የኢፌዴሪ መንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ትናንት በተለያዩ እና ወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰላማዊት ካሳ የሰጡ ሲሆን፤ ትኩረቱም ጠንካራ እና ወጥ የሆነ አንድ አገራዊ የመከላከያ እና ደህንነት ኃይል በመገንባት ሂደትን ጨምሮ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ያደረገ ነበር። የመግለጫው ሙሉ ይዘትም እንደሚከተለው ቀርቧል።
የመከላከያ እና የጸጥታው ዘርፍ ሪፎርም ሥራዎች
የሪፎርም ስራዎቻችን የመከላከያ ሠራዊታችንን በመሳሪያ፣ በቴክኖሎጂ፣ በሰው ኃይል እንደዚሁም በተለያዩ አስፈላጊ በሆኑ መንገዶች ሁሉ ማጠናከር ላይ ያተኮሩ ነበሩ። በአጭር ጊዜ ውስጥ በመከላከያ ሠራዊት ላይ የተሰሩት የሪፎርም ስራዎች ደግሞ ምን ያህል ውጤት እንዳስገኙ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተመለከትነው ነው። በተጨባጭም እንደ ሀገር ተደቅኖብን የነበረውን የህልውና አደጋ በዘላቂነት ለመቀልበስ ያስቻለ መሆኑንም ሁሉም የሚገነዘብ ሃቅ ነው።
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት የመጨረሻ ብሄራዊ ኃይላችን ነው። እንደሀገርም የህልውና የመጨረሻ ምሽጋችንም ይህ ብሄራዊ መከላከያ ኃይላችን ነው። እንደ ኢትዮጵያ በብዙ ሀገራዊና ቀጣናዊ ትኩሳቶች ለተከበበ ሀገር ያለጠንካራ መከላከያ ሠራዊት ጠንካራ ሀገርን መገንባት አይቻልም። ይህም እግዲህ ሠራዊቱን የተሟላ ስብዕና በማላበስ ፤ ሙሉ ኢትጵያዊነቱን በማላበስ፤ በሰው ሃይል በመሳርያ፤ በቴክኖሎጂ በሞራልም ጭምር ማጠናከር ዋነኛ ሀገራዊ አጀንዳችን ሆኖ መቆየቱ የሚታወቅ ነው።
ይህንን የሪፎርም ስራ መነሻ በማድረግ መንግሥት የሀገሪቱን ሉዓላዊነት እንዲሁም የግዛት አንድነት መጠበቅ የሚያስችል ጠንካራ መከላከያ ሠራዊት ለመገንባት የሚያስችል ብዙ ጥረቶች ነበሩ። ይህንንም በሰፊ ጥናቶች አስደግፎ ነው ሲከናወን የነበረው። ይህንን ጥናት ተከትሎም መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት የክልል ልዩ ኃይሎች በተለያዩ መዋቅሮች እንዲደራጁ የሚያስችላቸው ተግባራዊ እርምጃ መጀመሩመ ይታወቃል።
ይህ ስራ እንግዲህ ምንም እንኳን በጥናትና በቅድመ ዝግጅት ደረጃ ቆየት ብሎ የተጀመረ እንደሆነ ይታወቃል። እንግዲህ በሀገራችን የህልውና አደጋ ተደቅኖ እደነበር ይታወቃል። ይህንን መቀልበስ አስፈላጊ ነበር። እንዲሁም በሌሎች አካባቢዎች ላይ የነበሩ ሰላም መደፍረሶች ዘላቂ መፍትሄ እስኪያመጡ ድረስ በጥናቱ ላይ የተመለከቱት የመፍትሄ አቅጣጫዎች ተግባራዊ እንዳይሆኑ አድርጎ ቆይቷል።
የመንግሥት ዋነና ኃላፊነት ዜጎችን ደህንነት ማስጠበቅ እና የሀገር ህልውና ማስከበር እንደመሆኑ፤ ሀገራዊ ሰላምን በተሟላ ሁኔታ ማስጠበቅ የተጣለበት መንግሥት፤ ይህንን ኃላፊነቱን እንዲወጣ በተለያዩ ደረጃ ያሉ የማህበረሰብ ክፍል በተለያየ መልኩ ጥያቄ ሲያቀርብ እና መልዕክት ለመንግሥት ሲያስተላልፍ ቆይቷል። ይህንን ለማሳካት ደግሞ በሥነምግባሩ፤ በሰው ኃይሉ፤ ጠንካራ የሆነ እንዲሁም በመሳርያ የተደራጀ አንድ ጠንካራ የተማከለ ሠራዊትን መገንባት አስፈላጊ እንደሆነም በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲነሳ ቆይቷል።
አሁን ወደ ተግባር የገባው የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀት ስራም በሁሉም ክልሎች ውስጥ በተመሳሳይ ወቅት የተጀመረ ነው። በሁሉም ክልሎች በየደረጃው ባሉ በሚመለከታቸው አካላት በጉዳዩ አስፈላጊነት ላይ ከመግባባት ላይ በመደረሱ እንዲሁም አሁን ሀገሪቱ ውስጥ ያለው የተሻለ የሰላም ሁኔታ ከዚህ ቀደሙ በጣም የተሻሻለ በመሆኑ እና ይህንን ትልቅ ተልኮ ለማስፈጸም የሚያስችል መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ በሁሉም ክልሎች በየደረጃው ካሉ የሚመለከታቸው አካላት ጋር ጭምር ውይይቶችን በማድረግ ጭምር ነው ስራዎች የተጀመሩት።
በተለያዩ ወቅቶች ከብዙ አቅጣጫ ሲሰነዘሩ የነበሩ ሀገርን አደጋ ላይ የጣሉ ክስተቶችን ለመመለስ፤ እንደዚሁም የሀገርን ክብር ለማስጠበቅ በሁሉም ክልል የሚገኙ ልዩ ኃይሎች በጣም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸው የሚታወቅ ነው። ለዚህ ደግሞ መንግሥት ከፍ ያለ ዕውቅና ሲሰጥ ቆይቷል። ከፍተኛ መስዋዕትነትን በመክፈል ለሀገራቸው ብዙ አስተዋጽኦ ያበረከቱ የልዩ ኃይል አካላት አሉ። አሁን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ ልዩ ኃይሎች በመልሶ ማደራጀቱ ስራው ምርጫው ሙሉ በሙሉ ተጠበቆለት ፤ ፍላጎቱም እንዲሁ ተከብሮለት መንግሥት አማራጮችንም አስቀምጦለት ነው ይሄ የመልሶ ማደራጀቱ ስራ የሚከናወነው።
አንዱ፣ በየትኛውም ክልል የሚገኝ ልዩ ኃይል የኢትዮጵያ የህልውና ምሶሶ ወደ ሆነው፤ እንዲሁም ከራሱ አልፎ በአፍሪካ ብሎም በዓለም ጭምር ዕውቅና የተሰጠውን ጀግናው የመከላከያ ሠራዊታችንን መቀላቀል አንደኛው ነው። ይህ ደግሞ እንግዲህ ትልቅ ሀገራዊ ጥሪ መሆኑ ነው። በዚሁ አጋጣሚ አፅዕኖት መስጠት ያስፈልጋል። ሁለተኛው አማራጭ ደግሞ በዚያው ባለበት ክልል ያለውን የሰላምና የፀጥታ ሁኔታ ማስከበር ፤ የክልሉን ነዋሪዎች ጭምር ማገልገል የሚችልበትን እድል የሚሰጠውን የክልሉን የፖሊስ ሃይል መቀላቀል ደግሞ ሌላው ሁለተኛው የቀረበው አማራጭ ነው።
በሁሉም ክልሎች ውስጥ ጠንካራ የፀጥታና የወንጀል መከላከል ስራን ለመጀመር የፖሊስ ሃይሎች፤ የፀጥታ መዋቅሩ በከፍተኛ ደረጃ መደራጀትም፤ መጠናከርም ስላለበት እንደዚሁም ብቁ ባለሙያዎችም ስለሚያስፈልጉት ይህንን ሃይል ማጠናከር ደግሞ ትልቅ አስተዋፅኦ የሚኖረው ርምጃ እንደሆነ ሊሰመርበት ይገባል።
ከእነዚህ አማራጮች ውጪ ደግሞ ወደመደበኛ ኑሮ መመለስ የሚፈልግም አካል ካለ ይህም ሙሉ መብቱ ተጠብቆለት የሚከናወን ይሆናል ማለት ነው፤ ሶስተኛው አማራጭ ይህ ነው። ወደ ሲቪል ሕይወት መመለስ የሚፈልግ ኃይልም ካለ የመቋቋሚያ አስፈላጊ ድጋፎችን ለማድረግ በመንግሥት በኩል ዝግጅት ተደርጓል። ይህንንም ለማስፈፀም ከሁሉም ክልሎች ጋር አስፈላጊ የሆነ ምክክሮች ሲደረጉ ቆይተዋል፤ አሁንም እነዚህ ምክክሮች እየተደረጉ ነው የሚገኙት።
እነዚህ ሶስት አማራጮች በግልፅ ቀርበዋል። ይህንንም በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ ክልሎች ውስጥ በፖለቲካ አመራሩ ዘንድ፣ የመከላከያ እና የፖሊስ አመራሮች እንደዚሁም ደግሞ የልዩ ሃይል አመራሮች እና አባላት መካከል ቀጣይነት ያላቸው ንግግሮች እየተደረጉ ነው የሚገኙት።
ምክንያቱም ይሄ ስራ እንደስፋቱ መጠን፣ እንደዚሁም ደግሞ በሚያካትታቸው አካላት በመግባባትና በመነጋገር ላይ ብቻ ተመስርቶ የሚከናወን መሆኑን በዚህ አጋጣሚ መንግሥት ለማስገንዘብ ይወዳል። ሆኖም በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ በመረጃ እጦት እና የመርሃ ግብሩን ዋነኛ ዓላማ በተገቢው መልኩ ካለመገንዘብ የተነሳ አንዳንድ ያጋጠሙ ችግሮች እንደነበሩ ተመልክቷል።
እነዚህ ችግሮች ሊፈቱ የሚችሉት ስለ ስራው ዓላማ እና በውስጡ ስለያዛቸው ቁም ነገሮች ትክክለኛ የሆነ መረጃ በመስጠትና መግባባት ላይ በመድረስ ጭምር እንደሆነ መንግሥት ያምናል። ለዚህም ነው በመላ ሀገሪቱ በሁሉም ክልሎች መርሃ ግብሩን አስመልክቶ በተለያዩ አካላት በኩል ውይይቶች እየተካሄዱ የሚገኙት። ምክንያቱም በመግባባት እና በመነጋገር የሚካሄድ ተግባር በመሆኑ ነው።
አንደኛ፣ የክልል ልዩ ሃይልን መልሶ የማደራጀቱ መርሃ ግብር በሁሉም ክልሎች እየተተገበረ የሚገኝ መሆኑን ሁሉም ሰው ሊገነዘበው የሚገባ ሀቅ ነው። በአንዳንድ አካላት እየተነዙ ያሉ መረጃዎች አሉ። እነዚህን መከላከል የሚቻለው ስለጉዳዩ ትክክለኛውን መረጃ በመስጠት ነው። የመርሃ ግብሩ ዓላማ ምን እንደሆነ በማስገንዘብ፤ ከዚህ ባሻገር ደግሞ ከዚህ በፊት ምን ያህል በህብረተሰቡ ጥያቄ እየተነሳበት የነበረ ጉዳይ እንደነበር በማስታወስም፣ ከዚያ በሻገር ደግሞ እንደ ሀገር የኢኮኖሚ ሁኔታችንን እንዲሁም ነባራዊ ሁኔታውንም ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ እንደ ሀገር የምንፈልጋትን ትልቅ ኢትዮጵያ ለመመስረት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ምን ያህል አስተዋጽኦ ሊያበረክት እንደሚችል ተገቢውን መረጃ በመስጠት ጭምር ነው።
እነዚህን በአንዳንዶች የሚሰነዘሩትን የተሳሳቱ መረጃዎች መከላከል የሚቻለው ትክክለኛውን መረጃ ለተገቢው አካል በማድረስ ይሆናል። የክልል ልዩ ሃይልን መልሶ የማደራጀት ሂደት በሁሉም ክልሎች በተመሳሳይ እየተከናወነ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ማንሳት ያስፈልጋል። ሂደቱን አስመልክቶ ከዚህ ቀደም ጥልቅ ጥናቶች ተካሂደዋል። የሀገራችንም የክልሎች ነባራዊ ሁኔታም ከግምት ውስጥ ገብቶ ጭምር ነው ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው።
ሁለተኛው ጉዳይ፣ ይህ መርሃ ግብር ትጥቅን ከማስፈታት ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለው መሆኑ ነው። ይህንን ሂደት ትጥቅ ከማስፈታት ጋር ለማገናኘት እና ለማያያዝ እና በህብረተሰቡ ዘንድ የተለያዩ ውዥንብሮችን ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት ፍጹም የተሳሳተ እንደሆነ ሁሉም ህብረተሰብ ሊገነዘበው ይገባል። ጉዳዩ ትጥቅ ከማስፈታት ጋር ግንኙነት የለውም። እንዲያውም የሁሉም ኢትዮጵያዊ የሆነ፣ ሁሉንም በእኩልነት ማገልገል የሚችል፣ የሀገርን ሉዓላዊነት በተሟላ ሁኔታ ከሀገር ውስጥም ከሀገር ውጭ ሊሰነዘሩና ሉዓላዊነትን ሊዳፈሩ ከሚችሉ ጥቃቶች መከላከል የሚችል ጠንካራ የመከላከያ ሃይልን ለመገንባት የሚያስችል ትልቅ ሀገራዊ ጥሪና እድል ስለመሆኑ በዚሁ አጋጣሚ ተገቢ የሆነ ግንዛቤ መስጠት ያስፈልጋል። መገናኛ ብዙሃንም በዚሁ ላይ ሊሰሩበት እንደሚገባም ማንሳት እፈልጋለሁ።
ሕወሓትን በተመለከተ
በተለያየ መልኩ ከሕወሓት ጋር ተያይዞ የሚነሱ ጥያቄዎች አሉ። በሕወሓት በኩል በፕሪቶሪያው ስምምነትና ከዚያም በኋላ በተለያዩ በተካሄዱ ምክክሮች መሰረት ሕወሓት ሙሉ ለሙሉ ትጥቅ እንዲፈታ እየተደረገ እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል። ይህም ራሱን ችሎ የሚከናወን ተግባር ነው። በራሱ የተቀመጠለት የሂደት አግባብ አለ። ጉዳዩ የሚከናወንበት መርሃ ግብርም እንደዚሁ በግልጽ ተመላክቷል። ከዚህ በፊትም ይከናወን እንደነበረው ይህንኑ ጉዳይ የሚከታተሉና የሚታዘቡ ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች ጭምር ያሉበት መሆኑንም እዚህ ላይ ማስገንዘብ ያስፈልጋል።
የሕወሓት ትጥቅ የመፍታት ሂደት በተፈረመው ስምምነት መሰረት ያለማወላወል የሚፈጸም መሆኑን ማስገንዘብ ይገባል። ከሌሎች አገራዊ ዕቅዶች ጋር የሚገናኝ ሳይሆን ራሱን ችሎ በራሱ መርሃ ግብር የሚከናወን እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፤ ከሌሎች አገራዊ እቅዶች ጋርም የሚጣረስ እንዳልሆነም ግልጽ ማድረግ ተገቢ ነው።
በአጠቃላይ የክልሎችን ልዩ ኃይሎች መልሶ የማደራጀት መርሃ ግብር በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚካሄድ መሆኑን ሁሉም ሰው ሊገነዘበው ይገባል። በሁሉም ክልሎች የሚፈጸምና በከፍተኛ ጥንቃቄና መግባባት ጭምር የሚካሄድ በመሆኑ፤ በሂደቱ ወቅት በሁሉም ክልሎች ላይ ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ በተለይም አንዳንድ ቦታዎች ላይ የጸጥታ ስጋት ያለባቸው እንደዚሁም ሌሎች የማህበረሰብ ጥያቄዎች ባሉባቸው አካባቢዎች ላይ ሰላምና ደህንነትን ማረጋገጥ እንዲቻል የሀገር መከላከያ ሠራዊት በሁሉም ቦታዎች ላይ ስምሪቶችን ወስዶ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ዋና ዋና ተልዕኮዎች ተሰጥተውት ይህንኑ ተግባራዊ ወደማድረግ ሂደት እየገባ ነው የሚገኘው። ስለዚህ በዚህ በኩል የሚፈጠር ምንም አይነት ክፍተት አይኖርም ማለት ነው።
ይህ የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀቱ ተግባር ጠንካራ ሉዓላዊነቷ የተከበረ፣ ከአገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ሊሰነዘሩባት የሚችሉ የተለያዩ ጥቃቶችን በአግባቡ መመከት የምትችል ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት ዋነኛ አካል መሆኑን ሁሉም ማህበረሰብ ሊያውቀው ይገባል። ከዚህ በተቃራኒው ትልቁን አገራዊ ስዕል ወደ ጎን በመተው፣ የተለያዩ ሀሰተኛ መረጃዎች እየወጡ ነው። እነዚህ ሀሰተኛ መረጃዎች መውጣታቸውን ይቀጥላሉ፤ ምክንያቱም በዚህ ሂደት የዜጎችን ሰላምና ደህንነት በመንሳት ሂደት ውስጥ የሚጠቀሙ ብዙ አካላት መኖራቸው መረሳት የለበትም።
ስለዚህ በእነዚህ አካላት የሚሰነዘሩ ሀሰተኛ መረጃዎችን፣ የጥፋት መልዕክቶችንና በአጠቃላይ ሕዝብን ለማደናገር፣ አቅም የሌሌለው እንዲሁም የተበታተነ ኃይል ያላት ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚደረጉ ጥረቶች መሆናቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት በመንግሥት ደረጃም ይሁን በሁሉም ክልሎች ውስጥ በተመሳሳይ እየተፈጸመ የሚገኘው ይህ ትልቅ አገራዊ ተልዕኮ እንዲፈጸምና ውጤታማ እንዲሆን ከማድረግ አንጻር ማህበረሰቡ እነዚህን የተሳሳቱ መረጃዎችን ባለመስማት ባለማመንም ጭምር ሃላፊነቱን መወጣት አለበት። በመንግሥት በኩልም ትክክለኛ መረጃዎች በየጊዜው ወደ ሕብረተሰቡ እንዲደርሱ የተለያዩ ጥረቶች መደረጋቸውን የሚቀጥሉ ይሆናል።
ከአገር ውስጥም ከውጭም ክፉዋን በሚያስቡ ኃይሎች፣ የተጋለጠች ኢትዮጵያን ማየት በሚፈልጉ ኃይሎች ደግሞ የተመቸች ኢትዮጵያን ላለመፍጠር የሚደረግ ትልቅ ጥረት አለና የሚነዙት የተሳሳቱ መረጃዎች እነዚህን ሃይሎች የሚያግዙ መሆናቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ሕዝቡም ሆነ የጸጥታ ኃይሉ ሊደናገር አይገባውም። እነዚህን ሂደቶች በተመለከተ በሁሉም ክልሎች ውስጥ የሚካሄደው መርሃ ግብር ሂደት ምን ይመስላል የሚለውን በተከታታይ ለህብረተሰቡ የምናደርስ ይሆናል።
አሸባሪው ሸኔ እና ተያያዥ ሥራዎች
ከሰላምና ጸጥታ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የሚነሳው ሌላ ጉዳይ የሸኔን ጉዳይ ነው፤ በዚህ የሽብር ቡድን ላይ ከዚህ በፊት የተጀመሩት የተለያየ ወታደራዊ እርምጃዎች አሁንም ቀጥለዋል። በተለይ የመከላከያ ሠራዊት ቦታዎቹ ላይ ከገባ በኋላ በጣም ከፍተኛ የሆነ ውጤት እየተገኘበት መሆኑ ይታወቃል። በጣም በርካታ የሆኑ የሽብር ቡድኑ ይዟቸው የነበሩ አካባቢዎች አሁን ላይ ነፃ እየወጡ ነው። ነፃ የወጡትም ወደ መደበኛ የሕዝብ መገልገያ አገልግሎቶች ዳግም እንዲመለሱ የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ ነው የሚገኙት።
በተለይም ነፃ የወጡት አካባቢዎች ላይ ትምህርት ቤቶች፣ የገጠር ሆስፒታሎች፣ ጤና ጣቢያዎች ሌሎችም መንግሥታዊ መዋቅር አገልግሎት የሚሰጥባቸው የተለያዩ አገልግሎት መስጫዎች ተመልሰው የማደራጀቱ ስራዎች ብዙ የኦሮሚያ አካባቢዎች ላይ እየተከናወነ ነው የሚገኘው። ከምዕራብ ወለጋና ከሆሮ ጉርዱ በስተቀር በሌሎች አካባቢዎች ላይ በተለይ ደግሞ በሸኔ ምክንያት ተቋርጠው የነበሩ የተለያዩ የትራንስፖርት አገልግሎቶችም ዳግም እንዲጀመሩ እየተደረገ ነው የሚገኘው።
ከዛ ባሻገር ደግሞ እንደሚታወቀው መንግሥት ለዚህ ቡድን በይፋ የሰላም ጥሪ ማቅረቡ የሚታወስ ነው። ይህን ተከትሎ እንግዲህ በርካታ የሸኔ አባላት ትጥቃቸውን እያወረዱ ወደ ተሃድሶ ማዕከላት እየገቡ ነው የሚገኙት። የሰላም ጥረቱን ለማስተባበርም በብሄራዊ ደረጃ የተቋቋመው ኮሚቴ በርካታ ስራዎችን እየሰራ ነው የሚገኘው። በማህበረሰቡ በኩልም የሚቀርቡ ጥያቄዎች አሉ። እነዚህ ጥያቄዎች ዋነኛው የሰላም ሂደቱ በሀገር ሽማግሌዎች፣ በአባ ገዳዎች እንዲከናወን ብዙ ጥያቄዎችና ግፊቶች አሉ። ይህንን ደግሞ መንግሥት ሙሉ ለሙሉ ያከብራል።
ከማህበረሰቡ በኩል የሚመጡት እነዚህ ጥያቄዎች በተለይ የሕዝቡን ፍላጎት ባከበረ መልኩ በሰላም ጥረት ውስጥ የሚሳተፉ የሀገር ሽማግሌዎችና አባ ገዳዎችን እውቅና በመስጠትም ጭምር መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እያረገ፤ አሁንም የሰላም አማራጮችን ሙሉ ለሙሉ ክፍት አድርጎ እየሰራ ይገኛል።
እንደሚታወቀው መንግሥት ከመነሻው ጀምሮ ማንኛውም ነፍጥ አንግቦ አላማዬን በጦርነት፣ በጥቃት፣ በሽብር አስፈፅማለው የሚል አካል ሙሉ ለሙሉ የያዘውን ነፍጥ በማውረድ ሰላምና ደህንነትን በሚያረጋግጥ መልኩ ወደ ሰላም እንዲመጣ ለማድረግ ከዚህ በፊት በርካታ ጥሪዎችን ሲያደርግ ቆይቷል። ይሄም ተጨባጭ ውጤት የተገኘባቸው የተለያዩ ክልሎች የሚንቀሳቀሱና ከዚህ በፊት በሽብር ስራ ላይ የነበሩ የተለያዩ ቡድኖች አሁን የሰላም አማራጩን ተከትለው ወደ መደበኛ ማህበራዊ ኑሯቸው እየተመለሱ መሆኑ ይታወቃል። ይሄ የሰላም ጥሪ አሁንም በመንግሥት በኩል የሚቀጥል ነው የሚሆነው። ለሰላም ቅድሚያ ሰጥቶ ይሄንን አማራጭ የሚከተል ማንኛውም አካል ካለ የመንግሥት በር ሁሌም ክፍት ነው።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ መንግሥት በመላ ሀገሪቱ የሚያከናውናቸው የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥቄዎች አሉ፤ በሕዝቡ በኩል የሚነሱ። እነዚህን ለመመለስ እንዲሁም በዋነኛነት የዜጎችን ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ እንዲቻል የቀበሌ መዋቅሮችን ማጠናከር፤ በተለይ ከሕዝቡ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸው የዕለት ተለት ትስስር ያላቸው እነዚህ መዋቅሮች በመሆናቸው በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ የቀበሌ መዋቅሮችን በማጠናከር አቅማቸውን መገንባት እጅግ ወሳኝ የሆነ ተግባር መሆኑን መንግሥት በፅኑ ያምናል።
በዚህ መሰረት ከዚህ በፊት የፀጥታ ችግር የነበረባቸው አካባቢዎች ላይ የነበሩ፤ እንዲሁም በተለያየ መልኩ የመከላከያ ሠራዊታችን እንዲሁም ደግሞ በተለያዩ አካላት የፀጥታ መዋቅራችን የተከናወኑ ኦፕሬሽኖች ተከትሎ ነፃ የወጡ አካባቢዎች ላይ ቀበሌዎችን ጨምሮ በዚህ ውስጥ የሚገኙ መዋቅሮችን የማጠናከርና የማስፈፀም አቅማቸውን የማደራጀት ስራ እንደዚሁም በተለያየ መልክ ያሉባቸውን ክፍተቶችንም በመሙላት አቅማቸውን የመገንባት ስራ በመላ ሀገሪቱ እየተተገበረ ነው የሚገኘው።
ለአብነት፣ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኙ ስድስት ሺ 398 ቀበሌዎች የተውጣጡ ከ635 ሺ በላይ የሚሆኑ የቀበሌ፣ ከቀበሌ መዋቅር በታችም ቀጥታ ከህብረተሰቡ ጋር በተለያየ መልኩ ግንኙነት ያላቸው አመራሮች የተሳተፉባቸው የተለያዩ ምክክሮች እንደዚህም ደግሞ ሥልጠናዎች እየተደረጉ ነው የሚገኙት በአሁኑ ሰዓት። ሥልጠናው እንግዲህ በታችኛው መዋቅር አመራሮች መካከል የሀገራዊ ክልላዊና አካባቢያዊ ጉዳዮችን በጥልቀት የሚመለከቱበት ነው።
ሀገራችን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ በተጨባጭ እንዲገነዘቡ ለማድረግ ትልቅ አስተዋፅኦ ያላቸው መድረኮች ናቸው። ከዛ ባሻገር ደግሞ እነዚህ አካላት በተመደቡበት ቦታ ውጤታማ በሆነ መልኩ የተሰጣቸውን ኃላፊነት መወጣት እንዲችሉ አቅም የሚሰጣቸው እንደሆነ ታምኖበታል። በእለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸውም ከህብረተሰቡ የሚነሱ የተለያዩ ጥቄዎች አሉ። እነዛንም ወደ መድረክ በማምጣትም ጭምር ለውይይት እድልንም የሚፈጥር ነው።
ይሄ በመላ ሀገሪቱ ሲካሄድ የነበረ ሥልጠና በተለይም ቀደም ሲል ባነሳሁላችሁ ቁጥር በኩል ለአብነት ባነሳነው በኦሮሚያ ሲካሄድ የነበረው ሥልጠና ዛሬ የሚጠናቀቅ ይሆናል። ሠልጣኞች በተለያየ ርዕሶች የያዙ ሥልጠናዎች ሲከታተሉ ነበር። ከፌዴራል ጀምሮ የክልል አመራሮች እንደዚሁም ደግሞ በየደረጃው ያሉ አመራሮች የተሳተፉባቸው ናቸው እነዚህ ምክክሮች፤ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የልማት ስራዎችን በመጎብኘት ጭምር ምን ያህል ኃላፊነት እንደተጣለባቸው ህብረተሰቡ ከነዚህ አመራሮች ምን እንደሚጠብቅም ጭምር በግልፅ የተመላከተበት ስራ ነው ሲሰራ የነበረው። እነህም ጉብኝቶች ተጠናቀው ዛሬ ወደ መደበኛ ስራቸው የሚመለሱ ይሆናል።
ኮንትሮባንድ እና ተጓዳኝ ወንጀሎች
ሌላው ጉዳይ፣ እንደ ሀገር ከተደቀኑብን ትልቅ ፈተናዎች መካከል አንደኛው የሕገወጥ ንግድና የኮንትሮባንድ፤ እንደዚሁም በተለያየ መልኩ የሚፈጸሙ የንግድ አሻጥሮች ናቸው። ይሄ ሀገራችን ያላትን ከፍተኛ ሀብት እንዲባክን አድርጓል። ከዛ ባሻገር ኢትዮጵያ ያላትን እምቅ አቅም እንዳለ ሆኖ፣ ማግኘት የሚገባትንም ጥቅም እንዳታገኝ ትልቅ እንቅፋት ሆኖ መቆየታቸው ይታወቃል። ይህ እንግዲህ ዘርፈ ብዙ ችግር ነው፤ ከሀገር ውስጥም አልፎ ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ ጭምር የተዘረጋ ሰንሰለት ያለበት በመሆኑ የሚወሰዱት እርምጃዎች በፌዴራል፣ በክልል እንዲሁም በሀገር አቀፍ ደረጃም የሚከናወኑ የተለያዩ ተልዕኮዎች ናቸው።
ከእነዚህ ጉዳዮች መካከል ከሰሞኑ በሕገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ገብተው የተለያዩ የወርቅ እና ሌሎችም ማዕድናት ፍለጋ ላይ የተሰማሩ የነበሩ የውጭ ሀገር ዜጎችና ተባባሪዎቻቸው በተለያዩ ክልሎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ እየተደረገ ነው። እነዚህ አካላት ከውጭ ሀገር ወደ ኢትዮጵያ ሲገቡ የጸና የጉዞ ሰነድ የላቸውም፤ የመግቢያ ቪዛ፣ እንደዚሁም ደግሞ የመኖሪያ ፈቃድ፣ የመስሪያ ፈቃድም ሳይኖራቸው ነው በተለያዩ ቦታዎች ላይ እየተንቀሳቀሱ በሕገወጥ መልኩ የመዓድን ማውጣትና ማምረት ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩት። ከእነዚህ መካከል በሕገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ገብተው በጋምቤላ ክልል በሕገወጥ የወርቅ እና የተለያዩ ማዕድናት ፍለጋ ላይ የተሰማሩ 45 የውጭ ሀገር ዜጎች እና 3 ኢትዮጵያውያን ከእነ ኤግዚቢታቸው በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርገዋል። ምርመራም እየተጣራባቸውም ነው።
ከዚያ ባሻገር የጸጥታና የደህንነት የጋራ ግብረኃይሉ በወሰዳቸው የተለያዩ ርምጃዎች በተመሳሳይ ሁኔታ በሕገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ገብተው በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ውስጥ በሕገወጥ የወርቅና የተለያዩ ማዕድናት የፍለጋ እና ማምረት ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ 47 የውጭ ሀገር ዜጎች፤ እንዲሁም 9 ኃላፊነታቸው የተወሰነ የግል ማህበራት፣ ደግሞ 7 ኢትዮጵያውያን የዚህ ስራ ተባባሪ ሆነው በመገኘታቸው ከእነ ኤግዚቢቱ ጭምር በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል። እነዚህ አካላት ላይ ተገቢ የሆነ ምርመራ እየተጣራባቸው ነው የሚገኘው።
አሁን ሀገራችን ካላት የማዕድን ዘርፍ ተጠቃሚ እንዳትሆን በጣም አብዛኛው ሀብቷ በሕገወጥ መንገድ ወደውጭ ሀገራት እንዲወጣ እየተደረገ ነው። ተገቢ የሆነ ጥቅም ዜጎች ከሀገራቸው እንዳያገኙ ጭምር እየተደረገ በመሆኑ፤ ይህንን ለመቆጣጠር በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተወሰዱ ካሉ እርምጃዎች መካከል አንደኛው ይኸ ተግባር ነው። በኮንትሮባንድ ሀገር የሚያወጡና የንግድ ሰንሰለቱን ከሀገር አቀፍ እስከ ዓለም አቀፍ ደረጃ የተዘረጋ መሆኑንም እዚሁ ላይ መመልከት ያስፈልጋል።
ለዚህ ሕገወጥ ሥራ ምቹ ሁኔታን የፈጠረው ደግሞ ምንድነው ብሎ መጠየቅም ያስፈልጋል። በተለይ እነዚህ አካባቢዎች ላይ። ትልቁ ለዚህ ሥራ ምቹ የነበረው እነዚህ ሕገወጥ አካላት ወደ ሀገር ውስጥ ገብተው እነዚህ ቦታዎቹ ላይ የማዕድን መፈለግና ማውጣት ሥራ ላይ እንዲሰማሩ የሆነው የነበረው የሰላም መደፍረስ ነው ምቹ ሁኔታን መደፍረስ እንደፈጠረላቸው ማንሳት ያስፈልጋል።
አሁን በእነዚህ ክልሎች ላይ በተለይ ነፍጥ አንግበው የነበሩ፣ በተለያየ የሽብር ሥራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ የተለያዩ አካላት ወደ ሰላም መምጣታቸውን ተከትሎ ከመንግሥት ጋር እንዲሁም ከክልሉ ጋር በተለያየ መልኩ ወደ ሰላም ስምምነቶች ተደርሰው ወደ መደበኛ ኑሯቸው እንዲመለሱ መደረግ በመቻሉ፤ የሰላም እጦትን ሽፋን በማድረግ በጣም በርካታ ሕገወጥ ሥራ ይሰራባቸው የነበሩ አካባቢዎች አሁን ግልጽ እንዲወጡ አድርጓል። መንግሥት እነዚህን ወንጀሎች ተከታትሎ እርምጃ እንዲወስድባቸው ለማድረግ በጣም ምቹ አጋጣሚን የፈጠረው ሰላም በመኖሩ መሆኑን ሁሉም ሊገነዘብ ይገባል።
ሕገወጥ ተግባር በተለይ እነዚህ ቀደም ሲል ያነሳናቸው በኮንትሮባንድ እንዲሁም በሕገወጥ መንገድ ወደ ሀገር በመግባት ሲከናወኑ የነበሩ የማዕድን ማውጣትና መፈለግ ሥራዎች በጣም በርካቶችን ያሳተፈ ነበር የነበረው። ከሀገር ውስጥ ከኢትዮጵያን ባሻገር በዓለም አቀፍ ደረጃም ጭምር ሰንሰለቱ የተዘረጋ እንደሆነም ይታወቃል። ይህንን ደግሞ በቁጥጥር ስር ለማዋል ያለ ማህበረሰቡ ተሳትፎ ምንም ውጤት ማምጣት እንደማይቻል በግልጽ ማወቅ ያስፈልጋል።
በወንጀል ሥራው ላይ ተሳትፈዋል የተባሉትን ግለሰቦች ከእነኤግዚቢታቸው በቁጥጥር ሥር ማዋል የተቻለው በአካባቢው በሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ጥቆማ በመስጠታቸው፤ ምርመራዎች በሚደረጉበት ጊዜ፣ ጥናቶች በሚደረጉበት ጊዜ ሁሉ ማህበረሰቡ ከፍተኛ ትብብር ሲያደርግ እንደነበረ በተለያዩ አካላት በኩል ሲነሳ የነበረ ነው። ይህም ኦፕሬሽን ውጤታማ እንዲሆን ከፍተኛ ትብብር ላደረጉ የማህበረሰብ ክፍሎች፤ በየክልሉ ለሚገኙ ዜጎች መንግሥት ምስጋናውን ያቀርባል።
እነዚህ ሥራዎች ከፍተኛ የሆነ የኮንትሮባንድ ሕገወጥ ንግድ ሥራዎች አሁን ቀደም ሲል በጠቀስኳቸው ክልሎች ላይ ብቻ አይደለም፤ ሁሉም ክልሎች ላይ እየተፈጸመ ያለ ወንጀል ነው። ስለዚህ ይህንን ወንጀል ደግሞ ማስቆም የሚቻለው በተለይ በሀገራችን ኢኮኖሚ ላይ እየተፈጸሙ የሚገኙ እነዚህ ትልልቅ ወንጀሎችን ለማስቆምና ዜጎች የሚገባቸውን ጥቅም ከሀገራቸው ማግኘት እንዲችሉ ለማድረግና ለመከላከልም ጭምር፤ እነዚህን ወንጀሎች በሚፈጸሙበት ጊዜ ሕብረተሰቡ ከጸጥታ አካላት ጋር ያለውን ቅንጅት በማጠናከር ከዚህ በፊት ሲያደርግ የነበረውን ተግባር አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በዚሁ አጋጣሚ መንግሥት ጥሪውን ያቀርባል።
ግብርና እና የልማት ሥራዎች
በመጨረሻ የምንመለከተው የልማት ሥራዎች በተለይ የግብርናውን ዘርፍ ነው። ወቅታዊ የበልግ የበልግ እርሻ ስራ መረጃዎችን ስንመለከት፤ በ2015 የምርት ዘመን በበልግ ወቅት 2.2ሚሊዮን ሄክታር መሬትን ነው ለማልማት እቅድ የተያዘው፤ ከዚህም ውስጥ ወደ 24 ሚሊዮን ኩንታል ምርትም ይጠበቃል። እስከ አሁን ድረስ ባለው ወቅታዊ መረጃ ከግማሽ በላይ የሚሆን መሬት መታረሱን ነው የተለያዩ መረጃዎች የሚያሳዩት በሁሉም ክልሎች በተለይ በበቆሎ፣ ማሽላ፣ ስንዴና ጤፍ በዋንኛነት እንግዲህ በበልግ አብቃይ አካባቢዎች የሚመረቱ ምርቶች ናቸው። 92 በመቶ የሚሆነው እንግዲህ አነስተኛ ይዞታ በላቸው አርሶአደሮች ነው እነዚህ የእርሻ ስራዎች የሚፈጸሙት። 5 በመቶ ደግሞ በጠቃላይ ለሀገራዊ ምርትም ድጋፍ የሚያደርግ የእርሻ ዘመን/ወቅት ነው።
አረሶአደሩ ከፍተኛ ጥያቄ ከሚያቀርብባቸው እና ለልማት ስራውም ትልቅ አስተዋጽኦ ከሚያበረክቱት መካከል የአፈር ማዳበርያ አንደኛው ነው። ይሄም ደግሞ አቅርቦቱን ስንመለከት ለ2015/16 የምርት ዘመን ወደ 12 ነጥብ8 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበርያ ግዢ መፈጸሙን መረጃዎች ያሳያሉ። ከባለፈው ዓመት ደግሞ የከረመ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል አለ። ይህ የከረመው የአፈር ማዳበርያ ጋር ተደምሮ እንግዲህ በጠቅላላው ለ2015/16 የምርት ዘመን እስከ 15 ሚሊዮን ኩንታል የሚሆን የአፈር ማዳበርያ ለአሶአደሩ ለማሰራጨት ያስችላል። እንግዲህ ለበልግ ወደ 36 ሺህ 199 ኩንታል የሚሆን የአፈር ማዳበርያ ለስርጭት ዝግጁ ተደርጓል። በአጠቃላይ እንግዲህ እስከ አሁን የተሰራጨ የሚገኘውን ቁጥር ስንመለከት ወደ 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበርያ ነው።
አሁን ላይ ከፍተኛ የሆነ ዝናብ አለ። በተለይ የበልግን ዝናብ ለልማቱ በአግባቡ መጠቀም እንዲቻል ከዛም በሻገር በመስኖ ለምቶ የደረሱ ሰብሎችን በተገቢው መንገድ ያለብክነት መሰብሰብ እንዲቻል ሁሉም ማህበረሰብ በተለይ ደግሞ በዚህ ስራ ላይ የተሰማራው አካላት እና ድጋፍ የሚያደርጉ አካላትም ጭምር ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ ሊሰሩበት ይገባል። ምክንያቱም አሁን ያለው ዝናብ በመስኖ ስንዴ ሰብል ላይ ተጽኖ ሊያሳርፍ ስለሚችል ሰብል በደረሰባቸው አካባቢዎች ላይ በዝናቡ ምክንያት ብክነት እንዳይፈጠር በልዩ ትኩረት ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርበታል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 30/2015