የመንደርደሪያችን መደላድል፤
የሀገራዊ አስተሳሰባችን ውቅርና የጋራ ታሪካዊ እሴቶቻችንን አረዳድ፣ አቀባበልና ፍረጃ በተመለከተ የጋራ መግባባት ላይ ለመድረስ መቸገራችን ዋነኛው “የብሔራዊ ሕመማችን” ምልክት ስለመሆኑ ይህ ጸሐፊ በሚገባ ያምንበታል:: ከአሁን ቀደም በዚሁ ዐምድ ላይ ደጋግሞ ለመግለጽ እንደተሞከረው፤ ከሀገራዊ ታሪኮቻችን መሰዊያ ላይ ፍሙን ብቻ እየጫርን በትናንት መልካም ውርሶችና እሴቶቻችን ስሜታችንንና መንፈሳችንን በማሞቅ ጨለማችንን ከመግፈፍ ይልቅ አመዱን እየዛቅን በመበተን መናቆሩ እስከ ዛሬ ድረስ የትም ሊያደርሰን አልቻለም፤ ለወደፊቱም ቢሆን “የጋት ያህል” ፈቅ ሊያደርገን እንደማይችል አያያዛችን ምስክር ነው::
በታሪኮቻችን ይዘትና ምንነት ላይ ብቻ ሳይሆን በስያሜዎቻቸውም ላይ ሳይቀር ብዙ መጣረሶች እንደሚስተዋሉ “ዕድሜ ደጉ” ቆመን እንድናስተውል የተፈረደብን ይመስላል:: ለአብነት ያህልም በትናንትናው እለት አክብረን የዋልነውን ታሪካዊ የድል በዓል ስያሜ በተመለከተ እንዴት ሲውገረገር እንደኖረ ሳንረዳ የቀረን አይመስለንም:: ለዚህ ሁሉ ጥፋት በዋነኛነት ተጠያቂዎቹ ደግሞ ጥቂት የማይባሉ የብዙኃን መገናኛ ባለሙያዎችና የተለያዩ የኅትመት ዐውደ እለታት (Calendars) አሳታሚና አታሚ ተቋማት በቀዳሚነት ጣት ይጠቆምባቸዋል::
በርካቶች በሚያሳትሟቸው ዐውደ ዕለታት ገጾች ላይ የሚያዝያ 27 በዓልን “የአርበኞች መታሰቢያ” በማለት መግለጻቸው የተለመደ ነው:: በዓሉ በጀግኖች አርበኞቻችን የደምና የመስዋዕት ውጤት መገኘቱ እርግጥ ቢሆንም፤ በጦርነቱ የተሳተፉትን በተመለከተ ግን በዚያ ዘመን የኖሩትን ሁሉንም የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚወክሉ የኢትዮጵያ ልጆች በምልዓት አሻራቸውን ያተሙበት የመስዋዕትነት ድል ነበር::
ብዙዎች በአፍላው ጦርነት ጥሎ በመውደቅ፣ አንዳንዶች በውስጥ አርበኝነት፣ አንዳንዶች የልባቸውን በልባቸው አድርገው ከፋሽስቶች ጋር አብሮ በመሥራትና በመዋል ለአርበኞች መረጃ በማቀበል፣ አንዳንዶችም አርበኞችን በቤታቸው ውስጥ ሸሽገውና ደብቀው በማሳረፍና ግድ ሲልም በሕክምና በማገልገል፣ ብዙኃን ዜጎችም እንዲሁ ስንቅ በማቀበልና በስለላ ወዘተ. የተሳትፎው ወሰን ይህ ልኩ ተብሎ በማይወሰን መስዋዕትነት ድርሻቸውን ተወጥተዋል:: እርግጥ ነው “ከስንዴ መካከል እንክርዳድ…” እንዲሉ ከጠላት ጋር በማበር ክህደት ፈጽመው ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን የወጉ ባንዳዎችም እንደነበሩ በሚገባ ይታወቃል::
“የአርበኞች መታሰቢያ” የሚለው ስያሜ የተሸከመው ሌላው ስህተት በዓሉ በብሔራዊ ደረጃ ከፍ ያለ ክብርና እውቅና ተሰጥቶት ዕለቱ በመንግሥታዊ አዋጅ ተደንግጎና መደበኛ የሥራ እንቅስቃሴ ተዘግቶ በብሔራዊ ደረጃ የሚከበር በዓል እንጂ “ታስቦ ብቻ” የሚውል አይደለም:: ስለዚህም “መታሰቢያ” የሚለው ገለጻ ይህንን ብሔራዊ የድል በዓል አይመጥንም::
ሌላውና መታረም የሚገባው ስህተት “ሚያዝያ 27 የነፃነት በዓል” የሚለው አገላለጽ ነው:: በመሠረቱ ኢትዮጵያ በየትኛውም ዘመን በቅኝ ገዢዎች የወረራ ሙከራ ሲደረግባት ቢኖርም ወራሪዎቹ በሙሉ በእፍረት ተዋርደው ተባረሩ እንጂ የትኛውም ሀገርና መንግሥት በቅኝ ግዛት ባርነት ሥር ስላላንበረከካት “የነፃነት” ቀን የላትም:: በትናንትናው ዕለት ያከበርነው ብሔራዊ በዓላችንም “የድል በዓል” እንጂ ሌላ ስያሜ አይመጥነውም::
በየዓመቱ የሚከበረውን የሚያዝያ 27 ብሔራዊ የድል በዓል ስንዘክር ሊታወሱ የሚገባቸውን አንዳንድ ዋና ዋና ጉዳዮችን ጠቁመን እንለፍ:: የፋሽስት ኢጣሊያ ወረራን ተጋድለንና ተፋልመን በአርበኞቻችንና በሕዝባችን ብርቱ መስዋዕትነት አኩሪ ድል መቀዳጀታችንን አጉልተን የምንመሰክረው እኛ ብቻ ሳንሆን ዓለም በሙሉ ያረጋገጠው ገድላችን ነው:: ይህ የሕዝባችን የተጋድሎ ታሪክ እንደተከበረ ሆኖ ከበስተጀርባ እና ፊት ለፊት በመውጣት ወራሪውን የፋሽስት ኢጣሊያ መንግሥት በዓለም ፊት በመኮነን አጋርነታቸውን የገለጹልንና ድጋፍ ያደረጉልን ወዳጅ መንግሥታትና ሕዝቦችም መኖራቸው ሊዘነጋ አይገባም::
እርግጥ ነው ወራሪው የፋሽስት ኃይል አከርካሪው ተሰብሮ ጦርነቱ በድል ከተጠናቀቀ ሰማንያ ሁለት ዓመታት ቢቆጠርም ከላይ የጠቀስናቸውንና ከጎናችን ተሰልፈው ወይንም በርቀት ሆነውም ቢሆን ድጋፍ ላደረጉልን የክፉ ቀን ወዳጅ መንግሥታት በየዓመቱ ድላችንን ስንዘክር በፕሮቶኮል ንግግሮችና ከፍ ሲልም መንግሥት የጉዳዩን ክብደት ተረድተው ድጋፍ ላደረጉልን መንግሥታት በቋሚ መታሰቢያ እውቅና ቢሰጣቸው ወዳጅነቱንና የዲፕሎማሲ ግንኙነቱን በእጅጉ እንደሚያጠናክረው አሌ አይባልም:: ይህ ማለት ግን ለአንዳንድ ሀገራት ዜጎችና መንግሥታት ከአሁን ቀደም በስማቸው መንገድ፣ አደባባይ፣ ት/ቤትና በጥቂቱም ቢሆን አንዳንድ ተቋማት በስማቸው መሰየሙ የሚካድ አይደለም:: ጥያቄው በቂ ነው አይደለም? የሚለውና ሁሉንም አለማካተቱ ነው::
የ2008 ዓ.ም የሚያዝያ 27 የድል በዓል በተከበረበት ዓመት የተፈጸመን አንድ በአርአያነቱ ከፍ ያለ ተግባር ለአብነት እናስታውስ:: በተጠቀሰው ዓመት የተከበረውን የ75ኛውን ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ የድል በዓል ሙሉ ዝግጅቶች ለማስተባበር የጥንታዊ ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማኅበር እድሉን የሰጠው ይህ ጸሐፊ ለሚሠራበት ተቋም ሲሆን የማስተባበሩም ሙሉ ኃላፊነት የዚህ ዓምደኛ ነበር::
ከዋናው በዓል አስቀድሞ እጅግ በርካታ መርሐ ግብሮች የተከናወኑ ቢሆንም ሁለቱን ኩነቶች ብቻ በምሳሌነት ጠቅሰን ለማስታወስ እንሞክር:: የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓሉን ካደመቁት መካከል አንዱ ተጠቃሽ ተግባር ከኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ጋር በመተባበር ለ26 ያህል ጀግኖች አርበኞቻችን የመታሰቢያ ቴምብር መዘጋጀቱ ነበር:: ይህ የመታሰቢያ ቴምብር ሁሉንም አርበኞች ሊወክሉ ይችላሉ ተብሎ የታመነባቸው ጀግኖች አርበኞች የተካተቱበት ነው:: ከኢትዮጵያ ጎን ቆመው ከፍተኛ አስተዋፅዖ ያደረጉ እንደ እንግሊዛዊቷ ክብርት ሪታ ፓንክረስትን የመሳሰሉት ወዳጅ የውጭ ሀገራት ዜጎችም በቴምብሩ ላይ ምስላቸው እንዲገባ ተደርጓል::
ሁለተኛው ክንውን በዓይነቱ እጅግ የተደነቀው የሽልማት መርሐ ግብር ሲሆን ተሸላሚ መንግሥታቱ በጦርነቱ ወቅት ከጎናችን የተሰለፉባቸው ምክንያቶች የተለያዩ ነበሩ:: ለምሳሌ፡- እንግሊዝና ሰሜን አየርላንድ፣ ቻይና፣ሩሲያ፣ ሜክሲኮ፣ ኒውዚላንድ፣ ስዊድን፣ ደቡብ አፍሪካ፣ አርጀንቲና በቀጥታ ከሀገራችን ጎን ቆመው የድጋፍ ድምፃቸውን በማሰማት የፋሽስቶችን ወረራ በአንድም ሆነ በሌላ ተቃውመዋል፤ እንዳስፈላጊነቱም ልዩ ልዩ ድጋፎች አድርገውልናል:: ኬኒያ፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ናይጄሪያ፣ ጋናና ዩጋንዳ ደግሞ ከእንግሊዝ የቃል ኪዳን ጦር ጋር የተሰለፉ ወታደሮችን ያዋጡ ሀገራት ናቸው::
ምክንያቱ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ሥር ስለነበሩ ብቻ ሳይሆን በዋነኛነት ሊቆጠርላቸው የሚገባው ከኢትዮጵያ ሠራዊት ጎን ተሰልፈው የከፈሉት መስዋዕትነት ነው:: ከእነዚህ ሀገራት ዜጎች መካከል በጦርነቱ መሐል የወደቁት ወታደሮች መካነ መቃብር በድሬዳዋ ውስጥ እንደሚገኝ ይታወቃል:: የዘላቂ ማረፊያው ስም “No. 1” የሚባል ሲሆን ዛሬም ድረስ በጥንቃቄ እንደተጠበቀ ይገኛል::
ከላይ ከተዘረዘሩት መንግሥታት በተጨማሪ ከጦርነቱ በፊት ወታደራዊ ኤክስፐርቶችን ልኮ የረዳን የቤልጂዬም መንግሥትና በድሉ ማግሥት የየካቲት 12 የሰማዕታት ሐውልትን አሰርቶ በስጦታ የሰጠን የወቅቱ የሰርቢያ ሪፑብሊክ መንግሥትም ከተመስጋኞቹ መካከል ነበሩ:: የቀድሞው የሀገራችን ፕሬዚዳንት ክቡር ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ በክብር እንግድነት ተገኝተው ሽልማቱን ባበረከቱበት ወቅት ተሸላሚ ሀገራቱ በሀገራችን ውስጥ በሚገኙት አምባሳደሮቻቸው ውክልና የተሰማቸውን ስሜት የገለጹት ከቁጥጥር በላይ በሆነ ተመስጦ ውስጥ በመሆን ነበር:: “ኢትዮጵያ እንዴት ከ75 ዓመት በኋላ አሰበችን” በማለት:: ለማንኛውም ይህ በጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማኅበር ተነሳሽነት የተፈጸመው አስመስጋኝ ተግባር በመንግሥት ደረጃ ተጠናክሮ ቢፈጸም ውጤቱ ያማረ እንደሚሆን ይታመናል::
በወቅቱ ታትመው ከነበሩት ሰነዶች መካከል አንዳንድ ተጠቃሽ ታሪኮችን እየመዘዝን ለማስታወስ እንሞክር:: አርበኝነት የኢትዮጵያ ታሪክ አካል ነው:: የሀገራችን ሥርዓተ መንግሥታትም በነፃነት ቆመው የኖሩት፣ ሀገርና ሕዝብም ከቅኝ ተገዥነት ነፃ ለመሆን የበቃው በሕዝባችን የአርበኝነት ተጋድሎ ነው:: ከአክሱማዊው አፄ ካሌብ ጀምሮ በመካከለኛው፣ በጎንደር፣ እና በዘመናዊው ታሪካችን ውስጥ የአርበኝነት ታሪክ አብሮ አድጓል::
የእርስ በእርሱን መናቆርና ሥርዓተ መንግሥታቱን ለማማከልና ለማጠናከር የተደረጉትን መስፋፋቶች ትተን፣ ሀገርንና ወገንን በጋራ በመከላከል ረገድ ከቱርኮች፣ ከዐረቦች፣ ከድርቡሾች-ማሃዲስቶች፣ ከግብፃውያን፣ ከእንግሊዞች እና ከኢጣሊያኖች ጋር ተዋግተናል:: የነፃነት ታሪካችን የተቀረጸው በዚህን መሰሉ ውጣ ውረድ ውስጥ በመሆኑ የአርበኝነት ዋጋውና ታሪካዊ ቦታው ትልቅ ሥፍራ ይኖረዋል::
የፋሽስት ኢጣሊያ የዝግጅትና የወረራ ዜና መዋዕል፤
መስከረም 22 ቀን 1928 ዓ.ም ሐሙስ ማታ በ12 ሰዓት ቤኒቶ ሙሶሊኒ በጽሕፈት ቤቱ ሰገነት ላይ ብቅ ብሎ ንግግሩን ለመስማት ይጠባበቅ ለነበረው ለመላው የጣሊያን ሕዝብ ‹‹ኢትዮጵያን ለ40 ዓመታት ታግሰናታል! እንግዲህስ በቃ!›› ብሎ ረጅም የድንፋታ ንግግር ሲያደርግ የሕዝቡ ደስታ እጅግ በጋለ መልኩ ይስተጋባ ነበር:: ይህም በተንቀሳቃሽ የፊልም ምስል በዓለም ዙሪያ ታይቷል:: ጥቂት የማይባሉ ኢትዮጵያውያንም በቁጭትና በንዴት እንደተመለከቱት ይታመናል::
የሙሶሎኒ ንግግር ከመሰማቱ ሰባት ሰዓት ቀደም ብሎ መስከረም 21 ቀን 1928 ዓ.ም እኩለ ቀን ሲሆን ፋሺስቱ ጄ.ደ ቦኖ ከመረብ ወንዝ 50 ኪሎ ሜትር ራቅ ብሎ ለወረራ ሲዘጋጅ ነበር:: ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት ሲሆን 268‚000 የጦር ወታደር፣ 7‚000 መኮንኖች፣ 150 ታንኮች፣ 150 አዳኝና ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖች፣ 700 ልዩ ልዩ መድፎች፣ 6‚000 ከባድና ቀላል መትረየሶች፣ 6‚000 የጭነት የጋማ ከብቶች፣ 2‚300 ተሽከርካሪዎች ይዞ በመንቀሳቀስ ከጧቱ 3፡00 ሰዓት ተኩል ሲሆን መረብን ተሻግሮ ወደ ኢትዮጵያ ዘለቀ:: መረብን ሲሻገር የኢትዮጵያ ጦር በሚወስደው የመከላከልና የማጥቃት እርምጃ ችግር ይፈጥርብኛል ብሎ የነበረው የጠላት ጦር ስጋቱ እውን ሳይሆን ያለአንዳች ተቃውሞ ሰተት ብሎ ገባ::
የጣሊያኖችን ወረራ አስመልክቶ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መስከረም 22 ቀን 1928 ዓ.ም የክተት አዋጅ አስነግረው የጉዞ ነጋሪት መጎሰም ጀመረ:: ጣሊያኖች በኢትዮጵያ ላይ የዘመቱበት ሰበብ በብዙ መላምቶች ሊታጀብ ቢችልም ዋናውና ትልቁ ምክንያት ግን በዘመናዊ የዓለም ታሪክ ጥቁር ሕዝብ አንድን የአውሮፓ ኃይል አዋርዶ ያባረረውን ታሪክ በበቀል ለማደስ የተጠነሰሰ እንደነበር መገመትና ብሎም ማመን አያዳግትም::
ጣሊያኖች ለጦርነት 40 ዓመት ሲዘጋጁ ኢትዮጵያ ለጦርነት ዝግጅት ያደረገችው 3 ዓመት ብቻ ነበር:: በወቅቱ ሀገራችን የነበራት በአብዛኛው ዘመን ያለፈባቸው አንድ ሚሊዮን የሚገመቱ ጠብመንጃዎችና ወደ 150 ሚሊዮን የሚጠጉ ጥይቶች ብቻ እንደነበሩ በታሪክ ተመዝግቧል:: የጦርነቱ ጊዜ እየተቃረበ በሄደበት ወቅት የኢትዮጵያ መንግሥት ዘመናዊ መሣሪያዎችን ለመግዛት በነፍስ ወከፍ አንድ ብር ሕዝቡ እንዲያዋጣ የመንግሥት ሠራተኛም ከደመወዛቸው ሃያ በመቶ እንዲያዋጡ በማድረግ የተገኘውን ያህል ተሰብስቦና የሀገሪቱ ሀብት ተሟጦ ጥቂት የጦር መሣሪያ ግዢ መፈጸሙ ጣሊያኖችን ሳያሰጋቸው አልቀረም:: በተለይም አንዳንድ ዘመናዊ የሚሰኙ መሣሪያዎች ከቼኮስሎቫኪያ፣ ከቤልጅግና ከጀርመን በጂቡቲ በኩል አዲስ አበባ ሲደርሱ ንጉሠ ነገሥቱ እራሳቸው ባቡር ጣቢያ በመሄድ የመጣውን መሣሪያ በጉጉት መመልከታቸው ጣሊያኖችን ሳያሸብር አልቀረም::
ዘመናዊ መሣሪያ ታጥቀው በዘመናዊ የጦር ስልት ይከላከላሉ ተብሎ ተስፋ የተጣለባቸው በሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ገብተው የሰለጠኑ ጥቂት መኮንኖች ነበሩ:: ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በተገኙበት መጋቢት 7 ቀን 1927 ዓ.ም በጃንሜዳ ሰልፍ ያሳዩት 3‚000 የሚሆኑት እነዚያ መኮንኖችና ወታደሮች ነበሩ:: ቢሆንም 40 ዓመታት ያህል ኢትዮጵያን ለመበቀል ተዘጋጅቶ የመጣውን የጣሊያን ሠራዊት የሚከላከል ሙሉ አቅም ነበረን ለማለት ያዳግታል:: ለምሳሌ፣ መስከረም 23 ቀን 1928 ዓ.ም ጣሊያኖች የሰሜን ኢትዮጵያን ወሰን ጥሰው ሲገቡ አገራችን አንድም የመከላከያ ኃይል በአካባቢው ዘርግታ የመከላከል ተግባር ለመፈጸም አልቻለችም ነበር::
በኦጋዴንና በደቡብ ኢትዮጵያ በኩል ጣሊያኖች ኢትዮጵያን ለመውረር የቀየሱት እቅድ የሚላን ፕላን በመባል ይታወቃል:: እቅዱ በሦስት የተከፈለና ምዕራብ መሐልና ምሥራቅን ያካለለ የጦር እቅድ ነበር:: የመጀመሪያው የምዕራብ ጦር ግምባር የሚባለው የጠረፍ ከተማ የሆኑትን ዶሎንና አካባቢዋን ለመያዝ የተንቀሳቀው ነበር:: የዚህ ጦር አዛዥ ኮሎኔል ሚሼሊ ይባላል:: የሚሼሊ ጦር ጥቅምት 11 ቀን 1928 ዓ.ም በቀኑ 11፡00 ሰዓት ላይ ጦርነት ከፍቶ ወዲያውኑ ጣሊያኖች አካባቢውን በቁጥጥራቸው ሥር አዋሉት::
ይህ ጦርነት ሲከፈት ግራዝማች መኩሪያ ተሰማ የተባሉት የጠረፍ ጥበቃው አዛዥ በጀግንነት ተዋግተው ብዙ ቦታ ቆስለው እጄን ለጠላት አልሰጥም ብለው በጨካኙ የጠላት ጦር ተሰውተዋል:: አካባቢውም በጣሊያኖች ቁጥር ሥር እንደዋለ የግራዝማች መኩሪያን ጀግንነት ጠላትም ስለተገነዘበ በክብር እንዲቀበሩ አድርጓል::
ሁለተኛው ዕቅድ በመሐል ግንባር ተሰልፎ የሚጠባበቅን ጦር በማሰማራት የዋቢ ሸበሌን ሜዳማ መሬት ለመያዝ ነበር:: ይህም በጄኔራል ፍሩሽ የሚመራው ጦር ነበር:: የጣሊያኑ ጦር በጦር አውሮፕላኖች እየተረዳ ጥቅምት 15 ቀን 1928 ዓ.ም ቀላፎን ሺላቦን ለመያዝ ቻለ:: በኢትዮጵያ በኩል የጠረፍ ጦር አዛዥ የነበሩት ግራዝማች በላቸው የተባሉ ጀግና እጃቸውን ሳይሰጡ በጀግንነት ተዋግተው በጨካኙ የጠላት ጦር ተሰውተዋል:: ሦስተኛው የጦር እቅድ በምሥራቅ በኩል የተሰማራው የጣሊያን ጦር የሚመራው በኮሎኔል ማሊቲ ነበር:: በኢትዮጵያ በኩል ቆራሄንና አካባቢውን በአስተዳዳሪነትና በጠረፍ ጠባቂነት የተመደቡት ግራዝማች አፈወርቅ ወልደ ሰማያት ነበሩ:: ምሽጋቸው ዘመናዊ ነው ባይባልም ከአውሮፕላን ለሚዘንበው ቦምብ ግን በቂ መከላከያ ነበር ተብሎ በታሪክ ተጠቅሷል።
የመሐሉንና የሌላውን ክፍል የጠላት ወረራ በዝርዝር ለመዘከር ገጹ ስለሚወስነን ለማሳየት የተሞከረው ጥቂቱን ታሪክ ብቻ ለማስታወስ ነው:: ጀግኖቹ አርበኞቻችንና ሕዝቡ በምድር በዘመናዊ መሣሪያዎች እየወደቀ፣ በሰማይ በሚዘንብበት የመርዝ ጋዝ እየተንገበገበ በከፈለው መስዋዕትነት ነው ኢትዮጵያ በፋሽስት ወራሪዎች ላይ ድል ተቀዳጅታ አኩሪ ታሪክ ያስመዘገበችው:: እናም ሚያዝያ 27ን የድል ቀን ብላ የምታከብረው:: ሰላም!
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 28/2015