በየዘመናት ቅብበሎሽ፣ በየትውልዱ ዕድሜ ሁሉ ስለ ዓባይ ወንዝ ያልተባለ ያልተነገረ የለም። ጸሐፊያን በድርሰታቸው ፣ ከያኔያን በመድረካቸው፣ ሰዓሊያን በብሩሻቸው ስለዓባይ እልፍ ጉዳይን አንስተዋል። አባይ የታላቅነቱን ያህል ‹‹ውለታ ቢስ ነው›› ያሉ ወገኖች ደግሞ በስሙ ሲወቅሱት፣ ሲያዝኑበት ሲናደዱበት ኖረዋል።
አንጡራ ሀብታቸውን ይዞ ‹‹እብስ›› ሲል በዓይናቸው ያዩ ለዓመታት በቁጭት፣ በትካዜ ሸኝተውታል። ዝምድናውን ያላመኑበት፣ ባዕድነቱን የመሰከሩለትም በየጊዜው ስንኝ ቋጥረው ፣ዜማ ቃኝተው ‹‹ተው ስማን›› ሲሉት ኖረዋል። ዓባይ ግን በወቀሳ ብቻ መንገዱን አልተወም ፣በኃዘን ትካዜ ብዛት ከመፍሰስ አልቆመም። ከዘመናት በፊት የጀመረውን ጉዞ፣ ያለመቋረጥ ቀጥሎ ዛሬ ድረስ አለ።
እሱ ክረምት ከበጋ፣ ሌት ተቀን፣ ለአፍታ ቆሞ አያውቅም። ለም አፈሩን፣ወፍራም ቀጭን ግንዱን፣ ዓሳ፣ እንስሳውን እንዳሳፈረ በረሀውን ያቋርጣል። ብዙዎች ግን ስለጆሮ አልባው ወንዝ ዝም ብለው አያውቁም። በክራር ፣መሰንቆው ፣ በከበሮ በገናው እያሞገሱ ይወቅሱታል። እየጣሉ ያነሱታል። ዓባይን፣ ሀገር አቋራጩን ፣ በረሀ አቋራጩን ታላቅ ወንዝ።
ዓባይ በዘመናት ጉዞው ሲወደስም ሲወቀስም ኖሯል። ይህ እውነት ደግሞ በግጥም፣ በዜማው፣በአዝማሪ ጨዋታውና በእረኞች ውሎ ሁሉ ሲንጸባረቅ የኖረ ነው። ስለዓባይ ያገር አድባርነት፣ ያለጥሪት ያለአሻራ ዟሪነት ከጥንት እስከዛሬ ያልተባለ የለም።
ዓባይ፣ ዓባይ፣ ዓባይ ፣ ዓባይ
ያገር አድባር፣ የሀገር ሲሳይ
ያለሀገሩ ዘምሮ ፣ ያለወንዙ ገብሮ
ዓባይ ያለአሻራ ኑሮ።
ስለዓባይ ታላቅነት ያዜሙ በርካቶች ናቸው። የወቀሱት ፣ ያዘኑበትም እንዲሁ። ዓባይ ደግሞ የፍቅር፣ የታሪክ ተምሳሌት ጭምር ነው። በስሙ ተዚሞለታል። ስንኝ ተቋጥሮለታል፣ በረሀነቱን ለማሳየት፣ ኃያልነቱን ለመጠቆም ብዙዎች በራሳቸው አባባል ብዙ ብለውታል። ስለግዝፈት አስፈሪነቱ፣ አብረውት ስላሉት አውሬና ፍጥረታቱ ሁሉ ብዙ ተዘፍኖለታል። እንዲህ በሚል ማሳያ
የዓባይ ዳር ጉማሬ፣
ወጥቶ አደረ ዛሬ።
ባህሩን በታንኳ ሲቀዝፉ ብታይ
አረ ዓባይን በእግር ትገባለህ ወይ
ይሉትን ዜማ ያስታውሷል።
ወንዙን ተዋስኖ አገር ቆርጦ ለመሄድ፣ ዘመድ ወዳጅ አይቶ፣ጠይቆ ለመመለስ በዓባይ ሙላት ጊዜ አይሞከርም። ከጥጋቡ እስኪጎድል፣ ከመንገዱ እሰኪረጋጋ ዓይን ዓይኑን እያዩ መጠበቅ ግድ ይላል። ታዲያ የዛኔ አማራጭ ፍለጋን የባዘኑ መንገደኞች በዜማ፣ እንጉርጉሯቸው ስለዓባይ ወንዝ ሙላት እንዲህ ማለታቸው አይቀርም።
አባይም ቢሞላ ቢሞላ፣
መሻገሪያው ሌላ።
ዓባይም ሞላልሽ ሞላልሽ
ቀኑ ደረሰብሽ
ሌሎች የዓባይን መጉደል መታገስ ያቃታቸው ደግሞ የውስጥ ስሜታቸውን ፣ የከረመ ናፍቆታቸውን እንዲህ ሲሉ ይገልጹታል።
ዓባይ ጉደል ብለው አለኝ በታኅሣሥ፣
የማን ሆድ ይችላል እስከዛው ድረስ።
አንተ ወዲያ ማዶ፣እኔም ወዲያ ማዶ፣
አንገናኝም ወይ ተራራው ተንዶ።
ዓባይ ውሀ ሞልቶ ቁም ከልክሏል አሉ፣
በላይ አትመጣም ወይ እንደ እግዜሩ ሁሉ።
ዓባይ ጉደል ጉደል ቀጭን መንገድ አውጣ፣
የከፋው ወንድ ልጅ ተሻግሮ እንዲመጣ።
ዓባይን ተሻግሮ ዓባይ አለ ወይ፣
ሞትና መለየት አንድ አይደለም ወይ።
በዓባይ አቋርጠው፣ ወንዙን ተሻግረው የሚያልፉ ደግሞ ሁሌም የመንገዳቸውን ቀና መሆን አበክረው ይጠይቃሉ። እግረመንገድም የዓባይ መንገድ የፍቅራቸው፣የናፍቆታቸው ማሳያ ይሆናል። ይሁኔ በላይ በዜማው እንደቃኘው የዓባይ መንገድ ጉዞ።
የዓባይ ማዶ መንገድ ተሠራ ወይ፣
ጎጃም፣ጎንደር መንገድ አለቀ ወይ፣
ገስግሼ ልምጣ ወይ።
እንደ ዓባይ ጎዳና እንደጠመዝማዛው፣
ናፍቆትሽ ወዝውዞ ስቃዬን አበዛው።
ዓባይን ስለማንነቱ የወቀሱት፣ስለዕለት ግብሩ ያዘኑበት ቁጥራቸው ያይላል። በየዘመናቱ ስሙን እያነሱ፣ ግንድ ይዞ መዞሩን የሚነግሩት፣ የዘመድ ባዳ፣ የሰው አገር አገልጋይ እንደሆነ የሚጠቁሙት በርካቶች ናቸው። ድምፃዊት እጅግ አየሁ ሽባባው/ጂጂ/ ግን ስለአባይ ያላት እውነት ከሌሎች ይለያል።
ጂጂ ዓባይን በቁሙ አትወቅሰውም፣ በግልጽ አትዘልፈውም። የእሷ አተያይ ውበት ዕድሜው ላይ ያርፋል። ግርማ ሞገሱን ይቃኛል። የአገር ሲሳይነቱን ፣የሀገር ልብስነቱን፣ የገነት ውሀነቱን ያሳያል። ጂጂ በዜማዋ ዓባይን እንዲህ ብለዋለች።
የማያረጅ ውበት፣የማያልፍ ቁንጅና፣.
የማይደርቅ፣ የማይነጥፍ ለዘመን የጠና።
ከጥንት ፣ከጽንስ አዳም ገና ከፍጥረት፣
የፈሰሰ ውሀ ፈልቆ ከገነት።
ለጂጂ ዓባይ የሰው አገር ብቻ ሳይሆን የበረሀው ሲሳይ ጭምር ነው። ለዚህም ዓባይን ደጋግማ ‹‹የበረሀው ሲሳይ›› ትለዋለች። አለፍ ብላም ስለሱ ግድ ስለሚላቸው፣ወንዙ ሕይወት እስትንፋስ ስለሆናቸው ባዕዳን በስንኟ እንዲህ ገረፍ አድርጋ ትነግረናለች። በተለይ ግብጾችን።
የሚበሉት ውሀ ፣የሚጠጡት ውሀ፣
ዓባይ ለጋሲ ነው በዚያ በበረሀ።
ጂጂ ስለዓባይ ዕንቅልፍና ሰላም የሌላቸውን የጥቅም ተጋሪዎች ስሜት ሸንቆጥ ያደረገችበት ስንኝ ደግሞ እንዲህ ይደመጣል።
ብነካው ተነኩ፣አንገበገባቸው፣
መሆንህን ሳላውቅ ሥጋና ደማቸው።
ልክ እንደ ጂጂ ሁሉ የዓባይን እንክርዳድ ወዲያ ጥለው ገብስ ገብሱን ብቻ ያወሩለት አይጠፉም። እነሱ ስለዓባይ የሺህ ዓመታት ጉዞ ‹‹አበጀህ ፣ጎሽ ›› ሲሉ አያሞካሹትም። ለዘመናት ጥሪት ሀብታቸውን ለማጋዙ እማኞች ቢሆኑም ችግሩን በእኩል ይጋሩታል። ቀኑ ደርሶ ስደተኛውን ወንዝ ወደቤት አስኪመልሱት እንቅልፍ የላቸውም። ሁሌም እንደ ሰው ያዋዩታል፣ እንደወዳጅ ያማክሩታል። ይህ እስኪሆንም ቁጭታቸውን በዜማና ግጥም ይገልጹታል። እንደ ድምፃዊ አሸብር በላይ።
አንተ የሀገሬ ግርማ አንተ የሀገሬ ኩራት፣
እንደተጣላ ሰው ስትሸሽ ለዘመናት።
ሁሉም በጊዜው ነው ቅረብ እንተያይ፣
ዓባይ! ዓባይ! ዓባይ ! ዓባይ።
ድምጻዊ አሸብር ዓባይን እንደ ቅርብ ወዳጅ ባዋየበት ዜማው ዓባይ ከፍጥነት ሩጫው ተግ እንዲል፣ ከዘመናት ጉዞው እንዲታቀብ ይመክረዋል። ሕዝቡ ከእሱ ጉዳይ እንዳለው ፣ አጥብቆ እንደሚሻው ይነግረዋል። እንዲህ በሚል ቅኝት።
ዓባይ፣ዓባይ፣ዓባይ አባይ፣
ማን አለን ለኛ ከኛ በላይ፣
እስቲ ተግ በል አለን ጉዳይ።
ምድሩን አርሰው ገበሬው ይዝራ፣
ተምዘግዘግና ጨለማው ይብራ።
ድህነት ይውረድ ከላያችን ላይ፣
ይብቃው ቁጭቱ ወገኔ በዓባይ።
ክንድህን አሳየው ያገሬ ጀግና
ዓባይ ከወንዙ ላይ ቀጠሮ አለና፣
በል ነው ገና፣አረ ገና ገና፣
ዕድሜ ይሰጠን እንጂ እናያለን ገና።
ስለ ዓባይ የዘመናችን ዜማ ቅኝቶች የትናንቱ ቁጭት በሥራ ይተካ፣ያለፈው እንጉርጉሮ ይብቃ የሚል መልዕክት አላቸው ።
ዛሬ ያለፈው ታሪክ ሊቀየር ጊዜው ደርሷል። ለዘመናት እንደ ወንዙ የጎረፈው ዕንባ ሊታበስ፣ በለም አፈር ዝንቅ እንደ ደም የቀላው ውሀ ሊጠራ ቀን ወጥቷል። አሁን የዓባይ ዳር ጀምበር መልኳን ቀይራለች። እንደቀድሞው የዝምታ ኃዘን የላትም፣ በታላቁ ወንዝ እናት የምትፈልቀወ ደማቅ ጸሐይም ከላይ ሆና መታዘቧን ትታለች። የዘመናችን ዜማና ቅኝት ትርጓሜም መልካም ሆኗል። ኃዘን፣ ትካዜ፣ እንጉርጉሮ ይብቃ ፣ ክንዳችን ለህዳሴው ጉዞ ይጠንክር ፣ ይበርታ በሚል።
እንጉርጉሮ ይብቃ ይገባል ውዳሴ፣
ጉዞውን ጀምሯል ዓባይ በህዳሴ።
ትውልድ እንደ ጅረት የተቀባበለው፣
ቁጭት፣ጸጸት ስጋት ዛሬ ሊቋጭ ነው።
ዜመኞች ፣ ስለ ዓባይ ታላቅ ሕልማቸውን፣ ሀሳብ እቅዳቸውን ይወጥናሉ። በተባበሩ ክንዶች፣በዓባይ ወንዝ ትሩፋት ሀገር እንደምትቀና ታሪክ እንደሚለወጥ ይገልጻሉ። የፍቅር አዲስ ነቅዓጥበብና አበበ ብርሀኔ የጋራ ዜማ ምሳሌያችን ነው።
እንሂድ ወደ ዓባይ እንውጣ በደቦ፣
ወዴት ይደረሳል በአንድ በሬ ስቦ።
ተረባርቦ እንጂ ነው ትውልድን መቀጠል፣
መቼ ለምቶ ያውቃል አገር በተናጠል።
አንድም ሰው ሳንረሳ ሳይቀር ከኋላችን፣
አባይ ወደ አገሩ ወደ አንጀቱ ሲፈስ፣
ኢትዮጵያን ወረራት አንድ የአንድነት መንፈስ።
ኢትዮጵያን ህዳሴ ገና ጀማምሯታል፣
አፍሪካንም ገና ያጥለቀልቃታል።
እንሻገር በዓባይ ተያይዘን እጃችን፣
ከምኞት አልፈናል ከቃል ተሻግረናል፣
እንግዲህ ከዓባይ ጋር ሥራ ጀምረናል።
ይህ እውነቴ ቁጭት ሥጋና ደም ለብሶ ትውልድን ባነቃበት ዘመን የዓባይ ወንዝ ጉዳይ ዕንቅልፍ የሚነሳቸው ባዕዳን ለምን ማለታቸው አልቀረም። የእስከዛሬው ዕንቅልፍ አብዝቶ ይቀጥል ዘንድ ወፍራም ብርድልብስ ሊደርቡ የሚሹ ኃይሎች ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የህዳሴውን ጉዞ ለማደናቀፍ መጣራቸው አልቀረም። ታዋቂው ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን /ቴዲ አፍሮ/ ይህ ሩጫ የማይሆን ፣ የማይሞከር ሕልም ስለመሆኑ በተለየ ስሜት አቀንቅኗል። በዓባይ ጉዳይ ፈጽሞ ድርድር የለም ሲል።
ቼ! በለው አረ ቼ! በለው!
ቼ! በለው አባቱም ገዳይ ፣
ቼበለው!
እናቱም ገዳይ፣
ቼ! በለው
ድርድር አያውቅም፣
ቼ! በለው
በሀገሩ ጉዳይ።
ዓባይ የግሌን ባልኩኝ የጋራ፣
ካቃራት ምስር ፣
ግፍም ሳትፈራ።
የተቆጣ እንደው ፍቅር ታግሶ፣
የሚባላ እሳት ይሆናል ብሶ።
ማን ዝም ይላል ሆኖ ዜጋ፣
ደግሞ በዓባይ!
ድርድር የለም በአባይ ጉዳይ ።
እውነት ነው። ቴዲ እንዳለው እስከዛሬ ዓባይ አንጡራ ሀብታችንን ይዞ ወደ ባዕዳን ምድር ሲያቀና በትካዜ ከበር ቆመን ሸኝተነዋል። በራሳችን ለም አፈር ሀገረ ግብጽን ሲያለመልም እያየን ‹‹ዓባይ ማደሪያ የለው ግንድ ይዞ ይዞራል››ን ስንተርት ኖረናል። አሁን ግን ጊዜው ተለወጧል። ይህን ተረት በራሱ ጊዜ ተረት የሚያደርግ ትውልድ ክንዱን አጠንክሯል። በዓባይ ጉዳይ እንቅልፍ ለሚያጡት፣ አጥር ለሚነቀንቁት ሁሉ ቀልድና ድርድር አይኖርም።
ከዓመታት በፊት ድምጻዊት ገነት ማስረሻ በአንድ ዜማዋ ትንቢት ነው የሚያስብል እውነትን ነገረችን። ዓባይን ባሻገር እያስተዋለች ከልብ አዋየችው፣ ታላቁ ወንዝ ከሕዝቡ ቢያብር ቢስማማ ታሪክ እንደሚቀየር፣ ድህነት ይሉት ችግር እንደሚጠፋ ነገረችው።
እስከመቼ በጣሳ እንጠጣ? እስከመቼ በወጪት እንቅዳ? እስከመቼ ድሆች እንባል ? ስትል ጠየቀችው። እሷ ሥራችን ሁሉ ‹‹ሙያ በልብ›› ይሁን ስትል ከዓባይ ተማከረች። ዓባይ ገነትን ‹‹ እህ… ›› ብሎ የሰማት መሰለ። ገነት ማስረሻ አባይን ‹‹ጭስ አልባ ነዳጄ›› እያለች አሞካሸችው ። እንዲህ ስትል ።
ዓባይ ነጋ ጠባ ሀብቱን ያፈሰዋል፣
ጭስ አልባ ነዳጄ ብለው ምን ያንሰዋል።
እኳን ለእኛ ቀርቶ ከሰውም ይተረፋል፣
ጭስ አልባ ነዳጄ ብለው ምን ያንሰዋል።
አደባልቆት ሲሄድ ጥቁርና ነጩን፣
ግዮን አበሻ ነው ማን ይነካል የጁን።
ዓባይ አንተ እያለህ ታላቁ ወንዛችን፣
መሳለቂያ አንሆንም በድህነታችን።
ዓባይ አንተ እያለህ ጭስ አልባው ነዳጅ፣
አልመለከትም እኔስ የሰው እጅ።
ዓባይ እኔና አንተ ያለነው ቅርብ ነው፣
ከተስማማንማ ሙያ በልብ ነው።
ዓባይና ገነት ማስረሻ ጭውውታቸው ቀጥሏል። ታላቁ ዓባይ የከያኔዋን ቃል እያዳመጠ መፍሰስ መጉረፉን ይዟል። ገነት አሁንም ዓባይን አልተወችውም። ወቀሳ በሚመስል ግን ከተለመደው አባባል ወጣ ያለ ሀሳብ እየነገረችው ነው ። ዓባይ እያደመጠ ይጓዛል። እየተጓዘ ይጎርፋል።
ዓባይ እኔና አንተ ሳይሉን ቸር ሆነን፣
ፎከሩብን እንጂ ማን አመሰገን።
ስንት ዘመን ቁጭት ስንት ዘመን ግጭት፣
ስንት ዓመት በጣሳ፣ስንት ዓመት በወጪት።
ፍሰስበትና በሀገርህ ሜዳ፣
የሚቆጣም ካለ ያበጠው ይፈንዳ።
ዘመን ቢያስታርቀን ከዓባይ ብንስማማ፣
ይዘን ተጠጋነው አካፋና ዶማ ።
እውነት ነው። አሁን ጊዜና ዘመን ከዓባይ አስታርቆናል። የገነት የቀደመ የዜማ ትንቢትም ዕውን ሆኗል። የኢትዮጵያ ሕዝቦች ክንድ በኅብረት ተባብሮ ታሪኩን ገንብቷል። በአካፋና ዶማ የጀመረው ቁጭት ከህዳሴው ታላቅ ግድብ ደርሶ ታሪክ ተቀይሯል። አሁን ዓባይ ይሉት ወንዝ ማደሪያ አለው። አፈርም፣ግንድም ይዞ አይዞርም ።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን መጋቢት 24/2015