“አንዳንዴም በዋልድባ…”፤
ወደ መቶ ፐርሰንት የሚጠጋው የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድም ይሁን በሌላ፤ ባሕርይውና ስያሜው ቢለያይም፤ በሃይማኖቶችና በእምነቶች ጥላ ሥር መሰባሰቡን አስረግጦ የሚያስረዳን የሀገራዊ እስታስቲካችን ውጤት ነው፡፡ “የአይሁድ፣ የክርስትና፣ የእስልምና ሃይማኖቶችና ባሕላዊ እምነቶች ተጎራብተውና ተዋደው የሚኖሩባት” እየተባለች በዓለም ፊት ሞገስ ያገኘችው ሀገራችን በአድናቆት ስሟ የሚነሳው ሙሉ ለሙሉ ከችግሮች የጸዳች ስለሆነ ሳይሆን በአንጻራዊነትም ቢሆን የመልካሙ እሴት መዓዛ ይበልጥ ስለሚያውድና ብርሃኑ ከጨለማው ይልቅ የበረታ ጉልበት ስላለው ነው፡፡ እርግጥ ነው ለሃይማኖት ቁብ የማይሰጡ፤ ከፈጣሪም ጋር ጠብ እስከ መግጠም ወደ ኋላ የማይሉ ጥቂት “አምላክ የለንም ባዮች” እንደሚኖሩም አይጠፋንም፡፡
ስለዚህም “አንዳንዴ በዋልድባ…” እንዲሉ አልፎ አልፎም ቢሆን ይህንን በጎ እሴት እያስታወሱ መዘከሩ ለሀገራዊ ሰላማችን የሚኖረው ፋይዳ ከፍ ያለ ስለሆነ የምንደረደረው በዚሁ ሃይማኖታዊ ጉዳያችን ላይ ይሆናል፡፡ “ኢትዮጵያ በሰሞኑ የዐብይ ጾምና በረመዳን ‹ቅዱስ ወር› ምክንያት በጾምና በጸሎት ላይ ነች” ይህን አባባል የሰማሁት ከአንድ የቅርብ ወዳጄ ነው፡፡ ድንቅ ምልከታ ነው፡፡ በርግጥም ይህ ወር ሀገሬ እጆቿን ወደ ጸባኦት ዘርጋት ጉልበቶቿን መሬት ያስነካችበት የምሕላ ወራቷ ነው ቢባል ተገቢም አግባብም ይሆናል፡፡
አብዛኞቹ የሀገራችን ቤተ እምነቶች በቀኖናቸው፣ በዶግማቸውና በአስተምህሯቸው መሠረት “የጾምና የጸሎት አዋጅ በማወጅ” ምዕመኖቻቸው የፈጣሪን ፊት እንዲፈልጉ ማበረታታቸው በሰውም ዘንድ ሆነ በፈጣሪ ዘንድ የሚያስመሰግናቸው ተግባር ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን በዐብይ ጾም፣ የእስልምና እምነት ተከታዮች በረመዳን፣ የካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን፣ የወንጌል አማኞች፣ በዝርዝር ያልተገለጹ ሌሎች የልዩ ልዩ ቤተ እምነቶችና የባሕላዊ እምነት ተከታዮችም እንዲሁ በሥርዓተ አምልኳቸው መሠረት በጸሎት፣ በዱዓና በምልጃ እየቃተቱ ስለመሆናቸው ምድርና ሰማይ ምስክሮች ናቸው፡፡
ከአብያተ ክርስቲያናት እስከ መስጊዶች፣ ከምኩራብ እስከ ግለሰቦች ጓዳ ድረስ የሕዝበ ኢትዮጵያ ጉልበቶች ለጸሎት ተንበርክከው ፈጣሪያቸውን ከሚማጸኑባቸው ዋና ዋና ርዕሰ ጉዳዮች መካከል አንዱና ምናልባትም ከፍ ያለ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ የሀገራችን ወቅታዊ የሰላም ሁኔታ ሊሆን እንደሚችል መገመቱ አይከብድም፡፡
ከኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች የሚደመጠው የኪራላይሶን መቃተት፣ ለሙስሊሞች በአዛን የሚተላለፈው የጸሎት ጥሪ፣ ወይንም በአይሁዶች ቀንደ መለከት ድምጽ የመሰባሰቡ ዋና ጉዳይ “ኢትዮጵያ ነች ”። የዚህ ሁሉ ምዕመን ጸሎት፣ የሚፈሰው እምባና የምሕላ ጩኸት፣ ሶላቱና በንስሐ መቃተቱ ያስፈለገው ለምንም ሳይሆን የኢትዮጵያ ሕመም እንዲፈወስና የሕዝቧ ሰላም እንዲረጋገጥ ነው፡፡
ይህ ጸሐፊ “ከገዥያችን ሕገ መንግሥት” አናቅጽ መካከል በተለይም የመንግሥትና የሃይማኖት መለያየት ከተገለጸበት አሥራ አንደኛው አንቀጽ ጋር በፍጹም አይስማማም፡፡ “መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፤ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም” (ንዑስ አንቀጽ 3) የሚለው ድንጋጌ በተለየ ሁኔታ እውነታነቱና ገለልተኛነቱ እስከ ምን ደረጃ እንደሆነ ሳስብ ድንበሩ ይደበላለቅብኛል፡፡ ተግባሩና ድንጋጌው ስለማይጣጣምም የተአማኒነቱ ጉዳይ ጥርጥር ላይ ይጥለኛል፡፡ ይህንን ንዑስ አንቀጽ አዘውትሬ የምመስለው በሌሊት ወፍ ተፈጥሯዊ ባሕርይ ነው፡፡
ላብራራው፡- የሌሊት ወፍ በመብረር ችሎታዋ ከአዕዋፍ ዝርያ፣ ጫጩቶቿን አጥብታ በማሳደጓ ደግሞ ከአጥቢ እንስሳት ትመደባለች፡፡ ከአይጠ መጎጥ መልክ ጋር በመመሳሰሏም በተራ ዜጎች ዘንድ የእነርሱ ዝርያ ትሆንን አሰኝታ ግራ የምታጋባ አስተኔ (ብጤ) ፍጡር ነች፡፡ “የሌሊት ወፍ ሁለት እንቁላል ትጥላለች፤ አንዱን ሲሰብሩት አስኳል፤ ሌላውን ሲሰብሩት ፍላጻ” እየተባለም ብሂል ተነግሮላታል፡፡ በሕገ መንግሥታችን ጉዳይ ላይ ጊዜው ቀን ቆርጦ እስክንወያይበት ድረስ እኔና መሰል አስተሳሰብ የሚያራምዱ አስተኔዎቼ (ብጤዎቼ) በዚህ አንቀጽ ላይ ለመሟገት አጀንዳውን በይደር አስተላልፈን ቀኑ ቀን ሲያመቻችልን “ይግባኝ!” ብለን ክርክሩን እንቀጥላለን፡፡
ለማንኛውም በየቤተ እምነት አጥቢያዎቻቸው ደጀ ሰላም ላይ ተደፍተው “በኤሎሄ!” ድምጸት ለሚቃትቱ፣ በየመስጊዳቸው የአላህን ስም እየጠሩ በተሰበረ ልብ ለሚጸልዩ፣ በክርስቶስ ኢየሱስ ስም እየተማጸኑ “እግዚኦ!” ለሚሉ፣ በየምኩራባቸው ተሰባስበው በያህዌ ቅዱስ ዙፋን ሥር በመንበርከክ ለሚተጉ እና እንደየእምነታቸው በየጓዳቸው በራቸውን ከውስጥ ቆልፈው በፈጣሪያቸው ፊት ለሚያነቡትና በየሥራ መስካቸው “አምላክ ሆይ ስለ ኢትዮጵያ ተለመነን!” እያሉ ልባቸውን ከእጃቸው ጋር ከፍ አድርገው ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን በፈጣሪ ፊት በእምነት ለሚያቀርቡት ሚሊዮኖች በሚከተለው መልካም ቃል እንባርካቸዋለን፡፡
“የፍጥረተ ዓለም ፈጣሪ ፈጥኖ ጸሎታችሁን ይስማ፤ ጾማችሁንም ይቀበል፡፡ ፊቱን ያብራላችሁ፤ የርህራሄውን ድምጽም ያሰማችሁ፡፡ የምታለቅሱላት ኢትዮጵያ በጸሎታችሁ ትፈወስ፡፡ የዜጎቿ ልብም በሰላም ይረፍ፡፡ ለመንግሥት ሹመኞች ጥበብና ማስተዋሉን ያብዛላቸው። ለክፋት በርትተው የጥፋት ክንዳቸውንና ልባቸውን ላደነደኑትም ከሰይጣናዊ ድርጊታቸው መመለስ ይሁንላቸው፡፡ የሀገራችን ጠላቶች ሴራ ይክሸፍ፡፡ አሜን!” – “አንዳንዴ በዋልድባም…” ብለን ተንደርድረናልና እነሆ የወቅቱን የሕዝባችንን ጾምና ጸሎት አስታውሰን “በምሥጢረ ሃይማኖት ጉዳይ” ይህንን ያህል ለማለት ሞክረናል፡፡ ወደ ሌላው ምልከታ እናቅና፡፡
ለተጠየቅ ሙግት ግድ የሚሉን ስብራቶቻችን፤
ብላቴን ጌታ ማኅተመ ሥላሴ “ባለን እንወቅበት” በሚል ርዕስ በ1961 ዓ.ም ባሳተሙት መጽሐፋቸው ውስጥ የሀገራችንን ነባር ልማዳዊ የተጠየቅ (በላ ልበልሃ) የሙግት አካሄድ የገለጹት እንዲህ በማለት ነበር፡፡ “ሕዝባችን ብልህ ነው፤ ፈጥኖ የመረዳትና የማስረዳት ችሎታ አለው። የነገርን አካሄድ ይመረምራል፤ የአስተዳደር ምክር፣ ክርክር፣ ዳኝነትና ፖለቲካ የተፈጥሮ ገንዘቡ ናቸው” (ገጽ 18)፡፡
የተጠየቅ ሙግቱ (የበላ ልበልሃ) ፍልሚያው ፍዝ አይደለም፡፡ ማራኪና ተውኔታዊ ባሕርይ የሚንጸባረቅበት ጭምር ነው፡፡ አካሄዱን በተመለከተ ደራሲ ስለሺ ለማ “ተጠየቅ” በሚለው መጽሐፋቸው እንዲህ ይገልጹታል “ተውኔታዊ ባሕርይ የነበረው የከሳሽና የተከሳሽ አለባበስ፣ አቋቋም፣ ዘንግ አያያዝ፣ የሰውነት እንቅስቃሴ፣ የነገር አቀራረብና ባጠቃላይ ሞቅና ደመቅ ያለው ጥምር የአሞጋገት ስልት በእጅጉ ያስደንቃል፡፡
ተሟግቶ ለመርታት፣ ረትቶም እርካታን፣ ዝናንና ክብርን ለመቀዳጀት በቅድሚያ የተሟጋቹን ንቃት ብልህነትና ብርታት ይጠይቃል፡፡ ከዚህም የተነሳ ከሰውነት እንቅስቃሴ ሌላ በተለይ የመሟገቻ ቋንቋው በተዋቡ ቃላት፣ በምሳሌያዊ አነጋገር፣ በተረት፣ በአፈታሪክ፣ በእንቆቅልሽና በመሳሰሉት ዘዬዎች የበለጸገ ነው፡፡ የእነዚህ ሁሉ ውሕድ የችሎት ነጻ ትርዒት ነው እንግዲህ ወጪ ወራጁን፣ አላፊ አግዳሚውን ሁሉ ይማርክ የነበረው” (ገጽ 15)፡፡
አሁን ወደ ተጠየቁ ሙግት ዘልቀን እንግባ፡፡ ለመሆኑ ሀገራዊ ስብራታችን ስለምን በረታብን? የሀገሪቱ ቀዳሚ ለውጥ ናፋቂ ብኩን ትውልድ በእንጉርጉሮ፣ ደርግ በጠብመንጃ፣ ኢሕአዴግ በግፍ ለበስ አስተዳደሩ፣ ብልጽግና በእሹሩሩ ማባበያ እያዘመሩንና እያዘየሩን በመካደም ቤትኛ እንዲሆን የሙጥኝ ያለነው “ዲሞክራሲ” ለምን ሥር አልይዝ አለን? ስለምንስ ጣፋጭ ፍሬ ያፈራል ብለን ከሃምሳ ዓመት በላይ በትዕግስት ስንጠባበቅ ሆምጣጣ ፍሬ አፍርቶ ተስፋችንን ለማምከን ምክንያት ሆነ?
ቀደም ባለው ጽሑፌ “ኦ ዲሞክራሲ በስምህ ስንት ግፍ ተሠራ?” በማለት የቆዘምኩበት ጽሑፌ ብዙ ጉዳዮችን ስለነካካ “የአዋጁን በጓዳ” እንዳይሆንብኝ አንባቢ ቤትኞችን ደግሜ አላሰለችም፡፡ በአጭሩ ለመግለጽ ካስፈለግ ግን “ዲሞክራሲውም ሆነ ዲሞክራት ተብዬዎቹ ሁለቱም ታመው እያቃሰቱ ነው፡፡ ስለዚህም በስመ ዲሞክራሲ ስም ተስፋ የተገባልን ሁሉ እንኳን ሊተገበር ቀርቶ ያሉን ነባር እሴቶች ራሳቸው ተሰነጣጥረው ተሰባብረዋል፡፡
የመጀመሪያው ስብራታችን ከፍትሕ ሥርዓታችን ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ ትንቢተ ዕንባቆም የሚል ርዕስ የተሰጠው አንድ አስደናቂ መጽሐፍ አለ፡፡ ነብዩ ልክ በእኛ ዘመን አብሮ የኖረ ይመስል “ጩኸታችንን ነጥቆ” እንዲህ እያለ ፈጣሪን ይሞግታል፡፡ “እኛ ስንጮኽ የማትሰማው እስከ መቼ ነው? ስለ ግፍ ወደ አንተ እንጮኻለን አንተም አታድንም፡፡
ሕግ ላልቷል ፍርድም ድል ነስቶ አይወጣም፡፡ ስለዚህ ፍርድ ጠማማ ሆኖ ይወጣል” (ትንቢተ ዕንባቆም 1፡2 – 4)፡፡ ስብራታችንን የከፋ የሚያደርገው “ከማታ ተኩላ ይልቅ ጨካኞች” በየጊዜው የሚፈጽሙት ግድያና እገታ የወትሮ ልማድ ሆኖ እስኪቆጠር ድረስ እንድንለምደው መደረጉ ነው፡፡ ፍትሕ ሆይ ወዴት አለህ? “ይህንን ያህል ሺህ ሰው ተገደለ፣ አካለ ጎዶሎ ሆነ፣ ተፈናቀለ፣ ተሰደደ” የሚለው መርዶ መቼ ነው የሚቆመው? እኛ እንጠይቃለን መላሹም መልስ ይሰጠን፡፡
ሁለተኛው ስብራታችን የፖለቲካ ስብራት ነው። ምናልባትም ለስብራቶቻችን በሙሉ “አብሾ አጠጥቶ” ያሳከረን ይሄው የግሪኮችን ስም የያዘውና በውሰት አምጥተነው ቤታችንን እያናጋ ያለው በዲሞክራሲ ስም የተለበጠው ፖለቲካችን ሳይሆን አይቀርም፡፡ ድሮ ድሮ የመረዳት አቅማችን ጨቅላ በነበረበት ዘመን መምህራኖቻችን “Politics is a bad game” ሲሉን አይገባንም ነበር፡፡
ዛሬ በጉልምሳናና በዘመነ ሽበት እያስተዋልን ያለነው በእርግጥም ፖለቲካ ይሉት “የሥልጣን መናጠቂያ ዕቃ ዕቃ” እብደቱ ለይቶለት ጭርሱኑ ጨርቁን ጥሎ አደባባይ መውጣቱን ነው፡፡ ለሥልጣን ሲባል ምንም ነገር ከማድረግ ማንም እንደማይመለስ በብዙ ማስረጃዎች ካረጋገጥን ሰንብተናል፡፡
ሦስተኛው ስብራት የሞራልና የግብረ ገብ ስብራታችን ነው፡፡ ሽቅብ አንጋጦ አባቶችን መሳደብ፣ ታላላቆችን ማዋረድ፣ የእምነት መሪዎችን መዝለፍና ማንጓጠጥ የባሕል ያህል ተጣብቶናል፡፡ ማኅበራዊው ሚዲያ አቅላችንን ሰልቦ ካስገበረን ውሎ አድሯል፡፡ “እኔን የወለደኝ ፌስ ቡክ ነው እንዴ?” በማለት ወላጆችን እንደሞገተችው ልባም ሕጻን “እኛስ እንደ ሀገር የምንመራው በማኅበራዊ ሚዲያ ሆነ እንዴ?” ብለን “እንጠያየቅ” ብለን ብንዋቀስ ተገቢ ይመስለናል፡፡
ከሰብዓዊ ክብር ይልቅ የቁስና የነዋይ ጫና የበረታበት፣ አገልግሎት ለመስጠት ግዴታ ያለባቸው ዜጎች ያለመማለጃ የዜጎችን ጉዳይ ላለመፈጸም መጨከን ሌላው ስብራታችን ነው፡፡ የሕሊናን ጨርቅ ጥለው ባበዱ ገዳዳ ነጋዴዎች የሚፈጸመው የኢኮኖሚ አሻጥርና ሴራ ሕዝብ ሲያለቅስ እነርሱ ቤታቸውን ቆልፈው “ወይን ያስተፈስህ ለልበ ሰብ” እያሉ “ዋንጫ ኖር – Cheers” መባባላቸውን ቤታቸው ተገኝተን የዐይን ምስክር ባንሆንም በአደባባይ የገነነው ጠረናቸው ግን በሚገባ ድርጊታቸውን ያሳብቃል።
አራተኛው ስብራታችን በስመ ሃይማኖት አቅል የሳቱ ልምምዶች አየሩን መበከላቸው ነው፡፡ አንዳንዶች ፈጣሪን ራሱን ሻምላ አስጨብተው ከእነርሱ ጋር ቆሞ እንዲፋለምላቸው በአደባባይ ሲፎክሩና ሲያስፎክሩ ስንመለከት “እግዚኦ!” እያልን ብናማትብም ጸሎታችን አቅም አንሶት ሳይሆን አይቀርም፤ በነጋ በጠባ የምናስተውለው ክፋቱ እየበረታ ሲሄድ እንጂ ሲቀዘቅዝ አይደለም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ የበላ ልበልሃ ሙግቱን ከማን ጋር እንደምናደርግ ግራ ስለሚያጋባ በለመድነው “ሆድ ይፍጀው” ሽሽት “ፈጣሪ ሆይ ክብርህን አስጠብቅ” ብለን ማምለጡን መርጠናል፡፡
በብሔርና በቋንቋ ምክንያት የደረሰብንን ስብራት በተመለከተ ግን “በተከድኖ ይብሰል” ትዝብት ነካክተን የምናልፈው ሳይሆን በየቦታው በአፈርሳታና በአውጫጭኝ እየተጠራራን “ሌባው ለማ፣ ጀንበር በሰረቀ ቁጥር እየተቃጠልን እንዴት እንዘልቀዋለን” እንዳሉት ሸንጎኞች እኛም ዳር ዳር ከመዞርና ከማሳበብ ወጥተን በበላ ልበልሃ ሙግት ልንበረታ ይገባል፡፡ በነገራችን ላይ “ሌባው ለማ…” የሚለውን ታሪክ ለአንባቢያን ፈታ አድርጎ ማለፉ አግባብ ስለሆነ ፍቺውን ሳንርቅ በቅርቡ አስታውሰን እንለፍ፡፡
“በድሮ ጊዜ” እንዲሉ በአንድ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች በተደጋጋሚ ጊዜ ንብረታቸውን እየተዘረፉ ተቸገሩ ይባላል። ሌቦቹ ከሩቅ የመጡ ሳይሆኑ እዚያው በማኅበረሰቡ ውስጥ የሚኖሩ መሆናቸው በሹክሹክታም ቢሆን ነዋሪው ከአፍ አፍ እየተቀባበለ ማንነታቸውን አውቆታል፡፡ “ሌቦቹ እኔ አከሌ ናቸው” ለማለት ፍርሃት የተጫነው ነዋሪ እህህ እንዳለ ውሎ አምሽቶው የአውጫጭኝ ጉባዔ ብቻ ሆኖ ቀረ፡፡ ይህን መሰሉን የፍርሃት አዚም ለመግፈፍ አንድ ጠቢብ አባት ተገኙ ይባላል። እንደተለመደው አውጫጭኙ በተጠራ እለት በሕዝቡ መካከል ቆመው ከላይ የተነገረውን ቅኔ ለበስ ንግግር በማድረግ ሌቦቹ “ለማ፣ ሰረቀ እና ጀንበር” መሆናቸውን በጥበብ ንግግር አፈረጡት ይባላል። የበላ ልበልሃ ሙግታችንና የተጠየቃችን ፍልሚያ ገና አልተጠናቀቀም። ኢትዮጵያ ሆይ! ስብራትሽን ገና ዘርዝረን ስላልጨረስን ሳንታክት እንቀጥልበታለን፡፡ ዜጎችሽ በጾም ጸሎት እኛ ብዕረኞችም በተጠየቅ ሙግት ፈጣሪያችን “ብርሃን ይሁን ብሎ፤ ብርሃን እንደሆነው” የምሥራች እስኪያሰማን ድረስ በጥልቅ ጨለማ ከሚመሰሉት ሀገራዊ ችግሮቻችን ጋር የምናደርገውን ፍልሚያ ጠንክረን እንቀጥላለን፡፡ ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ፡፡
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን መጋቢት 23/2015