የመንደርደሪያችን ወግ
ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ይህ ጸሐፊ በሊቢያዋ የሲርት (Sirt) ከተማ ለመገኘት ዕድል አጋጥሞት ነበር። የመገኘቱ ዋና ዓላማ በየራሳቸው ሀገር ደረጃ እና በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ በበጎ ተጽእኖ ፈጣሪነታቸው በተሰባሰቡ የአፍሪካ ምሁራን ጉባኤ ላይ ለመታደም ነበር። ጉባዔው እንዲዘጋጅ ቀጥተኛ መመሪያ የሰጡትና የመወያያ አጀንዳውን የወሰኑት የቀድሞው የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ኮ/ል ሙሐመድ ጋዳፊ መሆናቸው ለጉባዔተኛው የተገለጠው በመክፈቻ መርሃ ግብሩ ላይ ነበር።
የጉባዔውን ዓላማ በተመለከተ ሌሎች እንደ ሽፋን የተጠቀሱ አፍሪካዊ ጉዳዮች የተነካኩ ቢሆንም በቀረቡት በርካታ የመወያያ ጽሑፎችና ይሰጡ በነበረው የተሳታፊያኑ አስተያየቶች ጎልቶ ይደመጥ የነበረው ማዕከላዊ ሃሳብ “የአፍሪካ ኅብረት ጽ/ቤት ከአዲስ አበባ መነሳት ይኖርበታል” የሚል ዋና አጀንዳ ነበር። የትኞቹ ሀገራት ይህንን ሃሳብ ጮክ ብለው ያንጸባርቁ እንደነበርና በዚህ ጸሐፊ ላይ ተፈጥረው የነበሩ ግልጽ ተጽእኖዎችን በተመለከተ ወደፊት በተገቢ ሁኔታና በዝርዝር ለማቅረብ ይሞከራል።
የኅብረቱ ጽ/ቤት ስለምን ከአዲስ አበባ ከተማ ሊነሳ እንዳስፈለገ በተሳታፊ ከተሰጡት በርካታ አሉታዊ አስተያየቶች መካከል አንዱና ለዚህ ጽሑፍ መጻፍ ምክንያት የሆነው፡- “አዲስ አበባ ከተማ የቆሸሸች ከተማ መሆኗ፤ አደባባዮቿና ጎዳናዎቿ፣ የአፍሪካ ሀገራት ኤምባሲዎች የሚገኙባቸው አካባቢዎችና ሠፈሮቿ በሙሉ በጭቃና በቆሻሻ ክምር የተከበቡ መሆናቸው” በስፋት እየተጠቀሰ ሀገሬ በብዙ የአፍሪካ ልጆች ስትነቀፍ ጆሮዬ እያደመጠ በጉባዔው መካከል ባይተዋር በመሆን ስሜቴ እንደዳመነ ሳልወድ የግድ አስተያየቶቹን አድምጫለሁ።
ውይይቱ የተቋጨው አዲስ አበባ ከተማ “አበባ – New Flower” የሚለው ስሟ ያማረው ለስያሜ አንዱ እውነታው ግን እጅግ ተቃራኒ ስለሆነ የአህጉሪቱ የመሪዎቹ ጉባዔ በጉዳዩ ላይ አጥብቀው ሊያስቡበት እንደሚገባ ምክረ ሃሳብ በመስጠት ውይይቱ እንደተጠናቀቀ አስታውሳለሁ። ምሁራኑም በሚያገኙት አጋጣሚዎች ሁሉ “የኅብረቱ ጽ/ቤት ከአዲስ አበባ እንዲነሳ በሚካሄደው ዘመቻ በንቃት እንዲሳተፉ ከአዘጋጁ ክፍል የአደራ መልእክት እንደተላለፈላቸውም ትዝ ይለኛል።
በዚያ ጉባዔ ላይ የተገኙት አብዛኞቹ የአፍሪካ ምሁራን በዚህ አጀንዳ ላይ አስተያየታቸውን ይሰጡ የነበረው በተሟሟቀ ስሜት ብቻ ሳይሆን፤ ጭብጨባም ጭምር እየታከለበት ነበር። በሀገሬ ላይ ይህንን መሰል አሸማቃቂ አስተያየት ሲዥጎደጎድ ተሸማቆ ማዳመጥ እንደ አንድ ዜጋ እንደምን ስሜትን እንደሚያቆስልና ቁጭት ላይ እንደሚጥል አንባቢው የሚረዳ ይመስለኛል። የአፍሪካ አንድነት ድርጀት በተቋቋመበት ሰሞን በሀገራችን ድምጻዊያን ከተዜሙት ዜማዎች መካከል ስለ አዲስ አበባ በስፋት የተደመጠው ዜማ፤
አማረች አሸበረቀች፣
ለአፍሪካ ኅብረት መሠረት ሆነች።»
የሚለውን መልዕክት በሃምሳ ዓመታት ዕድሜ ውስጥ ሀገሬ መተግበር ተስኖት ከነጭራሹ “የኅብረቱ ጽ/ቤት” ከአዲስ አበባ ይነሳልን መባሉ በአስተያየት ሰጪዎቹ ላይ ብቻ ከመፍረድ ባሻገር ራሳችንን በራሳችን መውቀስም በተገባን ነበር የሚል የግል አቋም ነበረኝ። ብዕረ መንገዳችንን “የኅብረቱ ጽ/ቤት ምን ሲደረግ ከአዲስ አበባ ይነሳል!” በሚል ሙግት የአህጉሪቱ መሪዎች በሚሰባሰቡባቸው መድረኮች ሁሉ ተገቢውን ታሪካዊና ወቅታዊ ማስረጃዎችን እየጠቀሱ በድፍረትና በጽናት ይከራከሩ ለነበሩት ቀደምት የሀገራችን መሪዎች ክብርና ሞገስ ይሁንላቸው።
“በራሷ አረም እባብ ይዛ ታስፈራራለች” እንዲሉም ይህ ጸሐፊ በዚያ ጉባዔ ላይ እንዲገኝ ጥሪ በደረሰው ወቅት ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ስለ ጉዞው ሁኔታውን በአግባቡ ለማሳወቅ ሞክሮ በወቅቱ ከነበሩ አንድ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊ “ጉዳዩ የግልህ እንጂ ሀገርን ስለማይመለከት መሄድ ያለመሄድ የራስ ጉዳይ ነው” በማለት የሰጡኝ መራራ አስተያየት ዛሬም ድረስ በአእምሮዬ ውስጥ እንዳቃጨለ ይኖራል።
«እንደ ስማቸው የሆኑ ከተሞቻችን»
የስማቸው ትርጉምና እውነታው ከተጣጣመላቸው የሀገራችን ከተሞች መካከል ሁለቱ ባሕር ዳርና አርባ ምንጭ ውብ ከተሞቻችን በቀዳሚነት ቢጠቀሱ አግባብ ይሆናል። ከመቶ ዓመት በላይ ያስቆጠረችው ውቧ የባሕር ዳር ከተማም ሆነች ከስልሳ ዓመታት ከፍ ያለ የዕድሜ ፀጋ የተጎናጸፈችውና በአስደናቂ የተፈጥሮ መስህብ የተባረከችው የአርባ ምንጭ ከተማ ሁለቱም ድምቀታቸውና ሳቢነታቸው ከስማቸው ጋር የሚገጥም ነው።
የጣና ውበት ድምቀቷ የሆነውና በቅርቡም በዐባይ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለው አዲሱ ድልድይ አገልግሎቱን ሲጀምር በርግጥም ከተማዋ የሀገራችን ፈርጥ እንደምትሆን በትልቅ ጉጉትና ተስፋ እየተጠበቀ ነው።
ተፈጥሮ ያለ ስስት እምቅ ሀብቶቿን በአደራ ያሸከመቻትና ከአርባ በላይ ምንጮች የሚንፎለፎሉባት “የእግዜር ድልድይዋ” መገኛ አርባ ምጭም በተለያዩ የልማት ትሩፋቶች ውበቷ እየደመቀ ስለሆነ ተናፋቂና ተወዳጅነቷ እየጨመረ በመሄድ ላይ ነው። “ስምን መልአክ ያወጣል” የሚለው ሀገራዊ ብሂል በእነዚህ ሁለት ከተሞች ላይ ገቢራዊ ሆኗል ቢባል ከግነት አያስቆጥርም። እነዚህ ሁለት አንጋፋ ከተሞቻችን እንደ ስማቸው እንዲሁ ስለሆኑ የትናንቶቹን ስያሜ አውጭና የዛሬዎቹን አስተዳዳሪዎች ብናመሰግን ለተሻለ ውጤት ስለሚያነቃቃቸው “አሹ! በርቱልን!” በማለት አክብሮታችንን እንገልጽላቸዋለን።
«እንደ ስሟ ለመሆን የምትታትረው አዲስ አበባችን»
አዲስ አበባ ከተማችን በልጆቿ ብቻ ሳይሆን በባዕዳንም ጭምር ብዙ ተብሎላታል፤ ብዙም ተብሎባታል። በርካቶች ዘፍነውላታል፤ በርካቶችም ወቅሰዋታል። አያሌዎች አድንቀዋታል፤ ሺህዎችም ተቀይመዋታል። በተቃርኖ የሚገለጹትን እነዚህን መሰል የአያዋ (አይ+አዎ፤ Paradox) ገለጻዎች በተመለከተ ብዙ ሲነገርና ሲጻፍ ስለኖረ የተባለውን ደግሞ መከለሱ አስፈላጊነቱ አልታየኝም። ይልቁንስ በከተማዋ ውስጥ እየተከናወኑ ያሉትን በጎ የልማት ጅምሮች በወፍ በረር ቅኝት እየጠቃቀስን አዲስ አበባን በማድነቅ እየተነቃቃ ባለው መንፈሷ ላይ ሙቀት መጨመሩ ይበልጥ ያተጋት ይመስለናል። የአዲስ አበባ ከተማ ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ለኪነ ጥበባት ባለሙያዎችና ለደራስያን ሚያዝያ 12 ቀን 2015 ዓ.ም የከተማዋን አስደማሚ ሰፋፊ ፕሮጀክቶች አስጎብኝቷል። የተጎበኙትን አስመስጋኝ ፕሮጀክቶች በተመለከተ ወደፊት በዝርዝር ለማቅረብ ስለሚሞከር ለጊዜው በአንድ ጉዳይ ላይ ብቻ አተኩራለሁ።
ከአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች መካከል በአንፃራዊነት አዲሱ የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ብዙ ወቀሳና እምባ ሲዘንብበት እንደከረመ በከተማዋ ነዋሪዎች ዘንድ የታወቀ ብቻ ሳይሆን በብዙ ማስረጃም የተረጋገጡ መረጃዎች በይፋ ለሕዝቡ ሲነገሩ መሰንበታቸውም አይዘነጋም። ይህ በዘርፈ ብዙ ችግሮች ተተብትቦ “በልጅነት ልምሻ” የተጠቃው ክፍለ ከተማ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ያሳየው የልማት እመርታ “ለካስ ከልብ ካለቀሱ እምባ አይገድም” የሚለውን ሀገርኛ ብሂል እንድናስታውስ ግድ ብሎናል።
በዚሁ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ውስጥ ያሉ አደባባዮችና የመንገድ አካፋዮች በተዋቡ አበቦች ተንቆጥቁጠው ማስተዋል በርግጥም አዲስ አበባ በአዛውነትነት ዕድሜዋም ቢሆን እንደ ስሟ እያበበች ስለመሆኗ በጥሩ አብነት ሊጠቀስ ይችላል። የክፍለ ከተማው ውጫዊ ገጽታ ብቻ ሳይሆን አስተዳደራዊ ዘርፉም የመነቃቃት መንፈስ እየተስተዋለበት ነው። ምሉዕ በኩለሄ ነው ለማለት ግን በፍጹም አይቻልም፤ ጊዜውም አይደለም። የዚህን ክፍለ ከተማ የልማትና የአስተዳደር ጉዳዮች በተለየ ሁኔታ በቅርበት እየተከታተሉ ለሚያስፈጽሙት ለክብርት የከተማችን ከንቲባ ለወ/ሮ አዳነች አቤቤ እስካሁን ለተመዘገበው ውጤት ማመስገኑ ተገቢ ይመስለናል። ቀሪ ሥራዎቹ የትዬለሌ መሆናቸውን ግን እንኳን እኛ ዜጎች ቀርተን መሪዎቿም ቢሆኑ ይጠፋቸዋል ለማለት ይከብዳል።
የኑሮው ጫና፣ የቤት ኪራዩ አይደፈሬነት፣ የቢሮክራሲው ጥልፍልፍነትና የፍትሕ ጥማቱ እዬዬ እያሰኘ የሚያስለቅሳቸውና ችግሩ ያጎበጣቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ከላይ የተገለጸው ዓይነት የማበረታቻ ምሥጋና ቁብ እንደማይሰጣቸው አይጠፋኝም። ይህንን ጽሑፍ
ለማንበብ እድሉ የሚገጥማቸው አንዳንድ ወገኖችም “ውጭውን በአበባ ከማስዋብ፤ የውስጥ ጠረንን ማሳመር” የሚሉ ብሶቶች ሊያቀርቡ እንደሚችሉም ይገባኛል። የሆነው ሆኖ ግን ለትችት እየተሽቀዳደምን ለምስጋና ንፉግ መሆን የሰብእና መገለጫ ስላልሆነ መልካም ሲሰራ “አበጃችሁ በርቱ!” ማለት “ላልተሰሩት ሥራዎች ማስታወስ” ለተሻለ ሥራ ስለሚያነሳሳ ማመስገኑ የግድ ይላል።
በዚህ ጸሐፊ እምነት በከተማችን ውስጥ የሚስተዋሉ በርካታ አስተዳደራዊ ህፀፆች መኖራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ በተለየ ሁኔታ ግን ዋና ዋና የከተማይቱን አደባባዮችን፣ የአውራ ጎዳና ዳርቻዎችንና አካፋዮችን በተዋቡ አበቦች ለማሳመር የሚደረገው ጥረት በተለየ ሁኔታ ሊደነቅ ይገባዋል። ለአንድ መቶ ሠላሳ ስድስት ዓመታት ያህል ስሟና ገጽታዋ እንደተቃረነ በጽኑ እንቅልፍ ስታንጎላጅጅ ለኖረችው አዲስ አበባ ለስሟ ትርጉም የሚመጥን ሥራ እየተሠራላት መሆኑ ለክርክር የማይዳርገው የተግባር ፍሬው በግልጽ ስለሚታይ ነው።
ለአብነት ያህል ከላይ በተቀስኩት የመኖሪያዬ ክፍለ ከተማ በሆነው በለሚ ኩራ እና በየካ፣ በቦሌ፣ በአራዳና በንፋስ ስልክ ላፍቶ ወዘተ. የከተማዋ ክፍሎች አደባባዮችና የመንገድ አካፋዮች ላይ ፈክተው የሚታዩት አበቦችና መናፈሻዎች ለከተማዋ ውበት ብቻ ሳይሆን ለነዋሪዎቿና ለእንግዶቿ ትልቅ የመንፈስ መነቃቃትና ደስታ እንደሚፈጥሩ መካድ አይቻልም።
ከተማዋን የሚያስተዳድሩት ሹማምንት ወደየክፍለ ከተሞች ወረድ በማለት የዘጠና ቀን እቅዳቸውን ሲገመግሙና የተጠናቀቁትንም ሲያስመርቁ በየሚዲያዎቹ እየተከታተልን ነው። እርግጥ ነው በየክፍለ ከተሞቹ በርካታ የችግር ቋጥኞች በሙሉ ተፈረካክሰው ደልዳላ ሜዳ እንዳልሆኑ ይገባናል። ነው ብለን ብንከራከርም ከአንባቢው ጋር ብቻ ሳይሆነ ጥሉ ከራሳችን ኅሊና ጋር እንደሚሆን አይታበልም። እንዲዚያም ቢሆን ግን ትርጉም ያላቸው በርካታ ፕሮጀክቶች በአዲስ አበባችን እየተተገበሩ መሆናቸውን ብንክድ ከራስ ጋር መጣላት ይሆንብናል። ለተከናወኑት መልካም ተግባሮች አመስግነን ባልተሰሩት ሥራዎች ላይ አቤቱታ ማቅረቡ ተገቢም አግባብም ይሆናል።
በተለየ ሁኔታ ግን በከተማችን ውስጥ እየተከናወኑ ያሉት የአረንጓዴ ልማት ሥራዎችና የማስዋብ ጥረቶች ግለታቸውን ሳይቀዘቅዝና የወረት ሩጫ ሳይሆን በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ አዲስ አበባችን “እንደ ስሟ ተለውጣለች” ተብላ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሳይቀር እንደምትወደስና በምሳሌነት እንደምትጠቀስ አንጠራጠርም።
ነፍሰ ሄሩ ድምጻዊ ዓለማየሁ እሸቴ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በፊት፤ “አዲስ አበባ ቤቴ” ብሎ ያንጎራጎረውና ሌላው ዘመነ አቻው ድምጻዊ ጌታቸው ካሣ “አዲስ አበባ” በማለት ያዜመው ሙዚቃ እንደ አዲስ ታድሰው የነዋሪዎቿ ዝማሬዎች የማይሆኑበት ምክንያትም አይኖርም። “እንደ ስሟ እንዲሁ…” በማለት በነጠብጣብ የምንተወው ሀረግ በመደምደሚያ ቃል ነፍስ ዘርቶና ደምቆ ጎላ ተብሎ እንዲገለጽ አሁን የተጀመረው መልካም ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል።
ለእስከ ዛሬው የአደባባዮቻችን ውበትና ድምቀት በየደረጃው ለሚገኙት የከተማዋ አመራሮች “ገለቶማ!” በማለት ምሥጋናችንን እናቀርባለን። በተለየ ሁኔታ ደግሞ አደባባዮቻችንንና ጎዳናዎቻችንን ለማስዋብ ቀን ከሌት ለሚደክሙትና በትጋት ተግባራቸውን ለሚከውኑት ባለ ወርቃማ እጆች የዕጽዋት ተንከባካቢዎችና የጽዳት ባለሙያዎች ከፍ ያለ የአድናቆትና የአክብሮት ምሥጋናችን ይድረሳችሁ እንላችኋለን። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 14/2015