ሰሞነኛ አስደንጋጩ መርዶ የአማራ ብልጽግና ጽ/ ቤት ኃላፊ የአቶ ግርማ የሺጥላ ግድያ ነው ። መርዶው ብዙኃኑን ያለልዩነት አሳዝኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድም ፤ «ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው አካላት የወንድማችንን የግርማ የሺጥላን ነፍስ ነጥቀዋል። ልዩነትን በሠለጠነ መንገድ መፍታት ባህል በሆነበት ክፍለ ዘመን፣ በሐሳብ የተለየንን ሁሉ በጠመንጃ ለማሳመን መነሣት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው። ተወልዶ ባደገበት አካባቢ፣ ከእኛ የተለየ ሐሳብ ማሰብ አልነበረበትም ብለው የሚያምኑ ነውጠኛ ጽንፈኞች የፈጸሙት አስነዋሪና አሰቃቂ ተግባር፣ ጽንፈኝነትን በጊዜ ታግለን ካላስወገድነው ወደ መጨራረስ እንደሚወስደን ጉልሕ ማሳያ ነው።» በማለት አውግዘውታል።
የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል ከፋለም ፤«በዛሬው ዕለት ወንድማችን አቶ ግርማ የሺጥላ በሥራ ላይ በነበረበት በታጠቁ ኃይሎች ግድያ ተፈጽሞበታል። እንዲህ ዓይነት እብሪተኝነት ውድቀትን እንጂ ድልን አያጎናጽፍም። ጥፋትን እንጂ ሰላምን አይሰጥም። የሕዝባችን የቆየ መገለጫው ሥርዓታዊነት፣» በማለት ኮንነውታል። የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በኀዘን መግለጫው፤ «በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ እና የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል በነበሩት አቶ ግርማ የሺጥላ ላይ የተፈጸመውን የግድያ ጥቃት በጽኑ ያወግዛል፣ ጥልቅ ኀዘኑን ይገልጻል፣ ለቤተሰቦቻቸው፣ ለሥራ ባልደረቦቻቸው እና ለመላው የአገራችን ሕዝብ መጽናናትን ይመኛል። » ካለ በኋላ በማስከተልም ፣ «የክልሉ መንግሥት አመራሮች ላይ ተደጋግሞ እየተፈጸመ ያለው የግድያ ጥቃት ክልሉን የቀውስ ማዕከል የሚያደርግ፣ የአገራችንን ሰላም እና መረጋጋት አደጋ ላይ የሚጥል የዜሮ ድምር ፖለቲካዊ ሽብር ውጤት በመሆኑ ድርጅታችን አብን በጽኑ የሚያወግዘው ወንጀል ነው። » ብሏል።
ባለፈው ሐሙስ ሰሜን ሸዋ መሀል ሜዳ ጎሳ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ በጥይት የተገደሉት የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በአንፆኪያ ገምዛ ወረዳ የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዘርፍ ኃላፊ በመሆን በታኅሣሥ 1988 ዓ.ም የአመራርነት ሥራን የጀመሩ። በዚያው ዓመት ሐምሌ ወር ላይ የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ሆነው ተሹመዋል። በዚህ የኃላፊነት ቦታ ላይም ለሰባት ዓመት ገደማ ቆይተዋል። በጥር 1995 ዓ.ም ከወረዳ ወደ ዞን በመሸጋገርም፤ የቀድሞው ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) የሰሜን ሸዋ ዞን ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ጉዳይ ኃላፊ መሆን ችለዋል።
ለአንድ ዓመት ገደማ በዚህ ኃላፊነት ቦታ የቆዩት አቶ ግርማ፤ በጥር 1996 ዓ.ም የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ሹመት አግኝተዋል። በ2002 ዓ.ም የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከደብረብሃን ዩኒቨርሲቲ በምጣኔ ሀብት (ኢኮኖሚክስ) ትምህርት ዘርፍ ያገኙት አቶ ግርማ፤ በዚያው ዓመት የሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ ሆነዋል። እስከ ግንቦት 2003 ዓ.ም ድረስ በዚሁ ቦታ ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ፤ የሰሜን ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ ሆነው ተሹመዋል።
በምክትል አስተዳዳሪነት ደረጃ ለአራት ዓመታት ገደማ የቆዩት አቶ ግርማ፣ ዞኑን የመምራት ኃላፊነት በመስከረም 2008 ዓ.ም ተረክበዋል። የሰሜን ሸዋ ዞንን ለሁለት ዓመት ገደማ የመሩት አቶ ግርማ፤ በ2012 ዓ.ም በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን የሁለተኛ ዲግሪያቸውን በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኘው የኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ ይዘዋል። በዚህ አጋጣሚ ለቤተሰባቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን እመኛለሁ። አብን በኀዘን መግለጫው እንዳወሳው እኔም ወደ ኋላ መለስ ብዬ ከዚህ ቀደም ማለትም ከአራት አመት በፊት በአማራ አመራሮች ላይ የተፈጸመውን ግድያ ለማውገዝ ያጠናቀርሁትን መጣጥፍ እንድመለስበት ምክንያት ሆኖኛል።
አዲሱ Irish Republican Army IRA በ2019 ዓ.ም በወርሀ ግንቦት በለንደንዴሪ በጠራው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ አንድ ንክ አንጋች ለፖሊሶች የተኮሳት ጥይት የ29 አመቷን ጋዜጠኛ ሊራ ማኪ ሥራ ላይ እንዳለች በአጭር ቀጫት:: BBCን ጨምሮ ታዋቂ ዓለምአቀፍ ሚዲያዎች ሊራ ስለምትወደው ሙያ መስዋዕት መሆኗን ሳያሰልሱ ዘገቡ:: የከተማዋ ነዋሪዎችም በድርጊቱ ክፉኛ በመቆጣት ተጠርጣሪውን አሳልፈው ከመስጠት አልፈው «በእኛ ስም አይሆንም ! » የሚል መፈክር አንግበው እንደገና አደባባይ ወጥተዋል::
አዎ ! ጋዜጠኛ ሊራን የገደላት በጥላቻ ተገፋፍቶ ታውሮ እንጂ ለእኛ ወይም ለIRA ብሎ አይደለም በማለት እዚያው በጠበልህ ብለውታል:: እኔም እንደገና በእኛ ስም አልሆነም እላለሁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የእነ አምባቸውን ግድያ አስመልክተው በወቅቱ ፤ «አምባቸውን እንኳን በጥይት ደብድቦ ለመግደል ለመቆጣት እንኳ የሚሰሰትለት ሰው ነው::» ብለዋል:: ስለ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄነራል ሰዓረ መኮንንም «ኢትዮጵያዊነትን፣ ዴሞክራሲያዊ ለውጥን በመደገፉ እንደ ገና ዳቦ ከታችና ከላይ እሳት እየነደደበት የነበረን አገር ወዳድ ጀግና መግደል፤ » ምን ያህል አረመኔአዊ ድርጊት እንደሆነ ተናግረዋል::
ወደ ዛሬው ነቃሽ መጣጥፌ ስመለስ ፤ Not In Our Name « በእኛ ስም አይሆንም » በአሜሪካ በመስከረም 1 1993 ዓ.ም በተለምዶ 9/11 ላይ አልቃይዳ በአሜሪካ ላይ የሽብር ጥቃት መፈፅሙን ተከትሎ አሜሪካ አፍጋኒስታንን ጨምሮ በኢራቅና በቀጣናው ያወጀችውን ጦርነት ዜጎች በመቃወም «በእኛ ስም አይሆንም » በማለት እ አ አ በየካቲት 23 2002 የተቋቋመ ሕዝባዊ ንቅናቄ ነው:: ቻርሊ ሀደን የተባለ ታዋቂ አቀንቃኝ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሊየር ኢራቅ ላይ ለፈፀሙት ወረራ ለፍርድ ይቅረቡ የሚል መልዕክት ያለው “ Not In Our Name “ የተሰኘ የዘፈን ሲዲ መልቀቁ ንቅናቄውን ይበልጥ አኸዝቦታል::
በአገራችን በተለይ ካለፈው አምስት አመት ወዲህም ሆነ ከዚያ በፊት እዚህም እዚያም በዘውግ በማንነት በጎሳ ስም ዜጎች እየተገደሉ እየተፈናቀሉ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት እየተዘረፈ የዜጎች በሰላም ወጥቶ የመግባት የመንቀሳቀስ መብት እየተገደበ የአገር የግዛት አንድነት አደጋ ላይ እየወደቀ የሕግ የበላይነት እየተደፈቀ ከፍ ሲልም እንደ አገር የመቀጠል ጉዳይ ጥያቄ ላይ እየወደቀ ነበር :: በሶማሊያና በኦሮሚያ፣ በቤኒሻንጉልና ኦሮሚያ፣ በአማራና በቤኒሻንጉል፣ በአማራና በትግራይ ፣ በጉጂና በጌዲዎ ፣ በቅማንትና በአማራ የተከሰቱ ግጭቶችንና አለመግባባቶችን በአብነት ማንሳት ይቻላል:: በጅግጅጋና በምዕራብ ኦሮሚያ የአገሪቱን የግዛት አንድነትና ሥርዓቱን አደጋ ላይ የጣሉ ለመስማት የሚዘገንኑ የሰብዓዊ መብት ጥቃቶችና ማንነትን መሠረት ያደረጉ የጅምላ ግድያዎችን ዛሬ ድረስ የምናስታውሳቸው ዋና ዋና ሰቆቃዎች ናቸው::
ሆኖም እነዚህን ሁሉ ጥቃቶች፣ ግድያዎች፣ ማፈናቀሎች፣ ጭፍጨፋዎች፣ ዘረፋዎች በእኛ ስም ጥቂት ፅንፈኞች የፈፀሟቸው ናቸው :: አዎ ! በእኛ በኢትዮጵያውያን ( በአማራ፣ በኦሮሞ፣ በትግራዋይ፣ በሶማሊያ፣ በሲዳማ፣ በጌዲዎ፣ በጉጂ፣ በጉምዝ በበርታ በቅማንት፣ በሸካ ስም ) የተፈፀሙ ናቸው:: የእኛን የብዙኃኑን ይሁንታ ድጋፍ ሳያገኙ በእኛ ስም ሲፈፀሙ «በእኛ ስም አይሆንም» አይደረግም:: አላልንም:: ይህ ዝምታ ቸልታ ነገ በፍትሕ አደባባይ ባያስጠይቀንም በትውልድ በታሪክ ማስጠየቁ ግን አይቀርም ::
ትናንት ክልሌን ለቀህ ውጣ ተብሎ የመጀመሪያው ወገናችን ሲፈናቀል እኛ ብዙኀኖች «በእኛ ስም አይሆንም :: » አፈናቃዩ እኛን አይወክልም ብለን ከጅምሩ አምርረን አቋማችንን ብናሳውቅና ብንታገል ኖሮ ኋላ ላይ ሚሊዮኖች ባልተፈናቀሉ:: ወሰኔን ገፍተሀል በሚል የአንድ ክልል ሚሊሺያ ከሌላው ጦርነት ገጥሞ ንፁሀንን ሲገደሉ ሲያቆስሉና ሲያፈናቀሉ «በእኔ ስም አይሆንም :: » ብንል እስከ ዛሬ በመቶዎች አልያም በሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ባልተገደሉ::
ስለሆነም በአንድም በሌላ በኩል በአገራችን ለተስተዋሉ ችግሮች ለተደቀኑ አደጋዎች እጃችን አለበት:: በትውልድም በታሪክም ተጠያቂ ነን:: በማህበራዊ ሚዲያዎች የጥላቻ የጎሰኝነት የቂም በቀል መርዘኛ ፍላፃዎች በስማችን ሲንበለበሉ ከፍ ሲልም የግጭት የጦርነት የመገንጠል ነጋሪቶች በስማችን በማንነታችን በፌስ ቡክ ሲጎሸሙ «በእኛ ስም አይሆንም:: » ብለን በአደባባይ ባለመጮሀችን በሀፍረት አንገታችን የሚያስደፉ ነውሮች ተፈፅመዋል:: እየተፈፀሙም ነው::
በስማችን በማንነታችን የሚነዛ የበሬ ወለደ ሀሰተኛ የተዛባ መረጃን የደባ የሴራ ፖለቲካን «በእኔ ስም አይሆንም:: » ለማለት አንደበታችንን ማን ሸበበው ? ብዕራችንን ማን አዶሎደመው ? የስልኮቻችንን የኮምፒዩተሮቻችን ኪቦርድ ማን ቆለፈው ? የቅስም ቀውሱን ድንዛዜውን ማን አጋባብን ? አንገታችንን ማን አደነደነው ? ልባችንን ማን ደፈነው ? ይሄ ሁሉ ኬሬዳሽነት ከየት መጣ ? ስንል ቆመን የምናስብበት ወደቀልባችን የምንመለስበት ወሳኝ ሰዓት ላይ እንገኛለን::
ጥቂቶች ስማችንን ማንነታችንን ነጥቀው በስማችን በማንነታችን የሚፈፅሙትን ግፍ ወንጀል በድፍረት ከአሁን በኋላ በቃ ! Enough is Enough ! «በእኛ ስም አይሆንም :: » በማለት የተነጠቅነውን ስማችንን ማንነታችንን ምርኳችን ካላስመለስን እንደ አገርም ሆነ እንደ ሕዝብ የተደቀነብንን አደጋ በቀላሉ መሻገር ይቸግረናል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እንዳስጠነቀቁት፤ «ጽንፈኝነትን በጊዜ ታግለን ካላስወገድነው ወደ መጨራረስ እንደሚወስደን ጉልሕ ማሳያ ነው ።»
እንዲሁም በፌዴራል በክልል በግልና በድርጅት መደበኛ ሚዲያ ማለትም በህትመትና በኤሌክትሮኒክስ ( በጋዜጣ ፣ በሬዲዮ ፣ በቴሌቪዥን ) በማንነታችን በስማችን ከአንድነት ይልቅ ልዩነት ከፍቅር ይልቅ ጥላቻ ከእርቅ ይልቅ ጥል ከመተባበር ይልቅ መፎካከር ከመነጋገር መኳረፍ ከመቀባበል መገፋፋት ሲቀነቀን ሲለፈፍ ሰምተን እንዳልሰማን አይተን እንዳላየን አንብበን እንዳላነበብን ያለፍነው ጽንፈኝነትና አክራሪነት ዛሬ በአገራችን ለተቀለሱት የጭፍን ጥላቻ የቂም የዘውጌ’ዊነት የደባ ፖለቲካ የመጠራጠር የመጠላለፍ መሪን የመብላት ጎጆዎች ዋልታና ማገር አቀብለዋል::
ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም መጀመሪያ በባህር ዳር በኋላ በአዲስ አበባ የተፈፀመው ጀብደኛ ግድያ የዝምታችን የድንዛዜአችን የግዴለሽነታችን የዕንዝህላልነታችን ከፍታ ጡዘት climax ማረጋገጫ ማሳያ ነው:: የቀጣይ አካሄዳችን የታሪካችን ወሳኝ መታጠፊያ ነው:: ከእያንዳንዱ የግጭት መካረር ጡዘት በኋላ የሁኔታዎች መቀየር የግድ መሆኑን መቀበል ተፈጥሮአዊም ሰዋዊም ነው:: ስለሆነም ድምጻችንን ከፍ አድርገን «በእኛ ስም አይሆንም:: » የምንልበት ቀን አፍጥጦ ደጃችን ላይ ደርሷል:: ቀኑን በአግባቡ መጠቀምም ዘመኑን የሚመጥን የሚዋጅ እርምት በጊዜ የለም ስሜት መውሰድ ደግሞ የቀረን ብቸኛ ካርድ ነው::
ከላይ ለማሳየት እንደሞከርሁት በስማችን በማንነታችን የሚነዙ ጽንፈኝነቶች፣ አክራሪነቶች፣ የጥላቻ መርዞች የደባ ፖለቲካ ሴራዎች የሚንበለበሉ የቂም ፍላጻዎች በጊዜ ባለመመከታቸው ዛሬ ጎልምሰው ተቋማዊ፣ ሥርዓታዊ ፣ መዋቅራዊ ሆነዋል :: ስለሆነም የሚመጥን ሕጋዊና ተቋማዊ እርምጃ የመውሰጃ ትክክለኛው ጊዜ ላይ ደርሰናል:: ኧረ እንዲያውም አርፍደናል::
አሜሪካውያን መብታቸውን ተጠቅመው በነፃና ዴሞክራሲያዊ ሂደት በድምጻቸው የሾሙት መንግሥት እንኳ ከአንዴም ሁለት ሦስቴ ያሰመሩለትን ቀይ መስመር ጥሷል ብለው ባመኑ ጊዜ አደባባይ ወጥተው «በስማችን አይሆንም:: » ብለውታል :: አሜሪካ ተገድጄ ገባሁበት በምትለው 2ኛው የዓለም ጦርነት በጃፓን የሔሮሽማና ነጋሳኪ ከተሞች የመጀመሪያውን የአቶሚክ ቦምብ ጥቃት ሲፈፅም:: በአሜሪካ የሚገኙ ጃፓናውያንንና ትውልደ ጃፓን አሜሪካውያንን ለደህንነቴ ያሰጉኛል በማለት በማጎሪያዎች ሰብስቦ ሲያጉር:: ቬትናምን ሲወር:: የመስከረም 1ዱን የአልቃይዳ የሽብር ጥቃት ተከትሎ ጆርጅ ደብሊው ቡሽ «ከእኛ ጎን ትቆማላችሁ አልያም በእኛ ላይ ተነስታችኋል:: » በማለት ኢራቅን አፍጋኒስታንን በወረሩ ወቅት አብዛኛው አሜሪካዊ አደባባይ በመውጣት ድምፁን ከፍ አድርጎ «በእኛ ስም አይሆንም:: » በማለት በመንግሥታቸው ላይ ጫና በመፍጠር ለውጥ አምጥተዋል::
ወደ አገራችን ስንመጣ በእኛ ላይ ራሳቸውን በጎበዝ አለቅነት የሾሙ በጣት የሚቆጠሩ ግለሰቦች፣ የመብት ወትዋቾች ፣ ጦማሪያን ፣ ሚዲያ ተብዬዎች በኢትዮጵያዊነታችን አልያም በማንነታችን ስም ትርምስ ቀውስ የእርስ በርስ ግጭት ጦርነት ዕልቂት ሲደግሱልን ዝምታን በመምረጥ የጥፋታቸው ተባባሪ እየሆንን ነው:: ትናንት በመሐል ሜዳ ከዚያ በፊት በአዲስ አበባ ፣ በጅግጅጋ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ በስማችን ለተፈፀመው ግፍ ፣ ሞት ፣ መቁሰል ፣ መነቀል በዝምታ ስለተመለከትን ሁላችንም ተጠያቂዎች ነን :: አዎ ! ወደድንም ጠላን ከግፈኞች ይልቅ ግፉ ሲፈፀም አይተው እንዳላዩ ሰምተው እንዳልሰሙ ሆነው ዝምታን የመረጡም ተጠያቂዎች ናቸው እንደሚባለው ከላይ እንዳልሁት በቀጣይ ትውልድ ታሪክ ይጠይቀናል ::
«ዛሬም በእኔ ስም አይሆንም !»
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 23/2015