አንዳንድ የድሮ ዘፈኖች የ“ድሮ”ነት አስታዋሾቻችን ናቸው። በዘፈን ግጥሙ ላይ ድሮነትን ካሳዩን ድምጻውያን አንዱ ክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ነው። “ምግብ እማ ሞልቷል አምላክ መች ነሳኝ /የፍቅር ራ’ብ ነው እኔን ያከሳኝ” ይለናል። ይህን ግጥም ወደ ዛሬ ብናመጣም ከነባራዊው ሁኔታ ጋር የሚገጥም አይሆንም። ዛሬ ቢሆን ግጥሙን ቀይሮ “ምግብ እማ ሞልቷል” የሚለውን ሀገር የሚለውጠው ይመስለኛል።
በአሁኗ ዓለም ፍቅርና ሰላም ማጣት ዋነኛ ችግር ከሆኑ ሰነባብተዋል። ለከፋም ጉስቁልና ዳርገዋታል። በተለይም በማደግ ላይ ላሉ ሀገሮች ሁኔታው በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ሆኖባቸዋል። በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ሆና ለመለወጥ በምትውተረተር ሀገራችን ላይ ደግሞ መልከ ብዙ ሆኖ ተገልጿል።
በአገር ውስጥ ተከስቶ የነበረው ጦርነት፣ ዓለም አቀፍ ጫናዎች፤ ሰው ሠራሽ የምርቶች እጥረት ጋር ተዳምሮ በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ የፈጠሩት ችግር ከፍ ያለ የኑሮ ውድነት እንዲከሰት አድርጓል። ‹‹ግርግር ለሌባ ያመቻል›› እንደሚባለው ወቅታዊ የሆነውን ሀገራዊ እውነታ መደበቂያ ያደረጉ ግለሰቦችና ቡድኖች በሚፈጥሩት ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አሻጥር አብዛኛው የማህበረሰብ ክፍል በኑሮ ውድነት እየተፈተነ ነው። ይህም ከኢትዮጵያዊነት ያፈነገጠ አዲስ ማንነት በጊዜ ካልተገራ ሊያስከትል የሚችለው አደጋ የከፋ እንደሚሆን ለመገመት የሚከብድ አይሆንም ።
እዚህ ላይ እንደ አንድ ኃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ ለረሳችን ልንጠይቀው የሚገባ ጥያቄ ያለ ይመስለኛል። ለእኔ፣ ለአንተ፣ ለሁላችን “ኢትዮጵያዊነት ምንድን ነው?” በዚህ ጥያቄና ልንሰጠው በምንችለው ምላሽ ውስጥ ሆነን እራሳችንን እንመልከት።
ኢትዮጵያዊነት ማለት ተካፍሎ ከመብላት ባለፈ ከሌለው ቀንሶ የመስጠት፣ የመተሳሰብና የመረዳዳት ማንነት ነው። ተካፍሎ ከመብላት ባለፈም በአንድ መአድ ከብቦ ያለችውን የሚቋደስ ማንነት ነው። ታዲያ የዛሬ ስግብግብነታችን ከየት መጣ? እንዴት መጣ? ብለን ስንጠይቅ የአብዛኞቻችን ምላሽ ራስ ወዳድ ነጋዴዎቻችንና ከችግሩ የፖለቲካ ትርፍ ይዘው የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች ልንል እንችላለን።
እርግጥ ነው ፖለቲከኞች በሕዝብ ችግር ፖለቲካ ቢሠሩም፤ ስግብግብ ነጋዴዎች የቱንም ያህል ለኑሮ ውድነቱ አይነተኛ ድርሻ ቢኖራቸውም ሕዝብ ኃይል ነውና ሕዝቡም የራሱ ድርሻ የለውም ብለን ለማሰብ የሚያስችል ድፍረት ሊኖረን አይችልም።
አብዛኛው በግብርና በሚተዳደርባት ሀገር ግብርናው በተሻለ አቅም ላይ አለ እየተባለ አስከፊ የኑሮ ውድነት ተከሰተ… ማለት በአንዳንድ መመዘኛዎች እውነትነት የጎደለው ነው። በእርግጥ ካለን ባህላዊና ያልዘመነ የአስተራረስ ዘዴ የተነሳ ከዘርፉ የሚገባንን ያህል ምርት ላንሰበስብ እንችላለን፤ ይህ ማለት ግን አሁን ያለውን የኑሮ ውድነትና የሸቀጦች ዋጋ መናር እዚህ ደረጃ ላይ ያደርሰዋል ለማለት አያስደፍርም።
ብዙ ማስታመም የሚፈልጉ ጉዳዮቿን እያስታመመች ነገን በምትናፍቅ አገር ላይ ከፖለቲካው ባሻገር በርካታ ራስ ወዳድ ነጋዴዎች ሰው ሠራሽ እጥረት ፈጥረው ማህበረሰቡን በኑሮ ውድነት በእጅጉ አማረውታል። ይህም ሕዝቡ ብዙ ተስፋ ባደረገበት መንግሥት ላይ ጣቱን እንዲቀስር አድርጎታል።
በብዙ የቤት ሥራዎች የተወጠረው መንግሥትም የተለያዩ አማራጮችን ተጠቅሞ ገበያን የማረጋጋት ሥራ በመሥራት ጤፍ ላይ የታየውን የዋጋ ንረት ለማረጋጋት እየሞከረ ይገኛል። ሰሞኑን በተካሄደው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 11ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ የኑሮ ውድነቱን አስመልክቶ ከተወካዮች ምክር ቤት አንድ ጥቁምታ ተሰጥቶ ነበር። አሁን ያለውን የኑሮ ውድነት ለማርገብ ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ አሻጥረኞችን መቆጣጠር እንደሚገባም ተገልጿል።
የመንግሥት ተቀዳሚ ተግባር የማኅበረሰቡን ጥያቄ መመለስ ነው። በዚህ ሰዓት የማኅበረሰቡ ጥያቄ ደግሞ የኑሮ ውድነት እና ከኑሮ ውድነቱ ጋር ተያይዞ የሚመጣው ጥያቄ ነው። በአሁኑ ሰዓት የኑሮ ውድነቱን አስመልክቶ ሁሉም የማኅበረሰብ አባል በአንድ አይነት ስሜት ውስጥ ነው። ይህ የሕዝብ ስሜት መንግሥት ላይ ተጋብቶ ገበያውን ማረጋጋትና የኑሮ ውድነቱ የተፈጠረበትን መንገድ ለማስተካከል ጥረት እየተደረገ ይገኛል።
ሕዝብ በደመወዙ ጤፍ ገዝቶ ካልበላ፣ በደመወዙ ከወር ወር ካልደረሰ ማህበራዊ ቀውስ ውስጥ ነን ብሎ መናገር ይችላል። ማህበራዊ ቀውስ ደግሞ ለፖለቲካዊና ለኢኮኖሚያዊ ቀውስ መንገድ የሚከፍት ነው። ይህ ነገር እንዲስተካከል ሕዝብና መንግሥት ተቀናጅተው መሥራት ይጠበቅባቸዋል። ገበያን ማረጋጋት ለመንግሥት ብቻ የሚተው ሥራ አይደለምና ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ ይገባል።
በተለይ አንዳንድ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ስለወቅታዊው የኑሮ ውድነት ሲናገሩ እንደሚሰማው፤ የምርት እጥረት እንደሌለና የኑሮ ውድነቱ የተፈጠረው በተለያዩ ሰው ሠራሽ ምክንያቶች እንደሆነ ሲያነሱ ይሰማል። በአሁኑ ወቅት የሕዝቡ ትልቅ ጉዳይ የሆነውን የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት ሰው ሠራሽ የተባሉ ችግሮችን በማጥራት ገበያውን ማረጋጋት ከሁሉም ይጠበቃል።
ሀገር የታማኝ ልቦች ነጸብራቅ ናት። እኔ በአንተ አንተ በእኔ የምንኖር። በእኔ ችግር ውስጥ የምታተርፍ ከሆነና በአንተ ማጣት ውስጥ ከፍታን የምሻ ከሆነ ሰውነት እዚያጋ ያበቃል። ሀገራችን በኢኮኖሚውም ሆነ በፖለቲካው አውድ የምትሰቃየው እንዲህ ባለ ጥሎ ማለፍ ውስጥ ነው።
ጥሎ ማለፍ ሩቅ አይወስድም። ጥሎ ማለፍ የእውቀትና የብልጠት መለኪያም አይደለም። መንገድ የሚዘጋ፣ ከዕድል የሚያርቅ የህይወት መሰናክል ነው። ተባብረን የበላነውና፣ ተባብረን የተራመድነው መንገድ ነው ሩቅ የሚወስደን። ሀገርና ሕዝብ የሌሉበት ምኞትም ሆነ ሀሳብ መጀመሪያው ጥሩ ቢመስልም መጨረሻው ውድቀት ነው። ለዚህ ደግሞ ምስክር የሚሆኑ ብዙ ታሪኮች አሉን።
የብቻ ትናንት የለንም። ኋላችን ቢታይ በአንድነት የረገጥነው የጋራ ዳና ነው የሚታየን። በጋራ ባሳመርነው የኢትዮጵያዊነት ጎዳና ላይ ተያይዘንና ተደጋግፈን የመጣን ነን። አሁን ላለችው ኢትዮጵያም የሚጠቅማት ያን የመሰለ የጋራ ዳና ነው። ልክ ለብቻ እንደመብላት ሁሉ አንዳንድ ነገሮች የሚጠቅሙን ይመስሉናል እንጂ ጠቅመውን አያውቁም። ራስ ወዳድነትንና ግለኝነትን ከማስተማር ባለፈ የሚፈይዱልን አንዳች ነገር የለም።
አሁን ለተፈጠረው የኑሮ ውድነት ለብቻ የተራመድነው ራስ ወዳድነታችንና ግለኝነታችን የራሱ አስተዋጽኦ አለው። ከዚህ ማህበራዊ ቀውስ ለመውጣት ራስ ወዳድነት የሸፈነው የኢትዮጵያዊነት መልክ መውጣት አለበት። ያ መልክ የቸርነት መልክ ነው። ያ መልክ አብሮ የመብላት፣ አብሮ የመኖር መልክ ነው። ያ መልክ በዓለም አደባባይ ያቆነጀንና አስደናቂ ሥርአትን የፈጠረልን መልክ ነው። ይህን መልክ ሸፍነን የምንፈጥረው ሌላ መልክ የለም።
ኢትዮጵያዊነት ሲነሳ ሁላችንንም የሚገርመን አንድ የጋራ እውነት ያለን ሲሆን፤ እርሱም ተካፍሎ የመብላት ባህላችን ነው። ይህ እኔና ሌላውን ዓለም የሚያስደንቀን ትልቅ እሴታችን ነው። በዚህ ባህላችን ብቻ ከዓለም እና ከታሪኳ ልዩዎች ነን።
ዓለም እኔነትን ባስቀደመበት፣ ብቻ መብላትን እንደ ሥልጣኔና እንደ ዘመናዊነት በያዘበት በዚህ ዘመን ላይ እኛ ኢትዮጵያውያን ግን በጋራ በመቆም፣ በጋራ በመብላት የማንነጣጠል ሕዝቦች መሆናችንን ለዘመናት አስመስክረናል። ይህ በየትኛውም የዓለም ክፍል የሌለ፤ የሚያኮራና የሚያስደንቅ ኢትዮጵያዊ መልክ ነው።
ይህ ለሰው ልጅ ክብር የሰጠ አንድነትን ያስቀደመ የሥልጣኔ አሻራ ነው። ይህ የእኛ ብቻ የሆነ የድንቅ ሥርዓት ውጤት ነው። ሁሌም እንደምለው ሥልጣኔ ራስን ከመውደድና የራስን እውነት ከመቀበል የሚጀምር ነው። ዘመናዊነት ከራስ እውነት ተነስቶ ወደ ሌሎች የሚተላለፈ የአስተሳሰብ ውጤት ነው።
እኛ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ቀደምት ሥልጡን ሕዝቦች ስለመሆናችን በርካታ ማስረጃዎች አሉ። ይህ ሁሉ ባይሆን እንኳን አብሮ መብላታችን፣ አብረን መቆማችን፤ በደስታና በሀዘናች ጊዜ መረዳዳታችን ቀዳሚነታችንን ከማሳየቱም በላይ የሥልጣኔ ፈር ቀዳጆች እንደሆንን አንዱ አመላካች እውነታ ነው።
በራስ ወዳዶች እየጠፋ ያለ በምንም የማይተካ ማንነት አለን። ይህንን መልክ ወደ ነበረበት መመለስ አለብን። የምንመልሰው ደግሞ እንደጥንቱ በአንድነትና በመተሳሰብ ስንቆም ነው። የእኔ ማጣት አንተን ሲያምህ፣ የአንተ ማግኘት እኔን ሲያስደስተኝ ነው። እንደለመድነውና እንደተለማመድነው ሥልጣኔ እንደመለሰለን ስይጥንና ውስጥ ለብቻ ቆመን ይሄን መልክ መመለስ አንችልም።
መጠየቅ አለብን፤ የምንሰማውን ሁሉ “እውነት“ ነው ብለን መቀበል ሳይሆን እውነትን የሚያስስ በመረጃ ላይ የተደገፈ የህይወት ልምድ ያስፈልገናል። ብዙዎቻችን ጤፍ ስለመወደዱ እንጂ እንዴትና ለምን እንደተወደደ ብንጠየቅ መልስ የለንም። መልስ የለንም ማለት ደግሞ ለችግሩ ፈጣሪዎች ጉልበት እየሆንን ነው ማለት ነው። ችግራችን መፍትሄ እንዲያመጣ መንግሥትን መጠየቅ፣ ወንጀለኞችን ማጋለጥ ይጠበቅብናል።
ለመፍትሄ የሚሆን ሀሳብና እውቀት ሳንይዝ “ጤፍ ተወደደ” እያልን ብናወራና ብናማርር ትርጉም የለውም። ሁላችንም ስለሀገራችን የሆነ አስተዋጽኦ ማድረግ ይኖርብናል። እስኪሆንና መንግሥት የሆነ ነገር እስኪያደርግ መጠበቅ ሳይሆን የሚጠበቅብንን፤ የድርሻችንን በመወጣት ለመንግሥት ጉልበት፣ ለራስ ወዳዶች ደግሞ ውርደት መሆን እንችላለን።
ስንጠይቅ ነው ችግሮቻችን ላይ እና ችግር ፈጣሪዎች ላይ የምንደርሰው። እንዴት ሆነ? በማን ሆነ? ለምን ሆነ? ብሎ መጠየቅ አሁን ላይ እንደሀገር የተጋረጡብንን የኑሮ ውድነቶች እና ሌሎች ችግሮቻችንን ማርገቢያ መንገድ ነው። አብዛኞቹ ችግሮቻችን ባለመጠየቅ የሚመጡ ናቸው። ለመብቱ የሚከራከር ማህበረሰብ ያስፈልጋል። ማንም ተነስቶ የዋጋ ጭማሪ ሲያደርግ ለምን የሚል ጥያቄ ልንጠይቅ ያስፈልጋል።
ራስ ተኮር የሆኑ ወጪት ሰባሪዎች ሆን ብለው የኑሮ ውድነትን በመፍጠር በሕዝቡ ላይ ግፍና በደልን እየሠሩ ነው። በተለይ ደሃው የኅብረተሰብ ክፍል በእነዚህ ውሸታምና አጭበርባሪ ነጋዴዎች እየተሰቃየ ያለበት ሁኔታ ጎልቶ ይታያል። ሕዝብን ከማገልገል ይልቅ ያልተገባ ትርፍና ጥቅም ለማግኘት በሸቀጦች ላይ ያልተገባ የታሪፍ ጭማሪ በማድረግ ጊዜውን ፈታኝ አድርገውታል።
ምርት በመደበቅ፣ በማሸሽና ሌሎች ማጭበርበሪያ መንገዶችን በመጠቀም ከመንግሥት እውቅና ውጪ በሆነ አሠራር ራሳቸውን ሲጠቅሙና ደሃ ሕዝብ ሲበዘብዙ ማየት አዲስ ነገር አይደለም። ወቅታዊውን የሀገራችን ችግር እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም ሀብት ለማጋበስና የኑሮ ውድነትን በመፍጠር መንግሥትና ሕዝብን ሆድና ጀርባ ለማድረግ እየሠሩ ያሉ የክፋት ልቦች እዚህም እዛም ተሰግስገው ይገኛሉ።
የነዚህ ግለሰቦች ስውር አላማ የታወቀ ነው። በአንድ ላይ ሆነን እነዚህን ህገ ወጦች በማጋለጥና ለሕግ በማቅረብ የኑሮ ውድነቱን ማስተካከል የሁላችንም ኃላፊነት ነው። መንግሥት ብቻውን የመፍትሄ አካል ሊሆን አይችልም። ሕዝብ እየጠቆመ መንግሥት እርምጃ ሲወስድ ነው ችግሮቻችን መፍታት የሚቻለው።
ገዢውም ሻጪውም፣ ነጋዴውም ሸማቹም አብሮ የሚኖር ነው። ከሌላ ፕላኔት የመጡ ወይም ደግሞ ለአንድ ጊዜ ታይተው የጠፉ ፍጥረቶች አይደሉም። ማን ምን እንደሚሠራ እናውቃለን። ሕገወጦችን በማጋለጥ ለራሳችን ውለታ ልንውል ይገባል። ወንጀለኞችን ደብቀን ኑሮ ተወደደ፣ ጤፍ ይህን ያህል ገባ ብንል ልክ አይደለም።
ለዘመናት አብሯቸው የኖረን ሕዝብ በማገዝና በመደገፍ በዚህ ክፉ ቀን ላይ ውለታውን እንደመመለስ ዞሮ ጨካኝ መሆን ውለታ ከመብላት ባለፈ ነውረኛ ድርጊት ነው። አብረው የማይኖሩ ይመስል፣ ይሄ ክፉ ቀን የማያልፍ ይመስል እንዲህ አይነት ያልተገባ ግፍ መሥራት ተገቢ አይሆንም።
ይህ ጊዜ ያልፋል። ሁላችንም የምንናፍቀው አዲስ ቀን ይመጣል። በዚህ የንጋት ዋዜማ ላይ እንደ አባቶቻችን ሥርአት እርስ በርስ መተጋገዝ እንጂ ሆድና ጀርባ መሆን የምንፈልጋትን ኢትዮጵያን አይፈጥርልንም። ይህ የኢትዮጵያዊነት መልክ አይደለም። በዚህ ሥርአት ውስጥ አልመጣነው። ይሄን የጭካኔ ተግባር አናውቀውም። ሥርአታችን አብሮ መብላት፣ አብሮ መጠጣት ነው። ሥርአታችን ተካፍሎ መብላት ነው። ያለው ለሌለው መስጠት ነው። እውነቱ ይኸው ነው!
እኛ ነውር የምናውቅ ሕዝቦች ነን። ነውራችን የት ሄደ? ደሃን እንደማስጨነቅ፣ ከደሃ ላይ እንደመውሰድ እኮ ግፍና ነውር፣ ሀጢያትና በደል የለም። እስካልተሳሰብን ድረስ የጥንቱን የአብሮነት መልክ መመለስ አንችልም፡፡ አብሮ ለመኖር ያለን አማራጭ አንድ ብቻ ነው፣ መተሳሰብ ነው።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 3/2015