ማሰላሰያ፤
ሀገራዊ ብሂሎቻችንን እንዳፈጁና እንዳረጁ በመቁጠር ሳንተች፣ ሳናጥላላና በጭፍን ሳንፈርጃቸው ረጋ ብለንና ጊዜ ሰጥተን ብንመረምራቸው እውቀትና ጥበብን፣ ባህልንና ነባር ጠቃሚ ወጎችን በሚገባ ልንማርባቸው እንችላለን:: በውሱን ቃላት የሚያስተላልፉት መልእክትም ለአንዴ ብቻ ገንነው የሚደበዝዙ ሳይሆን ከትውልድ ትውልድ በመሸጋገር ረጂም ዘመን የመኖር አቅም ያላቸው ናቸው::
እርግጥ ነው ከቋንቋችን ባህር ውስጥ የሚቀዱት ብሂሎች ሙሉ ለሙሉ በአዎንታዊ ትርጉማቸው ብቻ የሚደነቁ ሳይሆኑ ከስንዴ ወይንም ከገብስ ውስጥ አንዳንድ እንክርዳዶች እንደሚገኙ ሁሉ በአሉታዊ መልእክት አስተላላፊነታቸውም የሚታወቁ እንዳሉ የሚካድ አይደለም:: ዳሩ የምንሳሳላት ሕይወት ራሷ በተቃርኖ የተሞላች አይደለችምን? ያውም በአሉታዊና አወንታዊ ተሸርባ ግራ እያጋባችንና ቁም ስቅል እያሳየችን ችለን እንደምንኖረው መሆኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል::
በነገረ ብሂሎቻችን ይዘት ለመንደርደር የተፈለገው ዝርዝር ጽንሰ ሃሳቦቻቸው ላይ ጫን ብለን ትንታኔ ለመስጠት በማሰብ ሳይሆን፤ በርእስነት ለተጠቀምንበት አባባል የማሰላሰያ መንደርደሪያ ለመስጠት አስፈላጊ መስሎ ስለታየን ነው:: ስለዚህም “አትሩጥ አንጋጥ!” የሚለው ዕድሜ ጠገብ ብሂል ከጅማሬው “ሲፈጠር” እንዲያስተላልፍ የተፈለገው መልእክት፤ ከአቅም በላይ የሆነን ችግር ለመቋቋም በራስ መፍጨርጨር ብቻ ከመዳከር ይልቅ ዐይንን ወደ ፈጣሪ በማቅናት ትድግናውን መጠየቅም አስፈላጊ መሆኑን ለማሳየት ነበር::
እያደር ግን ብሂሉ በቀናነት ሊተረጎም የሚገባው የመነሻ ሃሳቡ ደብዝዞ ለስንፍና ማበረታቻ እንዲሆን መዋሉና አሉታዊ ትርጉሙም እንደ ጀብድ እየተቆጠረ ሲስፋፋ ማስተዋል የተለመደ ሆኗል:: ከሥራ ይልቅ ላብን ጠብ አድርጎ ሕይወትንና ኑሮን ከመምራት ይልቅ ሳይደክሙና ሳይሰሩ ለመክበር መመኘት እንደ ፋሽን ብቻ ሳይሆን እንደ ስኬት መንገድም መታየት ከጀመረ ውሎ አድሯል:: “አትሩጥ አንጋጥ!” መገለጫው ብዙ ቢሆንም አንዱንና ለሀገራችን ነቀርሳ የሆነውን ወረርሽኝ ብቻ የጥቆማ ያህል ለማሳየት አስፈላጊ መስሎ ስለታየን ይህንን ርእስ ለመምረጥ ግድ ብሎናል::
“ሰነፍ ሀሞቱ የቀጠነ ጠፍ”
“ሀሞቱ የቀጠነ” የሚለው ሀረግ የሚመደበው ከፈሊጣዊ አነጋገሮች ተርታ ነው:: ፈሊጣዊ አነጋገር በአጭሩ ሲበየን፤ “በየግላቸው ሲቆሙ የየራሳቸው ትርጉም ያላቸው ሁለት ወይንም ከዚያ በላይ ቁጥር ያላቸው ቃላት ተጣምረው ሲቀርቡ ከመጀመሪያው ይዘታቸው የተለየ አዲስ ትርጉም ሲሰጡ ፈላጣዊ አገላለጽ ነው” እንላለን:: ለምሳሌ፡- “ሀሞት” እና “ቀጠነ” የሚሉትን ሁለት ቃላት ለየብቻ የያዙትን ትርጉም ብንመረምር የየራሳቸው የሆነ ፍቺ አላቸው:: ነገር ግን “ሀሞቱ የቀጠነ” ብለን ስናጣምራቸው ግን ሀረጉ የሚወክለው “ሥራ ጠል፣ ወኔ ቢስ፣ ደካማ እና ሰነፍ” የሚል ትርጉም ይሰጠናል:: “ጠፍ” የሚለው ቃልም እንዲሁ የተሸከመው ትርጉም “ባድማ፣ ባዶ፣ ወና” የሚል ነው::
ስለዚህም “ሰነፍ ሀሞቱ የቀጠነ ጠፍ” የሚለው ብሂል በውክልና የሚቆመው በላቡና በወዙ ጥሮ ግሮ ከመብላት ይልቅ በወሬና በማምታታት ሕይወትን የሚመራን ብኩንና እርባና ቢስን ሰው ለማመልከት ይህ ሀረግ በጥሩ ገላጭነቱ መጥቀስ ይቻላል:: ሰነፍ ሰው በጥቅሉ ሀሞተ መራር አይደለም:: ከሥራ ይልቅ ሲያልምና ሲያቅድ ውሎ የሚያድረው “በምላሱ ብርታት” ለመኖር እንጂ በላቡ ፍሬ ኮርቶ ቤተሰቡን ለመምራትና ሀገሩን ለማኩራት አይደለም::
በሀገራዊ ቋንቋዎቻችን ውስጥ ስለ ስንፍና የሚናገሩ ብሂሎቻችንና ፈሊጣዊ አነጋገሮቻችን ብዙ ናቸው ከማለት ይልቅ “ስፍር ቁጥር የላቸውም” ብሎ መደምደሙ ይቀላል:: እንደ ብሂሎቻችን አበዛዝ ሁሉ የበርካታ ዜጎች የስንፍና መገለጫዎችም የዚያኑ ያህል የተበራከቱ ናቸው::
ለሥራ ከመትጋት ይልቅ ለወሬና ለማምታታት መፍጠንን ለመግለጽ፤ “ስንፍናና ዋንጫ ከወደ አፉ ነው” የሚለው አባባልም ብዙ ጊዜ ይጠቀሳል:: በዚህ ጸሐፊ ግምት ሀገሬን እንደ ክፉ የብጉንጅ ንፍፊት እየጠዘጠዛት ያለውና ሕዝብ እንዲማረር ምክንያት ከሆኑ ግዙፍ ብሔራዊ ችግሮቻችንና ፈተናዎቻችን መካከል በቀዳሚነትም ሆነ በተከታይነት የሚጠቀሰው ችግር በደላሎች የመወረሯ ፈተና ነው ቢባል ያስማማ ይመስለናል::
ከገጠር እስከ ከተማ፣ ከገበያ እስከ ፍትሕ አደባባይ፣ ከፖለቲካው መንደር እስከ ዝቅተኛው ሠፈር፣ ከላይ ቤት እስከ ታች ቤት፣ ከቤተ እምነት እስከ ትምህርት ቤት፣ ከሐኪም ቤት እስከ ሹመት ወዘተ. (ዝርዝሩን ላልዘልቀው ጀመርኩት መሰል) ደላላ ያልተቆጣጠረው ነፃ ሕይወትና “መሬት” ስለመኖሩ እርግጠኛ ለመሆን ያዳግታል::
ገበሬው ለማምረትና ምርቱን ለመሸጥ ሲፈልግ ላብ ያልፈሰሰበት የደላላ ጣልቃ ገብነት ግድ እስከ መሆን የደረሰ ይመስላል:: ለመገበያየት ደላላ፣ ንብረት ለመሸጥ፣ ለመለወጥና ለመከራየት ደላላ፣ ጉዳይ ለማስፈጸምና ያለ ተራ ለመገልገል ደላላ፣ ምናልባትም ወደፊት ነገሩ እየተጠናከረ ሲሄድ ለመሞትና ለመቀበርም “ደላሎች እኛ ካልወሰንላችሁ” እስከ ማለት ሳይደረሱ እንደማይቀር አያያዛቸው ይመሰክራል:: ደላሎች በቅቤ አንደበታቸው ማግባባት ብቻ ሳይሆን ማጋጨቱንም በሚገባ ተክነውበታል::
የድለላ ሥራ ሙሉ ለሙሉ በክፋትና በጥፋት ብቻ መጠቀስ እንደማይገባው ይህ ጸሐፊም ይሁን አንባቢዎች ይጠፋቸዋል ማለት አይደለም:: ሕግና ሥርዓትን በተከተለ የድለላ ተግባር ተሰማርቶ ራስንና ቤተሰብን ከመምራት በዘለለ በሚያምታቱ ደላሎች ምክንያት ለእንባና ለጸጸት የተዳረገው ዜጋ ቁጥር ቢሰላ ሺህ ምንተ ሺህ ጊዜ እንደሚበልጥ መገመቱ አይከብድም::
በደላሎች የተባ ምላስ ምክንያት ትዳርና ንብረት አደጋ ላይ የወደቁባቸው አጋጣሚዎች በሽበሽ ስለመሆናቸው ብዙ ሰው ምስክር ስለሚሆን “እንዲህ ነው እንዴ?” ብሎ የሚገረም አንባቢ ላይኖር እንደሚችልም ይታሰባል:: በደላላ ያልተጎዳ ወይንም ያላለቀሰ ሰው ካለ እርሱ በእድለኛነት ሊመሰገን ይገባዋል::
በደላሎች ተሹመው የድለላ መረቡን ያወሳሰቡ ብዙ አጋጣሚዎችም ከሹክሹክታ አልፎ ተርፎ በብዙኃን መገናኛ ዘዴዎች ሳይቀር ይፋ ሲደረጉ ሳንሰማ እንዳልቀረን እንገምታለን:: ለአንድ ማሕበረሰብ የማሕበራዊ ውድቀት ምክንያት ከሆኑት አደጋዎች መካከል አንዱ ዜጎች በዜግነታቸው የፈለጉትን አገልግሎት በተቀላጠፈ ሁኔታ ማግኘት ሲገባቸው “ይህንን ጉዳዬን ለማስፈጸም ማን ሊረዳኝ ይችል ይሆን?” በማለት ደላላ መፈለግና ማፈላለግ ሲጀምሩ ያን ጊዜ ፍትሕ አቧራ ይለብስና ሕገ ወጥነትና ድለላ ማበብ ይጀምራል::
ይህንን መሰሉ አረም “የሀገርን ሁለንተናዊ ገላ መውረር ሲጀምር” ያን ጊዜ በሽታው ሥር ሰዶ የዜጎች ኑሮ “ከሞቱት በላይ፤ ከቆሙት በታች” እንዲሉ ምሬትና እምባ ይከተላል:: እውነት እውነቱን አድምተን እንነጋርና በአሁኑ ወቅት በዚህች ምስኪን ሀገር ውስጥ ያለ ደላሎች ጣልቃ ገብነት የሚፈጸም ጉዳይና የሚቆም ገበያ ይኖራልን? በዕለት ተዕለት እንደምናስተውለው ከመሸማቀቅ ይልቅ እየተጀነኑ በይፋ ሲንጎማለሉና ሲፋንኑ በየአደባባዩና በየአገልግሎት መስጫና በየገበያው ማእከላት የምንመለከታቸው ደላሎችን አይደለምን? ስለዚህ ይህ ጉዳይ “የብሔራዊ እፍረታችን” አንዱ መገለጫ ነው ቢባል ይበዛበታል?
ሕዝባዊ አገልግሎት በሚሰጡ ተቋማት ቅትረ ግቢ ውስጥና ውጭ እንደ ጆፌ አሞራ ሲያንዣብቡ የሚውሉ ደላሎችን አላየሁም፣ አልሰማሁም የሚል አንድ ሰው ማግኘት ከተቻለ በእጅጉ ያስገርማል:: የቀበሌዎች፣ የወረዳዎች፣ የክፍለ ከተሞች ወዘተ. ሕዝባዊ ተቋማት በደላሎች ቫይረስ ተበክለው በሽተኞች ከሆኑ ሰንብቷል:: ሠንሠለታቸው ደግሞ ከላይ እስከ ታች የተያያዘ ስለሆነ ተገልጋይ ዜጎች እንዲተበተቡ የሚደረግበት ዘዴ እጅግ የረቀቀ ነው::
ፋይል በእጃቸው ይዘው ወደ እነዚህ ተቋማት የሚገቡ ባለጉዳዮችን አስቀድመው የሚቀበሏቸው የሰለጠኑ ደፋር ደላሎች ናቸው:: “እከሌ የተባለውን ሹም እኔ ስለማውቀው ጉዳያችሁን በቀላሉ አስፈጽማለሁ” የሚለው የተለመደ ማማለያቸው የትም የሚደመጥ ነው:: በኢምግሬሽን መ/ቤት፣ በትራንስፖርት፣ በንግድ፣ በጉምሩክ፣ በገቢዎች ወዘተ. ተቋማት አካባቢ እንደ ንብ ሲከቡ የሚውሉ ደላሎችን የሕግ ተቋማት አያውቁም ወይንም አልሰሙም ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው:: ካስፈለገ በእነዚህ በተጠቀሱ መንግሥታዊ ተቋማት ደጃፍ ላይ ተገኝቶ እውነቱን መረዳት ይቻላል::
ሌለው ቀርቶ “እከሌ የተባለውን ሐኪም” እኔ ላገናኛችሁ እችላለሁ፣ የልጆቻችሁ የትምህርት ውጤት ሪፖርት ካርድ እንዲሻሻል ከፈለጋችሁ “እኔ ልረዳችሁ እችላለሁ” የሚሉ ደላሎች ሆስፒታሉንም ሆነ ትምህርት ቤቶችን ሲመርዙ መክረማቸውን ሊመሰክሩ የሚችሉት ታማሚ ግለሰቦችና የተማሪ ወላጆች ናቸው:: የዘንድሮን አያድርገውና “የአሥራ ሁለተኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተናን ጥያቄዎች ልጆቻችሁ አስቀድመው እንዲያገኙ ከፈለጋችሁ እኛን አናግሩን” የሚሉ ደላሎች እንደነበሩ የትናንት ትዝታችን ነው:: እነዚህ ክፉ ነቀርሳዎችና መሰሎቻቸው ሀገርና ትውልድን ለመግደል ሰይፍ ከያዘ ጠላት በምን ሊለዩ ይችላሉ?
ድለላ ዛሬ ዛሬ ከማግባባት ደረጃ ከፍ ብሎ ወሳኝነት ደረጃ ላይ የደረሰበት ጊዜ ነው:: የቤት ዋጋ የሚተመነው በደላላ ነው:: የኪራይ ዋጋ የሚወሰነው በደላላ ፈቃድ ነው:: የመኪና ቀለምና ግምቱ እንዲህና እንዲህ ነው ተብሎ የሚወሰነው በደላሎች ጉባዔ ነው:: የእህል ዋጋና ስሌት የሚተነበየውና የሚተገበረው በደላሎች መልካም ፈቃድ ነው:: የገበያው ሙቀትና ቅዝቃዜ የሚለካው በደላሎች የበጎ ፈቃድ ቴርሞ ሜትር ነው:: አልፎም ተርፎ ለሟች በድን የሬሳ ሣጥንና የአበባ ጉንጉን ከየት መገዛት እንደሚገባ እንኳን “አቅጣጫውን የሚቀይሱት” ደላሎች ናቸው::
ደግመን እናስታውስና ድለላ ሁሉ ክፉና ሰይጣናዊ ባህርይ ያለው ነው ብሎ ለመደምደም ቢያስቸግርም በአጠቃላይ ሲገመገም ግን የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያዊያንን ኑሮና ተስፋ እያጨለመ ያለው አንዱ ትልቅ ብሔራዊና መፍትሔ የጠፋለት በሽታ የድለላ ወረርሽኝ መሆኑን ማመን የሚከብድ አይሆንም:: የሽንኩርት ዋጋ በደላሎች ከተወሰነ፣ ጤፍ በደላላ ትንፋሽ ከወረደና ከወጣ፣ ማንኛውም ጉዳይ ያለ ደላላ ጣልቃ ገብነት የማይፈጸም ከሆነ፣ ስደት እንኳን ሳይቀር በደላሎች የማስኮበለል ስትራቴጂ የሚተገበር ከሆነ ምን ቀርቶን በምን እንጽናና?
ሐቅ ሐቁን እንምከርና ከታች እስከ ላይ ያሉት የሕግ አስከባሪ ተቋማት ይህንን እንደ አሸን ፈልቶ ሕዝቡን ግራ ያጋባውን ክፉ ነቀርሳ በቁጥጥር ሥር ለማዋል በእርግጡ ቸግሯቸው ነውን? በእነዚህ ጨካኝ የማሕበረሰብ ነቀርሳዎች አማካይነትስ ዜጎች እስከ መቼ እምባቸውን እየረጩ ይኖራሉ? እስከ መቼስ ለመኖር ብቻ ሳይሆን ለመሞትም ጭምር የደላሎችን በጎ ፈቃድ እየተለማመንን እንኖራለን:: ግራ የገባው ግራ! ይሏል ይሄን ጊዜ ነው::
ደግመን አቤቱታችንን ጮክ አድርገን እናድርስና ሀገሬ ሆይ! ደላላ እየፈነጨብሽና ዜጎችሽም በደላሎች መከራ እያዩ የሚኖሩት እስከ መቼ ነው? እፎይታ አገኝተውስ በነፃነት ኑሯቸውን የሚመሩት እንዴትና በምን ሁኔታ ነው? ሀገርም “እንቆቅልሽ?” እየተባለች ልትጠየቅ ስለሚገባ “እንቆቅልሽ ኢትዮጵያችን ሆይ?” ብለን እንሞግትሻለን::
“ምን አውቅላችሁ!” ብለሽ እንዳትመልሺልንና “ሀገር ስጭን?” ብለን ስንከራከርሽም ሳትከፊብን ልብ ተቀልብ ሆነሽ በማድመጥ መፍትሔውን እንድታመላክችን “አቤት! አቤት!” እያልን እንማጠንሻለን:: “ሀገሬ ሆይ! ህሊና ቢስ ደላሎች በሕዝብሽ ላይ መርግምት እንደሆኑ ተሰምቶሻል? ተሰምቶሽ ከሆነስ ስለምን ችላ ብለሽ ዜጎችሽን አስመረርሽ? አልሰማሁም የምትይም ከሆነ ደግመን እናሰማሽ:: በደላሎች ምክንያት ዜጎች ተጨንቀዋል፣ ግራ ተጋብተዋል፣ ተሰቃይተዋል:: ስለዚህም ፍረጅልን! ክብርሽንና ዜጎችሽን “አትሩጥ አንጋጥ” በሚል ፍልስፍና ለተጠመቁ ሥራ ጠል ብሔራዊ ቅንቅኖች አሳልፈሽ አትስጭን:: ይሄው ነው:: ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ኅሊና:: “ኦሮማይ!” አለ ደራሲው::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 16/2015