«ያ የድል ብስራት ትንሳኤ መሆኑ ላይቀር ስንት ተሞከረ !? የምድር ነገሥታትና የሃይማኖት ጀሌዎች ተማከሩ፤ ሴራ አሴሩ፤ አሾፉ፤ ተዘባበቱ፤ ችንካር ቸነከሩ፤ ጦር ሰበቁ ፤ መቃብር አስጠበቁ ፤ የውሸት ወሬ አስወሩ ፤ ተሰረቀ አስባሉ ግን ገሀድ ሆነ ትንሳኤው በአዋጅ ተበሰረ፤ ብዙዎችን አሻገረ፤ የድል ዜማ ተዜመ፤ ዘሩ በዛ ምድርን ሸፈነች ፤ መላዕክት አሸበሸቡ ዕረፍት ሆነ የቀደመው ጭንቅ ተረሳ። ተፈፀመ። ለአገራችም ዛሬ አርብ ቢሆንም ትንሳኤ ይሆናል። አይቀርም።
ሰላሳ ዓመት የታነፀው ሕንፃ ሦስት ዓመት ተኩል ያገለገለው ቤተመቅደስ ቢፈርስም በሦስተኛው ቀን መነሳቱ ላይቀር ስንት ፉከራ ተፎከረ ግን በትንሳኤው የሁሉም ሴራ ከንቱ ሆኖ ቀረ ። በግለሰብም ፣ በማህበረሰብም በአገርም ደረጃ ትንሳኤ እውን መሆኑ ላይቀር በዲያብሎስ እና በጀሌዎቹ ስንት ምክር ተመከረ፤ ስንት ሴራ ተሴረ ፤ እንዴት ያለ ጥልቅ ጉድጓድ ተቆፈረ ግን ሁሉም ሙከራቸው በጌታና በኃይሉ ችሎት ከንቱ ሆኖ ቀረ ፤ ትንሳኤ ሊበሰር እነሆ ጫፉ ደርሰናል።
ክፉዎች ደግሞ ሬሳዋን ዜጎቿ ሰርቀውት እንጂ ኢትዮጵያ አልተነሳችም ለማለት ሰነድ ሰንደዋል የውሸት አዋጅ ነጋሪዎች በረብጣ ክፍያ አዘጋጅተዋል። ምፅ… መሆኑ ላይቀር ከንቱ መፍጨርጨር። በኋላማ ከሰሜን እስከ ደቡብ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ይጎሰማል የድል ዜማ እየተባለ በትንሳኤው ኃይል ተነስታለች እማማ። ብዙዎች ይሻገራሉ ከአገር አልፈው ለዓለም ትሩፋት ይሆናሉ የሚሆነው ይህ ነው የሚያምን ይሻገራል የማያምን ግን ይፎገራል።
የኢትዮጵያ ትንሳኤ መሆኑ ላይቀር፤ ማመን እንጂ መጠራጠር ቢቀር፤ አጀንዳው የእግዚአብሔር ነው ተብሎ ቢሰመር ፤ ማለትን እወዳለሁ ። …» ይሉናል በመንፈሳዊ ጽሑፎቻቸው ከማከብራቸው ጸሐፍት ግንባር ቀደም የሆኑት የውስጥ ደዌ እስፔሻሊስት ሀኪምና በአአዩ የጥቁር አንበሳ የሕክምና ኮሌጅ መምህር ዶ/ር አምሳሉ ቢተው ወርቄ ስለ ትንሳኤው «መሆኑ ላይቀር…!?» በሚል ርዕስ በፌስቡክ ገጻቸው ባስነበቡን አጭር ጽሑፍ።
መጋቢ ኤልደር ዊርዝሊንስ እንዲሁ ሰሞነኛውን ስቅለትና ትንሳኤን ታሳቢ በማድረግ «ዛሬ አርብ ቢሆንም እሁድ ይመጣል ። » የሚል ዘመን ተሻጋሪና ወርቅ ይትበሀል ትተውልን አልፈዋል። ጨለማ ፣ የምድር መናዎጥ ፣ ክረምት ፣ ሰደድ እሳት ፣ በረዶ ፣ ጎርፍ ፣ መገፋት ፣ መዋረድ ፣ መገረፍ ፣ መቸንከር ፣ መሰቀል ፣ መከዳት ፣ መሸጥ ፣ መሰቀል ፣ ወዘተረፈ አርብ ቢሆንም፤ መንጋቱ ፣ ብርሃን በጨለማ ላይ መንገሱ ፣ የምድር መናወጥ መቆሙ፣ ብራ ፀደይ መምጣቱ ፣ መከበሩ፣ መፈወሱ ፣ ትንሳኤ ፣ ቀን መውጣቱ ፣ የተሻለ ጊዜ መምጣቱ አይቀርም።
ክርስቶስ ሞትን ድልነስቶ እንደተነሳበት እሁድ ሁሉ ለእኛም ሆነ ለአገራችን ከችግር ፣ ከድህነት ፣ ከተመፅዋችነት ፣ ከኋላ ቀርነት ፣ ከፈተና ፣ ከወረርሽኝ፣ ከጭቆና ፣ ከአፈና ፣ ከጥላቻ ፣ ከጽንፈኝነት ፣ ከጎሰኝነት፣ ወዘተረፈ ነፃ የምንወጣበት አንገታችን በክብር ቀና የምናደርግበት ፤ ትንሳኤ’ችንን ፣ ህዳሴ’ችንን የምናይበት ቀን ይመጣል ። እሁድ ይመጣል ። «ዛሬ አርብ ቢሆንም እሁድ ይመጣል ። » እያልን በእምነት በተስፋ እንጠባበቃለን። ደግሞም ይሆናል ። አርብም አልፎ እሁድ መሆኑና መምጣቱ አይቀረም ይሉናል ሁለቱ ሊቃውንት።
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኃጢያታችን እና ለበደላችን ክቡር መስዋዕት ሆኖ እንደተሰቀለ ክርስቲያን የተባልን ሁላችን ከልባችን እናምናለን ፤ በየቀኑ እናሰላስላለን፤ በየዓመቱ ደግሞ የተከበረ በዓል አድርገን እናከብረዋለን። ነገር ግን እኛስ ከእርሱ ጋር እንደተሰቀልን እና ዕለት ዕለት መስቀሉን መሸከም እንደሚገባን እናውስተውለዋለን ወይ የሚል ብርቱ ጥያቄ ግን ማንሳት እወዳለሁ ይላሉ ዶ/ር አምሳሉ።
በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ባመንበት ጊዜ ሁሉ ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት በቀራንዮ በመስቀል ላይ ሲሰቀል እኛም ከእርሱ ጋር እንደተሰቀልን ማመንን የሚያካትት መሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው። ይህም ማለት አሮጌው ቀዳማዊ አዳማዊ ማንነታችን ፤ የኃጥያት ስጋ እና ራስ ተኮር አካሄዳችን በእርሱ መስዋዕትነት ከእኛ ተወግዷል ብሎ ማመን ነው። ዕለት ዕለት መስቀሉን መሽከም ማለት ደግሞ በዚህ እምነት ነፍሳችንን መስዋዕት ለማድረግ እስከምንደርስ ድረስ በሚያደርግ የእምነት ገድል እየተጋደልን በእርሱ ባለን እምነት መኖር ማለት ነው ። መስቀል እና መሰቀል ከክፉ ደዌ የተገላገልንበት ትምክህታችን ነውና ተገቢውን አንድምታዊ ትርጉም ልናተኩርበት ይገባል ።
መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ «አርብን» እንዳሳለፈ ሁሉ ደረጃው ይለያይ እንጂ በሕይወታችን መውደቅ መነሳቶችን ፣ ህማማትን ፣ አርቦችን አሳልፈናል። ማሳለፋችንም አይቀርም ። በግል ሕይወታችን፣ በትምህርታችን ፣ በፍቅራችን ፣ በትዳራችን ፣ በንግዳችን ፣ በሕልማችን ፣ በራእያችን ፣ በድርጅታችን፣ በሃይማኖታችን ፣ በጤናችን ፣ በቤተሰባችን ፣ በማህበረሰባችን ፣ በሕዝባችን ፣ በአገራችን ፣ ወዘተረፈ ላይ አርብ ሆኖብን (ቀን ጨልሞብን ) እንደ እየሱስ ክርስቶስ ፍርድ ተዛብቶብን ፣ ተገምድሎብን ፣ ታስረን ፣ ተገርፈን ፣ ተሰቅለን ፣ ተቸንክረን ፣ ተዋርደን ፣ ተፈትነን ፣ ባመነው ተክደን ፣ በባልንጀራችን በ ‘ 33 ‘ ብር ተላልፈን ተሰጥተን ፣ ሰማይ ተደፍቶብን ወዘተረፈ ይሆናል ። ዛሬም በእነዚህ አስቸጋሪ ሁኔታዎች እያለፍን ሊሆን ይችላል ።
ካለፉት ሁለት መቶ አመታት ወዲህ ያሉትን ጊዜያት እንኳ ብንወስድ እንደ ሕዝብ እንደ አገር ሺህ አርቦችን ፣ በድርቅ ፣ በርሀብ ፣ በቸነፈር ፣ እናት ልጇን እስከ መብላት የተገደደችበት እንደ ክፉ ቀን ያለ እንደ 67ቱ በርሀብ የሞተች እናቱን ጡት የሚጠባበት ፣ እንደ …77 … 87 … ወዘተረፈ ያሉ ጠኔዎችን ፣ ችጋሮችን አሳልፈናል። ዛሬም ከዚህ አዙሪት በቅጡ ሰብረን መውጣት አልቻልንም ። እንደ ኅዳር በሽታ ፣ ፈንጣጣ፣ ከ76 ወዲህ ደግሞ በኤች አይ ቪ/ኤድስ ፣ በኮቪድ – 19 የእልቂት ተፈትነናል ። በግብፅ ፣ በደርቡሽ ፣ በቱርክ፣ በእንግሊዝ ፣ በጣሊያን ፣ በሱማሊያ ፣ በኤርትራ ተወረናል ። ዛሬም የክተት ነጋሪት የሚያስጎሹምብን አልጠፉም ።
በመቶዎች ሊቆጠሩ በሚችሉ የእርስ በእርስ ግጭቶች አልፈናል። ከዘመነ መሳፍንት እንኳ ብንጀምር በመሳፍንቱ፣ በመኳንንቱ ፣ በነገስታቱ መካከል ለስልጣን፣ ለዘውድ ሲባል በተካሄደ የእርስ በእርስ ግጭት ጦርነት ወገናችን ተጨራርሷል ። አጼ ቴዎድሮስ ፣ አጼ ዮሐንስ፣ አጼ ምኒልክ ፣ ልጅ እያሱ ፣ ንግስት ዘውዲቱ ፣ ልዑል አልጋ ወራሽ ራስ ተፈሪ መኮንን ፣ መንግስቱ ፣ መለስና ዐቢይም ሆኑ አገራችንና ሕዝባችን ጉዳቱ ፣ ጥፋቱ ይለያይ እንጂ ሁሉም በእርስ በእርስ ግጭት ፣ ጦርነት ተፈትነዋል። የኢትዮጵያ ትንሳኤ መሆኑ ላይቀር ብዙ አርቦችን አሳልፈዋል ። ዶ/ር አምሳሉ ወደ አነሱትና የትህትና ንጉሥ ወደ ሆነው እግር ማጠብ ልመለስ ።
እግርን ማጠብ ከጥንት ዘመን ጀምሮ ሲፈፀም የነበረ የመንጻት፥ የአገልጋይነት፥ የትህትና እና የአክብሮት መገለጫ ነው ይሉናል ዶ/ር ። በዘመነ ብሉይ ካህናት የእንስሳት መስዋዕት ለማቅረብ እና ለአገልግሎት ወደ መገናኛ ድንኳኑ ሲገቡ እግራቸውን በመታጠብ ይነጹ ነበር ። በመካከለኛው ምሥራቅ ፥ በአይሁድ እና በኢትዮጵያውያን ዘንድም እንግዳን እግር አጥቦ መቀበል እና ማሰተናገድ የተለመደ ሰናይ ተግባር ነው ። በአብዛኛው የእንግዶችን የእግር ማጠብ ተግባር የሚፈፅሙት ደግሞ የቤት አገልጋዮች ነበሩ። ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በአፀደ ስጋ በተመላለሰበት ወቅት የእግር ማጠብን ሥርዓት በመፈፀም አንድምታዊ ምስጢሩን አስተምሮናል፤ እንድናደርገውም አዞናል። ራሱን ዝቅ አድርጎ እንደ ባሪያ እግራችን ሊያጥብ ጎንበስ ያለውን ንጉሥ እና ጌታ እንደ ጴጥሮስ ለመከልከል መሞከር ተገቢ አይደለም።
የዓለምን ቆሻሻ የሚያስወግደው አንድ ጊዜ የፈፀምነው ጥምቀት ዕለት ዕለት በእምነት በሕይወታችን እንዲሠራ መፍቀድ በዓለማዊነት ከመጠመድ ይጠብቀናል። ይህንንም እንደ መልከ ጸዲቅ ሹመት ለዘላለም ሊቀ ካህናት የሆነው ጌታ ያደርገዋል። እግር ማጠብን እርሱ እንዳደረገው እናንተም አድርጉት እንዳለን ዛሬ ብቻ ሳይሆን ሁልጊዜ ማድረግ ተገቢ ነው። በድፍን ጫማ እንኳን ቢሆን የሚንቀሳቀስን እና ብዙ አቧራ ያልነካውን እግር አጥቦ እንግዳን እና ወንድም እህቶችን ማስተናገድ ተገቢ ቢሆንም መንፈሳዊ አንድምታው ግን ትኩረት ያሻዋል።
፩) በመካከላችን አንዱ ሌላውን እንደ ባሪያ እንዲያገለግለው እና እንድናገለግለው መፈቃቀድ አለብን።
፪) በዓለም ባርነት እንዳንያዝ በመካከላችን በሥራ እና በእውነት የተመሰረተ ፍቅር እና የአንድነት ኑሮ ማጠናከር አለብን ።
፫) እርስ በእርሳችን በምልጃ ጸሎት መተሳሰብ ይገባናል። እኔ እንዳደረኩት እናንተም አድርጉት ያለው ጌታ እንዲሆንልን ጸጋውን ያብዛልን ይላሉ ዶ/ር አምሳሉ። አሜን እያልሁ ፤ ይሄን የፈጣሪ ትዕዛዝ በጀ ብለን አድምጠን በሕይወታችን እየተረጎምነውና እየኖርነው ነው ስል ዛሬም እጠይቃለሁ ።
ቢያንስ ላለፉት 2015 አመታት አዲስ አመትን ፣ መስቀልን ፣ ገናን ፣ ሰሞነ ሕማማቱን ፣ ጸለተ ሐሙስን ፣ ስቅለትንና ትንሳኤን 2ሺህ 15 ጊዜ ያከበርናቸው ቢሆንም የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ጨምሮ በዕለት ተዕለት ኑሯችን ስላልተረጎምናቸውና ስላልኖርናቸው እስከ ዛሬ ሰላምን ፣ ፍቅርን ፣ እርቅን ፣ መነጋገርን ፣ መቀባበልን ፣ መከባበርን፣ መተባበርን ፣ አንድነትን ፣ ወዘተ.እውን ማድረግ አልቻልንም ። አገርን ሕዝብን ከግጭት ፣ ከቀውስ ፣ ከመፈናቀል፣ ከመጠራጠር ፣ ከጥላቻ ፣ ከበቀል ፣ ከሴራ፣ ከደባ ፣ ወዘተ . መታደግ አልቻልንም።
እስኪ ለአንድ አፍታ እምነቶቻችንን ወይም ከዚህ አኳይ እንመዝናቸው። ባክነዋል ወይስ በአግባቡ ሥራ ላይ ውለዋል ! ? አሁን ከምንገኝበት አገራዊ ቁመና አንጻር ባክነዋል ቢባል የሚያስኬድ ይሆናል። ታዲያ እነዚህን ሃይማኖታዊና ባህላዊ ንብረቶቻችንን እንደ ጦር እቃ ለብሶ እንደ ጥሩር ደፍቶ መውጣት መግባት ፣ መመላለስ ለምን ተሳነን ? መልሱ ቀላል ነው። ላይ ላዩን እንከውናቸዋለን እንጂ አንኖራቸውም።
በቃል እናነበንባቸዋለን እንጂ በልባችን አላተምናቸውም። በዩኔስኮ ለማስመዝገብ እንሯሯጣለን እንጂ በሥርዓተ ትምህርታችን አካተን ትውልድን ለማነጽ አላዋልናቸውም ። በልቦና ውቅራችን አልተመዘገቡም አልታተሙም። ለብሔራዊ መግባባት ፣ እርቅ ፣ አንድነትና ሰላም ካላቸው ፋይዳ ይልቅ ስለሚስቡት ጎብኝትና ቱሪስት እንጨነቃለን ። ለእርዱ ፣ ለአውደ አመቱ ፣ ለድግሱና ለፌሽታው ድምቀት ተበድረንና ተለቅተን ሽር ጉድ እንላለን እንጂ ቀኖናውን አልኖርነውም። ይህ የተንሸዋረር እይታ ሊስተካከል ይገባል።
ባልንጀራህን ፣ ጎረቤትህን እንደ ራስህ ውደድ የሚሉ አብርሃማዊ እምነቶችን ማለትም ክርስትናን፣ እስልምናንና አይሁድን እየተከተልን እንዴት በጥል ግድግዳ ተለያየን!? በአንድ አምላክ በዋቄ ፈና እያመን ኢሬቻን በየአመቱ እያከበርን እየከወን ይቅር መባባል ለምን ተሳነን? መልሱን ለማግኘት ምስጢሩን ለማወቅ ሞራ ማስገለጥ ወይም ኮከብ ማስቆጠር አያሻም። መልሱ ቀላል ነው። እሱም ባህላዊ ንብረቶቻችንን በካዝና ቆልፈን አስቀመጥን እንጂ ሥራ ላይ ስላላዋልናቸው (ኢንቨስት) ስላላደረግናቸው ነው። አገራዊ ሰላምና አንድነት እውን ለማድረግ የተቆለፈባቸውን ባህላዊ ንብረቶች ከካዝና አውጥቶ በእያንዳንዱ ዜጋ ላይ በፍጥነት ማፍሰስ ኢንቨስት ማድረግ ይጠይቃል።
ለአገር ግንባታ በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ ወሳኝ ሚና ከሚጫወተው ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ሥርዓት በተጨማሪ ለዘመናት እንደ ሕዝብ ፣ እንደ አገር አጋምዶ ያቆየን ሃይማኖታዊና ባህላዊ ንብረታችን ነው። ሁነቱን፣ ክዋኔውን፣ መንፈሱን ጠብቆ ተንከባክቦና አልምቶ ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ ፣ ማስቀጠል፣ ማክበርና ማስተዋወቅ ትልቅ ኃላፊነትም አደራም ነው። ሆኖም የመጨረሻ ግብ ሆኖ ግን ሊወሰድ አይገባም። ቱባነቱን እንደጠበቀ ማደግ ዘመንና ትውልድ መዋጀት ይጠበቅበታል። አዎ ! የትውልዱንና የዘመኑን ህፀፅ የሚያርም ለምፅ የሚያነጻ ፣ የሚዋጅና የሚቤዥ መሆን አለበት።
ዘረኝነትን ፣ ጥላቻን ፣ ቂም በቀልን ፣ ደባን ፣ መከፋፈልን ፣ ወዘተ . መቤዥ ፣ መዋጀት አለበት። ባህላዊ ንብረታችንን ይበልጥ በማጎልበት ፣ በማልማትና በማስፋት ለመጻኢ እድላችን ፣ ለነገ ተስፋችን፣ ለእርቅ፣ ለሰላም ፣ ለአንድነት፣ ለሁለንተናዊ ብልፅግና፣ወዘተ. ልናውለው ይገባል። ስኬቶቻችንን የምናወድስበት፣ ፈተናዎቻችንን የምንሻገርበት ነገአችንን የምንተልምበት ጭምር አድርጎ ስለመጠቀም አበክረን ማሰብ ያስፈልጋል።
የፍቅር ፣ የእርቅ ፣ የሰላም ፣ የአብሮነት ፣ የማካፈል፣ የመተባበር ፣ የመተጋገዝ ፣ የመረዳዳት ፣ የምስጋና ፣ ወዘተ . ባህሎች ፣ ልማዶች ፣ እምነቶች ፣ ሃይማኖቶች ከፍ ሲልም ድምር ባህላዊ ንብረቶች ባለቤት እንዲሁም የጥንታዊት አገር ባለቤት ሆነን አንድነትን በመከፋፈል ከሰዋን ፣ ፍቅር ከጎደለን ፣ እርቅ ከገፋን ፣ ሰላም ከራቀን፣ አብሮነትን በቀዬአዊት ከተካን፣ ማካፈልን በስስት ከቀየርን ፣ መተባበርን በመለያየት ከለወጥን ፣ ምስጋናን በእርግማን ከተካን፣ ወዘተ . ምኑን ሙሉኡ ሆነው? ባለፉት ሦስትና አራት ዓመታት ያለፍንባቸው አገራዊ ውጣ ውረዶች፣ አሳፋሪ ድርጊቶች እውነት የእነዚህ ሁሉ መንፈሳዊና ባህላዊ ፀጋዎች ባለቤት ስለመሆናችን የሚመሰክሩ ናቸው ? ስል ለመጠየቅ እገደዳለሁ።
መልካም የትንሳኤ በዓል !!!
ወስብሃት ለእግዚአብሔር!!!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!!!
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 8 ቀን 2015 ዓ.ም