የሽግግር ፍትህ ሂደቱ ሊመራባቸው
የሚገቡ መርሆዎች
በሀገራችን የሚታሰበው የሽግግር ፍትሕ ሂደት የሚከተሉትን መርሆዎች ባማከለ መልኩ የሚቀየስ እና የሚተገበር መሆን ይኖርበታል::
1-1 ሀገራዊ ባለቤትነትን ማረጋገጥ፡
የሽግግር ፍትሕ ሂደት በመሠረቱ አንዲት ሀገር በራሷ ለራሷ ተግባራዊ የምታደርገው ፍፃሜ ነው። ሂደቱ ሊመራ የሚገባው በራስ ተቋማት እና ዜጎች ነው። ይህም የሀገር ሉዓላዊነት መርሕን በመጠበቅ የብሔራዊ ኩራት መገለጫ ጭምር ሆኖ እንዲታይ ያደርገዋል፡ ቀጣይት ላለው የሕግ የበላይነት እና ዘላቂ ተቋማዊ ግንባታም መሠረት የሚጥል ይሆናል::
ዐውድ-ተኮር ፤
የሽግግር ፍትሕ አቀራረጽ እና አተገባበር ከማኅበረሰብ የፍትሕና እርቅ እሳቤዎችና ፍላጎቶች የፈለቀ፣ ዐውዳዊ ልዩ ሁኔታዎችን ያገናዘበ መሆን ይኖርበታል። በተጨማሪም በተጋለጠ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ሴቶችና ሕጻናት እንዲሁም ሌሎች አካላት ያሉበትን ሁኔታ ጨምሮ የግጭቱን ባሕሪና ያስከተለውን የመብቶች ጥሰት ይዘት ያገናዘበ መሆን ይኖርበታል::
የሕዝብ ተሳትፎን ማረጋገጥ ፤
የሽግግር ፍትሕን ለመተግበር የሚደረግ የትኛውም ዓይነት ተቋማዊ አደረጃጀት የሕዝብ ተሳትፎ እና ሕጋዊነትን፣ የሂደቱን ነፃነት፣ ገለልተኝነት፣ ብቃት፣ አካታችነት፣ ውጤታማ እና ቀልጣፋ ክዋኔ፡ በቂ የሃብት ክፍፍልን፡ እና የሥልጣን ግልፅነትን እና በቂነትን መሠረት ያደረገ መሆን አለበት።
አካታችነት ፤
የሽግግር ፍትሕ ሂደት በሁሉም ምዕራፎች ሁሉንም አካላት በእኩልነትና በፍትሐዊነት ሊያሳትፍ ይገባል። እንዲሁም እንደ ሴቶችና ልጃገረዶች፣ አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞች እና ወጣቶች ያሉ የተገፉ፡ የተገለሉና ተጋላጭ የሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ልዩ ሁኔታና ፍላጎት መሠረት ያደረገ መሆን ይኖርበታል፡፡
የተቀናጀ አተገባበር፤
በተጨማሪም ሂደቱ የተለያዩ የሽግግር ፍትሕ ስልቶች እና መንገዶችን በማቀናጀት በተናበበ መልኩ ለመተግበር እና ውጤት ለማስገኘት የሚያስችል ሊሆን ይገባል:: አንዱን የሽግግር ፍትሕ ዘዴ ብቻ ተግባር ላይ ማዋል ወይም የተለያዩ መንገዶችን ሳያቀናጁ በሥራ ላይ ማዋል የተሳካ ውጤት እንዳይገኝ ያደርጋል።
በተጨማሪም ቁጭቶችን እና ጥያቄዎችን በመፍጠር ከሚያስገኘው ጥቅም ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል። ስለሆነም የተሳካ የሽግግር ፍትሕ ሂደት በሀገራችን እንዲኖር ካስፈለገ አንዱ የሽግግር ጊዜ ፍትሕ መንገድ ሌላውን የሚተካ ሳይሆን፡ ሁሉም የሚደጋገፉ እና የሚመጋገቡ መሣሪያዎች እንደሆኑ በመገንዘብ፣በመደጋገፍ እና በትብብር እንዲተገበሩ ማድረግ ያስፈልጋል።
የሽግግር ፍትሕ ዓላማዎችን ቅደም ተከተል እና ሚዛን መጠበቅ፡
የሽግግር ፍትሕ አማራጭ ሥልቶችን በማጣመር ለመተግበር የሚደረግ ውሳኔ በአንድ ወገን የሰላምና እርቅ፣ በሌላ ወገን የኃላፊነትና ተጠያቂነት ግቦችን እርስ በእርስ ለማጠናከር እና ተመጋጋቢነታቸውን ለማስጠበቅ፡ እንዲሁም አካታች እድገትን ለማምጣት ያለመ መሆን ይኖርበታል፡፡
ገለልተኛነት፤
አሠራሩ በሽግግር ፍትሕ ሂደትና አተገባበር ላይ ተሳታፊ በሆኑ አካላት መካከል መተማመንን መገንባት የሚያስችል፡ ወገንተኛ ያልሆነ በዓላማና በመርሕ ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል፡፡
የማስተባበር አደረጃጀት አማራጮች ፤
በኢትዮጵያ ለሚተገበረው የሽግግር ፍትሕ ሂደት ከላይ ከተቀመጡት የትኛውንም አማራጭ ብንከተል ተግባራቶቹ ከአንድ በላይ በሆኑ ተቋማት መከናወናቸው አይቀርም:: አዲስ ኮሚሽን በማቋቋም የሽግግር ሂደቱን ማከናወን የሚለው አማራጭ በክፍል ሁለት በተደጋጋሚ ቀርቧል:: ኮሚሽኑ አንዳንዶቹን ስልቶች በባለቤትነት የሚመራ፣ ሌሎች ተቋማትንም የሚያስተባብር እና የሚያቀናጅ ይሆናል። ስያሜው የሐቅ እና የእርቅ ኮሚሽን፣ ወይም የእርቅ እና የሰላም ኮሚሽን ወይም የእውነት እና እርቅ አፈላላጊ ኮሚሽን ወይም የሀቅ፣ የፍትሕ እና የእርቅ ኮሚሽን ሊባል ይችላል።
ይህም ተቋቁሞ ከነበረው የእርቀ ሰላም ኮሚሽን ትምህርት በመውሰድ እና ዓለማቀፍ ልምዶችን ግምት ውስጥ በማስገባት – በሕግ የሚሰጡትን ሥልጣን እና ኃላፊነቶች መወጣት የሚችል ተቋም ማደራጀትን ይጠይቃል::
ይሁንና ይህ አዲስ ኮሚሽን የማቋቋም አማራጭ ተቀባይነት ቢያገኝ እንኳ ቢያንስ ክስ ከመመሥረት እና ከማካካሻ ሥርዓት አንፃር የመሪነት ሚና የሚጫወቱ ሌሎች ተቋማት ኃላፊነት ይኖርባቸዋል::
በመሆኑም እነዚህን ተግባራት የማቀናጀት እና የማስተባበር ተግባር የሚቀር አይደለም:: ስለሆነም ስኬታማ እና የተሟላ ሂደት እንዲኖር ለማድረግ በሂደቱ ኃላፊነት ያለባቸውን ተቋማት ለማስተባበር የሚያስፈልገውን አደረጃጀት መተለም ያስፈልጋል:: ስለሆነም ፖሊሲውን በባለቤትነት የሚያስፈፅም እና በአተገባበሩ ላይ ክትትል የሚያደርግ ብሔራዊ የሽግግር ፍትሕ አስተባባሪ ቦርድ (ምክር ቤት) ማቋቋም አስፈላጊ ይሆናል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ በተጠቀሰው የማስተባበር አደረጃጀት ላይ አዲስ አቅም በማቆም ከላይ ከተቀመጡት ሁለት ተቋማዊ አማራጮች ጠንካራ ጎኖች እና ስጋቶችን በማቀናጀት የተለየ አደረጃጀት የሚፈጠርበት እድል ሊኖር ይችላል:: ይህ አማራጭ የሚከተለው መልክ ይኖረዋል፡፡
ብሔራዊ የሽግግር ፍትሕ አስተባባሪ ቦርድ (ምክር ቤት) ማቋቋም፤ ተቋሙ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲውን በባለቤትነት የማስፈፀም እና በፖሊሲው መሠረት ተቋማት ተግባሮቻቸውን ማከናወናቸውን የማረጋገጥ ኃላፊነት ይኖርበታል:: እንደ አግባብነቱ ተመሳሳይ አደረጃጀቶች በክልል ደረጃም ሊቋቋሙ ይችላሉ:: አባላቱም በፖሊሲው ላይ የተጠቀሱ ተግባራትን ለመፈፀም፣ ለመቆጣጠር ወይም ለመደገፍ ኃላፊነት ካለባቸው ተቋማት የተወከሉ እንዲሁም በነፃና አሳታፊ ሂደት ከባሕላዊ አደረጃጀቶች እና ከኅብረተሰቡ የሚመረጡ ሰዎች ይሆናሉ፡፡
ዝርዝር ጉዳዩ በሕግ የሚወሰን ቢሆንም የሚፈጠሩ አዲስ ተቋማትን ጨምሮ በውክልና የሚመደቡት የቦርዱ አባላት ከሚከተሉት ተቋማት የሚወከሉ ሊሆኑ ይችላሉ :: ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ከፌዴራል ፍርድ ቤቶች፣ ከፍትሕ ሚኒስቴር፣ ከፌዴራል ፖሊስ፣ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን፣ ከብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ከባሕላዊ ሥርዓቶች፣ ከታዋቂ ሰዎች፣ እና ከሀገር ሽማግሌዎች፡፡
ከኅብረተሰቡ የሚመረጡ አባላትን በሚመለከት – አዲስ ኮሚሽን ቢቋቋም አባላትን በመመልመል ሂደት ሊኖር የሚችለው ነፃ እና ገለልተኛ አካሄድን በመከተል የሚሰየሙ መሆን ይኖርባቸዋል:: የኮሚሽኑ ሰብሳቢ እና የሚቋቋመው ሴክሬታሪያት ኃላፊነት በነዚህ አባላት የሚያዝ ይሆናል። የቦርዱ አባላት በሙሉ ተዓማኒነት እና መልካም ስብዕና ያላቸው፡ በኅብረተሰቡ ዘንድም የሽግግር ፍትሑ ባለቤቶች ተደርገው ሊሳሉ የሚችሉ መሆን ይኖርባቸዋል::
ብሔራዊ የሽግግር ፍትሕ አስተባባሪ ቦርድ ሴክሬታርያት፤ አስተባባሪ ቦርዱ በሽግግር ፍትሕ ሂደቱ በተቋማቱ በቀጥታ የማይከናወኑ ተግባራትን የሚያከናውንበት እንዲሁም የማስተባበር ኃላፊነቱን የሚወጣበት በባለሙያዎች የተሟላ ሴክሬታሪያት ይኖረዋል:: አዲስ ኮሚሽን ከተቋቋመ ሴክሬታርያቱ በኮሚሽኑ ስር የሚደራጅ ይሆናል::
ይህ ካልሆነ ግን በሌሎች ሀገሮች ልምድ ለኮሚሽኖች የሚሰጡ እንደ እውነትን ማጣራት፣ ምሕረት፣ የእርቅ ሂደቶች እና የማካካሻ ሂደት ጉዳዮች ላይ ሴክሬታርያቱ መመሪያዎችን ያዘጋጃል፣ እንደ አግባብነቱ ይፈፅማል፣ተግባራቱ በሌሎች ተቋማትም ትኩረት ተሰጥቷቸው እንዲፈፀሙ የማድረጊያ አቅም ይሆናል።
ምንጭ /ኢትዮጵያ የሽግግር ፍትህ የፖሊሲ አቅጣጫ አማራጮች በሚል ጥር 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከባለድርሻ አካላት ግብዓት ለመሰብሰብ በተዘጋጀ መድረክ ለውይይት ከቀረበ ጥናታዊ ጽሑፍ የተወሰደ
አዲስ ዘመን እሁድ ሚያዝያ 1 ቀን 2015 ዓ.ም