/የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ «ጦርነት ይብቃ፤ ሰላምን እናጽና» በሚል መሪ ሀሳብ በተካሄው ሰላም የማፅናትና የዕውቅና መርሐ ግብር ላይ ያስተላለፉት መልእክት ሙሉ ቃል /
“ከፌዴራል መንግሥት ጋር የጀመርናቸው መልካም ግንኙነቶች በአጭር ጊዜ ውስጥ አዎንታዊ በሆነ መልኩ ትልቅ ደረጃ ላይ እንደሚደርሱ እምነታችን የፀና ነው። ከሁሉም አካባቢዎች የሚነሱና የሚመጡ እገዛዎችን የመጠቀም ባሻገር፤ ከምንም ነገር በላይ በጋራ መልማት፣ ሰላማችንን ማጠናከር የጋራ ዕጣችን መሆኑን አውቀን መንቀሳቀስ መቻል አለብን” ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳን ሙሉ ንግግር እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
የተከበሩ ዶክተር ዐቢይ አሕመድ፣ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የፌደራል መንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፤ የተከበሩ ሙሳ ፋቂ መሃማት፣ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር፤ የተከበሩ ቺፍ ኦሊሴንጎ ኦባሳንጆ፣ የአፍሪካ ኅብረት ከፍተኛ ደረጃ ፓናል ሰብሳቢ፤ የተከበሩ ኡሁሩ ኬኒያታ፣ የኬኒያ የቀድሞ ፕሬዚዳንት እና የፓናሉ አባል፤ የተከበሩ ዶክተር ሙፉዚሌ ምላንቦ፣ የደቡብ አፍሪካ የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የፓናሉ አባል፤ ሁላችሁም ወንድሞች እና እህቶች፣ ከፕሪቶሪያ ስምምነት መፈረም በኋላ በርካታ መሻሻሎችን አሳይተናል። ይህንን መሻሻል ለማየት፣ ወደዚህ የደረስንበትን ርቀት ለማየት፣ የቀሩንን ለማጠናቀቅ በግልጽ እዚህ መድረክ ላይ እንደተገለጸው ጦርነት ይብቃ ማለት አንድ ነገር ሆኖ፤ ሰላማችንን ማጽናት የእንዳንዱን ሰው ጥረት የሚጠይቅ ስለሆነ ይህንኑ ለመፈተሽ ፤ ይህንኑ ለማጠናከር የሚያስችል መድረክ ስለተዘጋጀ ያዘጋጁትን የሥራ ኃላፊዎች እና የኢፌዴሪን መንግሥት በዚህ አጋጣሚ ማመስገን እፈልጋለሁ።
ላለፉት ሁለት ሦስት ዓመታት እጅግ ደም አፋሳሽ ጦርነት ውስጥ አልፈናል። ሕጻናት አልቀዋል፤ ሴቶች፣ ሁሉም አይነት ተዋጊዎች ብቻ ሳይሆኑ ውጊያ ውስጥ ያልነበሩ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች አልቀዋል። ቅድም አንዳንድ ተናጋሪዎች ሲሉት እንደነበረው ልዩነቶቻችንን በሰለጠነ መንገድ መፍታት ሲገባን ጠመንጃ የመነቅነቅ አባዜ በርካታ መቶ ሺዎችን አስከፍሎናል ብቻ ሳይሆን ይህ ነገር ባይፈጠር ኖሮ ልንደርስበት እንችል የነበረ የእድገት ደረጃ ፣ የመረጋጋት ደረጃ ፣ የተሰሚነት ደረጃ፣ ወደ ኋላ እንዲመለስ በማድረግ ትልቅ አስተዋፅዖ አድርጓል።
በትግራይ በኩል ከፕሪቶሪያ መፈረም በኋላ ቺፍ ኦባሳንጆም እንደተናገሩት መፈረም አንድ ነገር ሆኖ ሰላሙ እንዲጸና ማድረግ እጅግ ወሳኝ ስለሆነ በርካታ ሥራዎች ተሠርተዋል። በመሠራታቸው ምክንያት የትግራይ ሕዝብ አሁን እየታየ ያለውን የሰላም ተስፋ ወደ ኋላ ሊመለስ የሚችል ምንም አይነት ነገር የሚታገስ ሕዝብ አይደለም። በእያንዳንዷ ደቂቃ፤ በእያንዳንዷ ሰከንድ ሰላሙ እንዲሰፋ፤ አሁንም በአንዳንድ አካባቢዎች የሚታዩ ችግሮች ሙሉ በሙሉ ተቀርፈው ወደ ተሟላ ኑሮው እንዲመለስ እንጂ፤ በአንድ ወይም በሌላ መልኩ ጥይት እንዳይተኮስ አሁን ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ይዘጋ ብለን የወሰንነው ጦርነት በአንድ ወይም በሌላ ምክንያት ወደ ኋላ እንዲመለስ ፍጹም ፈቃደኝነት የለውም።
ስለዚህ የፕሪቶሪያ ስምምነት ብዙ ያመጣቸው ለውጦች አሉ። እንደተባለው ከፕሪቶሪያ መፈረም በኋላ የድፍረት ርምጃዎች የተወሰዱባቸው አጋጣሚዎች አሉ። በዚህ አጋጣሚ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሂደቱ እንዲፋጥን በማድረግ የወሰዷቸውን ድፍረት የተሞላባቸው ርምጃዎች በዚህ አጋጣሚ ሳላደንቅ ባልፍ ንፉግነት ነው የሚሆነው። እነዚህ ድፍረቶች አሁንም መቀጠል መቻል አለባቸው። ድፍረት በሚያንሰን ሰዓት የሚያግዙን እነዚህ ድፍረቶች ስለሆኑ። ከፕሪቶሪያ በኋላ ብዙ ለውጥ ታይቷል። የሚቀሩ ጉዳዮች አሉ።
አሁንም በጋራ ሆነን መጀመሪያ የነበረን የመተማመን መንፈስ እጅግ በጣም ዝቅተኛ ነበር። ቀስ በቀስ ወደ ተሻለ የመተማመን መንፈስ እያሳደግነው መጥተናል። ይሄ የመተማመን መንፈስ ሌሎች አግዘውን የመጣ እንዳልሆነ በግልጽ መታወቅ መቻል አለበት። በመቀራረባችን፣ ሰላም አማራጭ የሌለው መሆኑን በመቀበላችን የመጣ መሆኑን ማወቅ ያስፈልጋል። ይሄ ማለት እዚህ ያሉ ወገኖች በተደጋጋሚ የሠሩትን ጥረት ለማሳነስ ሳይሆን፤ ወደፊትም ከጎናችን ሆነው የጀመርነውን እንድናጠናቅቅ በአፍሪካዊ የወንድማማችነት መንፈስ የጀመሩትን እስከመጨረሻው እንደሚቀጥሉበት ከጎናችን እንደሚሆኑ እምነቴን በዚህ አጋጣሚ መግለጽ እፈልጋለሁ።
እዚህ ውስጥ የተሳተፉ ታዛቢዎች አሉ፤ ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ፣ ማይክ ሃመር፣ሃና ቴተህ፣ አምባሳደር ባንኮሌ፣ ሁላችሁም በቀጣይ ሂደት ውስጥ የራሳችን የመተማመን መንፈስ ሰላምን የማጽናት ሥራ የኛና የኛ ሥራ ቢሆንም፤ የጀመርነውን እስክናጠናቅቅ ግን ወደፊትም ሀገራችን የጠፉ ማኅበረሰቦቻችንን፣ የፈራረሱ ተቋሞቻችንን ለመገንባት በምናደርገው እንቅስቃሴ ውስጥ፤ በሀገር ደረጃ ፍትሕን ለማስፈን በምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ውስጥ ሁሉ ከጎናችን እንደምትሆኑ በዚህ አጋጣሚ ያለኝን እምነት ለመግለጽ እፈልጋለሁ።
የትግራይ ሕዝብ ጦርነት ሰልችቶታል፤ ጠመንጃ የመነቅነቅ አባዜ በፍጹም አይኖረውም። በዚህ አጋጣሚ ከትግራይ ይዤ የመጣሁት የሰላምና የፍቅር መልዕክት ብቻ ነው። አሁንም ከአራት ዓመት በላይ ትምህርት የሚባል ያላዩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ልጆች አሉን፤ ትምህርት ቤት መግባት መቻል አለባቸው። አሁንም በ100 ሺህ የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች አሉን የኔን ወላጆች ጨምሮ መመለስ መቻል አለባቸው፤ ሥራቸውን መሥራት መቻል አለባቸው።
ሁሉንም ነገር ለሰላም በሚሆን መልኩ እናድርገው። ከጎረቤት ወንድም ሕዝቦች በተለይም ከአማራ እና ከአፋር ጋር ሊያጋጨን የሚገባ ነገር ሳይኖር ግጭት ተፈጥሮ በሁላችንም ዘንድ ታሪክ ይቅር ሊለው የማይችል ብዙ ጥፋት ተፈጽሟል። ይሄንን ነገር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ዘግተን ቋንቋችንን የሰላምና የመከባበር፣ ልዩነቶቻችንን በመከባበር፣ በመቻቻል እና በሕግ ብቻ ለመፍታት ዝግጁ ሆነን እስከሠራን ድረስ በጋራ ሀገራችንን ከመገንባት አልፈን በሁለቱም በሦስቱም ጎረቤት እህትማማች ወንድማማች ሕዝቦች መካከል ተፈጥሮ ያለውን መቃቃር የሚመስል ስሜት አስወግደን ወደ ተሻለ ደረጃ የማናደርስበት ምክንያት የለም ።
ፊት ለፊት አያቸዋለሁ ሐጂ አወል ትናንት ለመጀመሪያ ጊዜ ከዓመታት በኋላ ሀገር አቋራጭ አውቶብስ በአፋር በኩል አልፏል። በአፋር በኩል ማለፉ ትልቅ ነገር ነው። ሀገር አቋራጭ አውቶቡሶች ከአማራ ክልል በምንዋሰንባቸው በሁሉም አካባቢዎች፣ በሁሉም አቅጣጫዎች ማለፍ መቻል አለባቸው። ዶክተር ይልቃል ይሄ ኃላፊነት የአንተ ኃላፊነት ብቻ ሳይሆን የሁላችንም ኃላፊነት እንደሆነ በዚህ አጋጣሚ መግለጽ እፈልጋለሁ።
እንዳልኩት ከሚለያዩን ይልቅ አንድ የሚያደርጉን ነገሮች ይበልጣሉ። ፖለቲከኞች የሰላም ቋንቋ ማውራት መቻል አለብን። በአንድም ይሁን በሌላ መልኩ መርዝን የተፉ አንደበቶች ሰላምን፣ ፍቅርን መስበክ ሲጀምሩ እንደማየት የሚያስደስት ነገር ሊኖር አይችልም። ይሄንን ካደረግን አብዛኛውን የግጭት ምክንያት የምንፈታው ይመስለኛል። የሚያቃቅሩን የሚመስሉት አሁንም በሕግ እና በሕግ ብቻ መፍታት ያሉብን በርካታ ነገሮች ያሉ ቢሆንም፤ እንዳልኩት መድፈር ነው የተሻሉ ውጤቶችን ሊያመጣልን የሚችለው ደፍረን የማይደፈሩ የሚመስሉ ሥራዎችን ሰርተን ወደፊት መቀጠል እንደምንችል ማሳየት አለብን።
አሁንም በተደጋጋሚ ታዛቢዎች ያሉት ነገር አለ፤ በተደጋጋሚ የአፍሪካ ወንድሞቻችን የፓናሉ አባላት ያሉት አለ፤ ኢትዮጵያ ከዚህ በተሻለ ሰላሟን ያጣች አገር ሳትሆን ለጎረቤት አገር ሰላም የምትደርስ አገር መሆን ይኖርባታል። ይህን ማድረግ የሚያስችል ሁላችንም አቅማችንን ማስተባበር ይጠበቅብናል።
ይህን ለማድረግ ግን በውስጥ የሚከሰቱ ችግሮቻችንን በሰለጠነ መንፈስ ለመፍታት ያለን ዝግጁነት ለአንድ ወይንም ለሌላ አካባቢ የሚተው ሳይሆን፤ ሁሉም ግጭት የሚታይባቸው አካባቢዎችን የሚመለከት መሆን መቻል አለበት። ያው በነካ እጁ ዶክተር ዐቢይ ሌሎች አካባቢዎች የሚታዩ ግጭቶች ምልክቶችንም በሆደ ሰፊነት መንገድ በድፍረት ለመፍታት እንደሚንቀሳቀስ፤ ይህን ለማድረግ በሚደረገው ጥረት እኛም የበኩላችንን እንደምናደርግ በዚሁ አጋጣሚ መግለፅ እፈልጋለሁ።
ኢትዮጵያ ትልቅ ደረጃ ላይ የመድረስ፣ የሕዝቦቿን ሁሉን አቅም ተጠቅማ መልሳ ለሕዝቦቿ መልሳ የምትሰጥ ሀገር የመሆን አቅማ እጅግ ከፍተኛ ነው። ይህን ከፍተኛ አቅም እውን ለማድረግ የሚቻለንን ሁሉ ማድረግ መቻል አለብን። አሁንም ደግሜ ደጋግሜ እንደምለው የትግራይ ሕዝብ ጦርነት ሰልችቶታል፣ አንገሽግሾታል ብቻ ሳይሆን ሌሎች አካባቢዎች የሚወሰዱ ሕፃናትን ወደ ትምህርት ቤት በሰዓቱ ማድረስ መመለስ፣ማረስ ፣ማለስለስ፣ ማጨድ፣ መዝራት የሚባሉ ነገሮች ይናፍቁታል። ፈጥነን ወደ እዚህ መመለስ አለብን። ለዚህም የሁሉንም አቅም
መጠቀም ያስፈልጋል። ከምንም ነገር በላይ ጠንካራ ሠራተኛ የሆነው የትግራይ ሕዝብ ተመልሶ ወደ ሥራው ተሰማርቶ የሰላም ችግር ሳይሆን ምን ያህል አተረፍኩ? ምን ያህል አመረትኩ? በሚል ፉክክር ውስጥ እንዲገባ ለማስቻል የጀመርነውን ጥረት አጠናክረን የምንቀጥል ይሆናል።
ሁሉም ክልሎች የዚህ ተግባር ተሳታፊ እንደሚሆኑ እምነቴ የፀና ነው። ከፌደራል መንግሥት ጋር የጀመርናቸው መልካም ግንኙነቶች በአጭር ጊዜ ውስጥ አዎንታዊ በሆነ መልኩ ትልቅ ደረጃ ላይ እንደሚደርሱ እምነታችን የፀና ነው። ከሁሉም አካባቢዎች የሚነሱና የሚመጡ እገዛዎችን የመጠቀም ጉዳይ ሳይሆን ከምንም ነገር በላይ በጋራ መልማት፣ ሰላማችንን ማጠናከር የጋራ ዕጣችን መሆኑን አውቀን መንቀሳቀስ መቻል አለብን። ይህን ለማድረግ በበኩላችን ዝግጁዎች ነን።
በመጨረሻ ማንሳት የምፈልገው ነገር ሰላም በመፈክር ብቻ እንደማይመጣ አውቃለሁ። ቢያንስ ቢያንስ ግን የሰላምን ቋንቋ መናገር መጀመር፣ ቢያንስ ቢያንስ ግን የፍቅር ቋንቋ መናገር መጀመር በዙሪያችን ሊከሰቱ የሚችሉ ግጭቶችን ቅድም በሙዚቃ ድራማው ላይ እንደነበረው ከይዋጣልን መንፈስ ወጥተን በመረዳዳትና በሰለጠነ መንገድ ለመፍታት የሚያስችሉ ከባቢዎችን ለመፍጠር ስለሚያግዝ ሁላችንም እንደ ፖለቲካ መሪዎች ብቻ ሳይሆን እንደ ጸሐፍት፣ እንደ ተዋናይና እንደጋዜጠኞች መልካም ቋንቋን መለማመድና የየቀን ቋንቋችን የማድረግ ጥረት መጀመር አለብን የሚል እምነት አለኝ።
በዚህ አጋጣሚ በትግራይ ሕዝብና በራሴ፤ በጊዜያዊ አስተዳደሩ ስም ሰላም እንዲፀና እና ጦርነት እንዲበቃ የወሰነውንና የፈረምነውን ያህል፤ መልካም መሠረት እንዲይዝና ሰላም እንዲፀና ሁላችንም የበኩላችንን ጥረት እንደምናደርግ በዚህ አጋጣሚ እምነቴን ማረጋገጥ እፈልጋለሁ። አክባሪ ይስጥልኝ፤ አመሰግናለሁ።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 19/2015