የሰው ልጅ እንደ መጽሐፍ ተገልጾ የማያልቅ ድንቅ ፍጥረት ነው የሚባለው ያለ ምክንያት አይደለም:: በእርግጥም ሰው ተገልጾ አያልቅም:: የሰው ልጅ ማንነት በተለያየ መልኩ ሊታይ የሚችል የሚመነዘር እና በተለያየ መንገድ የሚዘረዘር ነው:: የሰውን ልጅ ማንነት ከቀይ ሽንኩርት ጋር የሚያመሳስለም አሉ::
ቀይ ሽንኩርት ተደራርቦ የተፈጠረ ነው፤ አንዱ ከአንዱ ጋር የማይገናኝ ነው:: የተለያየው ተደራርቦ ሲጠቀለል ሽንኩርት ይሆናል:: የሰው ልጅም እንዲሁ እንደ ሽንኩርት ተደራርበው በተፈጠሩ የተለያዩ ማንነቶች የተገነባ ነው:: አንደኛው ማንነት በሃይማኖቱ ላይ፤ ሌላኛው ማንነት ደግሞ በብሔሩ ላይ የተገነባ ነው:: የት አካባቢ ተወለደ? ወይም የት እንዳደገ? እንዲሁም የኖረበት አካባቢን በመግለጽ ጆኦግራፊያዊ ማንነቱን ማንሳት ይቻላል:: በሌላ በኩል የትምህርት ሁኔታው፣ የሚሠራው ሥራ እና ሌሎችም ብዙ ጉዳዮች የማንነቱ መገለጫዎች ናቸው::
ሰው አንተ ማን ነህ? ሲባል ከመለያ ስሙ ጀምሮ ብሔሩን፣ ሃይማኖቱን፣ የተማረበትን አካባቢ፣ ሙያውን፣ ሰፈሩን፣ ሌሎችም ከሌሎች የሚለዩትን እና ከአንዳንዶች ጋር የሚገናኘውን ጉዳይ በሙሉ መዘርዘር ይችላል:: ይህ ሆኖ እያለ ታዲያ በኢትዮጵያ ለምን የሰው ልጅ ማንነት በአንድ ጉዳይ ላይ ይወሰናል?
በሐረሪ እንዲሁም በሶማሌ ክልል አካባቢ እግርን ደራርቦ ተቀምጦ የጫማ ሶልን ማሳየት ትልቅ ድፍረት እና ስድብ ነው:: ይህ ብቻ አይደለም፤ ጫማን አጥልቆ ማስጠረግ እጅግ ፅዩፍ ተግባር ነው:: ይህ የተለየ የዛ አካባቢ ማህበረሰብ ባህል ነው:: ሐረር የኖረ ሰው ይህንን ጠንቅቆ ያውቃል::
ያ ሕዝብ ነውር የሚለውን ነገር በተቃራኒው ወደ ሌላ አካባቢ ብንወስደው ለሶማሌ ክልል ሕዝብ ነውር የሆነው ለሌላው ሕዝብ ምንም ማለት ላይሆን ይችላል:: ይህንን ከብሔር ወይም ከአንድ አካባቢ ሕዝብ ባህል ጋር የተያያዘ እንደሆነ ማሰብ ተገቢ ነው:: ለዛ ሕዝብ ይህ አንድ የማንነቱ አካል ነው::
የአንድ ሰው ማንነት በብሔር ውስጥ ሲገለጽ ከቋንቋው ጀምሮ አበላሉ፤ የሚኖርበት ሁኔታ፤ የኢኮኖሚ መስተጋብሩ፤ ደስታ እና ሐዘኑን የሚገልፅበት መንገድ፤ ጭፈራው እና የቀን አቆጣጠሩ እንዲሁም ብዙ የእርሱ ብሔር መገለጫ የሆኑ ነገሮችን መጥቀስ ይቻላል:: ነገር ግን የሰው ልጅ ማንነት ብሔር ላይ ብቻ የተመሠረተ አይደለም::
በሃይማኖት በኩል ያለውን ለማየት ብንሞከር፤ አንዱ ሃይማኖት የሚያመልክበትን መንገድ ሌላው ላይቀበለው የሚችልበት ሁኔታ ያጋጥማል:: ለአንዱ ጣኦት ተደርጎ የሚወሰድ ለሌላው እጅግ የተገባ የአምልኮ ሥርዓት ነው:: ምንም እንኳ ብዙ ሃይማኖቶችን የሚያቀራርብ እውነት ቢኖርም በአንዱ ሃይማኖት ውስጥ የሚፈፀመው በሌላ ሃይማኖት ውስጥ የማይፈፀሙ እና የሃይማኖቱ መለያዎች የዛ ሃይማኖት ተከታይ የማንነት መገለጫዎች ናቸው::
ለአንድ ሰው ትውልድ የማንነቱ መገለጫው ይሆናል:: የእዚህ ዘመን ትውልድ ለቴክኖሎጂ ካለው ቀረቤታ አንፃር እንኳ የተለየ ግንኙነት እንዳለው በማየት እንደመገለጫው መውሰድ ይቻላል:: የስልሳዎቹ ትውልድ ሰው በዛ ወቅት ከነበረው ሁኔታ አንፃር የተለየ ማንነት አለው:: የሰማኒያዎቹም በተመሳሳይ መልኩ ማንነቱ በዛ ትውልድ ላይ የተመሠረተ ነው:: በተመሳሳይ መልኩ የሁለተኛው ሺ ልንለው የምንችለው ይህንንም ዘመን አጠቃልሎ የያዘው ትውልድም የራሱ መለያ ማንነት አለው::
ከጆኦግራፊ አንፃር ለማንሳት ሲሞከርም ሃይማኖቱ የተለያየ ቢሆንም፤ በርሃ አካባቢ የኖረ ሰው ምንም እንኳ ብሔሩ በበረሃው አካባቢ በአብዛኛው ከሚኖረው ሰው የተለየ ቢሆንም በዛ አካባቢ በመኖሩ ብቻ ከአካባቢው ማህበረሰብ የሚጋራቸው የተለያዩ አስተሳሰቦች ይኖራሉ:: ይህ በራሱ አንዱ የማንነት መገለጫው ነው::
በትምህርት አካባቢም ለመጥቀስ ያህል በጂግጂጋ ዩኒቨርሲቲ የተማረው ሰው፣ ሐዋሳ፣ ወልቂጤ፣ አርባ ምንጭ ወይም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተማረው ሰው በተለያየ መልኩ አስተሳሰቡ የሚለይበት ሁኔታ አለ:: የትምህርት አካባቢ ብቻ ሳይሆን የሥራ አካባቢ በራሱ ማንነትን የሚገነባ ነው:: በአንድ ተቋም መስራት በአንድ ጉዳይ ላይ ተቀራራቢ ሃሳብ እንዲኖር የሚያስገድድ ነው፤ በአንድ ተቋም እና በአንድ አካባቢ የሚሠራ ሰው የሙያውን ዓይነት ጨምሮ የተለየ ማንነትን የሚይዝበት ሁኔታ አለ::
በሌላ በኩል በዓለም ደረጃ ከሚጠቀሱ ማንነቶች መካከል አንደኛው የጾታ ማንነት ነው:: የጾታ ማንነት በግልፅ እንደሚታወቀው ከሴትነት እና ከወንድነት ጋር የተሣሠረ ሲሆን፤ ወንዱን ሴት፤ ሴቷንም ወንድ ማለት አይቻልም:: በየራሳቸው ሁለቱም አካላት የራሳቸው ማንነቶች አሏቸው:: ሴት መሆን ወንድ ከመሆን በእጅጉ የተለየ ነው:: ይህ በራሱ የማንነት አንዱ መገለጫ ነው::
የኢኮኖሚ አቅም ጉዳይም እንዲሁ አንድ የማንነት አካል ስለመሆኑ ይገለፃል:: በኢኮኖሚ ደረጃ ዝቅተኛ፣ መካከለኛ እና ከፍተኛ ተብለው ተከፋፍለው የሚቀመጡት ደረጃዎችም እንዲሁ የማንነት መለኪያዎች ናቸው:: የኢኮኖሚ መለኪያዎች ብቻ ሳይሆኑ የዕውቀት ደረጃቸውም በተመሳሳይ መልኩ የማንነት መገለጫ ሆነው የሚቀርቡበት ሁኔታም አለ::
የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች እና የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪዎች በአንድ ጉዳይ ላይ የሚኖራቸው አስተያየት የተለያየ ሊሆን እንደሚችል እሙን ነው:: የታሪክ፣ የሳይኮሎጂ፣ የሶሾሎጂ ተማሪዎች፤ ከሒሳብ ባለሙያ ሃሳባቸው በእጅጉ የራቀ ሊሆን እንደሚችል እሙን ነው:: እንዲህ እያልን እንዘርዝር ካልን የሰው ልጅ በብዙ መልኩ የተለያዩ ማንነቶች አሉት::
ምንም እንኳ ብዙ ምሁራኖች የሚስማሙበት የብሔር፣ የሃይማኖት፣ የሙያ ፣ የባህል እና የፆታ ማንነቶች ተጠቃሽ ቢሆኑም ከላይ እንደተዘረዘሩት ዓይነት ማንነቶች በእያንዳንዱ ዜጋ ውስጥ አሉ:: ታዲያ ይህ ሁሉ የተለያየ ማንነት እያለ ለምን በአንዱ ላይ ብቻ ማተኮር አስፈለገ የሚለው አጠያያቂ ጉዳይ ነው::
በእርግጥም ማንነት በእጅጉ መከበር አለበት:: በደንብ ተረጋግጦ መታወቅ ያለበት እና ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያሻው በፍፁም አንዱ በሌላው ማንነት ላይ መቀለድም ሆነ ማሾፍ አይችልም:: በማንነት ላይ ማሾፍ ወይም የሰዎችን ማንነት ማጥላላት እና ዝቅ ለማድረግ መሞከር አደጋው የሰፋ እና የከፋ ሊሆን እንደሚችል ነጋሪ አያሻም::
በተለይ እንደ ኢትዮጵያውያን ባሉ እጅግ እልኸኛ በሆነ ሕዝብ ውስጥ ማንነት ላይ ማሾፍ ትልቅ ዋጋን የሚያስከፍል በመሆኑ መጠንቀቅ ተገቢ ነው:: ይህ እንዳለ ሆኖ ስለማንነት ሲነሳ አንድ ጉዳይ ላይ ብቻ ማተኮር ይብቃ! አንድ የብሔር ማንነት ብቻ ሳይሆን ሁሉም ማንነቶች መከበር አለባቸው! በተረፈ ሌሎቹ ጉዳዮች ተከትለው የሚመጡ በመሆናቸው ብዙ አሳሳቢ አይደሉምና ስለሌሎቹም ማንነቶች እናስተውል፤ እናስብ እንጨነቅ:: ሰላም!
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ምሕረት ሞገስ
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 14 ቀን 2015 ዓ.ም