በዱሮ በሬማ ታርሷል!”፤
የተሸከሙትን መልእክት ልብ ብለን ሳንመረምር ለዕለት ተዕለት አኗኗራችን ከምንገለገልባቸው የተግባቦት ብሂሎቻችን መካከል አንዱ፤ “በዱሮ በሬ ያረሰ የለም” የሚለው አባባል ቀድሞ ይጠቀሳል፡፡ ሸምተን ወይንም አርሰን “የዕለት ጉሮሯችንን ለመድፈን” የምንመገባቸው የዛሬዎቹ የእህል ዓይነቶች በትናንት በሬ ታርሰው ዘራቸው በቅብብሎሽ ከእኛ ዘንድ መድረስ ስለቻለ ብቻ ነው፡፡ የዛሬው አርሶ አደር ከትናንት ወንድሙ (እህቱ) በማሳው ላይ የሚዘራውን ዘር “በአደራ” ባይቀበል ኖሮ የሀገራችን ማሳዎች በሙሉ ጦም ውለው ጦም ባሳደሩን ነበር፡፡
እርግጥ ነው፡- በቅብብሎሽ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የኖረው የእህል ዘር ምናልባትም ሳይለቀም ወይንም ከአስተላላፊው “ቸልተኛነት” የተነሳ ጥቂት የእንክርዳድ ፍሬዎች ሊቀላቀሉበት ይችሉ ይሆናል። ልቅም ያለ ንፁህ የእህል ዘር ከትውልድ ትውልድ ቅብብሎሽ ተደርጎም እያለ ተቀባዩ ገበሬ ዘሩን በራሱ ማሳ ላይ ከዘራ በኋላ “ተቀብረው ያንቀላፉ” አንዳንድ የአረም ዘሮች የእርሻው መለስለስ ተመችቷቸው በመንቃት ከአዝመራው ጋር መሳ ለመሳ በማደግ ከዋናው ምርት ጋር ተቀላቅለው ጎተራ ሊገቡ ይችሉ ይሆናል፡፡
በጭካኔ የታወሩና በግፍ አብሾ የሰከሩ አንዳንድ ክፉ ግለሰቦችም በዕለት ግጭት ከተቀያዩሙት አርሶ አደሮች ማሳ ውስጥ በጨለማ እንክርዳድ በመዝራት “ደመኛቸውን” ለመበቀል እንደሚሞክሩ በአንዳንድ የሀገር ቤት የእሳት ዳር የቤተሰብ ጭውውቶች ውስጥ “በአያ እከሌ ማሳ ውስጥ ጠላት እንክርዳድ ዘርቶበት ሰብሉ ተበላሸ” እየተባለ መተረኩ የተለመደ ነው፡፡ እንዲያውም እኮ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥም ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ከላይ የተጠቀሰውን መሰል ምሳሌ በማብራራት አስተምሯቸዋል፡፡
“ኢየሱስም ምሳሌው እንዲህ ሲል ነገራቸው፡፡ መንግሥተ ሰማይ በእርሻው ቦታ ምርጥ ዘር በዘራ ገበሬ ትመሰላለች፡፡ ነገር ግን ገበሬውና ቤተሰቡ ተኝተው ሳሉ፣ ጠላት መጥቶ በስንዴው መካከል እንክርዳድ ዘርቶ ሄደ፡፡ ስንዴው በቅሎ ማፍራት ሲጀምር እንክርዳዱም አብሮ ብቅ አለ፡፡ የእርሻው ባለቤት አገልጋዮች ወደ እርሱ ቀርበው ‹ጌታ ሆይ፣ በእርሻህ ቦታ ጥሩ ዘር ዘርተህ አልነበረምን? እንክርዳዱ ከየት መጣ?› አሉት፡፡
እርሱም የጠላት ሥራ ነው አላቸው፡፡ አገልጋዮቹም፣ ‹እንክርዳዱን ሄደን እንድንነቅለው ትፈልጋለህ?› ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱ ግን፣ ‹አይሆንም፣ ምክንያቱም እንክርዳዱን እንነቅላለን ስትሉ ስንዴውንም አብራችሁ እንዳትነቅሉ ተውአቸው፤ እስከ መከር ጊዜ አብረው ይደጉ። በአጨዳ ወቅት እንክርዳዱን አስቀድማችሁ ንቀሉ፤ በእሳትም እንዲቃጠል በየነዶው እሰሩት፤ የስንዴውን አዝመራም ሰብስባችሁ በጎተራዬ ክተቱ አላቸው፡፡” (ማቴዎስ 13፡24 – 30)፡፡
ለትንተናችን ማጠንጠኛ የምናደርገው ዛሬ የምንዘራው የእህል ዘር በትናንት በሬ ታርሶ ትውልድና ዘመን እየተሸጋገረ የተቀባበልነው በረከት እንጂ እንደ ኢንዱስትሪ ሸቀጦች በፋብሪካ ተፈብርኮ የምናገኘው ያለመሆኑን አስረግጦ ለመናገር ነው፡፡ ስለዚህም የዘር እህል ክቡር ነው፡፡ ለእለት ፍጆታ አይቆላም፤ አይፈጭምም። የሚቀመጠውም በጥንቃቄ ነው፡፡ የዘር እህል ተስፋም ነው፡፡ በአንድ ጭብጥ የዘር እህል ውስጥ መቶ እጥፍ በረከት ታጭቆበታል፡፡
“መቼም አላለልኝ ከዘሩ ቁይልኝ” እንዳለው ባለሀገር፤ የዘር እህል ቋጠሮ ተፈትቶ ለዕለት ችግር ወይንም ለነፍስ አድንነት ይዋል ቢባል እንኳን በምክንያትነት የሚጠቀሰው የከፋ የድርቅ፣ የጦርነት ወይንም የመፈናቀል መከራ በአርሶ አደሩ ላይ ውድቆ ንብረቱም መቅኖ አጥቶ ከቀዬው ነቅሎ እንዲሰደድ ግድ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ እንዲያም ቢሆን ግን አንዳንድ ጽኑ እምነት ያለው አርሶ አደር “የዘር እህሌን ከምበላ ሞቴን እመርጣለሁ” የሚለውን መሃላውንና ቃል ኪዳኑን ላለማፍረስ ሲል ለዘር የቋጠራትን እፍኝ እህል በዱላው ጫፍ አንጠልጥሎ ለመሰደድ መጨከኑ አይቀርም፡፡
እግር ባደረሰው አካባቢ ሲደርስ ተፈጥሮ ፊቷን መልሳ የሚታረቁ ከሆነ ሊዘራ ተስፋ በማድረግ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ “የዘር እህል የትናንትናና የዛሬ ብቻ ሳይሆን፤ የነገ ተስፋም ጭምር ነው” የሚባለውም ስለዚሁ ነው። እናስ የዘር እህልና የሀገር ታሪክ እንዴት ተመሳሰሉ? ቀጥለን የምናብራራው ይሆናል፡፡
“ያለ ታሪክ ሀገር አይደምቅ”፤
ታሪክ ማን ነበርንን፣ እንዴት እየኖርን ነውንና የነገውን ውሎ አምሽቷችንን ተስፋ በሦስትዮሽ ሸርቦ ለአኗኗራችን ትርጉም የሚሰጠን የሕይወት ጉዟችን አሻራ የታተመበት የተመልካችን መስታወት ነው። ስለዚህም ነው፤ “History is not the past but a map of the past, drawn from a particular point of view, to be useful to the modern traveller.” የሚባለው፡፡ በዓለማችን ላይ በጎ ተጽእኖ አሳርፈው ካለፉት ተጠቃሽ ነፍሰ ሄር ግለሰቦች መካከል ጥቂቶች ስለ ታሪክ ፋይዳ የተናገሩትን አጫጭር ዘመን ተሻጋሪ ጥቅሶች በተቀራራቢ ትርጉም አስታውሰን ወደ ዋናው መዳረሻችን እንገሰግሳለን፡፡
አሜሪካዊው የሳይንስ ፊክሺን መጻሕፍት ደራሲውና የኤሮኖቲካል ኢንጂነር የነበረው ሮበርት ሔይንሌይ (እ.ኤ.አ 1907 – 1988) ስለ ታሪክ የተናገረው ተጠቃሽ አባባል በብዙዎች ዘንድ ይታወስለታል፡፡ እንዲህ ነበር ያለው፡- “ታሪኩን የማያከብር ትውልድ ትናንትም ይሁን ነገ በፍጹም የእርሱ አይደሉም፡፡” በፍልስፍና እውቀቱና በኮሚዩኒኬሽን የጥናት ዘርፍ ዘመን ተሻጋሪ ቀመር ያወረሰን ካናዳዊው ኸርበርት ማርሻል መክለኻን (1911 – 1980) ደግሞ ለታሪክ ብያኔ የሰጠው እንዲህ በማለት ነው፡- “ታሪክን የሚያከብሩና የሚያስታውሱ አሸናፊዎች ናቸው፤ ለታሪክ ክብር የማይሰጡት ግን በሦስቱ የጊዜ (ትናንት፣ ዛሬና ነገ) የትውልድ ቅብብሎሽ ሲኮነኑ መኖራቸው አይቀርም፡፡”
ለነጻነት ባደረገው ተጋድሎ በጥቁር አሜሪካዊያን ዘንድ ታሪኩ ደምቆ የሚነገርለት ማርቲን ሎተር ኪንግ ጁኒዬር (1929 – 1968) እና የትውልድ ሀገሩ የአሜሪካ 34ኛ ፕሬዚዳንት የነበሩትና በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የተባበሩትን የተለያዩ ሀገራት የቃል ኪዳን ጦረኞች በዋና አዝማችነት በማስተባበር ዝናን የተጎናጸፉት ድዋይት አይዘንሀወር (1890 – 1969) ስለ ታሪክ ምንነት እምቅ ሃሳብ የታጨቀባቸውን አባባሎች ትተው ያለፉት እንዲህ በማለት ነበር፡- “እኛ ታሪክ ሰሪዎች ሳንሆን በታሪክ የተሰራን ሕዝቦች ነን፡፡”፣ “የታሪክ ሁነቶች ሁሉ እኛ የዛሬዎቹ በምናይበት ምልከታ የሚፈረጁ ሳይሆኑ በትናንት ውጤታቸው የሚመዘኑ ሊሆኑ ይገባል፡፡”
የእነዚህን ዓለም አቀፍ ተጽእኖ ፈጣሪዎች ድንቅ አባባሎች በቀላል አገላለጽ ለመጭመቅ ብንሞክር የምንደርስበት ውጤት “ታሪክ እንደ ዘር እህል የሚታሰብና የሚከበር እንጂ የአንድ ሰሞን የወረት ስንቅ ያለመሆኑን ነው፡፡” እርግጥ ነው ታሪክ ልክ ከላይ እንዳስታወስነው እንደ ዘር እህል ሁሉ አልፎ አልፎ በእንክርዳድ ቅንጣቶች የሚመሰሉ ድርጊቶች ከውስጡ እየተመዘዙ መዘባበቻም ሆነ መዘበቻ ተደርጎ ሲቆጠርና ሲታሰብ እያስተዋልን ነው። ስህተት ነው። በዛሬ መነጽር እየተመረመረ አንክርዳዱ ብቻ ገዝፎ እየወጣ አሸናፊ ለመሆኑ ለውርርድ መቅረቡ ወይንም እንደ አስፈሪ የነገ ውርስ ያልኖሩበትን ታሪክ እየወንጀሉ መደንበር ያልሰከነ ማንነት መገለጫ ከመሆን ውጭ ምንም ፋይዳ አይኖረውም፡፡
በየትኛውም ሀገር ታሪክ ውስጥ “እንክርዳዱና ስንዴው” አብሮ መጎዳኘታቸው የተለመደ ሂደት ነው። “ከታሪክ መሰዊያ ላይ አመዱን ሳይሆን እሳቱን ጫሩ” የሚለውን አባባል በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ ላይ ደጋግመን ማስታወሳችንም ይኼው እውነታ ግድ ስለሚለን ነው። “ታሪክ ለጨዋ ሰው ክብሩ፤ አእምሮ ለጎደለው ነውሩ” እንዲል ሀገራዊ ብሂላችን፤ የታሪክ መደላድላችንን ንቅን ዛሬያችንን በራሳችን መሠረት ላይ ብቻ ለመጣል ብንሞክርና ብንኩራራ ትርፉ “በድቡሽት (አሸዋ)” ላይ ቤትን ከመገንባት እኩል መታየቱ አይቀሬ ይሆናል፡፡
ከአባቶቻችንና ከእናቶቻችን እየተላለፈልን የመጣውን ቋንቋ፣ ባህልና ወግ እሶሶ እያልንና እየዘመርን አክብረን በመቀበል፤ የታሪክ ጉዳይ ሲነሳ ግን ስለምን “የመፋለሚያ ሻምላችንን” ከሰቀልንበት ለማውረድ እንደምንጣደፍ ግራ ያጋባል፡፡ በማንኛውም ሀገር ታሪክ ውስጥ “እልል” ተብሎ የሚከበር ታሪክ እንደሌለ የዘርፉ ምሁራን አስረግጠው ይነግሩናል፡፡ መሠረታቸው ሲጣል ከእንክርዳድ ጋር “ተቦክተዋል” የሚባሉ የአንዳንድ ሀገራት ታሪኮች ዛሬ የሚታወሱት ቁስሉ በደረቀ ጠባሳ እንጂ፤ በሚያመረቅዝ ደዌ እየተፈረጁ አይደለም፡፡
አንድ ወዳጄ ሲመሰክር እንደሰማሁት- “የዛሬው የጀርመን ትውልድ በጎዎቹንና የሚኮሩባቸውን የታሪክ ውርሶቻቸውን ብቻ ሳይሆን በዘመነ ናዚ የተፈጸሙ አሰቃቂ ድርጊቶችንም ሳይቀር እንዲያውቃቸው የሚደረገው ለመበቃቀልና እንዲፋጁበት ታስቦ ሳይሆን የታሪካቸው እንክርዳድ መሆናቸውን እንዲማሩበት ለማሳሰብ ነው። ስለዚህም በጀርመን ውስጥ ባሉ ሁሉም የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ይህ ኮምጣጣ ታሪክ አዘውትሮ እንዲቀርብ የሚደረገው በዛሬና በነገ ታሪካቸው ውስጥ መሰል ስህተቶችና ድርጊቶች እንዳይፈጸሙ ለማስተማር እንጂ ትውልዱ ‹በእባብ ጉድጓድ ውስጥ› እጁን የመክተት ያህል እንዲዳፈር አይደለም፡፡”
የሀገራችንንም የታሪክ አረዳድ በዚሁ እውነታነት ብንፈትሸው ሳይበጀን አይቀርም። መቶና ሁለት መቶ ዓመታት፣ አርባና ሃምሳ ዓመታት ወደ ኋላ እየተንደረደርን “የታሪካችንን አረሞች” እየቃረምን “የታሪክ ፈጻሚዎቹ አጽም ከመቃብር ተቆፍሮ ወጥቶ የሞት ፍርድ እንዲፈረድባቸው” መወትወቱና “ያረጁ ዶሴዎችን” አቧራ እያራገፉ “አቃቤ ዛሬ” ለመሆኑ መጣደፍና መሽቀዳደም ትርጉም አይኖረውም። የሚሻለው “ያለፈው የታሪክ ስህተት እንዴት ይታረም? መሰል ጥፋቶች እንዳይፈጸሙስ ምን ይደረግ? ማን የትኛውን ድርሻ ይወጣ? ወዘተ.” በሚሉት መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ መሥራት እንጂ ከትናንቱ የከፋ ታሪክ ለመፈጸም መጀገን ከላይ እንደተገለጸው መሸነፍ ነው፤ እናም “ነፋስን እንደመጎሰም” የሚያስቆጥርም ነው፡፡
“በአንዱ ስትጠቁም ከጣቶችህ መሃል፣
ሦስቱ ግን ራስህን ይመለከቱሃል፡፡”
እንዳለው ዜመኛው፤ ያለፈን ታሪክ ወደ ኋላ ተንጠራርተን እየተቸንም ሆነ እየረገምነው ዳግም ተመልሰህ ና! ወይንም ስህተትህን አርም ብለን ፍልሚያ ብንገጥም ጆሮው የተደፈነው ትናንት ምንም ምላሽ አይሰጠንም፤ ጆሮ ያላበቀለው ነገም መስሚያ የለውም።
ጆሮውን ያቆበቆበው ዛሬ ካለፈው ታሪክ ጋር ግብግብ ፈጥረን በእልህ እንጋልብብህ ብለን “ኮርቻችንን ብናመቻች” ይታዘበን ካልሆነ በስተቀር አበጃችሁ ሊለን አይችልም። የሚያዋጣው ሰከን ብለን በማስተዋል ስህተት ያልነውን የታሪክ እንክርዳድ እየነቀስን ማስወገድ እንጂ “በስንዴ ከሚመሰለው ትሩፋቱ ጋር አብረን ለመንቀል መዳፈሩ በጀግንነት አያሸልምም፡፡“ድምጻዊው እንዳለው ባሸለበው ትናንት ላይ “ጣታችንን እየቀሰርን” መፎከሩና ማስፎከሩ ምን እርባና ይኖረዋል? ከትናንት ከወረስነው የታሪክ ህፀፅ በከፋ ደረጃ እኛ የዛሬዎቹ ሦስት እጥፍ ስህተት እየሠራን ነጋችንን እያቆሸሽን እንደሆንስ? እንምከርበት፤ እንመካከርበት፡፡ ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ፡፡
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን እሁድ ሚያዝያ 1 ቀን 2015 ዓ.ም