የመነሻ ሃሳብ፤
በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ የመጋቢት 17 ቀን 2015 ዓ.ም እትም ላይ አንድ ዜና ወደ አንባቢያን ደርሶ ነበር። የዜናው ርእስ፤ “በኢትዮጵያ ለእርሻ ከሚውለው መሬት ሰባ ሚሊዮን ሄክታሩ አሲዳማ ነው” የሚል ነበር። በዜናው ዝርዝር ሃሳብ ውስጥ “አራት ሚሊዮን ሄክታር አሲዳማ መሬት ምርት ለማምረት የማይቻልበት ደረጃ ላይ መድረሱ” በሚገባ ተሰምሮበታል።
በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት ዘርፍ የአፈር ሀብት ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ አማካይነት የተገለጸው ይሄ ሀገራዊ እውነታ ለሙያው ቅርበት ባላቸው፣ በአስፈጻሚና በፈጻሚ ተቋማት ባለሙያዎች ዘንድ ብቻ ሳይሆን ከአፈር ጋር ተቆራኝቶ ለሚያኖረን ባለውለታ ለአርሶ አደሩና ለመላው የሀገሪቱ ዜጎች ጭምር ጉዳዩ በእጅጉ ማሳሰቡ የሚቀር አይደለም። ሚሊዮን ርሃብተኞች በሚገኙባት ሀገር በሚሊዮን የሚቆጠር ሄክታር መሬት ታማሚና መካን ሲሆን ያሳስባል፤ ያስጨንቃልም።
ይበልጥ በሥጋት የልባችንን ትርታ እንዲጨምር ከሚያደርጉት የሥራ ኃላፊው ገለጻዎች መካከል የሚከተሉት መደምደሚያዎች በእጅጉ በሀገራዊ ተስፋ ችን ላይ ጥላቸውን አክብደውብናል። አንደኛ፡- ኢትዮጵያ ማግኘት ካለባት ምርት ግማሹን እያጣች ነው። መሬቱ ቢታከም ኖሮ ሀገሪቱ አሁን ከምታመርተው ምርት ከሃምሳ እስከ መቶ በመቶ እጥፍ ምርት ማምረት ትችላለች።
” ሁለት፡- “በአሲዳማነት ከተጠቃው አፈር ሕክምና የተሰጠው ሦስት በመቶ ብቻ ነው።” ሦስት፡- “አንድ ሄክታር አሲዳማ መሬት ለማከም በትንሹ 30 ኩንታል ኖራ ያስፈልጋል። ይህ 30 ኩንታል ኖራ በግዥ ይቀረብ ቢባል እንኳን ከ30 ሺህ ብር በላይ ይጠይቃል። ሰፋ ተደርጎ አሲዳማ መሬቱን አክሞ ጤንነቱን ለመመለስ በጠቅላላው እስከ 45 ቢሊዮን ብር በጀት ይጠይቃል።” ኃላፊው በዝርዝር የገለጹልን ሪፖርት ነው።
በመሠረቱ ኢኮኖሚዋን በግብርና ዘርፍ ላይ አንተርሳ ለምትኖረውና ህልውናዋ ከአፈር ጋር ለተቆራኘው ሀገራችን ይህ ዜና አሳሳቢ ተብሎ ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በዘርፉ ባለሙያዎች፣ በባለጉዳዩ ሚኒስቴር መ/ቤትና በመላው ዜጎች ዘንድ “የመፍትሔ ያለህ” እየተባለ የሚጮኽበት ዋና ሀገራዊ አጀንዳ ሊሆን በተገባ ነበር።
ይህንን ዜና ያነበቡና ከተለያየ የመረጃ ምንጮች ያዳመጡ የዘርፉ ባለሙያዎች ወይንም ቀደም ብለው “ምሥጢሩን” እያወቁ ዝምታን በመምረጥ “ዝም አይነቅዝም” የሚል የ“ዳተኝነት” መርህ የሚከተሉ ቀዳሚ ተጠያቂዎች ስለምን ተረጋግተው ሊቀመጡ እንደቻሉ የመጠየቅ መብት ያለው አስፈጻሚውና በተለይም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ እስካሁን ስለምን “ጆሮ ዳባ ልበስ” እንዳለ በካርዳችን ለሥልጣን ወንበር ያበቃናቸውን አባላቱን አምርረን እንሞግታቸዋለን። ከእነርሱ በላይ ከፍ ያለ አካል ካለም “ይግባኝ!” ብለን አቤቱታችንን እናቀርባለን።
ሀገሪቱ ልታመርት የምትችለውን ሃምሳ ከመቶ በረከት ያሳጣንን ይህንን “የተፈጥሮ መርገምት” ስለምን ኢትዮጵያ እንኮኮ ብላ ተሸክማ እንደኖረች ችግሩ ተፍረጥርጦ ሊገለጽልን ይገባል። ምናልባት በተጫነን ሀገራዊ “አዚም” ተሸንፈን የችግሩ ክብደት አልተሰማን ከሆነም ብንመክርበት አይከፋም። በብዙ ሀገራዊ ችግሮቻችን ምክንያት “ድባቴ” ውስጥ ወድቀን የማሸለባችን ውጤት ከሆነም “አእምሯችን ውስጥ ያለውን የተስፋ መቁረጥ ብጉንጅ አፍርጠን” ልንፈወስ ይገባል።
“ሀገራዊ ድባቴያችን” ወሰኑ ይህ ልኩ የሚባል ብቻ ሳይሆን ከእኛ የሚፎካከር ሀገር ስለመኖሩም እርግጠኞች አይደለንም። የኑሮ ውድነቱ ከደመና በላይ ከፍ ብሎ ቁልቁል ተጭኖ “እህህ” እያልን ነው። የፖለቲካው ጡዘት ናላችንን አዙሮ ሲያጥወለውለን “የባሰ አታምጣ” ከማለት ውጭ ምንም አልፈየድንም። ማህበራዊ መስተጋብራችን ውሉ ጠፍቶበት ሲጎለጎል እያስተዋልን “ክፉ ቀንና ቅዝምዝም የሚታለፈው ጎንበስ ተብሎ ነው” በሚለው ፈሊጥ ራሳችንን አስክነናል። በኤሎሄ ጩኸት ወደ ጸባኦት እየቃተትንም “ነገም ሌላ ቀን ነው” በማለት በተስፋ በመኮራመት ከጣሪያችን በታች ተሰባሰብን ቀንን እንገፋ ካልሆነ በስተቀር እየተወራጨን አልተንፈራገጥንም።
ስለዚህ፡- አፈራችን ለበደነበት የአሲዳምነት አደጋም “ዘጠኝ ሞት መጣ ቢሉት አንዱን ግባ በለው” እንዳለው መከራኛ ዜጋ በድባቴ ውስጥ ብንሆን ላይፈረድብን ይችል ይሆናል። ምናልባትም ያንን ዜና እንደ ወትሮ የእለት ክስተት ቆጥረን ማለፋችን ስለዚሁ ይሆን ወይ ብለን ብንጠይቅ ፖለቲካውንና ፖለቲከኞችን የምናስከፋ አይመስለንም። ለማንኛውም መነሻ ሃሳባችንን በዚህ የማጠቃለያ ሃሳብ “በልጥ አስረነው” (ትኩረት ቢሰጠውም ባይሰጠውም ለማለት ነው) “የምሥጢረ አፈርን” ነገረ ጉዳይ ከግብርናና ከኢኮኖሚ ጉዳይ ነጠል አድርገን ሌሎች “አፈር ጠቀስ” ጉዳዮችን በማስታወስ የጠነነውን ርእሰ ጉዳይ ለማለዘብ እንሞክራለን።
«አፈር እንደ ዋዛ»
ይህ ንዑስ ርእስ ይህንን ጸሐፊ ለአንድ ሀገር አቀፍ ሽልማት አብቅቶት እንደነበር ለኩራት ሳይሆን ለትዝታ ያህል ማስታወሱ ቦታው እንደሆነ ያምናል። በ1978 ዓ.ም የባህል ሚኒስቴር አዘጋጅቶ በነበረው ሀገር አቀፍ የሥነ ጽሑፍ ውድድር በአጭር ልቦለድ ዘርፍ ያሸነፈው ይህ አምደኛ ተወዳድሮ የሁለተኛ ደረጃ ማእረግ ያገኘበት “አፈር እንደ ዋዛ” በሚል ርእስ ያዘጋጀው ጽሑፍ ነበር። የርእሱ ውስት ከራስ ወደ ራስ መሆኑን ልብ ይሏል።
ከዚያ አሸናፊ ጽሑፍ መካከል ጥቂት ኃይለ ቃላትን እንዘክር። “ከሕጻንነቴ ጀምሮ እየተከተለ ያቃጭል የነበረው የአፈር አደራ በጉልምስና እድሜዬም መደውሉን አልተወም። ዋ! ለካንስ አፈራችን ኢትዮጵያችን ናት። ድንበሯን የጀግኖች አጥር ያጠረው። እናም ህልውናችን፣ አርማችን፣ ኩራታችን፣ እስትንፋሳችን፣ የብልጽግና መገኛ ሀብታችን (ብልጽግና የተጠቀሰው በዛሬ ይዘቱ እንዳልሆን ልብ ይሏል – ሆይ ጉድ ቃላትም ያስፈሩን ጀመር!?)፣ ሀብታችን፣ የአጽማችን ማረፊያ ርስታችን፣ ውርሳችን፣ ይህ እንደ ዋዛ የምንናየው አፈራችን ለካስ እኛነታችን ነውና? ሳላውቀው ሳናውቀው! አፈር ቴክኖሎጂና ሳይንስ፣ አፈር ግብርና፣ አፈር ዳር ድንበር፣ አፈር፣ አ.ፈ.ር፣ አ-ፈ-ር…” “ስሞተኛውና ሌሎች አጫጭር ልቦለዶች፤ ዳግላስ ጴጥሮስ፤ ገጽ 38 – 51።)
«ምሥጢረ አፈር»
አፈር በርግጥም ምሥጢር ነው፤ ጥበብም ነው። ለዓለማችን ተመራማሪዎች ዕንቆቅልሽ ሆነው ከኖሩት “ድፍን ዕንቅላል” ከሚባሉ ርእሰ ጉዳዮች መካከል አንዱ አፈር ነክ ምሥጢር መሆኑም እርግጥ ነው። የዘርፉ ሳይንቲስቶች የምርምር ውጤት የሆነው ማረጋገጫ በራሳቸው ቋንቋ እንደሚከተለው ይነበባል።
“One teaspoon of topsoil contains around one billion individual microscopic cells and around 10,000 different species” ይገርማል። በአንድ የሻሂ ማንኪያ የሚዘገን አፈር በቢሊዮን የሚቆጠሩ “ፍጥረቶችን” አቅፎ ይዟል። የጥናት ውጤቱ ማጠቃለያም በተነጻጻሪነት እንዲህ ተድምድሟል። “One teaspoon of soil contains more living organisms than there are people in the world” (Capital coalition, August 31/2017):: እውነታው ይህ ብቻ አይደለም፤ ሦስት ሴንቲ ሜትር (አንዳንዶች አንድ ሴንቲ ሜትር ይላሉ) አፈር ለመፍጠር/ለመፈጠር (generating ይሉታል)1000 ዓመታትን እንደሚፈጅ ሳይንቲስቶች ግምታቸውን ሰጥተዋል።
አፈር እስከዚህ የከበረና ምሥጢር የተሸከመ የፈጣሪ ችሮታና ስጦታ ብቻ ሳይሆን ሌላም የገዘፈ ትርጉም አለው። እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት የሰው ልጅ ራሱ የተፈጠረው ከአፈር ነው። በፍጻሜውም ወደ አፈር መመለሱ እውነት ነው። ይህንን ማረጋገጫ ከሚሰጡን የቅዱሳት መጻሕፍት መካከል ጥቂት ጥቅሶችን እናስታውስ። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወትን እስትንፋስ እፍ አለበት፤ ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ። አፈር ነህና ወደ አፈርም ትመለሳለን ‹አለው›” (ዘፍጥረት 2፡7፣ 3፡19)።
በቅዱስ ቁርዓን ውስጥም በተመሳሳይ ይዘት ተገልጧል። “አላህ ሰውን ከአፈር ፈጠረው። ከዚያም ለርሱ (ሰው) “ኹን” አለው፤ ኾነም (ሱረቱ አል-ኢምራን 2፡59። ያ ሁሉንም ነገር አሳምሮ የፈጠረው፤ የሰውንም ልጅ አፈጣጠር ሂደት ከጭቃ የወጠነ (አምላክ) ነው። (ሱረቱ አል-ሰጃዳ 32፡7)”
አፈር የዚህን ያህል የላቀ ክብር ካለውና የሰው ልጆችም የተፈጠርነውና የተሸከምነው ገላ በአፈር የተለበጠ ማንነት ከሆነ ዘንድ ስለምን በሚሊዮን ሄክታር የሚቆጠረው የኢትዮጵያ የአፈር ፀጋ በአሲዳምነት ተፈርጆ ዘር እንዲያመክን ፈረድንበት? ስለምንስ ፈጣሪ በቸርነቱ ያደለንን አይተኬ ስጦታ አጣጥለን እንዳልባሌ ጉዳይ በቸልታና በግዴለሽነት እንክብካቤ ነፈግነው።
የመከነ አፈር የተለየ ክብካቤ ተደርጎበትና ታክሞ በቀጣይነትም በጎርፍ ከመሸርሸር ቢጠበቅና በእጽዋት ቢሸፈን መልሶ የማገገም ተስፋ እንዳለው የዘርፉ ተመራማሪዎች ያረጋግጣሉ። አፈራችን በተጠቀሰው ከፍተኛ ጉዳት ተጠቅቶ በአሲዳምነት ቢፈረጅም፤ ኢትዮጵያ በየክረምቱ በተከለቻቸውና ወደፊትም በምትተክላቸው በሚሊዮን በሚቆጠሩ የእጽዋት ችግኞችና ሰፋፊ የእርከን ሥራዎች ልትመሰገን ይገባል። ይህ ሀገራዊ ተፈጥሮን የመታደግ ርብርብ እየተሄደበት ባለው ፍጥነት የሚቀጥል ከሆነ የመከነው አፈራችን ተፈውሶ የበረከት ምንጭ እንደሚሆን ለማመን አይቸግርም።
ከአፈር ተፈጥሮ አፈር የተሸከመው ማንነታችን ሲፈተሽ፤
የሰው ዘር በሙሉ የተፈጠረው ከአፈር እንደሆነና የፍጥረት ሩጫውን ሲፈጽምም ወደ ወጣበት አፈር እንደሚመለስ በቅዱሳን መጻሕፍት እማኝነት ማረጋገጣችን ከላይ በዝርዝር ቀርቧል። ይህንን እውነታ መነሻ በማድረግም ማንነታችንን መፈተሹ ማስተዋል ስለሆነ በጥቂት ወሳኝ መሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ከራሳችን ጋር እንድንነጋገር ጸሐፊው ዳግላስ “እባካችሁ ሞክሩት” ብሎ ይማጸናል።
እያንዳንዳችን የተሸከምነው አፈር ለም ነው ወይንስ ዘር አምካኝ አሲዳም አፈር? ከተሸከምነው የአፈር ቁልል ውስጥ ምን ያህል መቶኛው ለሌሎች መልካም ፍሬ አፍርቶ ስንቶቹን ታደገ? በተለየ ምልከታ እድልና ጊዜ ተገጣጥሞላቸው የሕዝብ አገልጋይ የሆኑ ሹመኞች ምን ያህል ከአሲዳምነት ባህርይ ራሳቸውን ጠብቀዋል። ዘር ዘርተው ለዛሬውና ለነገው ትውልድ ፍሬ እንዲያፈሩበት በአደራ የተቀበሉት ሥልጣናቸውስ ምን ያህል ለምርታማነት አብቅቷቸዋል።
በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ገበሬና ዘር የሰጠው ድንቅ አስተማሪ ምሳሌያዊ ታሪክ (Parable) እዚህ ቦታ ቢጠቀስ ቦታው ይመስለናል። “እነሆ አንድ ገበሬ ዘር ሊዘራ ወጣ። ሲዘራም ሳለ አንዳንዱ ዘር መንገድ ዳር ወደቀ፣ ተረገጠም፣ የሰማይ ወፎችም በሉት። ሌላውም በጭንጫ መሬት ላይ ወደቀ፤ ጥልቅ መሬትም ስላልነበረው ወዲያው በቀለ፤ ፀሐይ በወጣ ጊዜ ግን ጠወለገ፤ ሥርም ስላልነበረው ደረቀ። ወፎችም መጥተው ለቅመው በሉት።
አንዳንዱ ዘር አፈሩ ስስ በሆነ ድንጋያማ መሬት ላይ ወደቀ፤ አፈሩ ስስ ስለሆነም ፈጥኖ በቀለ። ነገር ግን ፀሐይ ሲመታው ጠወለገ፤ ሥር ባለመስደዱም ደረቀ። አንዳንዱም ዘር በእሾህ መካከል ወደቀ፣ እሾሁም አደገና ቡቃያውን አንቆ አስቀረው። ሌላው ዘር ደግሞ በጥሩ ለም መሬት ላይ ወደቀ፤ ፍሬም አፈራ፤ አንዱ መቶ፣ አንዱ ስልሳ፣ አንዱም ሠላሳ ፍሬ ሰጠ። ሰሚ ጆሮ ያለው ይስማ!” (የማቴዎስ ወንጌል 13፡3 – 9)።
የዚህ ጽሑፍ ማጠቃለያም ይኸው ሃሳብ ነው። ቁጥራቸው ያነሰ ቢሆንም አንዳንድ ባለስልጣናት የተሸከሙት የሥልጣን ዘር በመልካም መሬት ላይ ስለተዘራ ቀን ከሌት ሕዝቡን በትጋት እያገለገሉ መልካም ፍሬ ሲያፈሩ እየተመለከትን ነው። ለእነዚህ ሹመኞች ያለን የምሥጋና ቃልና ማበረታቻ ነው። ተግተው በሥልጣን ወሰናቸው ዙሪያ በርካታ የተንዠረገጉ ፍሬዎችን እንዲያፈሩም ምኞታችን ነው።
አንዳንዶችም አሉ፡- በሾሃማው ልባቸው ላይ የሥልጣን ዘር ተዘርቶ ሕዝብን ሲያስለቅሱ ውለው የሚያድሩ። ለእነዚህ መሰሉ ሹመኞች ልብ ይስጣቸው ከማለት ውጭ ምንም ማለት አይቻልም። ሕዝቡን በጉቦና በመማለጃ፣ በሴራና በተንኮል በማስመረር የሥልጣን ዘመናቸውን በመፈጸም የተመኩበት ካባቸው ወልቆ ተራ ሰው የሆኑ እለት ማሕበረሰቡን የገረፉበት ጅራፍ እነርሱ ጀርባ ላይ እንደሚያርፍ ቢጠረጥሩ አይከፋም።
በአንዳንድ ድንጋይ ልብ ሹመኞች ላይ የተዘራው የሥልጣን ዘርም ያለ ውጤት “እከሌ” አሰኝቶ ከማስጠራቱ በዘለለ ፍሬ የማያፈሩ “ውሎ ገብ” የሚባሉ ዓይነቶች ናቸው። በተለይም የፖለቲካ ካድሬ የተሰኙት ቁጥራቸው የበዛ ነው። እነዚህ ሕዝብ በአግባቡ ከማስተዳደር ይልቅ በጭንጫና ደንዳና ልባቸው ሕዝብን የደም እምባ በማስነባት ውለው የሚገቡ ችግር ፈጣሪዎች “እርሶ ያሰኛቸው” ጀንበር ሲጠልቅና ተራ ሰው ሲሆኑ ከማሕበረሰቡ የሚገጥማቸውን አደጋ ከወዲሁ ገምተው ድንጋዩን ልባቸውን ወደ ሥጋ ልብነት ቢለውጡ ይበጃቸው ይመስለናል።
ለሕዝብ ኖረው ለሕዝብ እስከ መሞት የጨከኑና መንግሥታዊ ሥልጣናቸው በለም ልባቸውና መንፈሳቸው ላይ የተዘራባቸውን ትጉሆችና ታታሪዎችን ደግመን እናመስግን። እነዚህ ሹመታቸው እንደ ሺህ ሞት የሚያስፈራቸው የሕዝብ ልጆች ቁጥራቸው አነስተኛ ቢሆንም በፍሬያቸው እየመዘንናቸውና በየሥራ መስካችንና በየጓዳችን እያደነቅናቸው ስንባርካቸው መዋላችን አልቀረም።
በመቶ፣ በስልሳ፣ በሰላሳ እጥፍ የሚቆጠረው ፍሬያቸውም በራሱ መዓዛው ከሩቅ መጣራቱ አልቀረም። ለኢትዮጵያ የምንመኘው እንደነዚህ ዓይነቶቹን ለሕዝብ የተሰጡ “የወርቃማ” ፍሬ ባለጸጎችን ነው። እንደነዚህ አይነት ባለሥልጣናት ከበዙልን “አሲዳም አፈር የተሸከሙቱ” እየከሰሙ ስለሚሄዱ ተስፋችን ይለመልማል። “ጆሮ ያለው ይስማ!” አዋጅን ደግመን በማወጅ ለሕዝባችን ሰላምን ለዜጎችም በጎ ፈቃድን እንመኛለን። የመከነው ሀገራዊ አፈራችንም ሆነ የተሸከምነው የማንነታችን ቁልል አፈር ሁለቱም ለፍሬ ይብቁልን። ሰላም!
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ) gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 7 ቀን 2015 ዓ.ም