ቁምላቸው አበበ በአማራ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፤ በደቡብ መገናኛ ብዙኀን፤ በጋዜጠኝነትና በታሪክ ባለሙያነት ያገለገሉ ሲሆን፤ የደቡብ ኤፍ ኤምን ከባልደረቦቻቸው ጋር በመሆንም አቋቁመዋል።በፌዴራል ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅትና በአለ በጅምላ በኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተርነት አገልግለዋል። ከአአዩ በቋንቋና ታሪክ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን የሰሩ ሲሆን፤ በዚሁ ዩኒቨርሲቲ በጋዜጠኝነትና ኮሙዩኒኬሽን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በማጠናቀቅ ላይ እያሉ ባጋጠማቸው ድንገተኛ ህመም ተስተጓጉሏል። ጥልቅ ሀሳብ ያዘሉ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ፁሑፎችን በማህበራዊ ሚዲያና በተለያዩ ጋዜጦች በማውጣት ይታወቃሉ።
መኃልየ-መኃልይ ዘሰሎሞን ከሁሉም የሚበልጥ የሰለሞን መዝሙር ማለት መሆኑን በዚህ ዓምድ ደጋግሜ የገለጽሁ ቢሆንም ዛሬም የመጣጥፌ ርዕስ ማድረግን ስለመረጥሁት ለማስታወስ እወዳለሁ። የሁለት ፍቅረኛዎች ንግግር ተደርጎም ይወሰዳል። የፍቅረኞች ንግግር በግጥም ነውና ምት፣ዜማ አለው። ሰለሞን ስለ ሙሽራውና ሙሽሪት ፣ ስለፈጣሪና ስለ ቤተ ክርስቲያን የዘመራቸውን 1ሺህ 5 መዝሙሮችን ይመለከታል። ሙሽራው ልዑል እግዚአብሔርን ሲወክል ሙሽራይቱ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት።
መኃልየ እንደ ለዘብና ወረብ አይነት በፍጥነት የሚዘመር ጥዑም መዝሙር ነው። መዝሙሮቹ በተለያየ ስልት ዜማ ቢደጋገሙም ያው ስለፈጣሪና ቤተ ክርስቲያን ክብር ፣ ቅድስና የሚመሰክሩ ናቸው። ይህ መጣጥፍ ዛሬ ለምንገኝበት አንጻራዊ ሰላም ዋጋ የከፈሉ ግለሰቦችንና ተቋማትን የሚዘክር፣ የሚያወድስና የሚያከበር ሆኖ ስለአገኘሁት፤” መኃልየ-መኃልይ ዘ ሰላም ጀግና “ማለትን መርጫለሁ።
ለተደረሰው የሰላም ስምምነት እርሾና መሰረት ሆኖ ያገለገለውና ዛሬ ላይ ፍሬ ለማፍራቱ ዋናው ምክንያት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሰላምን ከአንገት ሳይሆን ከአንጀት መሻታቸው ነው፤ ይሄንን ደግሞ በፕሪቶርያው ስምምነትም ሆነ ከዚያ በኋላ በነበረው የትግበራ ምዕራፍ በቁርጠኝነት በመተግበር አረጋግጠዋል። ስለሆነም ዛሬ ለምንገኝበት አንጻራዊ ሰላም ያበቁንን ጠቅላይ ሚኒስትሩንና ጥምር ኃይሉን “መኃልየ-መኃልይ ዘ ጠቅላይ ሚኒስትሩና ጥምር ኃይሉ፤”ብያለሁ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቅድመ ጦርነቱ፣ በጦርነቱም ሆነ በድኅረ ጦርነቱ ለሰላም ያላቸው ቁርጠኝነት ተከታታይነትና ወጥነት ያለው መሆኑ፤ ከአንዴም ሁለት ሦስት ጊዜ በተግባር አረጋግጠዋል። ከዚህም ባለፈ ለሰላም የሄዱበት ርቀት፤ ጦርነት የመንግሥታቸው ፍላጎት እንዳልሆነና ፍላጎታቸው ልማትና ብልጽግና እንደሆነ መወትወታቸው፤ መንግሥታቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለመደራደር ዝግጁ መሆኑን መግለጻቸው፤ ሕወሓት ለሰላም እድል ፈንታ እንዲሰጥ አድርጎታል። ለሰላም ያላቸው ፍላጎት በአፍሪካ ኅብረት ፣ በምዕራባውያንና በዓለምአቀፉ ማኅበረሰብና ተቋማት ዘንድ ሳይቀር እውቅና ማግኘቱ ሌላው ምክንያት ነበር።
እንደ የኢትዮጵያ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ድርድር፤ “ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ” የሚል ዘመኑንና ትውልዱን የዋጀ መርሕ የኅብረቱን ተቋማት ያነቃቃና እውቅና የሰጠ ታሪካዊ አጋጣሚ ሲሆን፤ ኅብረቱንም የድርድሩ አስኳል እንዲሆን አደፋፍሮታል። የምዕራባውያን ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነትን ማስቀረት ከመቻሉ ባሻገር ምዕራባውያን ሳይወዱ ይሄን መርሕ እንዲቀበሉ አስገድዷቸዋል።
ምዕራባውያን የመንግሥትን የሰላም ቁርጠኝነት ለመቀበል ጊዜ ቢወስድባቸውም ፤ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋቂ መሐመት በወቅቱ መንግሥት ጦርነቱን በሰላም ድርድር ለመቋጨት ያሳየው ቁርጠኝነት ይበል የሚያሰኝ ነው በማለት የምዕራባውያንን በስጋት ላይ ያነጣጠረ የስጋት ደመና ገፈዋል። የአፍሪካ ኅብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ “የጠየቅኩትን ትኩረት ሰጥተውኛል። በሚገባው ልክ አስተናግደውኛል። አደራዳሪነቴን ተቀብለውኛል። “ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሰላም ያላቸውን ቁርጠኝነት መስክረዋል። ወደ አደራዳሪዎች ስንመለስ ደግሞ በተለይ የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ኦባሳንጆ በታሪክ ድርሳናችን በወርቃማ ብዕር ተጽፎ ሲዘከር ይኖራል።
የአደራዳሪዎች ሚናም በቅጡ እውቅና ሊቸረው ይገባል። የአፍሪካ ኅብረት “ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ” የሚለውን መርሕ አበክሮ በመቀበል የሰላም ድርድሩን በመምራትና በማሳለጥ የአንበሳውን ድርሻ ቢጫወትም የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ተደጋጋሚ ጥረት ግን ከፍ ያለ ነው። በዚህ እድሜያቸው በማይመች ሁኔታ በተደጋጋሚ ወደ አዲስ አበባና መቀሌ በመመላለስ ስምምነቱ እውን እንዲሆን ያበረከቱት አስተዋፅዖ ምንጊዜም ሀገራችን አትረሳውም።
ከ10 ተከታታይ ቀናት እልህ አስጨራሽ ጥረት በኋላ ፕሪቶሪያ ላይ የሰላም ስምምነቱ ሲፈረም ኦሉሴጎን የተፈጠረባቸው ስሜት በራሱ ብዙ ይናገራል። የቀድሞው የኬኒያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬኒያታና የደቡብ አፍሪካ የቀድሞዋ ፕሬዚዳንት ፉምዚል ማምቦ ንጉካ አበርክቶም በልኩ እውቅና ሊቸረው ይገባል።”መኃልየ-መኃልይ ዘ ኦባሳንጆ” ብያለሁ።
ከሁሉም በላይ ለአፍሪካዊ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔ የሚለው መርሕ አፍሪካውያን ያለማንም ጣልቃ ገብነት ችግሮቻቸውን መፍታት እንደሚችሉ ከማረጋገጡ ባሻገር በትልቅ የእንችላለን መንፈስ የተመራ የሰላም ፍኖተ ካርታ ነው። በትግራይ ፣ በአማራና በአፋር ክልሎች የደረሰው ውድመት ከብዙ መቶ ቢሊዮኖች በላይ የሚገመት ነው ማለት ይቻላል። መቶ ሺዎችንም ለሞት ፤ ከቤት ንብረታቸው ያፈናቀለ ነው። የሰላም ስምምነቱ እንግዲህ ይሄን አውዳሚና ዘግናኝ ጦርነት ነው ያስቆመው።”መኃልየ ዘ አፍሪካ ኅብረት”ብያለሁ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የተደረሰውን የሰላም ስምምነት አስመልክቶ በወቅቱ በአርባ ምንጭ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ላይ እያሉ ባስተላለፉት መልዕክት፤”… አሁንም ለሰላም ላባችንን ብናፈስ፣ በጦርነት የወደሙብንን አካባቢዎች መልሶ ለመገንባት ካለን ላይ ብናዋጣ እናተርፋለን እንጂ አንጎዳም። በሙሉ ልብ ትግራይንና የትግራይን ሕዝብ ለመገንባት ወደቀደመው የሀገር ስሜት ለመመለስ አብረን እንድንቆም በታላቅ ትህትና እጠይቃለሁ፤ …” ብለዋል። የዛሬ ሁለት ዓመት አካባቢ ማለትም ከሰሜን ዕዝ ጥቃት በኋላ ጀግናው የመከላከያ ሠራዊት ትግራይን ሙሉ በሙሉ በተቆጣጠረበትና ጊዜያዊ አስተዳደር በተቋቋመበት ለክልሉ መልሶ ማቋቋም ቀድመው የደረሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ነበሩ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ከመጽሐፋቸው ሽያጭ 200 ሺ ብር ከአንድ ወር ደመወዛቸው ጋር እንዲሁም ሦስት ቦቴ መኪናዎችን ለንጹሕ መጠጥ ውሃ ማመላለሻ ለግሰዋል። የፌዴራሉ መንግሥት ደግሞ ለመልሶ ግንባታ ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጓል። የኦሮሚያ፣ የጋምቤላ፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች 282 ሚሊዮን ብር መቐሌ በመገኘት በመለገስ አለኝታነታቸውን አረጋግጠዋል። የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስቴር በተለይ ለትምህርት ዘርፉ መልሶ ግንባታ 320 ሚሊዮን ብር በጀት አዙሮ እየሠራ ነበር። ከዚያ በፊት የአፋርና ሌሎች ክልሎች እንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የተለያዩ ተቋማት ለትግራይ ሕዝብ የገንዘብና የተለያዩ የዕለት ደራሽ ድጋፎችን አድርገዋል።
የፌዴራል መንግስት ከ4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ወገኖች እርዳታ ያቀረበ ሲሆን፤ ዓለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅቶችም የጩኸታቸውን ያህል ባይሆንም መጠነኛ ድጋፍ ማድረጋቸው አይረሳም። ይህ አኩሪ የተቀናጀ ርብርብ ዜጎችን ከረሀብና ከጠኔ ከመታደጉ ባሻገር የትግራይ ሕዝብ በክፉ ቀኑ የሚደርስለት አለኝታ መንግሥትና ወገን እንዳለው ያረጋገጠ ነበር። ዕጣ ፈንታውና መጻዒ እድሉ ከኢትዮጵያ ጋር መሆኑንም ያስመሰከረ ሠናይ ተግባር ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ መሪነት ከመጡበት ሰዓት አንስቶ በትግራይ ክልል ይህ ቀውስ እንዳይቀሰቀስ ትሕነግን ለማግባባት ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም። ያላደረጉት ጥረት የለም። እውነት ለመናገር የሰላምን ውድ ዋጋ እንደ እሳቸው አበክሮ የተረዳ አልነበረም። ከበዓለ ሲመታቸው የፓርላማ የመጀመሪያ ንግግር እስከ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ያላደረጉት ጥረት አልነበረም።
ለሰላም ካላቸው ቁርጠኝነትና ጦርነት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ በውትድርና ሕይወታቸው ጠንቅቀው ስለሚያውቁት፤ ጓደኞቻቸውንና ወንድማቸውን ስለነጠቃቸው፤ ጦርነት የሀገርን ኢኮኖሚ ምን ያህል እምሽክ ድቅቅ እንደሚያደርግና እንደሚያወድም አበክረው ስለተገነዘቡና የ117 ሚሊዮን ሕዝብ መጻኢ እድልን እንደሚወስን በመረዳታቸው፤የትግራይ ሕዝብም ጦርነት ይበቃዋል በሚል እምነት እንዲሁም ለትግራይም ሆነ ለሌሎች ሕዝቦች ደህንነት ሲሉ እስከ መጨረሻው ሰዓት ሆደ ሰፊነትንና ትዕግስትን መርጠዋል።
ሀገሪቱን ከጠብመንጃ አዙሪት ለማውጣትና ከዚህ ቀደም የነበሩ ገዥዎች ያልሄዱበትን የሆደ ሰፊነትና ቁጭ ብሎ የመነጋገር መንገድ በመምረጣቸው በልኩ እውቅና ሊሰጣቸውና አብዛኛው ዜጋ ከጎናቸው ሊቆም ሲገባ መንግሥታቸው በልፍስፍስነት ከመወቀሱ ባሻገር ፓርቲያቸውም ሆነ እሳቸው ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ ደጋፊያቸውና ተከታያቸው ብዥታና ድንጋሬ ላይ እንዲወድቁ አድርጓል።
ሰከን ብሎ ለተረዳው ግን ለሰላም ያላቸው ቁርጠኝነት የሀገራችንን ፖለቲካና ታሪክ እንደ አዲስ የሚበይን ፤ የሀገሪቱን ሕልውና በጽኑ መሠረት ላይ የሚያኖር እና መጻዒ ዕድሏን ወገግ የሚያደርገው ነው። በሰላሙ ግንባር ለተመዘገበው ድል የእሳቸው፣ የደጀኑ ሕዝብና በየደረጃው ያለው ወታደራዊና ሲቪል አመራር የተንሰላሰለና የተቀናጀ ብልህ አመራር በመስጠቱ መሬት ላይ በተቀዳጀነው ወታደራዊ ድል የተገኘ መሆኑን ከፍ ብሎ ለመግለጽ ተሞክሯል።
በአጠቃላይ ለቀጣይ ልማታችን ዋንኛ መሠረት የሆነውን ሰላማችንን በግርግር እንዲመጣ በየትኛውም መልኩ አስተዋፅዖ ያደረጉ አካላት ሁሉ ምስጋና ይገባቸዋል፤ በዚህም በተለመደ የማመስገን ባሕላችን ከልባችን እናመሰግናለን። ለሰላማችን ያበረከቱልን ጥልቅ አስተዋፅዖ በሰላም ግንባታ ታሪካችን ውስጥ ከፍ ያለ ስፍራ ይኖረዋል። መኃልየ-መኃልይ ዘ ሰላም ጀግና!።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ማክሰኞ ሚያዝያ 17 ቀን 2015 ዓ.ም