ሰላም የማይጠግነው ቀዳዳ፣ የማይጥፈው ጨምዳዳ የለም:: የዓለም ውበት ከሰላም ደም-ግባት ውስጥ የሚቀዳ ነው:: እንደ ሀገር ውበታም መሆን ካሻን ዘረኝነት ያልገባበት፣ አንድነት የዋጀው በሰላም ወስፌ የተጣፈ ኢትዮጵያዊነት ያሻናል:: አሁን ላይ ለሀገራችን ያለበስናት ቀሚስ ምን አይነት ነው? የአብሮነትን ነው የእኔነትን? የዘረኝነትን ነው፣ የኢትዮጵያዊነትን? መልሱ ቀላል ነው:: የዘረኝነትን ሸማ ነው ያለበስናት::
የዘረኝነት ሸማ ደግሞ የሰላም ወስፌ ያልነካው፣ የጥላቻና የራስ ወዳድነት በርኖስ ነው:: እንደ ሀገር በሰላምና በአብሮነት ለመቀጠል፣ የጀመርናቸውን የማደግና የመበልጸግ ህልሞቻችንን እውን ለማድረግ ሀገራችንን ያለበስናትን አዳፋ የብሔር ሸማ በወንድማማችነት መቀየር አለብን::
ይሄ ሀገር ለመስራት፣ ትውልድ ለማስቀጠል መሰረት የሚሆነን ሁላችንንም የሚያግባባ እውነት ነው:: ከዚህ እውነት ውጭ በብሔር ተቧድነን፣ በእኔነት ጎልምሰን የብቻና የተናጠል ሀሳብ እያሰብን የጋራ ሀገር መፍጠር አንችልም:: በብዙዎቻችን ዘንድ ኢትዮጵያ ሀሳባዊ ሀገር ናት:: ይቺን ሀሳባዊ ሀገር እውነት በሆነ መንገድ ወደ ሀገርነት ለመቀየር የጋራ ሀሳብ፣ የአብሮነት መንፈስ ያስፈልገናል::
ሀገራችንን ያለበስናትን የዘረኝነት ማቅ እስካላወለቅንላት ድረስ የምንናፍቃት ኢትዮጵያ ላይ አንደርስም:: ከሀሳብ የዘለለ ተግባር ተኮር የሆነ የንቅናቄ አብዮት ሳንፈጥር እንዲሁ እንደተመኘናት ነው የምንቀረው:: ዘመኑ ሰልጥኖ ከሰውነት ባለፈ ለእንስሳ ዘብ የመቆም ጊዜ ላይ ደርሷል:: እኛ ብቻ ነን እርስ በርሳችን የተጨካከነው:: እኛ ብቻ ነን በአንድ ሀገራችን ላይ ጨክነን የማትወለድን ሀገር ስናምጥ የምንኖረው::
የብሔር ጥብቆ የጋራ ሀገር አይሰራም:: አንዱን ሸፍኖ አንዱን አስበርዶ መከፋፈልን ነው የሚፈጥረው:: የዘረኝነት ሀሳብ ተራማጅ እሳቤ አይደለም:: እንዳውም በዚህ ዙሪያ ጥናት የሚያደርጉ አንዳንድ ግለሰቦች የዘረኝነት እሳቤ እጅግ ኋላ ቀር ከመሆኑ የተነሳ በዝግመተ ለውጥ ከተፈጠረው ከመጀመሪያው የሰው ልጅ እሳቤ ያልተሻለ ነው ይላሉ::
የጋራ በሆነች ሀገር ላይ፣ ታሪክ ባህሏ የሁሉ በሆነ ምድር ላይ፣ ሰማኒያና ከዛ በላይ ውበቶችና ማንነቶች ባደመቋት ህብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያ ላይ እኔነትን ማቀንቀን ምን የሚሉት ብላሽነት እንደሆነ ለሁላችንም የተገለጠ ነው:: ከዘመን ጋር የሚራመድ፣ ለጊዜው የሚፈጥን ሀሳብ ማሰብ፣ ሰውነትና ማንነት፣ ፖለቲካና ፖለቲከኛ ማጣታችን ሀገራችንን መቀመቅ ውስጥ እየከተተ ያለ ድርጊት ነው::
ሀገራችንን መታደግ አለብን:: ሀገር አዘምማ፣ ማህበረሰብ ታሞ እንዴትም ብናስብ ትክክሎች አንሆንም:: የሀሳባችን መነሻና መድረሻ ሀገርና ሕዝብ ሊሆን ይገባል:: በሀሳባችን ሀገር ካልሰራን፣ ትውልድ ካልቀረጽን አደራ በሎች ነን:: በዘመናት ሂደት ውስጥ ብዙ አደራ በል ተፈጥረዋል:: ሀገራችን በዚህ ልክ አዝማና ኋላ ቀር ሆና የሰነበተችው እውነተኛ በሚመስሉት ሀሰተኞች ነው::
ሀገርን ለመታደግ መጀመሪያ የችግሩ ሁሉ ምንጭ የሆነውን ራሳችንን መግራት አለብን:: ኢትዮጵያን እያስጨነቃት ያለው የራሳችን ሀሳብ ነው:: ከሰላም ተኳርፈን በተጨማደደ ፖለቲካ የተጨማደደ አስተሳሰብ በማራመድ ቀና ማለት የተሳናት ሀገር ለመፍጠር ብዙ ርቀት ተጉዘናል::
የሰላም ሀሳብ ያስፈልገናል:: ከተቻለ ተነጋግሮ ከመገባባትን ባህል እናድርግ፤ ካልተቻለ ግን አለመግባባቶቻችን ወደ ጦርነት እንዳይወስዱን መንገድ መዝጋት ከሁላችንም የሚጠበቅ ጉዳይ ነው:: የሀገራችን አብዛኛው ታሪክ የጦርነት ታሪክ ነው:: ጀግኖቻችን ዛሬም ድረስ የሚወደሱት ጦር ሜዳ ላይ በፈጸሙት ጀብድ ነው::
አሁን ገለን ጀግና የምንሆንበት ሳይሆን ምረንና ይቅርታ አድርገን ጀግና የምንሆንበት ነው:: አሁን ጊዜው በይዋጣልን እልፍ ብኩርናን የምንሽትበት ሳይሆን በሰላም ሀሳብ ወደ አንድነት በመምጣት ጀብድ የምንሰራበት ነው:: የዓለምን የጦርነት ጀብድ ለአፍታ መለስ ብለን ብንቃኝ ምናልባትም ብዙ መቶ አመታትን ያስቆጠሩ የጦር ጀግኖችን ብንቆጥር ነው:: እነናፖሊዮን፣ እነታላቁ ስክንድር . . . ጀግንነታቸው የብዙ መቶ አመት ነው::
በዚህ ዘመን ገሎ የተዋረደ እንጂ ገሎ የከበረና አንቱታን ያገኘ ጀግና የለም:: በዚህ ዘመን ገሎ ፈሪ የሚባል እንጂ ብርቱ የተባለ የለም:: ጊዜው በሰላም ሀሳብ ጀግና የሚኮንበት እንጂ ገለው የሞቱ ወይም ደግሞ በወንድማማች ጦርነት ብርቱ የሆኑ ሀያላኖችን እያወደሱ የሚኖርበት አይደለም::
ሞቶ ጀግና የሆነ እየሱስ ብቻ ነው:: ዓለም እንደ እየሱስ ጀግና የላትም:: ብዙዎቻችን ጀግና የተባልነው ገለን ስለሞትን ነው:: እየሱስ ግን ሞቶ ነው ያሸነፈው:: እየሱስ ሁሉን የማድረግ ስልጣን እያለው ግን በሰላቾቹ ፊት ዝቅታን መረጠ:: ፍቅር እንዲህ ነው በሚጠሉን ክፉ ልቦች ውስጥ ገብተን ንጽህናን መዝራት ነው:: በጥላቻ በተሞሉ እኩይ ሰውነቶች ውስጥ የሰላም ዜማ ማቀንቀን ነው::
እንደ ሀገር ከምንምነት መውጫ ቀዳዳችን የሰላም ሀሳብ ብቻ ነው:: በብሔርና በዘረኝነት የቀመቀምነውን አዳፋ ጥብቆ የሚሽር የአንድነትና የወንድማማችነት ሸማ ተጎናጽፈን ቀጣዩን ጊዜ በአብሮነት መቀበል ይኖርብናል:: ሰውነት መነሻና መድረሻው ሀገር ነው:: ሰው ያለ ሀገር፣ ሀገርም ያለ ሰው ምንም ናቸው:: ይሄ በዓለም ላይ የተጻፈ የሰው ልጅ ሁሉ የጋራ እውነትና እምነት ነው::
ሁሉም የሰው ልጅ እውነቶች ከሀገርና ሕዝብ ቀጥለው የሚመጡ ናቸው:: የአንድ ሀገር ሉዓላዊነት የሚለካው በሕዝቦቿ የአንድነትና የመተማመን መንፈስ ነው:: ሕዝቦች በጋራ ጉዳያቸው ላይ አንድ አይነት ሀሳብና አመለካከትን ካላዳበሩ ጠንካራ ሀገርና ትውልድ መፍጠር አይቻላቸውም:: ጠንካራ ሀገርና ሕዝብ መፈጠሪያቸው ጠንካራ አንድነት ውስጥ ነው:: ጠንካራ አንድነት ደግሞ ዝም ብሎ አይመጣም::
ጠንካራ አንድነት እንዲመጣ ሕዝቦች ልዩነቶቻቸውን በውይይት መፍታት ይጠበቅባቸዋል:: ተነጋግሮ መግባባትን ልማድ ማድረግ ግድ ይላቸዋል:: በጋራ ጉዳያቸው ላይ የጋራ ህልምና ራዕይ ሊኖራቸው ይገባል:: ይህ ባልሆነበት ሁኔታ የሚፈጠር ጠንካራ ሀገር አይኖርም:: የምዕራባውያን የስልጣኔ ታሪክ መነሻው አንድ ሀገርና ሕዝብ ነው:: ዛሬ ላይ ከራሳቸው አልፈው በሁሉ ነገራቸው ተጽዕኗቸውን እያሳረፉ ያሉ ሀገራት ይህን የሀይል ክንድ ያገኙት ተባብሮ በመስራት፣ ተባብሮ በማሰብ፣ ተባብሮ በመቆም ነው::
ሁሉም መንግስት፣ ሁሉም ዜጋ ከሀገሩ የሚጠብቀው ነገር አለ:: ግን ደግሞ የትኛውም ግለሰባዊ ፍላጎት ከሀገርና ሕዝብ አይበልጥም:: አሁን ላይ ሀገር ለመፍጠር በምንሮጠው ሩጫ ያልተረዳነው አንድ ነገር ቢኖር ይህ ነው እላለሁ:: የምንሮጠው ከፍላጎቶቻችን ጋር ነው:: ሁሉ ነገራችንን ለሀገራችን ሰጥተን በታማኝነት ስንታገል አንታይም::
ሀገር ትቅደም እኔ ልከተል ስንል አንደመጥም:: የዜጎች ግለሰባዊ ፍላጎቶች ከሀገር መፈጠር በኋላ የሚፈጠሩ ናቸው:: ሀገር ሳንፈጥር፣ ተነጋግረን ሳንግባባ የምንፈጥረው ግለሰባዊ ፍላጎት የለም:: አሁን ላይ ችግር እየሆነ ያለው ከሀገር በፊት ፍላጎቶቻችንን ማስቀደማችን ነው:: ያለፉትን አመታት የጦርነትና የመገፋፋት ታሪኮች መለስ ብለን ብናይ በፍላጎቶቻችን በኩል የመጡ ሆነው እናገኛቸዋለን:: የግል ፍላጎት ከሀገር ፍላጎት ሲቀድም አደጋ አለው:: ሀገር ከፍላጎት ሲቀድም ግን ጥያቄዎቻችን መልስ የሚያገኙበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም::
አሁን ላይ ሀገራችን ባላት አቅም፣ ባላት የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ ምህዳር የእያንዳንዳችንን ፍላጎት የመመለስ አቅም የላትም:: መጀመሪያ ተነጋግረን እንግባባ:: በአንድ ሀሳብ አንድ ሀገር መፍጠርን እንልመድ:: ከዛ ሁሉም ነገር በራሱ ጊዜ መስተካከል ይጀምራል:: ሀገራችንም የእያንዳንዳችንን የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ ችግሮቻችንን የመፍታት አቅም ታዳብራለች::
የሀገር ጉዳይ ሁሌም ከፊት ነው:: ከየትኛውም የግል ጉዳያችን ጋር ሊስተካከል አይገባም:: ከፍ ብዬ እንደገለፅኩት በኢኮኖሚያቸውና በስልጣኔአቸው ከፊት የቀደሙ ሀገራት ለልዕልና ያበቃቸው አንድ ምስጢር ቢኖር ለጋራ ጥቅም በጋራ መስራታቸው ነው:: እኛም በጋራ በማሰብ፣ በጋራ በመስራት ያጣናቸውን መልካም እድሎቻችንን መመለስ እንችላለን።
ብዙ ጥያቄዎች አሉን፤ እንዲስተካከሉ የምንፈልጋቸው ብዙ ነገሮች አሉ። እነዚህ ጥያቄዎች፣ እነዚህ ፍላጎቶቻችን መልስ የሚያገኙት የጋራ የሆነ ህልምና ሀሳብ ሲኖረን ነው:: ፍላጎቶቻችንን ወደ ጎን ብለን ጠንካራ ሀገርና ሕዝብ መፍጠሩ ላይ ብንበረታ ኖሮ ዛሬ ላይ እነዚያ ሁሉ ጥያቄዎቻችን ባልኖሩ ነበር::
ከእኔነት ወጥተን ከሁሉ በፊት ለሀገርና ሕዝብ ብንለፋ ሀገራችን ለእኛ ፍላጎት መልስ ታጣለች ብዬ አላስብም:: አብዛኞቹ የዓለም ሀገራት ታሪኮቻቸውን የገነቡት ከፍላጎታቸው ቀጥለው ነው:: አብዛኞቹ የዓለም ስልጡን ሀገራት ሕዝባቸውን አርነት ያወጡት ፍላጎታቸውንን ችላ ብለው ነው:: ሀገር ጠንካራ በፅኑ መሰረት ላይ እንድትቆም ሕዝቦች ልዩነታቸውን፣ ፍላጎታቸውን፣ ጥያቄዎቻቸውን ለአፍታ ወደ ጎን ብለው ሀገራዊ ጉዳይ ላይ ማተኮር አለባቸው የሚለው ሀሳብ ሚዛን የሚደፋ ሆኖ እናገኘዋለን::
የፍላጎት ጉዳይ የእኛን ሀገር አሁናዊ ሁኔታ በደንብ ይገልጸዋል ብዬ አስባለሁ:: ከትላንት እስከዛሬ በዚህ እውነት ውስጥ የተጓዝን ነን:: ሀገር ከመፍጠር ይልቅ ራሳችንን ለመፍጠር የምንታትር ነን:: ከሀገር የቀደመ እንጂ ከሀገር የቀጠለ ምንም ነገር ሳይኖረን እስካሁን ከርመናል::
ግለሰባዊና ቡድናዊ ፍላጎቶች ከሀገር ፍላጎቶች በላይ ዋጋ ያላቸው ቢሆኑ ኖሮ ከየትኛውም ሀገርና ሕዝብ በላይ እኛ ነበር የምንጠቀመው:: ግን እውነታው ከዛ የራቀ ነው:: ከሀገር የቀደመ ግለሰባዊም ሆነ ቡድናዊ ፍላጎት ሀገር የሚያኮስስ፣ ልማት የሚያቀነጭር ነቀርሳ ነው::
ሁሉን ትተን ወደ ሰላም እንይ:: የተደበቁብን በረከቶቻችን ከሰላም በኋላ የሚገለጡ ናቸው:: እንደ ሀገር ልማታችን፣ ብልጽግናችን በጥላቻ ደመና የተከለለ ነው:: ብርሀን እንዲወጣልን ወደ ምስራቅ እንይ:: ወደ ሰላም አድማስ እናንጋጣ:: ያኔ በጽልመት ቁር የተደበቀችውን፤ አንደርስ ያልንባትን ኢትዮጵያ እንደርስባታለን::
ሰላም የምንም ነገር መሰረት ነው:: ያለፉትን የጦርነት ጊዜአቶች አሁን ካለው የሰላም መንፈስ ጋር በማነጻጸር የሰላምን ዋጋ መረዳት እንችላለን:: በርዕሴ እንዳነሳሁት ጥላቻ ወለድ ቀዳዳዎቻችን በሰላም ወስፌ የሚጣፉበት ጊዜ ላይ ነን:: ከሰላም ውጭ ሁሉም ነገር ደርሶናል:: ሁሉንም ነገር ከበቂ በላይ አይተነዋል::
ሁላችንም ወደ ራሳችን ማየት ትተን ወደ ሀገራችንና ወደ ሕዝባችን ማየት ይኖርብናል:: ከፍላጎቶቻችንን የሚቀድሙ በርካታ ሀገራዊ ጉዳዮች አሉ:: ለነዛ የጋራ ጉዳዮቻችን ቅድሚያ በመስጠት መንቀሳቀስ ነው ቀዳዳዎቻችንን የሚጠግንልን:: የለያዩንን ነገሮች በባህላዊና በሳይንሳዊ መንገድ እየፈተሽን ከፍላጎቶቻችን በላይ የሆነች ኢትዮጵያን መፍጠር ይጠበቅብናል::
ሀገር የነፍስ ቦታ ናት:: ሀገር በልባችን ውስጥ እንደምንሰማት የህላዌ ትር ትር የመኖራችን ዋስትና ናት:: ሀገር የስሜት፣ የፍላጎት፣ የህልሞች ሁሉ ቀዳሚ ናት:: ቅድሚያ ለሚሰጠው ቅድሚያ እየሰጠን መጓዝ እንጂ በተፋለሰ ቅደም ተከተል የምንፈጥረው የጋራ ህልም አይኖርም:: መጀመሪያ ለሀገራችን እንልፋ:: ከዛ ሀገራችን ለእኛ ትለፋለች::
ብሔራዊ ምክክሩ ሀገር በመፍጠር ረገድ የጎላ ድርሻ አለው:: እንደ ሀገር እንደ ዜጋ የሚያስፈልገንን ማወቅ አለብን:: ላለፉት ብዙ አመታቶች በማይጠቅሙን ነገሮች ላይ ጊዜና ጉልበታችንን ስናባክን ነበር:: አሁን የተሻለ ነገር የምናይበት፣ የበለጠ ነገር የምንሰማበት እንዲሆን ሁላችንም አእምሮና ልባችንን ማደስ ይኖርብናል:: በትላንቱ ቦታ ላይ እንደ ትላንቱ የምናስብበት ጊዜ ላይ አይደለንም::
ሀገራችን አዲስ አስተሳሰብ፣ አዲስ ልብና መንፈስ ያስፈልጋታል:: ትውልዱ ፍቅርና ይቅርታ የዋጀው ነፍስና ስጋ ይፈልጋል:: ሰላምና መቻቻልን መሰረት ባደረገ ሕዝባዊ ምክክር ሀገር ልንፈጥር ዝግጅት ላይ ነን:: በዚህ ብሔራዊ ምክክር ላይ እንደ ዜጋ፣ እንደ መንግስት፣ እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ከእያንዳንዳችን በሀገር አሻጋሪ የተቃኘ ሀሳብ ያስፈልጋል::
ይሄ ሀገራዊ ምክክር ፍላጎቶቻችንን ገለን ለጋራ ጥቅም በጋራ የምንሰራበት ነው:: ሀገራችንን አስቀድመን እኛ የምንከተልበት ሕዝባዊ ንቅናቄ ነው:: ከዚህ አለፍ ባለ ሁኔታም ከፊታችን የሽግግር ፍትህ ትግበራ እየመጣ ነው:: ይህን በመሰለው የፍትህና የተጠያቂነት መንፈስ ጥላቻ የቀደዳቸው፣ ዘረኝነት ያወደማቸው፣ ጦርነትና እኔነት ያወየባቸው አዳፋ መልኮቻችን በተጠያቂነት እንደሚጸዱ እናምናለን::
የመታደስ ጊዜ ላይ ነን:: የምንታደሰው ደግሞ በሀሳብ የበላይነት እንጂ የተረሱ ትርክቶችን በማስታወስ፣ የመቶ አመት ታሪክ በመቁጠር አይደለም:: የምንታደሰው በደልን በመርሳት፣ ምህረትን በማድረግ ነው:: ትላንትን የሚረሳ፣ ዛሬን የሚያወድስ ልብ ያስፈልገናል:: በዚህ ሀገራዊ ምክክር ላይ ባህላዊ የሽምግልና ስርዓቶቻችን ዋጋ አላቸው ብዬ አምናለሁ::
እነዚህን ባህላዊ ስርዓቶች በመመለስና በማጠናከር ያጣናቸውን ሀገራዊ በረከቶች መመለስ ይቻላል:: እንዲሁም ደግሞ ከባህላዊ ስርዓት አባቶቻችንን፣ ከዘመናዊው ደግሞ በእርቅ ኮሚሽን በኩል ልምድ ያላቸውን በማከል ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም መንገድ ጠራጊ ሀሳቦችን ማዋጣት እንችላለን:: ብሔራዊ እርቅ ለብሔራዊ ሰላም ዋስትና ነው:: ብሔራዊ ተግባቦት ለብሔራዊ አንድነት ዋልታና ማገር ነው:: ያጣናቸው መልካም ነገሮች ሁሉ ይህን ሀገራዊ ምክክር ተከትለው እንደሚመጡ ተስፋ ማድረግ ቀዳዳዎቻችንን ለመድፈን መሰናዳት ይኖርብናል::
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 14 ቀን 2015 ዓ.ም