የአባይ ግድብ/የኢትዮጵያ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ/ ገጥሞት ከነበር የኮንትራት አመራርና አስተዳደር ችግር፣ የማስፈጸምና የመፈጸም ውስንነት፣ ከውስብስብ ሙስና፣ ብልሹ አሰራርና ዝርክርክነት ተላቆ ከለየለት ክሽፈት ድኖ ነፍስ የዘራው በለውጡ ማግስት በተሰጠው በሳል አመራር ስለሆነ የለውጡ ትሩፋትና ደማቅ አሻራ ያረፈበት ሜጋ ፕሮጀክት ነው ማለት ይቻላል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ”እንደ ስሙ አንድምታው ከኢኮኖሚያዊ አውታርነት አድማስ ባሻገር ነው።
ሰሞኑን በተለይ ከኢትዮጵያ ፕሬስ ኤጀንሲ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አረጋዊ በርሄም ያረጋገጡት ይሄን ሀቅ ነው። የኢትዮጵያን የሕዳሴ ጉዞ ችቦ የለኮሰም ነው ይቻላል። ከአንድ ዓመት በኋላ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ የብርሀን ጭላንጭል ለናፈቃቸው ከ50 ሚሊየን በላይ ወገኖች ጸዳል ሊሆን አሽቷል። በተደጋጋሚ በሚከሰት የኃይል መቆራረጥና እጥረት አሳሩን እየበላ ለሚገኘው ኢንዱስትሪም ሆነ ሌላ የኢኮኖሚ ዘርፍ የምስራች ይዟል።
የኤሌክትሪክ ኃይል በመሸጥ በዓመት ከ1 ቢሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ለማስገኘትም አልሟል። ከሁሉም በላይ ኢትዮጵያ በቀጣናው ከፍ ሲልም በአፍሪካም ሆነ በዓለም የሚኖራትን ጂኦፖለቲካዊ ተጽዕኖ ከፍ ያደርጋል። ይህ አንድላይ ሲደማመር ለኢትዮጵያ ሕዳሴ መበሰር ነጮች እንደሚሉት የመስፈንጠሪያ ሰሌዳ/spring- board/ይሆናል። ገጥሞት ከነበረው የለየለት ክሽፈት በለውጡ አመራር ቆራጥ ውሳኔ ድኖ ለዚህ መብቃቱ ታላቅ ገድል ነው።
የኢትዮጵያ ሕዳሴ ወሳኝ መታጠፊያ /critical juncture/የሆነው ይህ ግዙፍ ሕልምና ራእይ እውን ሆኖ ከአንድም በሁለት ተርባይን 550 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለማመንጨት የበቃው በመላው ኢትዮጵያዊ ርብርብ ነው። ከሊስትሮ እስከ እንጨት ለቃሚ፤ ከሕጻናት እስከ አረጋውያን፤ ካጣ ከነጣ ድሀ እስከ ባለጠጋና ባለሀብት፤ ከአገሬው እስከ ዲያስፖራው፣ ወዘተረፈ ጠጠር ያልጣለ የለም። ከእለት ጉርሱ ቀንሶ፣ ከልጆቹ ጉሮሮ ቀምቶ የታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቦንድ ገዝቷል። ገንዘብ አበርክቷል። ለግሷል። ጉልበቱንና እውቀቱን አዋጥቷል። ከፍ ሲልም ህይወቱን ሰውቷል። በድምሩ ከ20 ቢሊየን ብር በላይ አዋጥቷል።
በአገሪቱ ታሪክ ኢትዮጵያዊ በሞላ ያለ ልዩነት እስላም ክርስቲያን፤ አማራ ኦሮሞ ትግሬ ጉራጌ ሀድያ፤ ሳይል በአንድነት ሰራዊትና ደጀን የሆነለት ግዙፍ ፕሮጀክት ነው። በነገራችን ላይ በአገሪቱ ታሪክ በብዙ ሚሊየን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ለአንድ ሜጋ ፕሮጀክት ይሄን ያህል ገንዘብ አዋጥተው አያውቁም። የዛሬው ትውልድ በሕዳሴው ያሳየው ርብርብ የቀደሙትን ትውልዶች ክብረ ወሰን ሁሉ ሰባብሮታል ማለት ይቻላል። ተደቅኖበት ከነበረ የለየለት የክሽፈት አደጋ ታድጎ በእነዚህ ቀውጢና ፈታኝና እልህ አስጨራሽ ዓመታት ሁሉ ጥርሱን ነክሶ በአጭር ታጥቆና ህልቆ መሳፍርት ለሌለው ጫና አንድ ጊዜም ሸብረክ ሳይል ለዚህ ያበቃው የለውጥ ኃይልም ያለ ምንም ስስትና ንፍገት በልኩ እውቅና ሊቸረው ይገባል።
የእንችላለን መንፈስን ለኢትዮጵያውያን ከፍ ሲልም ለመላው አፍሪካ ያጋባው የሕዳሴው ግድብ ዳግማዊ አድዋ ነው። ካለምንም እርዳታና ብድር በዜጎች አበርክቶና በመንግስት በጀት እየተገነባ ያለ ተምሳሌታዊ ብሔራዊ ፕሮጀክት ነው። እስካሁን ወደ 200 ቢሊየን ብር የሚጠጋ ወጭ የተደረገለት ሲሆን የሲቪል፣ የኤሌክትሪካልና የብረታ ብረት ገጠማው የስራ አፈጻጸም ከ91 በመቶ በላይ ደርሷል።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ሁለተኛ ተርባይንን የሀይል ማመንጨትን ካስጀመሩ በኋላ ባስተላለፉት ጥልቅና ወካይ መልዕክት፤” በታሪክ ውስጥ ማለፍና ታሪክ ሠርቶ ማለፍ የሚባሉ ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ በታሪክ ውስጥ ማለፍ ዕድል፣ ታሪክ ሠርቶ ማለፍ ግን ዕድልም ድልም ነው፡፡ ይሄ ትውልድ በዓባይ ግድብ ጉዳይ ባለ ዕድልም ባለ ድልም ነው፡፡ የሺ ትውልድ ጥያቄ በሚመለስበት ዘመን ተገኝቶ ግድቡ ሲገደብ በዓይን ማየት፣ በእጅ መዳሰስ፣ በእግር መርገጥ ባለ ዕድል ሲያደርግ፤ ለግንባታው ገንዘባቸውን፣ ዕውቀታቸውንና ጉልበታቸውን ከለገሡት፣ በዲፕሎማሲና በሚዲያ ለዓባይ ከሚከራከሩት፣ ታሪክ ሠሪ ጀግኖች ወገን መሆን ደግሞ ባለ ድል ያደርጋል፡፡
እነሆ አሁን የሕዳሴ ግድብ ከንድፍ አልፎ፣ ግንባታው ተገባድዶ፣ ግዙፍ ውኃ በጉያው ይዞ ኃይል ማመንጨት ጀምሯል። ዛሬ ዓባይ ተረት ሳይሆን የሚጨበጥ እውነት ነው፤ ከዘፈን-እንጉርጉሮ ወጥቶ ኢትዮጵያን በብርሃኑ ሊያደምቃት፣ ኃይል ሆኖ ሊያበረታት ከጫፍ ደርሷል። በፈጣሪ ርዳታና በኢትዮጵያዊ ወኔ ሙሉ በሙሉ ግንባታውን አጠናቅቀን የልባችን እንደሚሞላ አልጠራጠርም። እንኳን ደስ ያለን!!”ብለዋል።
የመጀመሪያውን የውሃ ሙሌት ሐምሌ 15 ቀን 2012 ዓ.ም 4 ነጥብ 9 ቢሊዮን ሜትር ኩብ ውሃ እንዲይዝ አድርገዋል። ሁለተኛው የውሃ ሙሌት ደግሞ ባለፈው ሐምሌ 12 ቀን 2013 ዓ.ም 13 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትር ኩብ ውሃ በመያዝ ተጠናቋል። ይህ አገራዊ ግዙፍ የብርሃን እሸት የምስራች እንካችሁ ብሏል። ካለፈው የካቲት 13 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በአንድ ተርባይን ብቻ 275 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት ጀምሯል። የሁለተኛው ተርባይን ደግሞ 275 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት ጀምሯል። ሶስተኛው የውሃ ሙሊት ደግሞ ተጠናቋል። ግድቡ የያዘው የውሃ መጠንም ወደ 22 ቢሊየን ሜትር ኩብ አድጓል። የቀሪዎቹ ተርባይኖች ገጠማ፤ የግድቡ ግንባታና የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎችም በአንድ ዓመት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።
በክቡር ጠቅላይ ሚንስትር አመራር ግድቡ ገጥመውት የነበሩ ስር የሰደዱ ብልሹ አሰራሮች፣ ሙስናና ደካማ የኮንትራት አስተዳደር ተለይተው የእርምት እርምጃ መወሰዱ ታላቁን የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ከክሽፈትና ውድቀት ታድጓል። ለኢትዮጵያውያን እራትም መብራትም የመሆን ተስፋውን ሁለት ተርባይኖችን በማንቀሳቀስ ወደ ሚጨበጥ እውነት ተቀይሯል፡፡ ሌሎች ተርባይኖችን ወደ ስራ ለማስገባትም በከፍተኛ ትጋት እየተሰራ ይገኛል፡፡
ይሄ የአገር ተስፋ እውን እንዳይሆን ግብጽ በራሷ ብቻ ሳይሆን ከቅርብም ከሩቅም ያሉ ወዳጆቿን በማስተባበር ከፍ ያለ ጫና ለማድረስ ሞክራለች፤ የተፋሰሱን አገራት ጉዳይ ከአህጉር አልፎ ዓለማቀፍ አጀንዳ ለማድረግም ብዙ ለፍታለች፡፡ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ጉዳዮች አፍሪካዊ መፍትሄ የሚል መርሆዋ ወደ ድል እያራመዳት መሆኑን ስትገነዘብ ደግሞ የዓባይ ግድብን ጉዳዩን ከአፍሪካ ሕብረት በማውጣት ወደ መንግስታቱ ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳነት ለማሳደግ ያደረገችው ጥረት አገራችን በጥብቅ ዲፕሎማሲያዊ ዲስፕሊንና በጥበብ በተመራ አለማቀፍ ግንኙነት አገራትን ከጎኗ በማሰለፍ የተደገሰላት ደባ እንዲከሽፍ ከማድረጓ ባሻገር የግድቡ ጉዳይ የተፋሰሱ አገራትና የአፍሪካ ሕብረት እንጂ የመንግስታቱ ድርጅት አለመሆኑን ማረጋገጥ ችላለች።
ድርድሩም ለሁለተኛ ጊዜ ወደ አፍሪካ ሕብረት ተመልሷል። ምንም እንኳ ግብጽና ሱዳን ሰበብ አስባብ እየደረደሩና ፍላጎታቸውን በሌላ መንገድ ለማራመድ ላይ ታች እያሉ ቢሆንም። ጣልቃ ለመግባት አሰፍስፈው የነበሩ ምዕራባውያንም እርማቸውን እንዲያወጡ አድርጋለች። ሆኖም ዛሬም ሆነ ጥንት ግብፅ አልተኛችልንም። አባይን ከመነሻው ለመቆጣጠር ከ11 ጊዜ በላይ ልትወረን ልታስገብረንና ቅኝ ልትገዛን ሞክራ እንዳልተሳካላት የታሪክ ድርሳናት ያትታሉ።
ግድቡ በአሁኑ ሰዓት ከ22 ቢሊዮን ሜትር ኩብ በላይ ውሃ በመያዝ ራሱን መከላከል የሚችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል። ግብፅ ለዘመናት ኢትዮጵያ ሰላም ሆና አንድነቷ የሚጠናከርና ልማቷም የሚፋጠን ከሆነ አባይን ጨምሮ ገና የውሃ ሀብቷን ታለማለች በሚል በስጋት ላይ ያነጣጠረ ስጋት ከውስጥ ተላላኪዎቿ ጋር በመሆን ኢትዮጵያውያንን ለመበታተን ሰርታለች። ሆኖም የግብፅና የተላላኪዎቿ የቀን ቅዠት በጀግኖች ልጆቿ ይመክናል። እየመከነም ይገኛል።
አይደለም ዛሬ ሶስተኛ ዙር ግድባችንን ሞልተን፣ ሁለተኛ የብርሃን እሸት ቀምሰን፤ ያለአንዳች ኮሽታ ብሔራዊ ምርጫ አካሂደንና በሚያስገርም ሁኔታ በአገራችን ተደቅኖ የነበረን ቀውስ ቀልብሰን፤ ከአራት ዓመት በፊት በሴራ ፖለቲካ፣ በተላላኪዎችና በባንዳዎች ደባ በየእለቱ ቅርጹንና ይዘቱ እየቀያየረ በሚቀፈቀፍ ቀውስ መሀል ሆነን የጀመርነው አንደኛው የውሃ ሙሌት ዛሬ 3ኛ ዙር ደርሷል ። ከዚህ በኋላ የሚቀሩን ሙሌቶችም ያለ ምንም ስጋት ይከናወናሉ። በዚህም ቅኝ ካለመገዛት ጋር ብቻ ተያይዞ የነበረውን ነጻነትና ሉዓላዊነት በኢኮኖሚያዊ በብልፅግና ለመድገም ጉዞዋን ጀምራለች። በድህነትና በተመፅዋችነት አንገታቸውን ደፍተው የነበሩ ዜጎች አንገታቸውን ቀና አድርገው በኩራት እንዲራመዱ የሚያደርግ ብሔራዊ (ፍላግሺፕ) ፕሮጀክት ባለቤት መሆን ችላለች።
ነጋድራስ ገብረህይወት ባይከዳኝ እንዳሉት በድህነትና በኋላ ቀርነት የሚማቅቅ ሕዝብ የተሟላ ሉዓላዊነት ሊኖረው አይችልምና። ስንዴ እየለመኑ፣ እየተመጸወቱ ሉዓላዊነቷን ያላስደፈረች፤ በነጻነት ታፍራና ተከብራ የኖረች ብሎ መመጻደቅን ድሉን ሙሉኡ አያደርገውም። ሆኖም መጀመሪያ ሁለተኛውና ሶስተኛው የሕዳሴው ግድብ ውሃ ሙሊት፤ አሁን ደግሞ 2ኛው ዩኒት ኃይል ማመንጨት መጀመሩ የቀጣናውን ጂኦፖለቲክስ እንደ አዲስ በይኖታል። የግብፅን የውሃ ዲፕሎማሲና ፖለቲካም ከንቱ አድርጎታል።
ሻሎም ! አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 28/2015