አንድ የሥነ-ሰብ ተመራማሪ (anthropology) ወደ ደቡብ አፍሪካ ገጠራማ መንደር ለሥራ አቀና:: በቆይታው ከሕፃናት ጋር ተግባቦት ፈጠረ:: ሕፃናቱ ለማስደሰትም ሽልማት ያለው ጨዋታ አዘጋጀ:: ለጨዋታውም በማንጎ የተሞላ አንድ ቅርጫት ከዛፍ ሥር አስቀመጠ:: ሕፃናቱን ከዛ አንድ መቶ ሜትር እንዲርቁ አደረገ፤ ከዛም እንዲህ አላቸው፡-
‹‹እኔ ጀምሩ ስል ቀድሞ ቅርጫቱ ጋር የደረሰ የፈለገውንና የሚችለውን ያህል ማንጎ ይወስዳል ፣ይበላል::›› ጨዋታው ተጀመረ:: ሕፃናቱ ግን ያልተጠበቀ ነገር አደረጉ:: ከጨዋታው አፈነገጡ፣ ሁሉም እጅ ለእጅ ተያይዘው እኩል ወደ ቅርጫቱ ሮጡ:: ከዚያም አንድ ላይ በቅርጫቱ ውስጥ ያለውን ማንጎ በአሸናፊነት ተካፍለው መብላት ጀመሩ:: የሥነ ሰብ ተመራማሪውም በመገረም ‹‹ለምን እንዲህ አደረጋችሁ?›› ሲል ጠየቃቸው:: ሁሉም በአንድነት ‹‹ኡቡንቱ›› ብለው መለሱለት ::
በመቀጠል አንዱ ሕፃን፤ ‹‹እንዴት ሌሎች ጓደኞቻችን ተከፍተው አንድ ልጅ ብቻውን ይደሰታል? ይሄ ባሕላችን አይደለም›› አለ:: ‹‹ኡቡንቱ›› የቃሉ መሠረት የደቡብ አፍሪካው የዙሉ ማኅበረሰብ ሲሆን ትርጓሜውም ‹‹ለመኖሬ ምክንያት አንተ ነህ፤ ላንተም መኖር እኔ›› የሚል ሰብዓዊነትን ያዘለ ፍልስፍና ነው:: ይህን ጽሑፍ ያገኘሁት ከአንድ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጽ ነው:: ለጽሑፌ ግብዓት ስለሚሆነኝ ተጠቅሜበት እንደሆነ ይታወቅልኝ::
ኢትዮጵያ ድሀ ሀገር ናት ብሎ ማውራት ለቀባሪው አረዱት ስለሚሆንብን ተዉት:: ግን ድህነትን አስቡት:: አስቡት ስንል ደግሞ ቆዝሙለት ተክዙለት እያልን አይደለም:: ድህነትን በመቆዘም፣ በመቦዘንም ሆነ በመተከዝ መራቅም ማራቅም አይታሰብም::
በርዕሳችን ‹‹ምቾት አይገኝም በምኞት›› ስንልም ከላይ እንደጠቀስነው በማሰብ፣ በመተከዝ፣ በመቃቃር፣ በመናቆር ከድህነት አንወጣወም ለማለት ነው:: ምሳሌያዊ ብሂላችንም ይህንን ሲገልጸው ‹‹ ሹመትና ቁመት አይገኝም በምኞት›› ይለዋል::
ሰዎች ታታሪ ሠራተኛ ከሆኑ ድህነት ይዋጋሉ:: አንባቢዎቼ ለዚህ ደግሞ ማስረጃ አምጣ ብላችሁ ደግሞ እንዳታጨናንቁኝ:: ጠንካራና ታታሪ ሠራተኛ ሆኖ ራስንም ሆነ ሌሎችን ማየት አንድ ሠርቶ ማሳያ ላቦራቶሪ ስለሚሆን ራሳችሁን ከጠንካራ ሠራተኛ ጎን አግኝታችሁት ውጤቱን እዩት እላችኋለሁ::
ተረቱ ላይ እንደተገለጸው ማንጎውን ቀድሞ ሮጦ የደረሰበት የቻለውን ያህል መውሰድ ይችላል የተባሉት የዙሉ ሕፃናት ትዕዛዙን ሰምተው ተያይዘው በጋራ ሮጠው ሁሉ አሸነፉ እና ማንጎውን አገኙ:: ሕፃናቱ ለምን በጋራ ሮጣችሁ ሲባሉ ብዙዎች ተከፍተው ጥቂቶች ብቻ ሊደሰቱ ባሕላችን አይፈቅድም አሉ::
እኛም ትልቁ ጠላታችን ድህነት ነው:: ከድህነት የከፋ ሌላ ጠላት የለንም:: በየወቅቱ የሚስተዋሉ ችግሮቻችን መሠረት ይኸው ድህነት ነው። ከዚህ ውጪ ሁላችንም የአንዲት እናት ሀገር ልጆች መሆናችን ለፍቅር ለችግር ምንጭ ሊሆን አይችልም::
ምቾት ያልነው የሀብት እርከንን ነው:: በምኞት ከባለሀብቶች ጎራ መቀላቀል አንችልም:: ድህነት ትልቁ የሕዝብና የሀገር ጠላት ነው:: እኛ እርስ በእርስ በረባው ባልረባው፤ እየተቃቃርን፣ እየተናቆርን ታሪካዊ ጠላታችን ድህነትን መዋጋት አንችልም:: ልክ እንደ ደቡብ አፍሪካው ዙሉ ማኅበረሰብ እሳቤ ኢትዮጵያዊ እርስ በርስ ይፈላለጋል፣ ይደጋገፋል ::
ጠላታችንን ድህነትን የምንዋጋባቸው ተስፋ ሰጪ ጅምሮች ግን የሉም ማለት አይደለም:: በመንግሥት ደረጃ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አመርቂ ውጤቶች እየመጡ ነው:: በዚህ ንቅናቄ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሁለት ቢሊዮን ዶላር ተኪ ምርቶች ማምረት ላይ በትኩረት ሲሠራ ቆይቷል::
በዚህ ንቅናቄ 1ነጥብ 15 ቢሊዮን ዶላር የሚሆነው ምርት ምግብና ምግብ ነክ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ለጋዜጣችን የሰጠው መረጃ ያሳያል:: እሴት በተጨመረበት በእንጀራ ኤክስፖርትም 28 ሚሊዮን ዶላር ተገኝቷል:: መቼም ይሄን የጤፍ እንጀራ ምርት ከሚሸምቱት መካከል የእኛው ዲያስፖራዎች እንደሚሆኑ ይታመናል::
ከነዚህ መካከል በዓረብ ሀገሮች፣ በአውሮፓና በአሜሪካ የሚኖሩ ዜጎች ይገኙበታል:: ኤርትራውያንም እንዲሁም ትውልደ ኢትዮጵያውያን እስራኤሎችም (ቤተ እስራኤል) የእኛን እንጀራ በውጭ ከሚገዙት መካከል ናቸው:: ዲያስፖራዎች የጤፍ እንጀራ ከኢትዮጵያ ሲወስዱ ሀገራቸውንም እየረዱ ባሕላዊ አመጋገባቸውንም ለውጭ ዜጎች እያስተዋወቁ በመሆኑ ጠቀሜታው ‹‹ በአንድ ወንጭፍ ሁለት ወፍ›› እንደሚሉት ዓይነት ነገር ነው::
ዲያስፖራዎች ከሀገር ውስጥ ቡና እየወሰዱ ባሕላዊ የጀበና ቡና ማፍላት ሥርዓታችንንም እያስተዋወቁ እነርሱም ገቢ እያገኙ በመሥራትም፤ ማር ከሀገር ወስደው እንደጠጅ የመሳሰሉ መጠጦችንም በማምረትና በመሸጥ ቢንቀሳቀሱ ተጨማሪ ገቢ ማግኘት ይችላሉ፤ የሀገርንም የውጭ ምንዛሪ ገቢ ያሳድጋሉ:: በዚህ ረገድ በጋራ እየሠሩ ለውጥ ሊያመጡ ይገባል::
ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይ .ኤም ኤፍ) በቅርቡ በከለሰው 2023 የምጣኔ ሀብት ትንበያም ኢትዮጵያ ከሰሐራ በታች ከሚገኙ ግዙፍ ኢኮኖሚ እንደሚኖራትም ማስታወቁ ትልቅ ተስፋ ነው:: በአሁኑ ወቅትም ከአፍሪካ አምስት ጠንካራ ምጣኔ ሀብት ካላቸው ሀገሮች አንዷ ሆናለች::
ይህ የበለጠ ስኬታማ እንዲሆን ልዩነቶችን በሰለጠነ መንገድ በጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት መፍታት እንጂ ጦርነት ዘላቂ መፍትሔ አያመጣም:: ከሕውሓት ጋር የተደረገው ጦርነት የሰው ሕይወት ሀብት ቢባክንም ከሁለት ዓመት በኋላም ሰላም ያገኘነው በጠረጴዛ ዙሪያ በውይይት ነው::
እነዚህ መልካም ጅምሮች ሲጠናከሩ ድህነት የምንዋጋበት አቅም የበለጠ ይጎለብታል:: እርሻችን ከዝናብ ጥገኝነት ተላቆ ወደ መስኖ እንዲሸጋገር በትኩረት እየተሠራ መሆኑ የሚደገፍ ነው:: ከግብርና ሚኒስቴር የወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት በተለያዩ የውሃ አማራጮች 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር በመስኖ ማልማት ተችሏል::
በመስኖ የማልማት ሂደቱ በሚቀጥሉት ዓመታት የበለጠ ሲጠናከርም፤ የእርሻ ቦታ የበለጠ እየሰፋ የሰብል ምርቱም የበለጠ እየጨመረ እንደሚሄድ ያስታውቃል:: ጅማሬው በመስኖ የማምረቱ ልምድ እየተጠናከረ ሲሄድና ሲስፋፋ ደግሞ አርሶ አደሩም አርብቶ አደሮች ገቢያቸውን የሚያሰፉበት መንግሥትም በኤክስፖርት የግብርና ምርት የተሻለ ገቢ የሚያገኝበት ነው::
በዘንድሮ በበጋ መስኖ ምርት መንግሥት በቁርጠኝነት በመሥራቱ ገበሬውን በማትጋቱ ከውጭ ይገዛ የነበረውን እህል ማስቀረት ተችሏል:: ይህ ብቻ ሳይሆን የበጋ መስኖውን ምርት የውጭ ገቢ አስገኝቷል:: በቀጣዩ በጋ ደግሞ መንግሥት በቁርጠኛ አመራር ገበሬዎችን በማስተባበር በበጋ መስኖ እንዲያመርቱ ሲያደርግ የአምራች ገበሬዎች ብዛትና የሚገኘው የምርት መጠን ከዚሁ በእጥፍ ሊበልጥ እንደሚችል ጥርጥር የለውም:: መንግሥት ድህነት ለመዋጋት በበጋ መስኖ ያሳየው ውጤታማ ጅማሮ በቀጣዩ ጊዜያት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት::
ምናልባት መንግሥት የበጋ መስኖውን ምርት ወደ ውጭ ኤክስፖርት በመላኩ ሸማቹ ሕዝብ የምርቱን ውጤት ሊረዳው አይችል ይሆናል:: ነገር ግን በቀጣዩ የበጋ መስኖ ምርቱ ወደ ውጭ ኤክስፖርት ከመላኩ በተጨማሪ ለሀገር ውስጥ ሸማቹም ተርፎ በቅናሽ ዋጋ የበጋ ስንዴ ምርት ሊሸምት የሚችልበትን መንገድ ሊመቻች ይችላል::
በዘንድሮው ክረምትም አረንጓዴ ችግኝ በመትከል ሀገራችንን ደን በደን የሚያደርገውም ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥል:: በአራተኛው አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ታስቧል:: ይህም ግብርና ሚኒስቴር በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ማሳያ ነው::
ይህም ውጤቱን እያየነው ያለውን የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ኤሌክትሪክ የማምረት ጅማሮ የበለጠ የሚያጠናክርልን፤ የግድቡን ኤሌክትሪክ የማምረትም ሆነ ውሃ የማጠራቀም አቅሙንም የበለጠ የሚያሳድግልን ስለሆነም የዘንድሮውን ክረምት እንናፍቀዋለን:: ከወዲሁ ኤሌክትሪክ ወደ ጎረቤት ሀገራት እየላክን የተወሰነ የውጭ ምንዛሪ ማግኘታችን በቀጣይ ደግሞ ሀገራችን የውጭ ምንዛሪ የምታገኝባቸውን አማራጮች የሚያሰፋልን ተስፋ ሰጪ ጅማሬ ነው::
ለሁሉም እጅ ለእጅ ተያይዘን በመደመር፣ በመተባበር ድህነትን እንዋጋ:: መጽሐፉ ‹‹ለመሥራት የማይወድ ቢኖር አይብላ›› እንደሚለው ሁሉ ወጣቶች ለሥራ በመትጋት መበርታት አለባቸው:: ምዕራባውያን ‹‹የሥራ ፈት አዕምሮ የክፉ መንፈስ ቤተ ሙከራ ነው›› እንደሚሉት ሥራ ከፈታን በሴሰኝነት እና ሱሰኝነት ተጠምደን ድህነት የሚፈነጭብን ይሆናል::
ድህነት ለማራቅ መፍትሔው ከአንገታችን ሳይሆን ከአንጀታችን መሥራት አማራጭ የለውም:: ይህ ዘላቂ እንዲሆን ድህነቱም መሐይምነቱም ጽንፈኝነቱም ከላያችን እንዲራገፍ እጅ በእጅ ተያይዘን የጋራ ጠላታችንን ድህነትንና አላዋቂነትን መዋጋት አለብን:: ኡቡንቱ!
ይቤ .ከደጃች ውቤ
አዲስ ዘመን ግንቦት 15/2015