የመደላድል ወግ፤
ከአገራዊ ብሂሎቻችን መካከል “ሰማይ ተቀደደ ቢሉት፤ ሽማግሌ ይሰፋዋል አለ ይባላል” የሚለው አገላለጽ በርግጥም የሰማይን ወርድና ርዝመት ያህል የገዘፈ መልእክት አምቆ እንደያዘ መረዳት ይቻላል። ዋናው የመልእክቱ ጭብጥ በሽምግልናና በንግግር የማይፈታ ችግርና ቅራኔ እንደሌለ ለማሳየት ነው። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የከበሩ የባህልና የትውፊት ፀጋ በታደሉ አገራት ዘንድ ለሽምግልና የሚሰጠው ክብር እጅግ የላቀ ነው። “ሽማግሌ ሲጠፋ የአገር ፊት በማዲያት ይጠቁራል” የሚባለውም ስለዚሁ ሳይሆን አይቀርም።
ሽማግሌዎች በተያዙት የእርቅ ሂደት ተው ሲባል ያልተወ፣ ይቅር ተባባሉ ሲባል ልቡን ያደነደነና በእምቢታው የጸና ግለሰብም ሆነ ቡድን ማሕበረሰቡ በአሜንታ ከተቀበለው ሥርዓት፣ ወግና ባህል ጋር የመጋጨት ያህል ስለሚታመንበት እንደ ቀድሞው በለመደው አኗኗር ልቀጥል ቢል በእጅጉ መቸገሩ አይቀርም። በይቅርታ የመቀባበልን ብርታት ለመግለጽ ሲፈለግም “ይቅር ለእግዜር ወድቆ አይሰበር፤ ሞቶ አይቀበር” እየተባለም ይሞካሻል።
“ልቡ ለቂም፣ ቃሉ ለበደል፣ እጁ ለመግደል” የጨከነና የበረታ ሰው እንኳን ቢሆን የአበው/እመው የማሸማገል እውቀትና ጥበብ ደንዳና ልብን ለመስበር፣ መራራ ቋንቋን ለማለዘብና ደም የነካ እጅንም ሳይቀር የመፈወስ አቅሙ ከፍ ያለ ነው። ስለዚህም ነው “እርቅ ደም ያደርቅ” እየተባለ በምሳሌ የሚነገረው።
ሰሞኑን በተከታታይ ያከበርናቸው የክርስትናና የእስልምና ሃይማኖታዊ ክብረ በዓላት በዋነኛነት ያስተላለፉልን ታላቅ የጋራ መልእክት በእርቅ ጉዳይ ላይ ያተኮረ ነበር። የእርቁ ማእከላዊ ጭብጥ ደግሞ ሰው ከራሱ፣ ሰው ከፈጣሪው፣ ሰው ከሰውና ሰው ከተፈጥሮ ጋር ተስማምቶ መኖር እንዲችል የሚያበረታታና የሚያስተምር ነው።
ይቅርታ ማድረግን አስመልክቶ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ ተደጋግሞ የሚጠቀስ አንድ አስደናቂ ታሪክ ተመዝግቧል። “ጴጥሮስ ወደ ኢየሱስ ቀርቦ፤ ጌታ ሆይ ወንድሜ ቢበድለኝ ስንት ጊዜ ይቅር ልበለው? እስከ ሰባት ጊዜ ነውን? አለው። ኢየሱስም መልሶ ‹እስከ ሰባ ጊዜ ሰባት እንጂ እስከ ሰባት ጊዜ ብቻ አልልህም። ” ብሎ መለሰለት” (ማቴዎስ 18)።
እለት በእለት ለሚያጋጥሙን በርካታ እርቅ ተኮር ጉዳዮች ከዚህ ታሪክ ብዙ ቁምነገሮችን መቅሰም ይቻላል። መበደልም ሆነ ይቅር መባባል “እንደ መስቀል ወፍ” በሕይወታችን ውስጥ ዓመት እየጠበቀ አንድ ጊዜ የሚከሰት አጋጣሚ አይደለም። እያንዳንዱ ሰው በተለያዩ ምክንያቶችና ጉዳዮች ሳይግባባ ቀርቶ ሊጋጭ ወይንም ሊገጩት፣ ሊበድል ወይንም ሊበድሉት፣ ሌሎችን ሊያሳዝን ወይም እርሱ ራሱ ሰዎችን ሊያሳዝን መቻሉ ከተፈጥሯዊ ማንነታችን ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው።
ከራስ ጓዳ እስከ ሕዝብ አደባባይ፣ ከቤተሰብ እስከ ማሕበረሰብ፣ ከትዳር እስከ አገር መጋጨት፣ መኳረፍና ይቅር መባባል በቁጥርም ሆነ በዓይነት ተወስኖ የሚጠናቀቅ የአንድ ሰሞን ጉዳይ ብቻ አይደለም። ስለዚህም ሳይሆን አይቀርም ጴጥሮስ የራሱ ግምት በመስጠት ይቅርታን በሰባት ጊዜ ብቻ መወሰኑ ትክክል ያለመሆኑን ኢየሱስ የነገረውና “ሰባትን በሰባት አባዝትህ 490 ጊዜ ይቅር ለማለት ወስን” በማለት ስለ ይቅርታ ያስተማረው። በዚሁ ቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ የሚታረቁ ብቻም ሳይሆኑ “የሚያስታርቁም ጭምር ብፁዓን ናቸው” ተብሎ ተጽፏል። ብፅዕና መተርጎም የሚገባው በመንፈሳዊ ምሥጢርነቱ ብቻ ሳይሆን በእለት ተእለት የሥነ ምግባር ትምህርትነቱ (Ethical Admonition) ጭምር መሆን ይገባዋል።
“አገር ያለ እርቅና ምክር አይጸናም”
በአገራችን ባህሎችና ወጎች ውስጥ ብቻ ሳይሆን በታሪካችን ድርሳኖች ውስጥ ሳይቀር የሽምግልና አተገባበሮች፣ እርቅና ሰላም የማውረድ ተሞክሮዎችና ልምምዶች እጅግ የበዙ ናቸው። የውጭ ወራሪዎች ሉዓላዊ ድንበራችንን በደፈሩባቸው ወይንም ጥቃቶች ባደረሱብን የታሪክ አጋጣሚዎች ሁሉ የአካባቢው ተጎራባች አገራትና የሩቅ መንግሥታት ጭምር ጣልቃ በመግባት ግጭቶቹና ጦርነቶቹ በንግግርና በሰላም እንዲፈቱ የተደረጉባቸው ታሪካዊ አጋጣሚዎችም እንዲሁ በርካቶች ናቸው። ለሌሎች አገራት የውስጥና የውጭ ችግሮችም ኢትዮጵያ በአሸማጋይነትና በአደራዳሪነት የተፈለገችባቸውና የተጋበዘችባቸው እውነታዎችም እንዲሁ ዝርዝራቸው እጅግ የበዛ ነው።
የቅርብ ዘመናቱን ታሪካችንን ብናስታውስ አንኳን በወታደራዊው የደርግ መንግሥት ከሻዕቢያና ከሕወሓት ጋር የነበረው አስከፊ ጦርነት በሰላማዊ መግባባትና ሽምግልና እንዲፈታ በተለያዩ መንግሥታት፣ ቡድኖችና ግለሰቦች አማካይነት ተደጋጋሚ ጥረቶችና ሙከራዎች መደረጋቸው ይታወሳል።
የሕወሓት/አህአዴግ ሠራዊት ግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ.ም አዲስ አበባን የተቆጣጠረው የደርግ መንግሥት ተደራዳሪዎች ከቡድኖቹ መሪዎች ጋር በአሜሪካው ጎምቱ ፖለቲከኛ በሚ/ር ሄርማን ኮኸን አደራዳሪነት ለንደን ከተማ ውስጥ በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ እየተነጋገሩ በነበረበት ወቅት መሆኑ ይታወሳል። ችግሮቹን በሰላምና በንግግር ከመፍታት ይልቅ የሁለቱም ወገን መሪዎች የልባቸው እብሪት “በባሩድ ጭስ” ታፍኖ ስለነበር መግባባት ሳይቻል ቀርቶ አገሪቱ እንደምን ዛሬም ድረስ ልትወጣው ወደማትችለው አረንቋ ውስጥ ተዘፍቃ አበሳዋን እንደምታይ በብዙ ማስረጃዎች ማመላከት ይቻላል። “የአንድ ቀን ስህተት ያለ ዓመት አይመዘዝ” እንዲሉም የዚያ የልብ ድንዳኔ ጦስ ትቶት ያለፈው ጠባሳና እያመረቀዘ ያለው ቁስል ዛሬም ድረስ ለፈውስ እያስቸገረን እንዳለ አኗኗራችን ምስክር ነው።
በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ሚያዝያ 28 ቀን 1990 ዓ.ም ተጀምሮ ለሁለት ዓመታት ያህል የዘለቀው አውዳሚው ጦርነትም ከሁለቱም ወገን በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች እንደረገፉበትና የየአገራቱ ኢኮኖሚ ተንኮታኩቶ ከመላሸቁ የተነሳ የሁለቱም አገራት የድህነት ደረጃ አሽቆልቁሎ “ከዜሮ በታች” በሚባልበት ደረጃ ላይ መድረሱ የጋራ መራራ ታሪካችን አካል ነው።
በታኅሳስ 3 ቀን 1993 ዓ.ም የሁለቱ አገራት መሪዎች አልጀርስ ላይ በደረሱበት “ስምምነት” መሠረት ጦርነቱ ጋብ ያለ ቢመስልም የድንበር ላይ መፋጠጡ ተጠናክሮ በመቀጠሉ ለረጅም ዓመታት “ተኩስ አልባ” ግዳጅ ላይ መክረማቸውም አይዘነጋም። በቀላል ቋንቋ መግለጽ ካስፈለገ “የዐይነ ቁራኛው ደፈጣና መፋጠጥ” እንዳለ ሆኖ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮችና በየሚዲያዎቻቸው እየተጠዛጠዙ መበሻሸቁን ተክነውበት ነበር።
ይህ ውጥረት የመቋጫ ምዕራፍ ላይ ሊደርስ የቻለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመጋቢት 2010 ዓ.ም ሥልጣን በያዙ በጥቂት ወራት ውስጥ ሐምሌ 2010 ዓ.ም አስመራ ከተማ በመገኘት ሁለቱን አገራት ጋርዶ የነበረው ጥቁር የጥላቻ መጋረጃ ከተቀደደ በኋላ መሆኑን ልብ ይሏል።
“ደም ያደረቁ አሸማጋዮች”
“ያልታደልሽ እንዴት አደርሽ” እንዲሉ፤ የኢትዮጵያ ፈተናዋ መልኩና ልኩ ይህ ዳርቻህ የሚባል ዓይነት እንዳልሆነ ለማንም ይጠፋዋል ተብሎ አይገመትም። አንደኛው አገራዊ ቀዳዳችን ሲደፈን ሌላው እየተሸነቆረ፣ የተወላገደው ሲቃና ቀናው እየጎበጠ ማማጥንና “ኤሎሄ እያሉ መቃተትን” የባህል ያህል ተቀብለን አብረን እንድንኖር የተፈረደብን ይመስላል።
ማክሰኞ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም እኩለ ሌሊት ላይ ጀግናውን፣ ርሁሩሁንና ለአገርና ለሕዝብ ሉዓላዊነትና ልዕልና መጠበቅ በግዳጅ ቀጣናው ላይ በተጠንቀቅ ቆሞ የሚታደገን የሰሜን እዝ ሠራዊት በሕወሓት ተከድቶ በኢትዮጵያ ምድር የዘነበው መከራ ገና በአግባቡ ተመዝግቦና ተተርኮ ስላልተጠናቀቀ ዝርዝሩን ለማቅረብ በእጅጉ ያዳግታል። ክስተቱ በትናንትና ጀንበር የተፈጸመ ስለሆነ የጉዳቱን ልክ እንዲህና እንዲህ ብሎ መከለሱ አስፈላጊነቱ አልታየንም።
ምን ያህል ወገን እንደረገፈ፣ ምን ያህል ሀብትና ንብረት እንደወደመ፣ በሕዝቡ ላይ የደረሰው የሥነ ልቦና ህመምና ቀውስ ጠግጎ ገና “የቁስሉ ፋሻ” ስላልተፈታና በአግባቡ ስላልተሰነደ ጊዜ ሰጥቶ መታገሱ ተገቢ ይመስለናል። ይህንን ደም ያቃባ ክስተትና በቂም የተቋጠረ ልብ በሰላማዊ ንግግር በመግባባት መፍታት እስካልተቻለ ድረስ አገሪቱ ከገባችበት አረንቋ ፈጥና እንደማትወጣ በመታመኑ ውሳኔው መራራ ቢሆንም አንድ እርምጃ ግን መወሰድ ነበረበት።
በዚሁ መሠረትም በአፍሪካ ኅብረት ስምሪት ሰጭነት በቀድሞዎቹ የናይጄሪያና የኬኒያ ፕሬዚዳንቶች በክቡር ኦሊሴንጎ ኦባሳንጆና በክቡር ኡሁሩ ኬኒያታ አሸማጋይነት በኢትዮጵያ መንግሥትና በሕወሓት መካከል ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ የሰላም ስምምነት መፈረሙ ይታወሳል። የስምምነቱን አተገባበር በተመለከተም በኬኒያ ናይሮቢ በተደረጉ የሁለት ዙር ንግግሮችና ውይይቶች አማካይነት “እርቀ ሰላም ወርዶ” የጦር መሣሪያ ላንቃዎች እንዲዘጉና ጠብ ቀስቃሽ መቆራቆዞች እንዲረግቡ ተደርገዋል።
ከሰላም ስምምነቱ በኋላም በተደረሰባቸው መግባባቶች መሰረት በሁለቱም ወገኖች አበረታች ተግባሮች እየተከናወኑ ሲሆን ሕዝቡም በእፎይታ መተንፈስ መቻሉ እየተስተዋለ ነው። የትግራይን ደመና አክብዶ ሕዝቡን ለመከራ የዳረገው ስቃይም ቀስ በቀስ እየተገፈፈ ስለሆነ ሰላማዊ የሕዝብ ለሕዝብ እንቅስቃሴው በመነቃቃት ላይ ይገኛል።
የእርቀ ሰላሙ ውጤት ከጮርቃነት ወደ ብስል ፍሬነት ጎምርቶ የተፈጠረው የታሪክ ስብራት ሙሉ ለሙሉ ተፈውሶ ጠባሳው እስኪድን ድረስ ብዙ የሚሰሩ ቀሪ አገራዊ ሥራዎች እንዳሉ አይጠፋንም። ለሰላሙ መተግበር ቀዳሚ ትኩረት ሊሰጥ የሚገባው ለፖለቲካ ውሳኔ መሆኑ ባይካድም የመንፈሳዊ ሥልጣንም ሊዘነጋ አይገባም። መላው ሕዝብ ኢትዮጵያ በጾምና በጸሎት ፈጣሪውን በመማጸን ያደረገው አስተዋጽኦ በፍጹም የሚረሳ አይደለም።
በአንጻራዊ መልኩም ቢሆን የነበረው የተካረረ ውጥረት ረግቦ “የሰላማችን ርግብ” ከቁስለቷ በማገገም የዘንባባ ቀንበጥ በአፏ እንደያዘች በሰማዩ ላይ ለመቅዘፍ እያቃሰተችም ቢሆን መብረር ጀምራለች። ሙሉ ለሙሉ ተፈውሳና ዝማሬ አክላበት በሰማያችን ላይ ደምቃ እንደምትከንፍ ተስፋ እናደርጋለን።
የኢትዮጵያ የሰላም ሁኔታ ግድ ብሏቸውና የመከራችን ክብደት ተሰምቷቸው እርቀ ሰላሙ ገቢራዊ እንዲሆን ከአገራችን ጎን የነበሩና የቆሙ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት፣ ግለሰቦችና ቡድኖች በርካቶች መሆናቸውን አንዘነጋም። በተለይም የአህጉራዊው አፍሪካ ኅብረት መሪዎችና የሰላሙን ስምምነት በስኬት እንዲያስፈጽሙ የተወከሉት ቀደም ሲል የጠቀስናቸው ክቡር ኦባሳንጆ ኦሊሴንጎንና ክቡር ኡሀሩ ኬኒያታን የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ስለ ድካማቸውና አስተዋጽዋቸው በልዩ ሁኔታ ማመስገኑ አግባብ ብቻ ሳይሆን ተገቢም እንደሆን ይታመናል።
ስለዚህም ኢትዮጵያ ሆይ ስለተደረገልሽና ለእኛም ለሕዝቦችስ ስለተደረገልን መልካምነትና በጎነት አሸማጋዮቹን የሰላም መልእክተኞች በምስጋና አክብሪልን። እኛ ዜጎችም ድምጻችንን ከፍ አድርገንና እንደ ባህላችን ዝቅ ብለን አክብሮታችንን እንገልጽላቸዋለን። ለአፍሪካ ኅብረት ጽ/ቤት ኃላፊዎች፣ ለሁለቱ አንጋፋ የአፍሪካ አባቶች እና በሰላም ስምምነቱ ሂደት ውስጥ ሚና ለነበራቸው ለበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት በምስጋናችን ቃል ማክበራችን እንደተጠበቀ ሆኖ ውለታችሁ በትውልዶች ሁሉ ዘንድ እንዲታወስና በታሪካችን ውስጥ ጎልቶ እንዲሰነድም የተቻለውን ሁሉ ጥረት እናደርጋለን። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 15 ቀን 2015 ዓ.ም