ባለፈው እሁድ (ሚያዝያ 15) የአዲሲቷን ኢትዮጵያ ተራማጅ እሳቤ እውን ያደረገ የምስጋናና የአብሮነት መርሀ ግብር ተካሂዷል። “ጦርነት ይብቃ ሰላምን እናጽና” በሚል መሪ ቃል የሰሜን ኢትዮጵያን ጦርነት በሰላም እና በንግግር እንዲቋጭ ላደረጉ አካላት በወዳጅነት አደባባይ የምስጋናና የእውቅና ስነስርአት እውን ሆኗል።
በስነስርዐቱ ላይ የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን እና የአዲስ አበባ ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ የተገኙ ሲሆን፤ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ መሀመድ፣ የናይጀሪያው የቀድሞ ፕሬዚዳንትና የአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴንጎ ኦባሳንጆ፣ የቀድሞው የኬኒያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ አምባሳደር ማይክ ሀመር፣ የኢጋድ ሊቀመንበር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ እንዲሁም የክልል ርዕስ መስተዳድሮች እና ሌሎች እንግዶችም የስነስርዐቱ አካል ነበሩ።
በዝግጅቱ ላይ ያለፈችውንና አሁን ያለችውን ኢትዮጵያ እያነጻጸሩ የተለያዩ እንግዶች ንግግር አድርገዋል። ከሰላም በኋላና ከሰላም በፊት የነበረችውን ሁለት መልክ ኢትዮጵያ እያስታወሱ የሰላምን ዋጋ በማግነን የጦርነትን እሳቤ በመኮነን ስለአንድነት የተሰሙ ድምጾች እልፍ ነበሩ። ከነዚህ የሰላም አዋጅ ድምጾች ውስጥ አንዱ የቀድሞው የኬኒያ ፕሬዚዳንት የኡሁሩ ኬንያታ ንግግር አንዱ ነው። በንግግራቸው “ኢትዮጵያውያን በሰላምና በአንድነት የቆየና የነበረ አብሮነታቸውን እንዲቀጥሉ፣ የአንድነትና የወንድማማችነት መንፈሳቸውን አጠናክረው በተሻለ ሊተጉ ይገባል” ሲሉ ተናግረዋል።
እዚህ ላይ ሊጠቀስ የሚገባው የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት የአቶ ጌታቸው ረዳ ንግግር ነው። ርዕሰ መስተዳደሩ የነበረውን የጦርነት ጊዜ በማስታወስ “የትግራይ ህዝብ ጦርነት ሰልችቶታል፣ አንገሽግሾታል” ያሉ ሲሆን ከዚህ ጋር የሚዛመድ የሰላም፣ የአንድነትና የእርቅ ድምጻቸውን አሰምተዋል። ርእሰ መስተዳድሩ “ከትግራይ ህዝብ ይዤ የመጣሁት የሰላምና የፍቅር መልዕክት ብቻ ነው” ያሉ ሲሆን “ሁሉንም ነገር ሰላም መር በሆነ እሳቤ እናድርገው። ከጎረቤት ህዝቦች፣ ከአማራና ከአፋር ጋር ሊያጋጨን የሚገባ ነገር ሳይኖር አብሮነታችንን በሰላም ማስቀጠል ለምንፈልገው ሰላም የላቀ ዋጋ አለው” ሲሉ ተደምጠዋል።
ከዚህ ጋር አያይዘው ለአራት ዓመት ያክል ትምህርት ያልጀመሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተማሪዎች በክልላችን ያሉ ሲሆን የእኔን ቤተሰብ ጨምሮ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች አሉን። በቀጣይ እነዚህ ነገሮች ተስተካክለው ሰላማችን ሙሉ እንዲሆን ሁላችንም መረባረብ አለብን ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን በመርሀ ግብሩ ላይ ለሰላም አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት የምስጋና ሽልማት የተሰጠ ሲሆን በቀጣይም ኢትዮጵያ ከነሙሉ ሰላሟ ጸንታ እስክትቆም ድረስ የአጋር አገራት ትብብር ይቀጥላል ሲሉ በስነስርዐቱ ላይ የተገኙት የውጪ አገራት ዜጎች ተናግረዋል።
ከዚህ ጋር ተያይዞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ የሰላም ሂደቱን የበለጠ ለማጠንከርና አስተማማኝ ለማድረግ በታቀደ ሀሳብ መሰረት በቀጣይ ሳምንት በብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት የተመራ የልኡክ ቡድን ወደ መቀሌ እንደሚያቀና የተናገሩ ሲሆን፤ የልኡክ ቡድኑ የሁሉንም የክልሎች ርዕሰ መስተዳድሮችን ያካተተ እንደሚሆንም ጠቁመዋል።
ለሰላም የምንችለውን ሁሉ በማድረግ አገር እንፈጥራለን ያለው የጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት ካሳለፍነው ተምረን መጪውን የተሻለ ለማድረግ በሁሉም ረገድ ተግባቦት የታከለበት ርምጃ እየወሰድን እንገኛለን ብለዋል። ከዚህ ጋር ተያይዞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ የተጀመረውን የሰላም ጉዞ ዘላቂና አስተማማኝ ለማድረግ ሌላ የሰላም ዜናም አብስረዋል። “የኢትዮጵያ መንግስት ከሸኔ፣ ወይም ደግሞ ራሱን ’የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት’ እያለ ከሚጠራው ታጣቂ ቡድን ጋር ከነገ በስቲያ በታንዛኒያ ድርድር እንደሚጀምር”
ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አያይዘውም “በዚህ ድርድር ላይ የሚሳተፉ ወገኖች የዛሬዋን ቀን እያሰቡ፣ ከግጭት፣ ከጦርነት እንደማናተርፍ አውቀው ህግ እና ስርዐትን በተከተለ መንገድ ይቅር ተባብለን አገራችንን በጋራ ማነጽ እና መገንባት እንድንችል እና የወለጋ ህዝብ አሁን ካለበት ስቃይ እፎይ ማለት እንዲችል ሁሉም ወገኖች የበኩላቸውን እንዲያደርጉ ከወዲሁ ጥርዬን አቀርባለው” ብለዋል።
ከዚህ እውነት በመነሳት አገራችን ለሰላም ያላትን ቁርጠኝነት መረዳት ይቻላል። የሰላም እጦት በሁሉም መስክ ዋጋ ሲያስከፍለን መቆየቱ የአደባባይ ሀቅ ቢሆንም ልዩነታችንን አቻችለን በእርቅና በተግባቦት ወደፊት መቀጠል ተስኖን ነበር። በዚህ ሰላምን በኃይል ለማምጣት በመሞከር እሳቤ ውስጥ ብዙ ዋጋዎችን ከፍለን ዛሬ ላይ በሰላምና በእርቅ ለምስጋና ቆመናል። የትኛው እንደሚበጀን አይጠፋንም። የጠፋን በመነጋገርና በላቀ የሀሳብ የበላይነት ተነጋግሮ መግባባት ነው። ሰው የሚስተው ባልገባውና ባልተረዳው ነገር ላይ ነው። የእኛ ስህተት ግን ባወቅነውና በተለማመድነው እውነት ላይ ነው። ጦርነት ለዘመናት መገለጫችን ሆኖ እንደቆየ እናውቃለን።
በጦርነት ብዙ የሞትና የአካል መጉደል ስብራቶችን እንዳስተናገድን እናውቃለን። ይሄ ሳይበቃን በድህነት ላይ ቁምጥና ሆኖብን በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ ህይወታችን ምን ያክል ኪሳራ እንዳደረሰብን የአደባባይ ሀቅ ነው። ይሄን ሁሉ እውነት ይዘን ለዳግም ስህተት ወደ ጦርነት መግባታችን ለሰሚው ግራ ከመሆኑም በተጨማሪ አቻ የሌለው የስህተትና የአለማወቅ አባዜ ነው። ሰው ከወንድሞቹ ጋር ይረዳዳል፤ ይተባበራል እንጂ ከወንድሞቹ ጋር ጦርነት አይገጥምም። በአገራችን እንዲህ ያለውን ነውር የሚያወግዝ፤ “ወንድሙን ታግሎ የጣለ ጀግና አይባልም” የሚል ብሂል አለ።
እነዚህን መሳይ አስተማሪ ተረቶች የተነገሩት በአባቶቻችን አንድነትና ወንድማማችነት ላይ ተመስርተው ነው። እኛም በተግባራቸው ላይ ቆመን ሰላሳና ስልሳ መቶም አፍርተን ድህነትን “ምን አባክ” ማለት ሲገባንና ልማትና ብልፅግናን ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ ስንችል የተሰጠንን የአንድነትና የአብሮነት ስነቃል በእኔነት ለመሻር እየተንፈራገጥን እንገናኛለን።
የአባቶቻችን የሆነ ሁሉ ውብ ነው። ያለፉበትን፣ ያሸነፉበትን፣ ጽናትና ልዕልናን ያገኙበትን ምስጢራቸውን ነው የሰጡን። እንዴት በአንድነት አገር እንደሰሩ፣ እንዴት ብለው ወራሪውን ፋሽስት አሳፍረው እንደመለሱ፣ እንዴት ብለው ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን እንዳቆዩልን በስነ ቃል አማካኝነት አስተላልፈውልናል። እንዴት ብለው ከአለም እንደቀደሙ፣ እንዴት ብለው የአፍሪካ የነጻነትና ቀና የማለት ብስራት እንደሆኑ፣ እንዴት ብለው በሉአላዊነትና በክብር፣ በጀግንነትና በወንድማማችነት እንደቆሙ ነግረውናል። የአባቶቻችን እውነት ወደ ፊት ለመሄድ የወርቅ ምንጣፋችን ነው።
ያን ምንጣፍ የናቅን ጊዜ፣ ያን ምንጣፍ የተጸየፍን ጊዜ በደም የቆመውን ኢትዮጵያዊነት እየሻርን ነው። ያን ምንጣፍ “አይረባም” ያልን ቀን፣ ያን መረማመጃ “አሮጌ ነው” ያልን ቀን ማንነታችንን እየካድን ነው። በደም የተገመደ፣ በታሪክ፣ በባህል የተሳሰረ አንድነታችንን እያላላን ነው። ዓለም የሌላትን፣ በምንም የማናገኘውን ወርቃማ እድላችንን እያጣን ነው።
አባቶቻችን ወንድሙን ታግሎ የጣለ ጀግና አይባልም ሲሉን የወንድም ደም የራስ ደም ነው እያሉን ነው። ወንድምህ ቢያስቀይምህ በፍቅርና በይቅርታ እቀፈው፣ ይቅር በለው እያሉን ነው። ወንድሙን ታግሎ የጣለ ጀግና አይባልም ሲሉን አገር ማለት አንተና እሱ ናችሁ። ከአንተ ውስጥ እሱን አጉድለህ ሙሉ መሆን አትችልም። አንተ ኢትዮጵያዊ የተባልከው በእሱ ውስጥ ነው። እሱም ኢትዮጵያዊ የሆነው በአንተ በኩል ነው፤ እናም ቢገልህና ብትገድለው ኢትዮጵያን እየገደላችኋት ነው እያሉን ነው።
ሌላው ለሁላችንም አዲስ ያልሆነ ግን ደግሞ እምብዛም ስንጠቀምበት የማይስተዋል ስነቃል አለ። “ድር ቢያብር አንበሳን ያስር” የሚል። በዚህ የተጠቀሙ፣ ተጠቅመውም ያተረፉ ብዙ ኢትዮጵያውያን አሉ። አድዋን እና ሌሎች የጋራ ድሎቻችን በዚህ ስነቃል በኩል የተፈጠሩ ናቸው ማለት ይቻላል። ሁሉንም ትተን እንኳን “ኢትዮጵያ” የሚለው ስም የተሳለውና የተቀለመው በዚህ ስነቃል በኩል ነው። ኢትዮጵያዊነት አንድ ትርጉም ቢኖረው አንድነት ነው የሚሆነው። ይሄ አንድነት ደግሞ በ“ድር ቢያብር አንበሳን ያስር” ምሳሌያዊ አነጋገር አማካኝነት እውቅና ያገኘ ነው። ታዲያ የእኛ መነጣጠል፣ የእኛ መለያየት ከየት የመጣ ነው?
በወንድም ደም ጀግና ከመሆን ይልቅ፣ በማይጠቅመንና አባቶቻችን ባላወረሱን እኔነትና ብቻነት ተነጣጥለን ከምንጓዝ መለያችን በሆነው የጋራ ስማችን አብረን ብንቆም ነው የሚያዋጣን። ዛሬ ላሉብን እና ነገ ለሚኖሩብን ችግሮቻችን ጀግና በሌለው በወንድም ሞት ከምንለፋ ተቧድነንና ተረዳድተን እንደ አንበሳ ሊሰለቅጠን የደረሰ ችግራችንን ብንገጥመው ነው የሚሻለው።
ድር ቢያብር አንበሳ ያስር የሚለው አባባላችን በአሁኑ ዘመን ጥቅም ላይ ሲውል አይታይም። “ለምን?” ካልን መልሱ “በመለያየትና በመነጣጠል ስለሰለጠንን” ነው የሚሆነው። ስልጣኔአችንን ከአንድነት ካልጀመርንና በወንድማማችነት ካላበቃን ተጣልቶ መታረቅ፣ ተገዳድሎ መጨባበጥ ነው እጣ ፈንታችን የሚሆነው።
የሚያስፈልገን ተጣልቶ መታረቅ፣ ተገዳድሎ መጨባበጥ ሳይሆን ሳንጣላና ሳንገዳደል በፊት ችግሮቻችንን መፍታት ነው። ትላንትን መለስ ብለን ብናይ ደስታን የሚሰጠን ምንም ነገር የለም። ሞተንና ገለን የታረቅን ነን። ሳንሞትና ሳንገል ጀግንነታችንን በእርቅና በሰላም ውስጥ መፈለግ ነው እንደ አገር በረከት፣ እንደ ግለሰብ ጀግና የሚያስብለን።
በጦርነት ውስጥ ጀግና መሆን ይብቃን። ጀግና ለመሆን ከተሰናዳን ጀግና ልንሆንባቸው የምንችልባቸው እልፍ የድህነትና የኋላ ቀርነት ነውሮች አሉብን። ከእንግዲህ ባለችው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደ ፖለቲከኛ፣ እንደ ዜጋና እንደ አንድ አገር ወዳድ ትውልድ ጀግንነታችን በፍቅርና በሰላም፣ በልማትና በይቅርታ ውስጥ እናድርገው።
ያለን አማራጭ ድር ቢያብር አንበሳን ያስር በሚለው ብሂል ላይ ቆመን እንደ አንበሳ እያገሳ ሊውጠንና ተስፋ ሊያስቆርጠን ፊታችን የቆመውን ድህነትና ኋላ ቀርነት መፋለም ነው። ስልጣኔን አንድ ቃል ቢገልጸው ጠንካራ ሀሳብ ከጠንካራ አብሮነት ጋር የሚል ይሆናል። ታሪኮቻችን ጦርነት የተቆራኛቸው ጠንካራ ሀሳብ ከጠንካራ ወንድማማችነት ጋር ስላጣን ነው።
ለዓለም ሰላም አስተዋጽኦ የነበራት አገራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሰላም ያለህ በሚሉ የሰቆቃ ድምጾች መዋጧ አንድም ራስ ወዳድነት፤ አንድም ሰላምን በኃይል የማምጣት ልምምዳችን የፈጠረው ነው። በሀሳባችን ውስጥ ያለችውን ኢትዮጵያ ለመውለድ፣ ሁሌ ድምጽ ማጉያ በያዝን ቁጥር እንድትፈጠር የምንሻትን ኢትዮጵያ ሆና ለማየት ከለመድነውና ከተለማመድነው፣ አሸናፊ ከሌለው ግፊያ እንላቀቅ።
አንደኛነት ከሌለው የወንድማማችነት ግፊያና ትንቅንቅ ወጥተን የጋራ ቤታችንን መስራት ነው ከዓለም እኩል የሚያራምደን። ድር ቢያብር አንበሳን ያስር ብለን ስንነሳ ነው ሀይል የምናበጀው። ፖለቲካችን ሀሳብ የለውም። ካለውም ሩቅ የማይወስድ ቅርብ አዳሪ ሀሳብ ነው። ሀሳብ የሌለው ፖለቲካ ደግሞ እየገደለ የሚሞት፣ እያደማ የሚጨባበጥ ነው።
ጊዜው የሰላምና የእርቅ እንደመሆኑ እንደ ህዝብ የሚያስብ ፖለቲካና ፖለቲከኛ የምንሻበት ጊዜ ላይ ነን። እንደ ህዝብ ማሰብ ኢትዮጵያዊነትን ማስቀደም ነው። ከፖለቲከኞቻችን አፍ ይልቅ በህዝብ ልብ ውስጥ ያለችው ኢትዮጵያ ታስፈልገናለች። የፖለቲከኞቻችን ኢትዮጵያ የማስመሰል ኢትዮጵያ ናት። ይህን ሁሉ ዘመን ተጉዘን አልደረስንባትም። እናም በህዝብ ልብ ውስጥ ወዳለችው የአንድነትና የወንድማማችነት ኢትዮጵያ እንመልከት።
ነገ ከትላትና ከዛሬ የተሻለ እንደሚሆን ከሰላም ጅምሩ መረዳት ይቻላል። ሕወሓት ከፌደራል መንግስት ጋር እጅ ለእጅ በመጨባበጡ ምክንያት የምንናፍቀውን የሰላም አየር በመሳብ ላይ እንገኛለን። በሌላ በኩል የሸኔ ቡድን በድርድር ሰላም አውርዶ ሌላ መጨባበጥን ስናስተናግድ ያኔ ሁሉም ነገር መልካም ይሆናል። እኔም ያንን እውነት ነው በህዝብ ልብ ውስጥ ያለችው ኢትዮጵያ ያልኳችሁ።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ማክሰኞ ሚያዝያ 24 ቀን 2015 ዓ.ም