ዓለምና እኛ ያልተግባባንበት ወይም ደግሞ ልዩነት የፈጠርንበት አንድ መስመር የማይሞላ፣ የገነገነ ልማድ አለ፤ የፉክክር መንፈስ – ትንሳኤን በፉክክር ውስጥ የመፈለግ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ልማድ።
የዓለም መልክ የምክክር መልክ ነው። የዓለም ስልጣኔ የውይይትና የተግባቦት ስልቸ አንደርስበትም። ከስልሳ ዓመት ወዲህ ያለችው ኢትዮጵያ ትንሳኤዋ የተሳለው በፉክክር ውስጥ ነው። የእኔ፣ የአንተ፤ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ ሌላም ሌላም በሚል ትርክት ውስጥ።
የዓለም ልምድም ሆነ ታሪክ እንደሚያሳየው ይህ ጽንሰ ሀሳብም ሆነ ንድፈ ሀሳብ አገርና ህዝብን አይጠቅምም። “ይጠቅማል” ከተባለ እንኳን ኢትዮጵያን ለሚጠሉና ክፉዋን ለሚመኙ ጠላቶች ብቻ ነው። ከጠቀመም የስልጣን ጥም ላለባቸው ፖለቲከኞች ብቻ ነው። ጉዟችን እንዴትም ይሁን በምክክር እስካልተራመድን ድረስ ትንሳኤ የለንም።
ትንሳኤ ቃሉ ብርሀን ነው። መሻገር ነው። መታደስ ነው። ብርሀንና መሻገር መታደስና መለወጥ በምክክር ውስጥ ካልሆነ በሌላ በምንም እንዳይደረሱ ሆነው የተቀመጡ ናቸው። አልደርስ ያልናቸው የእድገትና የስልጣኔ አምባዎች የራቁን ችግር ፈቺ የምክክር ልማድ ስለሌለን ነው።
በፍቅር ካልሆነ የስኬት መጨረሻዎች ሩቅ ናቸው። በውይይት ካልሆነ የድልና የእድል ወደቦች የማይደረሱ ናቸው። ከእኔና ከአንተ ከሌላውም ሰው በተወጣጣች አገር ውስጥ፣ በመቶ ሀያ ሚሊዮን ህዝብ ልማድና እምነት በቆመች አገር ፉክክር እያስከፈለ ያለውን አላስፈላጊ ዋጋ አለማስተዋል አሳዛኝ እውነታ ነው።
ስልጣኔ ከሀሳብ የሚጀምር የእቅድና የክዋኔ ውህደት ነው። ምክክር በታከለበት ሀሳብ አገር መፍጠር ካልቻልን በፉክክር ለማንም የማትሆንን አገር ነው የምንፈጥረው። ይሄ ደግሞ እንደመጣንበት ትላንትና በጦርነትና በእልኸኛነት እንድንቆም ከማድረግ ባለፈ እርባና የለውም።
ኢትዮጵያ የማንም አይደለችም። የሁላችንም የጋራ ቤት ናት። አለላና ስንደዶ፣ አክርማና ሰንበሌጥ በአንድ ላይ ሆነው ሞሰብ እንደሰሩ ሁሉ እኛም በአንድ ላይ ሆነን ነው ኢትዮጵያን የሰራንው። የእኔ፣ የአንተ ወይም ደግሞ በብሄር ተቧድነን ጉራጌና ሺናሻ ስንባባል ስር ሰዶ ያጠነከረንን የኢትዮጵያዊነት ገመድ እያላላን ነው።
ይሄን ሀሳብ የሚያጸና፣ ይሄን እውነት የሚያስረግጥ በምክክር የታገዘ “የእኛ” የሚል የጋራ እውነት ያስፈልገናል። እኛ እየተጋፋን ልናጠባት አያስፈልግም፣ ኢትዮጵያ ሰፊ ነች፣ ነበረች። እኛ እየተቧደንን ልናሳንሳት አይገባም፣ አገራችን ግዙፍ ነች፤ ነበረች። ክብራችን እዲገዝፍ፣ ልዕናችን እንዲጸና “እኔ”ነት የሌለባት፤ “እኛ”ነት የሰፈነባት አገር መገንባት ይጠበቅብናል።
ካለንበት ከድህነት የምንወጣበት፣ ከኋላቀርነት የምናመልጥበት አንድ አቋራጭ መንገድ የምክክር መንገድ ነው። ችግሮቻችን ችግር እየፈጠሩ፣ ፖለቲካችን ነውጥ እየፈጠረ የምንገነባው የጋራ አገር አይኖረንም። አድዋ እኮ ከአንድነት ባለፈ የምክክር ውጤት ነው። ብዙ የልዕልና ታሪኮቻችን እኮ የአባቶቻችን የአንድነትና የተግባቦት መንፈስ ነፍስ የዘራበት ነው።
ችግሮቻችንን ከዚያም ከዚም ለቅመን ለውይይት ክፍት በሆነ የጋራ መድረክ ላይ እናቅርባቸውና እንወያይባቸው። ከዛም ወደ ትንሳኤ በሚወስደን የጋራ አጀንዳ ላይ እንምከር። ይሄ ጤነኛውና አዋጩ፤ አሁን ላለችው ኢትዮጵያ የሚበጅ፣ ሞትና ጉስቁልናዋን የሚያስቀር የትንሳኤ መንገድ ነው።
የአገራችን አብዛኞቹ ችግሮች ከፖለቲካው መንጭተው ወደ ህዝብ የሚፈሱ ናቸው። ኢትዮጵያ መጥፎ ፖለቲከኛ እንጂ መጥፎ ህዝብ የላትም። የህዝብ ፍቅር ዛሬም እንደ ድሮው በአንድነትና በኢትዮጵያዊነት የሚያምን ነው። ዛሬም እንደጥንቱ ተከባብሮና ተቻችሎ የሚኖር ነው። ችግር የሆኑብን ራስ ወዳድ እና አክራሪ ፖለቲከኞች ናቸው። ያልነቃና ያልበቃ ፖለቲካ ህዝብ ሊያነቃ አይችልም። ያልነቃና ያልበቃ ፖለቲከኛም አገር ሊለውጥ አይቻለውም።
ትንሳኤያችን ያለው ለአገር በሚበጅ የምክክር መንፈስ ውስጥ ነው። በእውቀት ነቅተን በእውነት ካልተራመድን ስለኢትዮጵያ መጻኢ እድል ዋስትና የለንም። ምን አይነት አሻራን እያሳረፍን እንደሆነ ራሳችንን እንጠይቅ። በኢትዮጵያ ላይ ኃላፊነት ያለበት መንግስት ብቻ እንደሆነ አምነን የተቀበልን የዚህ ትውልድ አሳቤዎች ብዙ ነን። የራሳችን ኃላፊነት የዘነጋን።
አባቶቻችን ካስተማሩን ጋር የሚጣረስ ፖለቲከኞቻችን ያስተማሩን ብዙ ልማዶች አሉን። አገር የማይገነባ፣ ወደ ነገ የማያራምድ ብዙ የስህተት ትርክቶችን ከፖለቲከኞቻችን ወስደናል። ዛሬ ላይ ያ ልማድ ነው ተነጋግረን እንዳንግባባ፣ ተመካክረን እንዳንስማማ እክል የፈጠረብን።
አባቶቻችን ያስተማሩን ስለ መቻቻል አብሮ ስለመኖር ነው። ይህም ለአገር ህልውና ወሳኝ እንደሆነ ጭምር። በእነሱ ልብ ውስጥ አገር እንጂ ብሄር የገነነ አልነበረም። ፖለቲከኞቻችን ያን የአባቶቻችንን እውነት ቀይረው የችግር ምንጭ አደረጉብን።
በአድዋ ድል ውስጥ ጥልቅ አገር ነበር። አባቶቻችን ለአንድ አገራቸው ሲሉ ነበር የተዋደቁት። እኛም ዛሬ ችግራችንን ለመፍታት፣ ከድህነት ለመውጣት የፖለቲከኞቻችን የራስ ወዳድነት እውቀት ሳይሆን የአባቶቻችን የመቻቻል እና አብሮ የመኖር እውቀት ያስፈልገናል።
አክራሪ ብሄረተኝነትትርፍ የለውም። የመከፋፈል እና ከዚህ የሚመነጭ ጥፋት ምንጭ ነው። እንደአባቶቻችን ያለ ብልህነት ውስጥ አገርን ያስቀደመ፣ ሰውነትን የተረዳ ፖለቲካዊ እውቀት ያስፈልገናል። በእውቀትና በተግባቦት የደፈረሰውን እያጠራን በአንድነት ከመኖር ውጪ አገር መገንቢያ የተሻለ እድል የለንም።
ያለፉ ስህተቶችን እየመዘዙ ለዛሬ ስልጣን መወጣጫነት መጠቀም በፖለቲካችን ውስጥ እያጋጠመን ያለው እና ብዙ ዋጋ እያስከፈለን ያለ አሁነኛ ችግር ነው። ትላንትን ለትላንት ትቶ ዛሬ ላይ በአዲስ አስተሳሰብ ለመራመድ ወደ ራሳችን መመልከት ይኖርብናል።
ሁላችንም ነገ በሚመጣው ፖለቲከኛና ፖለቲካ ውስጥ ስማችን እንደሚነሳ ብናውቅ በሌሎች ስህተት ማትረፍን እንተው ነበር። ይሄንና የመሳሰለውን የፖለቲካ ልማዳችንን እስካልቀየርን ድረስ ከፉክክር አንወጣም። ከፉክክር ብቻ አይደለም ተነጋግረንም መግባባት አይቻለንም።
ምክክር የለውጥ መንገድ ነው። ተመካክረንና ተግባብተን የጋራ ችግሮቻችንን በጋራ እስካልፈታን ድረስ ለህልሞቻችን ሩቅ ነን። ፖለቲከኞቻችን ለራሳቸው የምትመችን ሳይሆን ለትውልዱ የምትመችን አገር የመፍጠር ግዴታ አለባቸው። ህዝብ የፖለቲከኞቻችንን ድምጽ ብቻ ሳይሆን አንድነት ያለበትን የአባቶቹንም አደራ ጭምር ማስታወስ ይገባል።
ካልተመካከርን የትላንት ችግሮቻችን እንዲያሰቃዩን እየፈቀድንላቸው ነው። ካልተመካከርን ለክርክርና ለፉክክር መንገድ እየጠረግን ነው። ቤት በምሰሶ እንደሚቆም ሁሉ አገርም በምክክር የምትቆም ናት። ጣሪያ፣ ማገሩ፣ ወራጅና ምርጉ በምሰሶ መኖር ህልውና የሚያገኙ ናቸው።
እንደዚህም ሁሉ አገር የብዙ ብሄርብሄረሰቦች መናኸሪያ ናት። እነዚህ ሁሉ ብዙ አይነት ማንነቶች ተከባብረውና ተቻችለው እንዲኖሩ ቤቱን እንዳቆመው ምሰሶ ምክክር ያስፈልጋቸዋል። ምሰሶ የሌለው ቤት ቤት እንደማይሆን ሁሉ ምክክርና ውይይት የሌለበት አገርም ዋስትና የለውም።
እንደአገር ብዙ የምግባባቸውም ድንገትም የማንግባባቸውም ጉዳዮች ሌኖሩን ይቻላል። ይህ ነገም ሊቀጥል የሚችል እውነታ ነው። ጥልቁ ጉዳይ በጉዳዮቹ ዙሪያ በግልጽ መነጋገር መቻል ይህንንም ባህል አድርጎ ማስቀጠል ነው። ይህ ለዛሬም ሆነ ለነገ ችግሮቻችን ትክክለኛው ፈውስ ነው።
ፈውስ በሌለውና ህመም ብቻ በሆነባት አገር ላይ የሚመጣ የትንሳኤ ብርሀን የለም። ትንሳኤ በፍቅር የሚበራ ነው። ትንሳኤ በአንድነትና በወንድማማችነት የሚቀጣጠል የተስፋ እሳት ነው። ከትናንት ያልተማሩ ህዝቦች ጠንካራ አገር አይገነቡም። የእኔነትና የራስ ወዳድነት ድምጾች በራሳቸው አገር አይቀይሩም።
“የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል” እንደሚ ባለው አገራችን በእኔና በእናንተ ፉክክር ዛሬም አልተዘጋችም። ዛሬም ክፍቷን ናት። በፖለቲካው ውስጥ ፉክክር አለ። በኢኮኖሚው፣ በማህበራዊ ህይወታችን ውስጥ ፉክክር አለ። በአንድ አገር፣ በአንድ ታሪክ፣ በአንድ ስጋና ደም ውስጥ ቆመን ፉክክራችን ለምን እንደሆነ በቂ ተጠየቅ የለውም።
አገራችን ፉክክር አያስፈልጋትም። ተፎካክረን መጥተን ያልዘጋናቸው እልፍ የመከራ ዶሴዎች አሉን። የሚበጀን እነዛን በፉክክር ያልተዘጉ የጥላቻና የመለያየት አጀንዳዎች በምክክር መዝጋት ነው። የሚበጅን እነዛን እንዴትና በማን እንደተፈበረኩ የማናውቃቸውን መሰረት አልባ የጥላቻ ሴራዎች ማፍረስ ነው።
በእኛ ስህተት እኛ ነን የምንጎዳው። ከእኛ ውጪ ማንም የሚጎዳልን የለም። በእኔና በአንተ ፍቅር ኢትዮጵያ ክፍቱን የቀረ በራፏ መዘጋት አለበት። በእኔና በአንተ አንድነትና ወንድማማችነት እርቃ የወጣውን ገላዋ መሸፈን አለበት።
ለሁሉ የምትበቃን ሰፊ አገር የእኔ፣ የአንተ በሚል የህልውና ስጋት ውስጥ ልንከታት አይገባም። በእርቅና በምክክር ካልሆነ በፉክክርና የእኔ ያንተ በሚል መንፈስ ውስጥ ቆመን አገራችንን የጋራ ማድረግ አንችልም። የፉክክር ቤት ሁልጊዜም ክፍት ነው። ሁልጊዜም ኦና ነው። ማንም ገብቶ የሚወጣበት ባለቤት አልባ ነው።
ስንፎካከር አገራችንን ባለቤት አልባ እያደረግናት ነው። ስንፎካከር አገራችንን ለማንም እንዳትሆን እያደረግናት ነው። ከፉክክር ወጥተን መመካከር አለብን። አገራችንን የምንታደጋት አሁን ካለችበት ችግር የመንንታደጋት የእኔ፣ የአንተ ከሚል የፉክክር መንፈስ ወጥተን በጋራ ስንቆም ብቻ ነው።
እስካሁን የሄድንበት መንገድ ዋጋ ከማስከፈል ባለፈ አልጠቀመንም። ያን መንገድ መድገም ሌላ ዋጋ መክፈል ከመሆን ባለፈ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም። ለውጥ ያስፈልገና..የባህሪ ለውጥ፣ የአስተሳሰብ ለውጥ፣ ለውጥ . . . ያስፈልገናል።
በብሄራዊ ምክክር ኮሚሽን በኩል በተፈጠሩ የውይይት መድረኮች ላይ እድሎቻችንን መጠቀም አለብን። ተነጋግረን ለመግባባት፣ ተግባብተን አብረን ለመቆም ከመቼውም ጊዜ በላይ የምንተጋበት ወቅት አሁን ነው። ትላንት ዛሬን እንዳያበላሽብን፣ ዛሬ ወደ ነገ እንዳይሄድ፣ አላስፈላጊ አጀንዳዎቻችንን በምክክር እዚሁ ማስቀረት ይኖርብናል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን መጋቢት 29/2015