(ክፍል ፩)
እውነት ለመናገር ከለውጡ በፊት በነበሩ 27 ዓመታት የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂም ሆነ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እንደ ቅንጦትና ስጋት ይታይ ስለነበር ተገቢውን ትኩረት ሳያገኝ ቆይቷል። እንደ ሀገር ከሩብ ክፍለ ዘመን በላይ በራችንን ዘግተን ለሽ ብለን አሳልፈነዋል። በጎረቤት ሀገር ኬኒያም ሆነ በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ዘርፉ ያስመዘገበውን እምርታ ስንመለከት ምን ያህል ኋላ እንደቀረን እንረዳለን።
በአለፉት አራት ዓመታት ከእነ ውስንነቶቹ አበረታች ለውጥ እየታየ ነው ። የበይነ መረብ መስፋፋት፤ ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ የሚደረግ ሽግግር፤ ጥራቱና ተደራሽነቱ ላይ ዛሬም ውስንነት ያለበት ቢሆንም ኔትወርኩ 4ኛና 5ኛ ትውልድ ላይ መድረሱ ፤ የሞባይል ባንኪንግ መስፋፋት፤ ወዘተረፈ ይበል የሚያሰኝ ነው። ሰው ሠራሽ አስተውሎት AI (Artificial Intelligence) ትኩረት ተሰጥቶት በኢንስትቲዩት ደረጃ መቋቋሙና እየተሠሩ ያሉ ተስፋ ሰጭ ሥራዎች ዛሬ እሱ ላይ እንዳተኩር አድርጎኛል ።
የኢንዱስትሪ አብዮት በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጨረሻ ተጀምሮ በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተጠናክሮ የቀጠለ ወሳኝ የቴክኖሎጂና የኢኮኖሚ እምርታ ነው። አዳዲስ ፋብሪካዎች የተፈጠሩበት፣ የእንፋሎት ኃይል በስፋት ጥቅም ላይ የዋለበት፣ ማሽኖች ወደ ሥራ የገቡበት፣ ምርትና ምርታማነት የጨመረበት እና ከተሞች የተስፋፉበትና ዛሬ የምንገኝበት ዓለም የተበየነበት ታላቅ ክስተት ነው።
በሰው ልጆች ታሪክ ሦስት የኢንዱስትሪ አብዮቶች የተካሄዱ ሲሆን አራተኛውን ደግሞ ተያይዘነዋል። ሁሉም የየራሳቸውን አዳዲስ የፈጠራና ኢኮኖሚያዊ ማዕበል አስነስተዋል። የመጀመሪያው የኢንዱስትሪ አብዮት ችቦ በእንግሊዝ ተለኩሶ ወደ አውሮፓና ሰሜን አሜሪካ የተቀጣጠለ ሲሆን የዘመነ ፋብሪካና የእንፋሎት ኃይል መለያው ናቸው። ሁለተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት በ19ኛው መክዘ መገባደጃ ተጀምሮ እስከ 20ኛው መክዘ መጀመሪያ የቀጠለ ሲሆን እንደ መኪናና አውሮፕላን ያሉ መጓጓዣዎች፤ የኤሌክትሪክ ኃይልና የኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂዎች በስፋት ጥቅም ላይ የዋሉበት ነው ።
ሦስተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት ከ20ኛው መክዘ አጋማሽ ዛሬ ድረስ የቀጠለው ሲሆን የዲጂታል ቴክኖሎጂ በይነ መረብ ወይም ኢንተርኔት፣ አውቶሜሽን፣ ሮቦቲክስና ሌሎች ቴክኖሎጂዎች የተስፋፉበትና በስፋት ጥቅም ላይ የዋሉበት ነው። ብዙ ሊቃውንት አሁን የምንገኝበትን ጊዜ የአራተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት የተጀመረበት፤ የዲጂታል ቴክኖሎጂ የተቀናጀበት ፣ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ወደ ሥራ የገባበት፣ በይነ መረብ እያንዳንዱን የሕይወት ቅንጣትና የኢኮኖሚ ዘርፍ ማዳረስ የጀመረበት ከመሆኑ ባሻገር በአኗኗራችንና በግንኙነታችን ላይ የዝሆን ዳናውን እየተው ያለ ምዕራፍ ነው።
እጃችን የገባን ቴክኖሎጂ ተለማምደነውና ተዋውቀነው ሳናበቃ እጃችን ላይ የሚያረጅበትና በፍጥነት የሚለዋወጥበት ዘመን ነው። የዛሬ መጣጥፌ ትኩረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት ወይም AI (Artificial Intelligence)እሱ ላይ ያዝ አደርጋለሁ ። ለብዙዎቻችን የሰው ሰራሽ አስተውሎት አዲስ ግኝትና ቴክኖሎጂያዊ እመርታ የቅርብ ጊዜ ክስተት ቢመስለንም የዘርፉ ልሒቃን ግን ጥንስሱ ጥንታዊ ነው ሲሉ ሐተታ ተፈጥሮንና ሥነ ቃልን በዋቢነት ያወሳሉ።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ተስፋም ስጋትም ይዞ ወደፊት እየመጣ ያለው ሰው ሠራሽ አስተውሎት ግን የተጀመረው በ20ኛው መክዘ አጋማሽ ሲሆን የኮምፒውተር ሊቃውንት ስልተ ቀመር ወይም አልጎሪዝምና አስበው የሚሠሩ ማሽኖች ወደ ሥራ እየገቡበት ያለ ጊዜ ነው ። በ1943 ዓም ዋረን ማክኩሎችና ዋልተር ፒትስ በጋራ በነርቭ አውታረ መረብ የሚታገዝ ሒሳባዊ ሞዴል ወይም mathematical model of neural መፍጠራቸው ለዛሬው ሰው ሠራሽ አስተውሎት እርሾ ሆኖ አገልግሏል። በ1950 ዓ.ም አለን ተርኒግ እንደ ሰው ማሰብ የሚችል ማሽን ፈልስፎ ሙከራ አደረገ ።
በ1950ዎቹና 60ዎቹ General Problem Solver (GPS)እና ሎጂክ ቴዎሪስትን ጨምሮ በርከት ያሉ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ፕሮግራሞች በለጸጉ። በ1956 ዓም የዳርትማውዝ ጉባኤ “ሰው ሠራሽ አስተውሎት” ራሱን ችሎ እንዲጠና ከመወሰኑ ባሻገር ዛሬ የምንጠቀምበትን ይሄን መጠሪያውን አገኘ። በዚሁ ጉባኤ የተሳተፉ የዘርፉ ሊቃውንት AI ውስብስብ ችግሮችን የመፍታት አቅም እንዳለው ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ አደረጉ። በ1970ዎቹና 80ዎቹ በAI(Artificial Intelligence) ዘርፍ የሰውን ልጅ የመወሰን አቅም የሚተካከል የኮምፒውተር ፕሮግራም ለማበልጸግ ርብርብ ይደረግ ነበር። ዳሩ ግን በ1990ዎቹ የሚፈለገውን ያህል ውጤታማ ባለመሆኑ ምርምሮቹ መቀዛቀዝ ጀምረው ነበር። በ21ኛው መክዘ ደግሞ እንደገና ማንሰራራት ጀመረ ።
ከዚህ በኋላ ነጮች እንደሚሉት የተቀረው ታሪክ ነው። ሰውን ተክተው የሚሠሩ፣ ስልተ ቀመርን algorithm የሚረዱ ማሽኖች ሥራ ላይ መዋል ጀመሩ። በርካታ መረጃዎችን አብላልተው የሚሠሩ ከፍተኛ አቅም ያላቸው ኮምፒውተሮች ወደ ሥራ መግባታቸው ዘርፉን ያጎለብተው ጀመር። አሁን አሁን AI የማይገባበት የሕይወት ቅንጣት የለም። በጤናችን፣ በማኅበራዊ ሚዲያ አጠቃቀማችን፣ በመረጃ አፈላለጋችን፣ በፖለቲካችን፣ በትምህርታችን፣ በኢኮኖሚያችን፣ በምርምራችን፣ በግብርናችን፣ በማዕድን ፍለጋና ልማታችን፣ በአገልግሎት አሰጣጣችን፣ ወዘተረፈ እሱ በዚያ አለ። ለሰው ልጅ በርካታ ትሩፋት ይዞ የመጣ ቢሆንም ስጋት መደቀኑ አልቀረም ።
የሰው ሠራሽ ክህሎት በዚህ ከቀጠለና ያለ ሰዎች ጣልቃ ገብነትና ተሳትፎ ራሱን ችሎ መንቀሳቀስ ከጀመረ የሰውን ልጅ ከምድረ ገጽ ሊያጠፋ ይችላል የሚል ስጋት እየፈጠረ ነው። የArtficial Intelligence AI ጉዳይ ብርቱ ጥንቃቄ ይጠይቃል ይሉናል በጎግል የሰው ሠራሽ ክህሎት ቤተ ሙከራ የዲፕማይንድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዴሚስ ሀሳቢስ። ብዙዎቹ በAI ላይ ሙከራ እያደረጉ ያሉ ተመራማሪዎች እጃቸው ውስጥ የገባው ቴክኖሎጂ እጅግ አደገኛ መሆኑን በቅጡ የተገነዘቡ አይመስሉም ይላሉ ዋና ሥራ አስፈጻሚው። በዘረ አዳም ሕልውና ላይ አደጋ ስለደቀነው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ከተለያዩ ምንጮች ያጠናቀርሁትን መረጃ እንዲህ ላጋራችሁ ወደድሁ ።
Artficial Intelligence ወይም AI ግስጋሴ በሰው ልጆች ሕልውና ላይ የደቀነው አደጋ፤ ክፉኛ ያሳሰባቸውና ያስጨነቃቸው ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ለ6 ወር እንዲቆም በግልጽ ደብዳቤ መጠየቃቸው ሰሞነኛ መነጋገሪ ሆኗል። ኤለን መስክን ጨምሮ የAI አባቶች በመባል የሚታወቁ ከ1100 በላይ የዘርፉ ጉምቱ ሊቃውንት በፉክክርና በውድድር፤ እየተለቀቁ ያሉ የAI ግኝቶች በዚሁ ከቀጠሉ በሰብዓዊ ፍጡር ላይ አደጋ ሊደቅኑ ስለሚችሉ እንዲቆሙ መንግሥትንም ኩባንያዎችንም ተማጽነዋል።
ተማጽኖው የመጣው ጉግልና ማይክሮሶፍት ራሱን ችሎ የሚሠራ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ከለቀቁ በኋላ ነው ይለናል የእንግሊዙ ዜና አገልግሎት ሮይተርስ። በግልጽ ደብዳቤ እንዲቆም ከጠየቁት መካከል የStability AI ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኤማድ ሞስታ፤ ዮሹዋ ቤንጊዎ፣ ስቱዋርት ሩሶ፣ የአፕል መሥራች ስቲቭ ወዚናክ ሌሎች ኢንዱስትሪው ላይ የሚሠሩ ጉምቱዎች፤ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ፈጣሪዎቹን ጨምሮ ማንም ሊቆጣጠረው፣ ሊረዳውና ሊተነብየው የማይችል አደጋ በሰው ዘር ላይ ስለደቀነ እንዲቆም ተማጽነዋል። ሲቆም ደግሞ የዘርፉን ተዋናዮችን ያሳተፈ፣ ለሕዝብ ግልጽ የሚሆንና ክትትል የሚደረግበት ሊሆን ይገባል ሲሉ ያስጠነቅቃሉ።
ፈጠራ ሰዋዊ ነው። የሰው ልጅ ላለፉት 300,000 ዓመታት ከሌሎች ፍጥረታት በተለየ ኪነ ጥበባዊ ሥራዎችን፣ የምግብ አሠራር ዘዴዎችን፣ የፖለቲካ ማኒፌስቶዎችን፣ ማኅበረሰቦችን፤ ባጠቃላይ ያልነበሩ አዳዲስ ነገሮችን ፈጥሯል ይሉናል አንድሪው ቾውና ቢሊ ፔሪጎ በጋራ በTIME መጽሔት ባስነበቡን መጣጥፍ። ይሄን ተረክ እያዳመጣችሁ ባለበት በዚህ ቅጽበት እንኳ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ወይም Artificial Intelligence/AI/፤ ሰዓሊውን ተክቶ ረቂቅና ውብ ስዕሎችን እየሳለ፣ ሰዎችን ሆኖ በኢሜል መልስ እየሰጠ፣ ሙዚቀኛውን ሆኖ ሙዚቃን እየቀረጸ ነው ።
ወይም ዋና ሥራ አስፈጻሚውን ተክቶ ስለ ኩባንያው የዕቅድ አፈጻጸም ለታዳሚው ገለጻ እያደረገ ፤ አልያም በኮምፒውተር ኮድ የተፈጠረ ስህተትን ለይቶ መፍትሔ እየሰጠ፤ የሕንጻ ግንባታ ንድፍ እያዘጋጀ፤ ተማሪውን ተክቶ እየተፈተነ ፤ ጋዜጠኛውን ተክቶ መጣጥፍ እየጻፈ፤ ለሕመምተኛው የጤና ምክር እየሰጠ ሊሆን ይችላል። ምን አደከማችሁ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ያልገባበት የሕይወት ቅንጣት የለም ማለት ይቻላል። የመድኃኒትንና የቤት ዋጋን ከማውጣት አንስቶ እስከ መኪና መገጣጠምና በማኅበራዊ ሚዲያ የምንመለከተውን ማስታወቂያ እስከ መወሰን ደርሷል። በዚህ ተገርመን ሳናበቃ አዲስ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ወይም Generative AI ወደ ሥራ እየገባ ነው ይሉናል እነ አንድሪው በጹሑፋቸው ።
ይሄኛው አስተውሎት ጥራትና ጥልቀት ያለው አዲስ ጽሑፍ፣ ምስልና ድምጽ መፍጠር የሚችል ነው። አዲሱ የሰው ሠራሽ ክህሎት ወይም Generative AI ማኅበራዊ ሚዲያ ጥቅም ላይ ከዋለበት ጊዜ አንስቶ አስገራሚው ቴክኖሎጂያዊ ግኝት ወይም እምርታ ነው። የዚህ ግኝት አካል የሆነው ChatGPT የተሰኘው የድረ ገጽ ማፈላለጊያ ወይም ሰርች ኤንጅን ለምንጠይቀው ነገር ሁሉ ምላሽ መስጠት የሚችል ሰው ሠራሽ አስተውሎት ሲሆን፤ ሌላው አዲሱ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ወይም Dall-E የምናልመውንና የምንመኘውን ስዕል መሳል የሚችል ነው።
በተለይ ChatGPT ባለፈው ጥር ሥራ ላይ ከመዋሉ ከ100 ሚሊዮን በላይ ተጠቃሚዎችን በማፍራት፤ ኢንስታግራምና ቲክቶክ ይዘውት የነበረውን ክብረ ወሰን ሰብሯል ። በየቀኑ 13 ሚሊዮን ደንበኞች እየተጠቀሙበት ይገኛል። በመቶዎች የሚቆጠሩ አዳዲስ እንደ ChatGPT ያሉ የሰው ሠራሽ አስተውሎቶች ወደ ገበያው ለመግባትና ተጠቃሚዎችን ለማፍራት የሞት ሽረት ፉክክር ላይ ተጠምደዋል። ከMidjourney እስከ Stable Diffusion እና GitHub’s Copilot ውድድር ላይ ናቸው ይሉናል የመጽሔቱ ጸሐፊዎች ።
ምኑ ተነካና በዘርፉ ገና ለማመን የሚከብዱ ተዓምራትን እናያለን ይላሉ አዲሱን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ወይም Generative AI በቅርበት የሚከታተሉ ልሒቃን። እነዚህ ፈጠራዎች የምንሠራውን ሥራ አሠራርና በቀጣይ ከዓለማችን ጋር የሚኖረንን ተራክቦ በአዲስ መበየን ይጀምራሉ። በሌላ በኩል ደግሞ የሰውን ልጅ የፈጠራ ዕምቅ አቅም ያጎለብታሉ። ሳይንሳዊ ግኝትን ያበረታታሉ። የሰው ልጅ በሕልሙም ሆነ በእውኑ አሳካዋለሁ ብሎ ያላሰበውን ችሎታ ያጎናጽፋሉ ተብለው ይጠበቃል። የዓለማችንን ኢኮኖሚ በማሳደግም ከፍተኛ አስተዋፅዖ ይኖራቸዋል በሚል ተስፋ ተጥሎባቸዋል።
በ2030 ሰው ሠራሽ አስተውሎት የዓለምን ኢኮኖሚ በ15 ትሪሊየን ዶላር እንደሚያሳድገው እየተተነበየ ይገኛል። የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች በዘርፉ ያለውን ሰፊ የገበያ ዕድል በመመልከት በቢሊየኖች የሚቆጠር ዶላር ኢንቨስት እያደረጉ ነው። የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፈጠራና ጅምር ቢዝነስ startup መናኸሪያ በሆነችው የአሜሪካዋ ሲልከን ቫሊ ከተማ፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት AI ፈጠራን ለማሻሻል ወይም አዲስ ፈጠራን ለማውጣት ሌት ተቀን እየተሠራ ነው።
በሳምንታት ውስጥ ማይክሮሶፍትና የአልፋቤት ንብረት የሆነው ጉግል መጭው ዘመን የArtificial Intelligence፤ ወይም AI ነው በሚል ስትራቴጂያቸውን ከመከለስ ባሻገር ቢሊየኖችን ኢንቨስት እያደረጉ ነው ይሉናል የTIME መጽሔት ጸሐፍት። የቢል ጌቱ ማይክሮሶፍት በሰው ሠራሽ አስተውሎት ምርምር በሚያደርገውና ChatGPTን በፈጠረው OpenAI በኩል 10 ቢሊዮን ዶላር መድቧል። Dall-E በበኩሉ አዲሱን የሰው ሠራሽ አስተውሎት ማለትም Generative AI ሶፍትዌርን ከድረ ገጽ ማፈላለጊያው Bing ጋር ለማዋሐድ እየሠራ ነው።
በማይክሮሶፍት ኩባንያ በAI የታገዘ የድረ ገጽ ማሰሻ ChatGPT ስኬት መንፈሳዊ ቅናት ያደረበት ጉግል፤ “code red” በተሰኘ አስቸኳይ መርሐ ግብሩ Bard የተባለ የራሱን የድረ ገጽ ማሰሻ ወይም ማፈላለጊያ ለገበያው ይፋ አድርጓል። የማይክሮሶፍት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሳትያ ናዴላ፤ “ልንቀሳቀስ ነው። ስንቀሳቀስ ደግሞ በፍጥነት ነው። “በማለት፤ ኩባንያቸው ለሰው ሠራሽ አስተውሎት የሰጠውን ልዩ ትኩረት አስታወቁ ይሉናል አንድሪው ቾውና ቢሊ ፔሪጎ በጋራ በTIME መጽሔት በዚያ ሰሞን ባስነበቡን መጣጥፍ።
ሰው ሠራሽ አስተውሎት ላይ የሚሠሩ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ኩባንያዎች ዋጋ በኒውዮርክ የሽርክና ገበያ እየጨመረ ሲሆን፤ ባለሀብቶችና የሽርክና ገበያ ተንባዮች የGenerative AI ዋጋ እንደ ማይክሮ ሶፍቱ ዊንዶ 95 ወይም እንደ መጀመሪያው የአፕል አይፎን በፍጥነት ሊያድግ ይችላል ስላሉ ኢንቨስተሮች እየተሻሙት ነው። ተረጋግተውና ጊዜ ወስደው ሳያስቡ የወርቅ ማዕድን የተገኘ ያህል ሽርክና ለመግዛት የሚደረግ መሽቀዳደም ያልተጠበቀ መዘዝ እንዳያስከትል መሰጋቱን መጽሔቱ ይጠቁማል። ለዛሬ በዚህ ላብቃ። በመጨረሻውና ክፍል ሁለት መጣጥፌ ዓለምን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ እያነጋገረና እያወዛገበ ስላለው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ወቅታዊ መረጃዎችን አጋራችኋለሁ ።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
ቁምላቸው አበበ በአማራ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፤ በደቡብ መገናኛ ብዙኀን፤ በጋዜጠኝነትና በታሪክ ባለሙያነት ያገለገሉ ሲሆን፤ የደቡብ ኤፍ ኤምን ከባልደረቦቻቸው ጋር በመሆንም አቋቁመዋል።በፌዴራል ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅትና በአለ በጅምላ በኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተርነት አገልግለዋል። ከአአዩ በቋንቋና ታሪክ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን የሰሩ ሲሆን፤ በዚሁ ዩኒቨርሲቲ በጋዜጠኝነትና ኮሙዩኒኬሽን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በማጠናቀቅ ላይ እያሉ ባጋጠማቸው ድንገተኛ ህመም ተስተጓጉሏል። ጥልቅ ሀሳብ ያዘሉ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ፁሑፎችን በማህበራዊ ሚዲያና በተለያዩ ጋዜጦች በማውጣት ይታወቃሉ።
አዲስ ዘመን እሁድ ሚያዝያ 29 ቀን 2015 ዓ.ም