተካሄደው የዓረብ ሊግ የመሪዎች ጉባኤ ያሳለፈው የውሳኔ ሀሳብ የኢትዮጵያን መንግስት እንዳሳዘነ ገልጿል::
ውሳኔው በተለይም በግድቡ ዙሪያ ያለውን አለመግባባት በሰላማዊ ድርድር እንዲፈታ እየሰሩ ያሉትን የአፍሪካ ህብረትን እና አባል ሀገራትን ሚና የሚያኮስስ ነው ሲል አብራርቷል::
የውሳኔ ሃሳቡ ታሪክን ከሚጋራው የአፍሪካ እና የዓረብ ሀገራት ግንኙነት በተቃራኒ የተወሰነ ውሳኔ መሆኑንም አስገንዝቧል::በሊጉ የተላለፈው የውሳኔ ሃሳብ የግብጽን የናይል ወንዝ ፍትሃዊ ያልሆነ አጠቃቀም የሚደግፍ መሆኑንም አጽንኦት ሰጥቷል::
በእርግጥ የሊጉ መግለጫ እንደተለመደው የአንድ ወገን እይታን ብቻ የሚያቀነቅን መሆኑ ነው:: እንደሚታወቀው ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ የምታከናውነው በታችኞቹ የተፋሰሱ አገሮች ላይ ጉልህ ጉዳት ያለማድረስ መርሆንና ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን የተመለከቱ ዓለም አቀፍ ሕግና መርሆዎችን በጠበቀ መልኩ እንደሆነ በተደጋጋሚ አሳውቃለች::
ይህን እውነት ከመስማት ባለፈ መርምሮ ለመቀበል የሚቸገረው የግብፅ ስሪቱ አርብ ሊግ ግን እንደ ትናንቱ ሁሉ አባይን ከአረብ አገራት የውሃ ዋስትና ጋር ለማስተሳሰር ደፋ ቀና ማለቱን ቀጥሎበታል::
ግብፅም ግድቡን በሚመለከት የጋራ ተጠቃሚነት ያከበረ የሶስትዮሽ ውይይት መፍትሄን ከማስቀደም ይልቅ ለዘመናት የቆየውን የዓባይ ውሃን በብቸኝነት የመጠቀም ኢፍትሐዊነት ለማስቀጠል ጥረቷን ቀጥላለች::
ለአፍሪካ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሄን ከማፈላለግ እና በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር ለውይይት ከመቀመጥ ይልቅ፤ ዓባይን የአረብ አገራት ጉዳይ ለማድረግም አጀንዳውም በሊጉ በኩል እንዲራገብ እየተጋች ትገኛለች::
ይህ አካሄዷም ሁለት ነገርን ያስመለክታል::አንደኛው ግብፅ ከእውነታዎችና ከአዳዲስ የፖለቲካ ሁነቶች ጋር ራሷን አስታርቃ ከዓባይ ተፋሰስ አገሮች ጋር በትብብርና የጋራ ጥቅምን በማረጋገጥ መንፈስ መስራት እንዳልተዋጠላት ነው::
ሌላኛው ደግሞ ለአፍሪካ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሄን የሚለውን እሳቤ ለ‹መቀበል የምትቸገርና ለአፍሪካ ህብረት ሚና ያላትን የተንሸዋረረ እይታ ግልፅ አድርጋ የሚያስታውቅ ነው::ይሁንና ለአፍሪካ ችግር አፍሪካዊ መፍትሄ የሚለው መርህ ምን ያህል ውጤታማ እንደሆነ በኢትዮጵያ በኩል በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የተከሰተውን ጦርነት በሰላም የተቋጨበት መንገድ በራሱ በቂ ምስክር ነው::
ዛሬም ሆነ ነገ የዓባይ ግድብ አጀንዳም በተለይም ድርድሮች ሙሉ በሙሉ በአፍሪካ ምድር አፍሪካዊ መፍትሄ እንዲያገኙና በአፍሪካ ህብረት እንዲፈታ ኢትዮጵያ ሁሌም በሯ ክፍት ነው::በተሳሰቡ አገራት በተለይም በሶስቱ አገራት መካከል የሚካሄዱ ድርድሮችም ከአረብ ሊግም ሆነ ከምዕራባውያኑ ምድር ይልቅ በአፍሪካ ሕብረት መፍትሄ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ የተያዘው አቋም አበረታች እና ይበልጥ ፀንቶ መቀጠል የሚገባ ነው::
ምንም ይሁን ምን ኢትዮጵያ ግድቡን በሚመለከት የጀመረችውን በጋራ ተጠቃሚነት መርህ የተቃኘ የሶስትዮሽ ውይይት እንደ ትናንቱ ሁሉ ነገም ሆነ ከነገ ወዲያ አፅንታ ትቀጥላለች::ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና በተለይ ግብፅ ወደ ጋራ ተጠቃሚነት ስምምነት እንድትራመድ ግፊት ሊያደርግ ይገባል:: ጉዳዩ የአፍሪካ፣ ቀረቤታውም ለአፍሪካ እንደመሆኑ፤ ግብጽም አጀንዳው የአረብ ሊግ ሳይሆን የአፍሪካ ሕብረት መሆኑን ተገንዝባ ልትሰራ ያስፈልጋል::
ክብረአብ በላቸው
አዲስ ዘመን ግንቦት 16/2015