በዚህ ሳምንት ውስጥ በክርስትና እምነት ተከታየች ዘንድ በጾምና በፀሎት ሲታወሱ የሰነበቱት ቀናት ሰሙነ ሕማማት በመባል ሲጠሩ የዛሬው ዕለትም ቀዳሚት/ቅዳም ሥዑር (በተለምዶ ቅዳሜ ሹር ወይንም የተሻረው ቅዳሜ) ተብሎ ተለይቷል። በነገው ዕለተ ፋሲካም “ጌታችን ተመረመረ ዲያቢሎስ ተወገረ፤ የምሥራች ቄጤማ ተቀበሉ” በሚሉ ካህናት የመልካም ምኞት መግለጫ ክርስቶስ ሞትን ድል የነሳበት የትንሣኤው ብሥራት ይበሰራል። የክርስትና እምነት ዋና መልሕቅ የሆነው ይህ በዓል በእምነቱ ቤተሰቦች ዘንድ እጅግ ላቅ ያለ መንፈሳዊ ትርጉምና ከበሬታ ያለው ነው። እንኳን ለበዓለ ፋሲካ በሰላም አደረሰን።
ወደ ዝርዝር ጉዳዮች ከመዝለቃችን አስቀድሞ መብራራት የሚገባቸውን አንዳንድ አጠቃላይ ሃሳቦችን አፍታትተን እንለፍ። እግዚአብሔር አምላክ ከሰኞ እስከ ዐርብ ፍጥረታትን በሙሉ እና ክቡሩን የሰው ልጅ በአርአያውና በአምሳሉ ከፈጠረ በኋላ ያረፈበት ዕለት ቅዳሜ እንደሆነ ይታመናል። ቅዱስ መጽሐፍ ታሪኩን እንደሚከተለው ያብራራዋል፤ “ሰማይና ምድር ሠራዊታቸውም ሁሉ ተፈጸሙ።
እግዚአብሔርም የሠራውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጸመ። በሰባተኛውም ቀን ከሠራው ሥራ ሁሉ ዐረፈ። እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ አርፏልና” (ዘፍጥረት 2፡1-3)። የቅዳሜ ዕለት ታላቁ ሰንበት (ሰንበት ዐቢይ) በመባልም ይታወቃል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር አርፎ የዋለበት ዕለት በመሆኑም በልዩ ሁኔታ ይዘከራል።
ስለ ፋሲካ ጥንተ አመጣጥ ጥቂት እናስታውስ። ፋሲካ እስራኤላውያን ከግብፅ ባርነት ነፃ የወጡበት ዕለት ነው። የአወጣጣቸው ታሪክም እንደሚከተለው በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ ተተርኳል። “እኩለ ሌሊት በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር በግብፅ ምድር በዙፋን ላይ ከተቀመጠው ከፈርዖን የበኩር ልጅ ጀምሮ በግዞት እስካሉት እስከ ምርኮኞቹ በኩር ድረስ በግብፅ ምድር የተገኘውን በኩር ሁሉ፣ የእንስሳቱንም በኩሮች ሁሉ ቀሰፋቸው። ፈርዖንም ባሪያዎቹም ሁሉ ግብፃውያንም ሁሉ በሌሊት ተነሡ፤ የሞተ የሌለበት ቤት አልነበረምና በግብፅ ምድር ታላቅ ለቅሶ ሆነ። ፈርዖንም ሙሴንና አሮንን በሌሊት ጠርቶ፡- እናንተ የእስራኤልም ልጆች ተነሡ ከሕዝቤ መካከል ውጡ፤ ሂዱም አላቸው፤፡”
“በእስራኤላውያን ቤት ግን የሞት መቅሰፍቱ በሚያልፍበት ጊዜ የቤታቸው ጉበንና መቃን የጠቦት ደም ተቀብቶ ስለነበር ቀሳፊው ሞት ወደ ቤታቸው ዘልቆ በመግባት እንዳይገድላቸው ተከልክሎ ነበር”። እስራኤላውያን ከ430 ዓመታት የባርነት ሕይወት ነፃ ወጥተው ማርና ወተት ታፈሳለች ወደ ተባለችው የተስፋ ምድራቸው ወደ ከንዓን ጉዞ የጀመሩት በዚያ ታሪካዊ አስደንጋጭ ምሽትና ከዚያ ቀናት ቀደም ብሎ በተፈጸሙ በአጠቃላይ አሥር በሚያህሉ እጅግ ዘግናኝ ተዓምራት ደንዳናው የፈርዖን ልብ ከተሰባበረ በኋላ ነበር።
እስራኤላውያን ከግብፅ ባርነት ነፃ ለመውጣት ጉዞ የጀመሩበት ዕለትን በተመለከተ በአንዳንድ የሥነ መለኮት ማብራሪያዎች ውስጥ ዘመኑ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በግምት ከ1500 ዓ.ም ገደማ በፊት እንደነበረ ይገመታል። የዘመኑ ስሌት ዛሬም ድረስ በብዙ የዘርፉ ተመራማሪዎች ዘንድ ወደ ጋራ መግባባት አልተደረሰበትም።
ይህ የአይሁዳዊያን የፋሲካ በዓል (Pesach) በአንድ ወቅት ብቻ ተከብሮ የሚያበቃ ሳይሆን ከትውልድ ትውልድ እንዲተላለፍ ጭምር መለኮታዊ ትዕዛዝ ተሰጥቶበታል። “እግዚአብሔር በኃያል ክንዱ ከግብፅ ምድር አውጥቷችኋልና ይህንን ሥርዓት በተወሰነው ጊዜ በየዓመቱ ጠብቁት/ አክብሩት።” በዚህም አምልካዊ ትዕዛዝ ምክንያት እስከ ዛሬ ድረስ በአይሁድ እምነት እንደ አንድ ዐቢይ በዓል ተደርጎ በዝርዝር የተደነገጉ ሥርዓቶች ሳይጓደሉ መከበሩን ቀጥሏል።
በአዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ዘንድ ግን “ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶልናል” (1ኛ ቆሮንቶስ 5፡7) ተብሎ በተጻፈው መሠረት የፋሲካ ማዕከላዊ ትኩረት ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰዎች የኃጢአት ሥርየት ደሙን ያፈሰሰበት፣ የሞተበት፣ የተቀበረበትና በትንሣኤው ሞትን ድል ነስቶ ታላቅ የማዳን ተግባር የፈጸመበት ፍቅሩ እየታወሰ በዓሉ በየዓመቱ በታላቅ መንፈሳዊ ድባብና ድምቀት ይከበራል።
ተስፋቸውን ያመከኑ “የፋሲካ ልጆች”፤
በአንዳንድ የሥነ መለኮት ምሑራን የፋሲካ ልጆች (Children of Passover) በሚል ቅጽል የሚጠሩት እስራኤላውያን የግብፃውያንን የባርነት ቀንበር ሰባብረው ነፃ እንዲወጡ ምክንያት የሆናቸው ዋናው ጀግና መሪያቸው ሙሴ ነበር። “ማርና ወተት” ወደምታፈሰው የተስፋ ምድራቸው ለመድረስ 40 ዓመታት በፈጀ የምድረ በዳ ጉዞ የተፈተኑት እስራኤላውያን ተግዳሮታቸው ምድረ በዳው ብቻ ሳይሆን ከሠላሳ በላይ በሆኑ ነገሥታት በርካታ ጦርነቶች ተከፍቶባቸውም እያሸነፉ ጭምር ነበር ሲጓዙ የነበረው።
ሕዝቡ በምድረ በዳው ጉዞ ሲዝልና በጦርነቱ ብዛት ሲመረር፣ ከተጓዦች መካከል በሚያፈነግጡ አመፀኞችና አድመኞች ሕዝቡ ሲታመስ፣ ፈተናው ተደራርቦ ሲያይሉና ሲጨነቁም “ስለምን እግዚአብሔር ከግብፅ ምድር እንድንወጣ ፈቀደ” እያሉ ግራ ሲያጋቡት- “እባክህ አምላኬ ሆይ ይህንን ሕዝብ ተቆጥተህ ከምታጠፋና ቅዱስ ስምህ ከሚሰደብ እኔን ሙሴን ቀድመህ ግደለኝ” በማለት ራሱን ለሕዝቡ የኃጢያት ማስተሰርያ መስዋዕት አድርጎ ማቅረቡንም የሙሴ ግለ ታሪክ በግላጭ ይነግረናል።
“እግዚአብሔር ሰው ከባልንጀራው ጋር እንደሚነጋገር ፊት ለፊት ከሙሴ ጋር ይነጋገር ነበር” የተባለለት ሙሴ፣ ራሱ እግዚአብሔርም፡- “ከባሪያዬ ከሙሴ ጋር እኔ አፍ ለአፍ በግልጥ እነጋገራለሁ፤ በምሳሌም አይደለም” (ዘኁልቁ 12፡6 – 8) ተብሎ የተመሰከረለት እና “በምድር ላይ ካሉት ሰዎች ሁሉ ይልቅ እጅግ ትሑት ሰው ነበር” (ዘኁልቁ 12፡2) የሚል አድናቆት የተቸረው ሙሴ ፍጻሜው ያማረ አልነበረም። ያ ታላቅ የሕዝበ እስራኤል አባት፣ የጦር መሪ፣ ነብይ፣ የምሕረት አማላጅ፣ አስተማሪ፣ ሕግ ተርጓሚ፣ ፈራጅ ዳኛና የጥበብ መጋቢው “የፋሲካ ልጆች” አለቃው ሙሴ ታሪኩ የተጠናቀቀው በዕልልታና በሆታ በታጀበ ድል ሳይሆን በኅዘን ነበር።
“አይዟችሁ ወደ ተስፋችን ሀገር እየደረስን ነው፤ እግዚአብሔር ያዘጋጀልንን ርስት በድል አድራጊነት እንወርሳለን” እያለ ሕዝቡን እያጀገነ እንዳልመራ ሁሉ በአንድ ቅጽበታዊ ስህተት ምክንያት የተስፋው ምድር ዳርቻ ላይ ከደረሰ በኋላ እግሩ ምድሩን እንደማይረግጥ የሚከተለው መለኮታዊ ትዕዛዝ ወጣበት፡- “እግዚአብሔርም ሙሴም አለው፡- ለዘርህ እሰጣታለሁ ብዬ ለአብርሃምና ለይስሐቅ ለያዕቆብም የማልሁላቸው ምድር ትታይሃለች ያቻትልህ፤ በዐይንህ እንድታያት አደረግሁ፤ ነገር ግን ወደዚያች አትሻገርም አለው” (ዘዳግም 34፡4)። እጅግ ያሳዝናል።
የጓጓለትን ምድር በዐይኑ ብቻ አይቶ “አትገባበትም” የተባለው ሙሴ፡- “በምድረበዳ ሞተ፤ መቃብሩም የት እንደሆነ እንኳን እስከ ዛሬ ማንም አያውቅም” (ዘዳግም 34፡6)። የዚህ ሁሉ አሳዛኝ ፍጻሜ መንስዔው ትሑቱ ሙሴ በአንድ አጋጣሚ የእግዚአብሔርን ሥራ ለራሱና ለአሮን በመስጠት “ከዚህ ድንጋይ ውሃ አወጣንላችሁ” በማለቱ ለፈጣሪ ይገባ የነበረውን ክብር ለራሱና ለወንድሙ በመውሰዱና “እኔ ሙሴ!” በማለት ስለታበየ ነበር። እነሆ! የተላለፈበት የፍርድ ቃል እንዲህ ይነበባል፡- “በእስራኤል ልጆች መካከል በጺን ምድረ በዳ በቃዴስ ባለው በመሪባ ውሃ ስለ በደላችሁኝ፣ በእስራኤልም መካከል ስላልቀደሳችሁኝ፣ ምድሪቱን ፊት ለፊት ታያታለህ እንጂ ወደዚያች እኔ ለእስራኤል ልጆች ወደምሰጣት ምድር አትገባም።”
ተስፋው መክኖበት በምድረ በዳ ወድቆ የቀረው ሙሴ ብቻ አልነበረም። የሕጻናቱን ቁጥርና ሌሎች እስራኤላውያንን በፈቃዳቸው የተከተሏቸውን ባዕዳን ሳይጨምር ከግብፅ ከወጡት 601,730 ያህል እስራኤላውያን መካከል የተስፋቸውን ምድር የወረሱት ሁለቱ ኢያሱና ካሌብ ብቻ ነበሩ። ባለመታዘዛቸውና በአመጻቸው ምክንያት ሁሉም እንደ ትቢያ በንነውና እንደ በጋ ቅጠል ረግፈው የቀሩት በምድረ በዳ ውስጥ ነው። ተስፋቸው እውን ሆኖ የከንዓንን ምድር የወረሱት በምድረ በዳ የተወለዱትና የተዋለዱት ልጆች ብቻ ነበሩ። እንደ ዘርፉ ጠበብት ግምታዊ አኃዝ ከሆነ የተስፋ ሀገራቸው የደረሱት አንድ ሚሊዮን የሚገመቱት “የምድረ በዳ ትውልዶች” ብቻ ናቸው። በድል ጀምሮ በሽንፈት ማጠናቀቅ ይሏል እንዲህ ነው።
ዘመኗን በሙሉ “በሰሙነ ሕማማት ገመምተኛነት” የምናውቃት ኢትዮጵያ፤ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውያን የሰሙነ ሕማማት ዜና መዋዕል ታሪክ በዓመት አንድ ወቅት ብቻ የሚታሰብ ሳይሆን የእኛ ብቻ ስጦታ ሆኖ እስኪቆጠር ድረስ ሁሌም አብሮን እንደኖረ ነው። ቀደም ሲል ለመጥቀስ እንደተሞከረው ከሆሳዕና እስከ ቀዳሚት ሥዑር ያሉት ደመናማ ቀናት ኢየሱስ ክርስቶስን ለመያዝ አይሁድ ክፋት የጎነጎኑበት፣ ምክራቸውን በመሐላ ኪዳን በማጽናትም ጻድቁን ጌታ ይዘው የገረፉበት፣ የሾህ አክሊል በመጫን የተሳለቁበት፣ ወደ ቀራኒዮ እያጣደፉ ወስደው በመስቀል ላይ የቸነከሩበት፣ ገድለው የቀበሩበት… ምኑ ተዘርዝሮ ይዘለቃል፤ ብቻ ከሰኞ እስከ ቀዳሚት ሥዑር ባሉት ቀናት በክርስቶስ ጌታ ላይ የግፍ ወጀብ የዘነበበት የሰሙነ ሕመማት ዕለታት ነበሩ።
ይህንኑ የመከራ ሣምንታት ለማስታወስ ነው የእኛም “ሀገራዊ አየር” እስከ ዛሬዪቱ ዕለት ድረስ በሃሌሉያ ዝማሬ ሳይሆን በኪርያላይሶ የምሕረት ምልጃና “በኤሎሄ” መቃተት ሕዝበ ክርስቲያኑ ወደ ፈጣሪው እግዚኦ ሲል የሰነበተው። ለማስታወስ ያህል፡- “የሰሙነ ሕማማት ሀገራዊ ታሪካችንን” በወፍ በረረ ቅኝት መለስ ብለን በመቃኘት ራሳችንን እንፈትሽ። በኢትዮጵያ የረዢም ዘመናት ታሪክ ውስጥ ኪርያላይሶና የኤሎሄ የጣር ጩኸት ሳይደመጥ ያለፉ ሥርዓተ መንግሥታት ይኖሩ ይሆን? በግሌ እርግጠኛ ለመሆን እቸገራለሁ። ከመጻሕፍት ንባብ ይልቅ በሕይወት ያለፍንባቸውንና እየኖርንበት ያለውን ወቅት እንኳን ልብ ብለን ጠልቀን ብንመረምር “የሰሙነ ሕማማት” መከራችን ይህ ልኩ ተብሎ የሚቆጠርም “የሚመዘንም” እንዳልሆነ እንረዳለን።
ከግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወደ ደርግ የተደረገው ሽግግርና የወታደራዊው መንግሥት አገዛዝ የተጠናቀቀው ሀገሪቱ ከሰሙነ ሕማማት ድንጋጤና ኃዘን ሳትወጣ የኃዘን ጨርቅ በመልበስ እንደተቆራመደች ነበር። በሙሴ የመሰልናቸውና “ፋኖ ተሠማራ! ፋኖ ተሰማራ! እንደነ ሆችሚኒ እንደ ቼኩቬራ” እያለን “ቼ! በለው በማለት የፈከርንላቸው” የወቅቱ ሳይሞቅ ፈላ አብዮታውያን ወጣቶቻችን ታሪካቸውን የደመደሙት በፈርዖን ለሚመሰለው ለጨካኙ የጁንታ መንግሥት አሳልፈው በመስጠት ነበር። ሀገሪቱን በ“ሰሙነ ሕማማት ውስጥ ጥለው” እነርሱም እንደ እስራኤላውያን ልጆች በምድረ በዳ ወድቀው የቀሩት ምክንያት አልባ በሆነ የእርስ በእርስ ፉክክር እየተገዳደሉና በጨካኙ ልበ ደንዳና ወታደራዊ በትር እየረገፉ ጭምር ነበር።
እንኳን ኢትዮጵያን ለመታደግ ቀርቶ ለራሳቸውም ቢሆን “የወረደባቸውን መቅሰፍት” ለመቋቋም አቅምም ሆነ ብቃት አልነበራቸውም። “ሙሴዎቻችን” ብለን ያንቆለጳጰስናቸውም ተስፋ ወደ ገቡልን “የሕልም ዓለም” ሊያሻግሩን ቀርቶ ሀገሪቱ ባለችበት ቆማ ለመርገጥ እንኳን ባለመቻሏ ልጆቿን ለማኖር የተገደደችው ከሲዖል በማይተናነስ ፍዳ ውስጥ እንደተዘፈቁ ነበር።
ከደርግ ወደ ሕወሓት/ኢሕአዴግ፣ ከዚያም ወደ ብልጽግና የተደረጉት የሥርዓተ መንግሥታት ሽግግሮችም በስንት ጉዳዮች ሀገራችንን “ሰሙነ ሕማማት ላይ” እንደጣሏት በዝርዝር ማስታወሱ የትናንታችን ለዛና ወዙ ገና ጠፈፍ ስላላለ እንዲህና እንዲህ ነበር ብሎ መተረኩ እጅግም ላያስፈልግ ይችል ይሆናል። የለውጥ መሪዎቹ “በሙሴ”፣ ያስወገዱት ሥርዓት በፈርዖን፣ ሕዝቡም በእስራኤል ልጆች እየተመሰለ ሲተረክ ቢኖርም የዜጎች ኑሮ ከድጡ ወደ ማጡ ሲያሽቆለቁል እንጂ “በመና” የሚመሰል የሕይወት ለውጥ ማየት አልተቻለም።
“ሙት ወቃሽነቱን” ለጊዜው አቆይተን የዛሬያችንን ውሎ አምሽቶ ብቻ ብንፈትሽ እንኳን “ከሰሙነ ሕማማት” ነፃ ወጥተን ወደ “ትንሣኤ” እየተቃረብን ነው እንዳንል ብዙ ጉዳዮች አፋችንን ያሲዙናል። በተግባር ሲፈጸሙ የምናስተውላቸው፣ በስሜት ሕዋሳቶቻችን የምናሸታቸው፣ እያንዳንዳችን ላይ ተፈጽመው ምስክር የሆንባቸው መከራዎቻችን ይህ ልኩ የሚባሉ ዓይነት አይደሉም።
ከሃይማኖት ዶግማ እስከ ፖለቲካ “ኤሎሄያችን” ለጥጠን ለመነካካት የሞከርናቸው ጉዳዮቻችን እንዲህ እንደ ዋዛ በድምድማት የሚቋጩ አይደሉም። ያልተመለሱልን ሀገራዊ ጉዳዮቻችን እጅግ ብዙዎች ናቸው። ከዳቦ ረሃብ እስከ ፖለቲካ ቀውስ የተጫኑብን “የባርነት ቀንበሮች” እንኳን ከጫንቃችን ላይ ሊፈቱ ቀርቶ እንዲያውም ክብደቱ በርትቶብን በማስጎንበስ በእንብርክክ እያስኬደን እንዳለ አፋችንን አፍነን የምንቃትትበት የሲቃ ድምጻችን ምስክር ነው።
እስከ መቼ ኢትዮጵያ የሾህ አክሊል እንደ ደፋች ትኖራለች? እስከ መቼስ ቀራኒዮ ላይ ተቸንክራ “ኤሎሄ! ኤሎሄ! ላማ ሰበቅታኒ” እንዳለች ውላ ታድራለች? “የንጹሐንን የደም ግብር” የምንከፍልባቸው ሀገራዊ “ትምክህቶቻችን” መቼ ነው የሚለዝቡት? “አቤቱ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ተዋርደው ኑሯቸው ሰሙነ ሕማማት ከሚሆን ለሰላም ስል እኔ ዝቅ ብዬ እግር እስከማጠብ በመድረስ የክርስቶስን አርአያነት እከተላለሁ” የሚሉ ሙሴዎች መቼ ነው ወደ አደባባይ የሚወጡትና “ወደ ተስፋችን” የሚያፈልሱን? እስከ መቼስ ነው ከሰሙነ ሕማማት ቀጥሎ የሚመጣው ትንሣኤ ርቆብን ተስፋችን እንደመከነ የምንኖረው። ኢትዮጵያ ሆይ የትንሣኤ ጌታ ትንሣኤሽን ያፋጥንልሽ፤ እናም ነገ ትንሣኤ ይሆናል በይን። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ። ሰላም ይሁን!
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 7/2015