የሰው ልጆች ሕይወት በፈተና የታጀበ እንደመሆኑ መጠን በኑሮ ውጣ ውረድ ውስጥ ማለፍን ይጠይቃል። ኑሮ በአንድ በኩል ሲሞላ፤ በሌላ በኩል እየጎደለ ቀዳዳው እየበዛ ማግኘትና ማጣት እየተፈራረቁ የሚቀጥል ሂደት ነው።
በዚህ ረጅም የሕይወት ሰንሰለት ውስጥ ለማለፍ ደግሞ አንዱ ሲደክም፤ ሌላውን እየደገፈ በመረዳዳትና በመተጋገዝ ሕይወትን ለማስቀጠል በአብሮነት መጓዝ የግድ ይላል። መረዳዳትና መተጋገዝ ደግሞ መልካምነት ብቻ አብዝተው የሚጠይቁ የበጎነት ተምሳሌት ናቸው።
በተለይ ኢትዮጵያውያን ዘንድ መረዳዳትና መተጋገዝ የማንነታችን መለያ የሆኑት እሴቶቻችን ናቸው። የኢትዮጵያ ሕዝብ ሃይማኖት፣ብሔርና ቋንቋ ሳይመርጥ ሁሉም በአንድ ዓይን እየተመለከተ ያለው ፤ የሌለውን እየደገፈ በመስጠትና በመቀበል ውስጥ በአብሮነት እጅ ለእጅ ተያይዞ ረጅም ዓመታት የኖረ ሕዝብ ነው ።
እነዚህ ኢትዮጵያዊ እሴቶቻችን ከማኅበረሰቡ ጋር አብረው የኖሩ ጎልተው የሚታዩ የሁል ጊዜ ተግባራት ናቸው። በበዓላት ወቅት ደግሞ ከሌላው ጊዜያት ለየት ባለመልኩ ይከወናሉ። ኢትዮጵያውያን በተለይ ለበዓላት የሚሰጡት ቦታ ትልቅ በመሆኑ በበዓል ወቅት ዘመድ ከአዝማዱ ፣ጓደኛ ከጎረቤት ሁሉም በአንድነት ተሰብሰቦ የሚገናኝበትና በዓል በጋራ የሚያከብሩበት እንደመሆኑ መጠን ዘመድ አዝማድ፣ ጠያቂና ደጋፊ የሌላቸው፣እጅ ያጠራቸውን ሰዎች መጎብኘት የተለመደ ነው።
የወደቁትን ማንሳት፣ የደከሙትን መደገፍ ሰው በመሆናቸው ብቻ የምናደርገው የሰብዓዊነት ተግባር መሆኑን ሁሉም ሃይማኖቶች ሲደግፉትና ሲያስተምሩ የኖሩት አስተምሮት ነው። ከሃይማኖታዊ አስተምህሮቶቻችን ባሻገርም መረዳዳትና መደጋገፍ ባሕል ሆኖ እንዲቀጥል አበው ‹‹መስጠት ለራስ ነው፤ መልሶ ይከፍላል›› እያሉ በሰዎች መካከል መረዳዳትና መደጋገፍ አስፈላጊ መሆናቸው ሲያስተምሩን ኖረዋል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉም ባለው አቅም እርስ በእርስ እየተሳሰበ፣እየተደጋገፈና እየተረዳዳ የመኖር ባሕልን ያዳበረ ነው።
ከጥንት ጀምሮ እስካሁን ድረስ ኢትዮጵያዊ ትስስሮቻችና አብሮነታችን የተጋመዱት በተግባር በምንኖራቸው እሴቶቻችንን ነው። በተግባር የሚገለጹት እሴቶቻችን ያለው የሌለውን በመርዳትና በመደጋገፍ እጅ ለእጅ ተያይዘው በአብሮነትና በአንድነት በመጓዝ እስካሁን ሊያዘልቁ ችለዋል።
በዚሁ ሳምንት በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት የተከበረው የኢድ -አልፈጥር በዓል በተለየ መልኩ ሁሉንም ባሳተፈ ሁኔታ መረዳዳቱና መደጋገፉ የሚጠናከርበት ጊዜ ነው። የኢድ-አልፈጥር በዓል የሙስሊሙ ማኅበረሰብ ቤት ያፈራው በጋራ ተቋደሶ እርስ በእርስ በመረዳዳትና በመደጋገፍ የሚያሳልፉበት ነው። አስታዋሽ ያጣን ወገን በማስታወስ ያለው ካለው ላይ ፤ የሌለውም ደግሞ ከዚያው ላይ ቀንሶ በመስጠት የወገን አለኝታነቱን የሚያስመሰክርበት ነው።
በተለይ በኢድ -አልፈጥር በዓል መረዳዳትና መደጋገፉ በብዙዎች ዘንድ የሚታይና የሚዘወተር ነው። ይህ በብዙዎች ዘንድ በጉጉትና በናፍቆት የሚጠበቅ በዓል የበርካቶች እጅ ሰደቃ(ምፅዋት) ለመስጠት በሰፊው የሚዘረጋቡት በመሆኑ በርካታ ድጋፍ የሚሹ ወገኖች በሚደረግላቸውም ድጋፍ የወገናቸውን የአብሮነት የሚያዩበት በጋራ ማዕድ የሚቋደሱበት የእርስ በእርስ ቁርኝነት የሚጠናከርበት ወቅት ነው።
በምንም ጊዜ ቢሆን መስጠትም ሆነ በመቀበል አዲስ ባይሆንም ከሌላው ጊዜ በተለይ መልኩ በአፅዋማትና በበዓላት ወቅት የሚመፀውቱ (የሚሰጡ) ሰዎች እጆች እጅግ በዝተው ይታያሉ። ሆኖም ግን የበጎነት ተግባር በአፅዋማትና በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን ሁልጊዜ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረግን ይገባል ።
በተለይ በሀገራችን በርካታ ድጋፍ የሚሹ ሰዎች ባሉበት በዚህ ወቅት አበው ‹‹ያለውን የሰጠ፤ ንፋግ አይባልም›› እንደሚሉት በአካባቢያችን ፣ በየጎረቤታችንን ያሉ እጅ ያጠራቸውን ፣ ድጋፍ የሚሹ ሰዎች መጎብኘት ሰብዓዊ ግዴታችን ነው ። ሰውን ለመርዳትም ሆነ ለመደገፍ የሚያስፈልገው ሰው መሆን ብቻ በመሆኑ አጠገቡ ያለ ድጋፍ የሚያስፈልገውን ወገናችን በመመልከት በተቻለ አቅም ከተረዳዳን ችግርን ሙሉ ለሙሉ መቅረፍ ባይቻልም ማቅለል እንችላለን።
‹‹ሰውን መርዳት ደስ ይለኛል፤ነገር ግን ምን አለኝና ምኔን ልስጥ፣ ምን ልደግፍ — ››የሚሉ ሰዎች በርካታ ናቸው ፤ ሰውን መርዳትና መደገፍ (መስጠት) ምንም አይነት መስፈርት ሳይስፈልገው ሰው የሆነ ሰብዓዊ ፍጡር ሁሉ ሊያከናወነው የሚችለው በጎ ተግባር መሆኑን የሥነልቦና ባለሙያዎች ይናገራሉ።
ባለሙያዎቹ እንደሚሉት፤ ሰውን ለመርዳት ሲያሰቡ አሁን ምን አለኝና ሲኖረን ነው መስጠት ያለብን ብለን የሚያሰቡ ሰዎች አስተሳሰባቸው ትክክል አይደለም። መስጠትና መቀበል ተፈጥሯዊ ክስተቶች እንደመሆናቸው መጠን በመስጠት ሰውን መርዳት መቻል ደግሞ ከሁሉም በላይ ጠቀሜታ ለሰጪው ሰው ነው። ሰውን የሚረዳ ሰው ሰውን በመርዳቱ ብቻ ውስጡ የሚፈጥረው ደስታ ከሁሉ በላይ ነው።
መስጠት ሆነ መቀበል ውስጥ በሰጪውም ሆነ በተቀባይ ዘንድ የሚፈጠሩት የደስታ ስሜት ቀላል የሚባል አይደለም። በሚሰጡም ሆነ በሚቀበሉ ሰዎች ዘንድ ያለው ታላቅ ስሜት ሌሎች ሰዎች ላይ እንዲጋባባቸውና እንዲረዱ በማድረግ ያስፈልጋል። በተለይ መስጠት እየፈለጎ እኔስ ምንአለኝና ምኔን ልስጥ ነው የሚሉ ሰዎች በቂ ትምህርት የሚያገኙበት ይመስለኛል።
ሰው ሆነው መስጠት የማይችሉ ነገር እንደሌላ በመረዳት መስጠት በገንዘብና ቁሳቁስ ከመለካት ባሻገር በጥልቀት ማየት ያስፈልጋል። ፍቅር በመስጠት፣ትንሽ ጊዜን አብሮ በማሳለፍ እና በተለያዩ ተነግረው የማያልቁ በጎ ምግባራት በመኖራቸውን ሰዎች መርዳት እንደሚቻል ትምህርት ሊያገኙ ይገባል ።
እነዚህ ለሌሎች አርአያ ሊሆን የሚችል የመረዳዳትና የመተጋገዝ እሴቶቻችንን እንዲህ በበዓላት ወቅት ፍንትው ብለው እንደሚታዩ ሁሉ እንዲሁ እንደአማረባቸው እንዲቀጥሉ ማድረግ ይገባል። በተለይ በተለያየ ምክንያት ድጋፍ የሚሹ ወገኖቻችን በበዙበት በዚህ ወቅት አለንላችሁ ማለት ከሁላችንም ይጠበቃል።
በኢትዮጵያ ለመብላት ከተዘጋጀው ምግብ 30 በመቶ የሚበላ ሲሆን 70 በመቶው የሚጣል እንደሆነ መረጃዎች ያመላክታሉ። ከዚህ ውስጥ ከሚበላው ይልቅ የሚጣለው በልጦ ይታያል። ታዲያ የአኗኗር ዘይቤያችንን በመቀየር በአግባብ መጠቀም ከቻልን አይደለም ለወገን ለሌላውም መትረፍ እንችላለን ባይ ነኝ።
ለወገን ደራሽ ወገን ነው እንደሚባለው ሌላ የውጪ አካል መጥቶ እንዲረዳን አንጠብቅምና እኛው ለእኛ አለኝታ መሆን አለብን። ምንም የሌላቸው ድጋፍ የሚፈልጉ ወገናችን ከጎናችን ቁጭ በላ መብላት የሚያስችል ሥነልቦና የለንምና መረዳዳትን ባህላችን አድርገን ልናስቀጥል ይገባል። ኢትዮጵያዊ የመረዳዳትና የመተጋገዝ እሴቶቻችን እንዲያብቡ ሁላችንም የበኩላችን ኃላፊነት መውጣት አለብን። በኢድ- አልፈጥር።
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ትንሳኤ አበራ
አዲስ ዘመን ማክሰኞ ሚያዝያ 17 ቀን 2015 ዓ.ም