አሁን ላይ ተደጋግሞ ከምንሰማቸው ንግግሮች መካከል ‹‹ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ›› የሚለውን ሃሳብ ነው:: አባቶቻችን ‹‹የአገሩን ሰርዶ በአገሩ በሬ›› ማለታቸው ለዚሁ ነው:: ለራሳችን ችግር ሁነኛ የመፍትሔ ራሳችን ነን:: እኛ ኢትዮጵያውያን ሁልጊዜም የራሳችንን ችግሮች በራሳችን ተደጋግፈን የምንፈታ ቢሆንም በአፅዋማት ወቅቶች ግን የሚደረጉ መደጋጋፎች በአይነታቸው የተለዩ ናቸው::
በጾም ወቅቶች እርስ በርስ ከመደጋጋፍ አንጻር እኛ ኢትዮጵያውያን ስንተግብረው የኖርነው ሁነኛ መታወቂያችን ነው:: ተደጋግፈን ዓመታትን ብሎም ዘመናትን ኖረናል፤ ተሻግረናልም:: ዘመነኛ የሆነው የዘመኑ ትውልድ አባቶቹ ያቆዩትን የራስን ችግር በራስ የመፍታት እና የመተባባር እሴቶችን ከመተግበር አንጻር የተወሰኑ ዙሪያ ክፍተቶች ቢኖሩበትም አሁንም ከአባቶቹ የተማራቸውን አገር በቀል እውቀቶች እና እሴቶች እያስቀጠለ ይገኛል::
በቀደመው ጊዜ የነበሩን እሴቶቻችን እና አገር በቀል እውቀቶቻችን ለመሸርሸራቸው ምክንያት ለማወቅ ጥናት የሚጠይቅ ቢሆንም በእኔ ግምት ግን አንዱ እና ዋነኛው ምክንያት የአሁኑ ትውልድ አብዛኛዎቹን የአባቶችን የቀደመ ገድሎች የሚሰማው በተጨባጭ ሳይሆን በአፈ ታሪክ እና በተረትተረት ብቻ መሆኑ ይመስለኛል::
ብናውቅበት እንደ አገር ለችግሮቻችን መፍትሔ የምንሰጥባቸው የራሳችን መገለጫ የሆኑ በርካታ አማራጮች ያሉን ሕዝቦች ነበርን:: ከእነዚህ አማራጮች ውስጥ በሕይወት ኖረንባቸው ጭምር ለሌሎች ምሳሌ ሆነናል:: ለዚህም በአፅዋማቶቻችን ወቅት የምናደርገውን አንዳንዱን ተግባራት በቂ ማሳያዎች ናቸው:: እንቅስቃሴዎቻችን ሁሉ በጥበብ ተለክተው በጥበብ የተቆረጡ ናቸው::
የበርካታ የምዕራባውያን የስልጣኔ መነሻዎች የእኛ አገር በቀል እውቀቶች እና እሴቶች ሆነው ሳለ የአሁኑ ትውልድ ይህን አምኖ ለመቀበል ሲቸገር ይታያል:: በቀደመው ጊዜ፣ በተለይ በጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ለራሳችን ችግር መፍትሔው ራሳችን ከመሆን አልፈን ለሌላው ዓለም ሁሉ ስንተርፍ ስለ መኖራችን ከበቂ በላይ ማስረጃዎቹ ቢኖሩንም ነጮች ስላልነገረን ብቻ አምነን መቀበል ግን አንፈልግም:: ይህ ትክክል አይደለም! ሊታረም ይገባዋል::
በነገራችን ላይ ባህላዊ አልባሳቶቻችን፣አመጋገባችን፣ የባህላዊ ህክምና አሰጣጣችን፤ ግጭት አወጋገድ ዘዴአችን እና ሌሎች ተዝቀው የማያልቁ አገር በቀል እሴቶቻችን እኛ ኢትዮጵያውያን ትላንት ማን እንደነበርን ለዓለም ህዝብ በተግባር ተገልጠን የታየንበት ነው::
ያኔ ለሚያስፈልጉን ጉዳዮች ሁሉ መፍትሔዎቹ ራሳችን ሆነን ችግሮቻችንን አስወግደናቸዋል:: ህመሞቻችንን አክመናቸዋል:: ተግባራቸውን ተዋደንባቸዋል፤ አለህልኝ፤ አለሽልኝ ተባብለንባቸዋል::
እኛ የብዙ ችግሮች መፍቻ ቁልፍ ባለቤቶች ነበርን:: በአርምሞ እንጂ በንግግር፣ በተግባር እንጂ በዝርዝር ሊገልጹን የማንቻል ብዙ ነገር ያለን:: ቅይጥ ያሉ ሰበዞች የሰፏት ሞሶብ፣ ዓይነት ብዙ ድርና ማጎች የሸመኗት ጋቢ ነን:: ልዩ ልዩ ቅመሞች የሠሯት ወጥ፣ ብዙ ገባሮች የፈጠሯት ዓባይም እንደኛ ያለ ማንም የለም::
ብዙ ትውልዶች የከመሯት ተራራ፣ ከአራቱ አቅጣጫ ተሰብስቦ በአንድ ወፍጮ የተፈጨች እህል ነን:: በአንድነታችን የምንደምቅ፤ በልዩነታችን ህብረብሔራዊነትን የምናጸባርቅም እኛ ብቻ ነን:: ውበታችን በልዩነት ውስጥ ሳይሆን በአንድነት ውስጥ የሚያበራልን ነው:: ለዚህ አንድ አብነት ብናነሳ የጾም ወቅት በሙስሊሙም ሆነ ክርስቲያኑ ማህበረሰብ ዘንድ ሲጾም ከምግብ መከልከል ብቻ አይደለም፤ ክፉ ከመናገርና ከመተግበር የሚከለክል ነው::
ጾም ከሚያስገኘው መንፈሳዊ በረከት በተጨማሪ ለአካላዊ ጤንነት የሚሰጠው ጠቀሜታ አለው። የመጀመሪያው ሰውነታችን መቼ ምን ማግኘት እንዳለበት የሚነግረን ነው:: ምን መብላት እንዳለብን ትኩረት እንድናደርግም ያስችለናል። ሁለተኛው ክብደታችንን መቆጣጠርና፣ የካሎሪ መጠን መወሰን ስለሚያስችል ነው። ይሁንና ዋና ትኩረታችን የጾምን ጥቅም ማብራራት ሳይሆን ችግሮችን አብሮ መፍታት በመሆኑ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ:: ይህም የጾም ወቅት መልካም ተግባር ሲሆን፤ አንዱ ደግሞ ምጽዋት በሙስሊሙ አጠራር ደግሞ ሰደቃ ነው:: ይህንን በክርስትናው ስናነሳው ዓብይ ጾም ላይ ነንና ሳምንታቱ የተለየ ትርጓሜ ተሰጥቷቸው ለተቸገሩ ሁሉም ሰው ይደርስባቸዋል:: የመልካም ሥራ ማድረጊያ ቀናት ተደርገውም ይወሰዳሉ::
መመጽወት አንዱ የጾም አካል ነውና እንደግዴታም ተደርጎ ይወሰዳል:: ስለዚህም በክርስትናው ወራቱ በሙሉ የመስጠት ጊዜ ናቸው:: ወደ እስልምናው ስንገባም ይኸው ጉዳይ ይቀጥላል:: አሁን የገባው የረመዳን ጾም ደግሞ ለዚህ ምስክራችን ይሆናል:: ይህ ወቅት ለእስልምና እምነት ተከታዮች በረከት የሚታፈስበት ነው:: ምክንያቱም በሰደቃ የነፍስ ስንቅን ይሰንቃሉ::
ሰደቃ (ምጽዋት) የግዴታ አይደለም በበጎ ፈቃድ የሚተገበር መልካም ሥራ ነው:: የግዴታ ሲሆን በዘካ መልኩ ያደርጉታል:: ይህ ማለት ዘካ የኛ ሳይሆን የድሆች ገንዘብ ነው፤ የሀብታሞች የኑሮ መሰረት ደግሞ ድሆች ናቸው:: ስለዚህም የእነርሱን ገንዘብ መከልከል አይቻልም:: አንድ ሰው ይህንን ካደረገ ድርቅ ይመጣል፣ ዝናብ ይቀራል፣ አገር ይራባል ተብሎ ይታመናል:: በመሆኑም ለአገር፣ ለራስ በረከት ለማምጣት ሲባል ይህንን የማያወጣ ሰው አይኖርም:: ወደ ሌላኛውና በጎ ፈቃዱ ስንገባ ደግሞ መልካም ንግግር፣ ሰዎችን በሀሳብም፣ በገንዘብም ሆነ በጉልበት ማገዝ፣ የተጣሉትን ማስታረቅ የሚሉት ይካተታሉ::
የተራበን ሰው ያበላውን አላህ ነገ ከጀነት ፍሬ ያበላዋል:: የተጠማውን ያጠጣዋል:: የታረዘን ያለበሰውን ከጀነት ልብስ ያለብሰዋል:: የሰደቃ ጥቅሙ በዚህም ሆነ በመጨረሻው ዓለም ሰፊ ነው:: ለሰጭው ውስጣዊ እርካታ ሲሆን ለተቀባዩም ትልቅ ጥቅም አለው ተብሎ ይታመናልና በጾም ወቅት የሚተገበር ነው::
ሰደቃ መከራን ትመልሳለች፣ ችግርን ታስወግዳለች፣ እሳትን ታጠፋለች:: ሰደቃ ለብዙ ግላዊም ሆነ ማህበራዊ ችግሮቻችንና በሽታዎቻችን የታዘዘች ልዩና ዓይነተኛ መድኃኒት ናት:: የደረቀ ቀልባችን ይለስልስ ዘንድ ወላጅ አጥ የሆኑ ልጆችን ራስ እናብስ:: በሽተኞቻችንን ሰደቃ መስጠት በማብዛት እናክም:: የምጽዋት ትንሽ የለውም:: ምክንያቱም የአንድን ሰው ሰደቃ ያሳድጋትና ትልቅ ምንዳ ይሰጠዋል ተብሎም በሕዝበ ሙስሊሙ ዘንድ ይታመናል:: ይህ ታዲያ ከምን ይታደጋል ከተባለ መልሱ ቀላል ነው:: እንደሚታወቀው ይህ ወቅት ሁሉም በችግር ላይ ችግር የተደራረበበት ነው::
ችግር በተደቀነበት ጊዜ ሃይማኖት ተገን ሆኖ፤ መፍትሔ አመላካቾች ችግሮችን የሚፈታባት አገር ብትኖር ኢትዮጵያ ናት:: ታዲያ ለምን የአገራችንን ችግር በአገራችን መፍትሔ ማስቀጠል አቃተን ከተባለ መልሱ ቀላል ነው:: እኛነታችንን ያለመቀበላችን ሁኔታ ይመስለኛል::
ሰው መጀመሪያ በራሱ እምነት ካለው መጀመሪያ ችግሩን ለመፍታት የሚነሳው ከቤቱ ነው:: ማንም ችግሩን ሳይሰማበትም ነገሮችን አልጋ በአልጋ ማድረግ ይቻላል:: ሆኖም በራሱ የማይተማመን ከሆነ ግን ገና ያልተተገበረውን ሀሳቡን ሳይቀር ይበትነውና ለሌሎች መወጣጫ ይሆናል:: ሀሳቡ ተቀምቶበትም ባዶ እጁን አጨብጭቦ ይቀራል:: እንደ አገር እየሆነም ያለው ይህ ይመስለኛል:: የእኛ የሆነ ብዙ ነገር አለን:: ግን የሌሎች አገራት ማንነት ይናፍቀናል:: ሳንሰራና ያለንን ሳንጠቀምበት በዓይናችን መስረቅ ብቻ ላይ ተጠምደናል:: እርሱ ብቻ አይደለም ለአገሩ የሚሰራ ስናይም ያመናል:: ለመጣል የማንቆፍረው ድንጋይ አይኖርም::
ባህል አክባሪው፤ ሃይማኖቱን ጠባቂው፤ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት ለማልማት የሚጥረውን ከዚህ ውጣልኝ፤ እዚህ ማልማትና መኖር አትችልም ማለት ከጀመርንም ሰነባብተናል:: ይህ ደግሞ ‹‹ …. አሳይተህ ጭብጦውን ቀማው›› ለሚሉ አገራት መንገድ ጠራጊ ነው:: እኛን አባልተው እነርሱ የሚጠቀሙበትን ስርዓት ይዘረጋሉ:: ከየአበባው ተቀስማ በአንድ ቀፎ የተሠራችውን ማር አገራችንን እኛ ሳንጠቀምባት እነርሱ መጠው መጠው ይጨርሷታል:: የሚያስተርፉልን ነገር እንኳን አይኖርም:: ምክንያቱም በሌሎች አገራት ላይ አድርገውት አይተናል::
ስለዚህም ከየእህሉ ተዋጥቶ በአንድ ማድጋ በመልካም ሴት የተጠመቀችውን ጠላ፣ ከየእንጨቱ ተለቅማ በአንድ ጽንሐ የታጠነችውን መልካም ሽቱ ያላት ዕጣን የሆነችውን አገራችንን ላለማስነጠቅ ያለንን አይተን በአንድነታችን ችግሮቻችንን ልንፈታ ይገባል:: ቁልፋችን ብዙውን ነገር የሚፈታ ነውና ከመዛጉና ከመጣሉ በፊት እንጠቀምበት በማለት ሀሳቤ እቋጫለሁ:: ሰላም!!
ክብረ ነገስት
አዲስ ዘመን መጋቢት 26 ቀን 2015 ዓ.ም