የታሪክ ድርሳናት እንደሚስረዱትም፤ የኢትዮጵያ ታሪክ ከ3000 ዓመታት በላይ ወደ ኋላ ይመዘዛል። በእነዚህ ዓመታት ውስጥ የተለያዩ መንግስታዊ አስተዳደሮችና ሥርዓቶች ተፈራርቀዋል። እንደ ሀገርና ሕዝብ እነዚህ ሂደቶችን አልፈን አሁን ያለንበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ከ1966 ዓ.ም ቀድም ብለው የነበሩት በአብዛኛው በአፄው ሥርዓት ላይ ያተኮሩ፣ ንጉሳዊና እና ዘውዳዊ ሥርዓቶች ነበሩ።
በዚሁ አስተዳደራዊ ስርአት ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮቿንም ስታስተናግድ ቆይታለች። በዚህም ሀገሪቱ የቆየና፣ የጎለበተና ታሪክ ጠገብ የሀገረ መንግስት ታሪክ ባለቤት ነች። በእነዚህ ዘመናትም የተለያዩ ታሪካዊ ክስተቶችን አስተናግዳለች፤ አሁንም እያስተናገደችም ነው። ከክስተቶቹ መካከልም ከሁለት ዓመት በፊት በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል የተካሄደውን ጦርነት ለመመማሪያ ይሆን ዘንድ ማንሳት ተገቢ ነው።
ይህ ጦርነት እንደ ሀገር በሕዝባችንም በሀገራችንም ላይ ከባድ ጉዳት አድርሷል። በጦርነቱ በትግራይ እና በሌሎች አጎራባች ክልል በሚኖሩ ዜጎች ላይ የሞት፣ የአካል ጉዳት መፈናቀልና የንብረት ውድመት ደርሷል። ክስተቱ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ውስጣዊ እና ውጫዊ ጫናዎች የበረቱበት ነበር። በዚህም በአገሪቱ ላይ በርካታ ጫናዎች ደርሰዋል። በፌደራሉ መንግስት እና በሕወሓት መካከል በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተደረሰው የሰላም ስምምነት በኋላ ግን ነገሮች በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛሉ።
የዚህ ጽሁፍ ዋነኛ አላማ በጦርነቱ የደረሱ ጥፋቶችን መዘርዘር ሳይሆን፤ የችግሩ ሰለባ የሆኑ ዜጎቻችንን እንዴት መካስና ማቋቋም ይቻላል በሚለው ላይ ያተኮረ ነው። በቅርቡ ወደ ስራ የገባው አዲሱ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ከዚህ አንጻር ምን ይጠበቅበታል የሚለውን ኃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ ለመጠቆም ነው።
በርግጥ ጊዜያዊ የሽግግር መንግስቱ ወይም አስተዳደሩ የክልሉ ሕዝብ ከሁሉም በላይ የሚፈልገውን ሰላም በሁለንተናዊ መንገድ የማስፈን ኃላፊነት እንዳለበት ብዙም ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም። ሰላም ማስፈን የቅድሚያ ቅድሚያ ስራው መሆን አለበት። ለዚህ ደግሞ እራሱን ለፕሪቶሪያው ስምምነት ማስገዛት፤ ለዚህ የሚሆነውን ቁርጠኝነቱን በየእለቱ ማደስ ይጠበቅበታል። ሰላም የሁሉም መሰረት ነውና።
ሰላሙን ተከትሎ ቀጣይ የሆነውን የሕዝቡን የልማት እና የተሻለ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ ይጠበቅበታል። ከአጎራባች ክልሎች ጋር ያለውን ግንኙነት ከማደስ ጀምሮ፤ በጦርነቱ ምክንያት በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ያሉ የክልሉ ዜጎችን ችግር መፍታትንም የሚያካትት መሆን አለበት። ይህንን ደግሞ የክልሉን ሕዝብ በሚመጥንና በሚገባው መልኩ ሊተገብር ይገባል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ የክልሉን ሕዝብ የሚመጥን ስራ መሠራት አለበት ሲባል ዘርፈ ብዙ እሳቤዎችና ትርጉሞችን ያዘለ ነው። በጦርነት ውስጥ የከረመ ሕዝብ ብዙ ነገር ያስፈልገዋል፤ ይጠይቃልም። በማህበራዊ፤ ፖለቲካዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊና ስነልቦናዊ ምስቅልቅሎችን ለማረምና ለማስተካከል ከተለመደው አሰራር ውጭ የተለየ ቆራጥነትና የአመራር ብቃትና ጥበብ ይጠይቃል። የሁሉንም አቅሞች መጠቀምና የሕዝብ ሁለንተናዊ ተሳትፎም ያስፈልጋል። ለጋሽ አካላትን ማስተባበርና ወደ ስራ እንዲገቡ ምቹ ሁኔታ መፍጠርንም የግድ ይላል።
በምጣኔ ሀብት ረገድ ጦርነት የደቆሰውን መሰረት ልማትና ኢኮኖሚው መልሶ እንዲያንሰራራ የተለያዩ አማራጮችን አስቦ መንቀሳቀስ ይጠበቅበታል። ወደ ክልሉ የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ጨምሮ የውጭ አገር አልሚዎች እንዲገቡ በስፋት መንቀሳቀስ፤ ለዚህ የሚሆን ግልጽ የሆነ አሰራር ማስቀመጥ እና እለት እለት አሰራሩን መቆጣጠር ያስፈልጋል። ከዚህ በፊት የነበሩና ለስራ የማይመቹ አሰራሮችና መመሪያዎች ከማረምና ከማሻሻል በዘለለ አዳዲስና ወቅቱን የሚዋጁ አሰራሮች መከተልና መመሪያዎችን ማውጣት አስፈላጊ ነው።
እንደሚታወቀው ትግራይ ብዙ ታሪካዊ ስፍራዎች፤ አስደማሚ መልከአ ምድራዊ አቀማመጦች፤ በርካታ ተፈጥሯዊ፣ ባህላዊና ታሪካዊ ሀብቶች የታደለች ክልል ናት። የ3000 ዓመት የሓ ጥንታዊ ቤተ መቅደስ፣ የ2000 ዓመት የአክሱም ጥንታዊ ሃውልቶች፣ ከ4ኛው እስከ 15ኛው ክፍለ ዘመን እንደተሰሩ የሚታወቁ በመቶዎች የሚቆጠሩ ከአለት ድንጋይ ተፈልፍለው የተሰሩ ውቅር አብያተክርስቲያናት እና ገዳማት እንዲሁም ሌሎች በርካታ ታሪካዊና አርኪኦሎጂካዊ ስፍራዎች የሚገኙበት ናት። እነዚህ ስፍራዎች በርካታ ቱሪስቶችን በመሳብ የክልሉን የኢኮኖሚ አቅም በማሳደግ ሊኖራቸው የሚችለው ሚና የት የለሌ ነው። አሁን ግን እነዚህ ሁሉ ስፍራዎች ከስም በዘለለ እንደ ቀድሞ የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ አገር ጎብኚ የላቸውም።
የአክሱም መንደሮች የሚጎበኛቸው ባለመኖሩ ፆም እያደሩ ነው። በየዓመቱ በአክሱም ፅዮን ማርያም ንግስ በዓል የሚታደሙ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን አክሱም ናፍቀዋል። አክሱምን ካዩ ሶስት አመታት አልፏቸዋል። ይህ ወደ ነበረበት መመለስ አለበት። ለሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትም እጅግ ወሳኝ ነው። በተመሳሳይ 3000 ዓመት የሓ ጥንታዊ ቤተ መቅደስ እና ሌሎች ታሪካዊ ሥፍራዎችም በተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ናቸው። እነዚህን ወደ መስመራቸው ፈጥኖ በመመለስ ረገድ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ሚና የላቀ ነው።
አዲሱ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ለዜጎች ሰላምና ደህንነት፣ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ የመሥራትና መኖር መብት፣ የሴቶችና ህፃናት መብት ለማክበርና ለማስከበር፤ ተፈናቃዮችንና የቀድሞ ተዋጊዎችን መልሶ ለማቋቋም እንዲሁም ለኢትዮጵያ አንድነትም በፅናት ሊሠራ ይገባል። ሁሌም ማወቅ ያለብን ነገር አለ። ሰላም በእጃችን ነው። ሰላምን ለማስፈን ደግሞ ዋነኛ ተዋናይ መሆን ያለብን እኛው ነን።
የሰላም ባለቤት ሕዝብ ነው። ሕዝቡ ሰላሙን ሊጠብቅና ሊያስከብር ይገባል። በዚህ ውስጥ ደግሞ የመንግስትም ሚና በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በእርግጥ ጦርነት ትናንት ካስከፈለው ያልተገባ ዋጋ አንጻር ለትግራይ ሕዝብ በሰላም አስፈላጊነት ዙሪያ መንገር የሚያስፈልገው አይደለም።
እንደ ኢትዮጵያዊ ለእኛው ከእኛ በቀር ማንም አይቆረቆርልንም የሚል ጠንካራ አቋምና ባህል መያዝ አለብን። ለትግራይ ሕዝብ ከአማራና አፋር ሕዝብ በላይ የሚቆረቆር ይኖራል ብዬ አላስብም። ለአማራና አፋር ሕዝብም ከትግራይ ሕዝብ በላይ የሚቆረቆር አለ ብዬ አልገምትም። በሌላው የኢትዮጵያ ሕዝብም ተመሳሳይ ነው።
ምንም እንኳን ያልተጠበቁ ክስተቶች ቢኖሩም የታሪክን ሁነትና የነበረውን መስተጋብር ግን የሚያናጥፈውና የሚቆረጥ ልል ገመድ ያለ አይመስለኝም። በእነዚህ ሕዝቦች መካከል የነበረው ሁኔታ አይጎድለም የሚል የፀና እምነት አለኝ። በጽኑ ታሪክና መሰረት ላይ የተገነባን መሰረት ወቅታዊ ክተተቶችና ያልታሰቡ አጋጣሚዎች ሙሉ ለሙሉ ሊያደበዝዙት አይችሉም።
ባለቤት ሲጮህ ነው ጎረቤት ሊረዳና ሊያግዝ የሚችለው። ስለዚህ እኛ የሚያምርብን እርስ በእርስ ስንረዳዳ ነው። ልማትና ዕድገት፣ ዲሞክራሲና ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት ሊመጡ የሚችሉት ምን ጊዜም ከሰላም በኋላ ነው። ሰላም ከሌለ ሁሉም ነገር የለም። በመሆኑም በየትኛው ቦታ እና ሁኔታ ውስጥ ያለን ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ስለ ሰላም መስራት ይጠበቅብናል። ስለ አንድነትና መቻቻልም ጊዜ ወስደን መስበክ ይገባናል።
በተለይም ደግሞ የትግራይ ክልል አዲሱ አመራር ትግራይን የሚመጥን ሰላም፤ ዴሞክራሲ፤ ልማት ማስፈን የሕልውና ጉዳይ አድርጎ መውሰድ አለበት። በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ያልተገባ ዋጋ የከፈለው ሕዝብ ካጎነበሰበት ቀና እንዲልና ስነ ልቦናዊ ጫናው እንዲቃለል ብዙ አስቦ ብዙ መስራት ይጠይቃል።
መሬት የነኩ ሰላማዊ እንቅስቃሴዎች በክልሉ መተግበር ለይደር የማይተው ጉዳይ ነው። ከአጎራባች ክልሎች ጋር ያለውን ቅራኔ ፈጥኖ በመፍታት የጥርጣሬ ፖለቲካን እስከ ወዲያኛው መሸኘት አስፈላጊ ነው። በአጠቃላይ በዚህ ወሳኝ ወቅት የትግራይን ሕዝብ የሚመጥን ሁሉን ተኮር ሥራ ማከናወን ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ይጠበቃል፤ ይህንን ማድረግ ታሪካዊ ግዴታም ጭምር ነው። ውጤታማ ስራ እንዲሰራ ደግሞ የሕዝቡና የሌሎች የፖለቲካ ኃይሎች ድጋፍም ሊለየው አይገባም።
ዶክተር ጀኔኑስ
አዲስ ዘመን መጋቢት 29/2015