ጉድለት ያየንበትን ሰው ማስተዋል የጎደለው ብለን እንወቅሰዋለን፡፡ አዙሮ አለማየቱንም ልናሳየው እንሞክራለን፡፡ ነገሮችን በትእግሥት የሚያልፍ ሰውም እንዲሁ ሆደሰፊነቱን እንመዝነዋለን፡፡ ሆደ ሰፊነት፣ አስተዋይነት፣ አዙሮ ማየት፣ እነዚህ ቃላት ለመባል ብቻ የተቀመጡ አይደሉም፡፡ ሰዎች በዕለት ተዕለት ኑሯቸው ውስጥ የሚያልፉባቸው በመሆናቸው ጭምር ነው፡፡
በዚህ ወቅት ብዙ ዓይነት አለማስተዋል እንታዘባለን። በትራንስፖርት ዘርፍ ላይ የምንታዘበው አለማስተዋል ግን ከሁሉም ይለያል፡፡ አስተዋይነት የጎደለው ነው በሚል ብቻ የሚታለፍ አይደለም፡፡ በተደጋጋሚ ነው የሚፈፀመው፡፡ የሥነምግባር ግድፈት ተደርጎም ይወሰዳል፡፡ እንዲታረም የሚያደርግ አካልም የለም፡፡ ድርጊቱ ትክክል ተደርጎ እየተወሰደ በመሆኑ በሌላውም ላይ እየተጋባ ነው፡፡ ተገልጋዩን ተባባሪ እስከማድረግ ተደርሷል፡፡
ዘርፉን የሚመራው አካልም በዝምታ እያለፈው በመሆኑ የቻለ ተገልጋይ እየተናነቀ መብቱን ለማስከበር ጥረት ያደርጋል፡፡ያልቻለው ደግሞ ተበሳጭቶ ያልፈዋል፡፡ ግን እስከመቼ እንዲህ በትራንስፖርት ዘርፉ የሚስተዋለው ነገር በየጊዜው አዳዲስ ነገር እየፈጠረና መረን እየለቀቀ ይሄዳል፡፡ ለችግሩ ማሳያ ለጽሑፌ መነሻ እንዲሆነኝ አንድ በከተማ ውስጥ እና አንድ ደግሞ በአገር አቋራጭ አገልግሎት ላይ ያለኝን ትዝብት ላካፍላችሁ፡፡ የከተማውን ላስቀድም፤
ከመርካቶ አራት ኪሎ ነው መጓዝ የፈለኩት፡፡ ተራውን ጠብቆ የሚጭነው ታክሲ ውስጥ ለመግባት ስሞክር ከየት መጣ ሳልል ረዳቱ በሩን ይዞ የምሄድበትን ጠየቀኝ፡፡ ወደ አራት ኪሎ እንደምሄድ ነገርኩት፡፡ ቦታ የለም አለኝ፡፡ ክፍት ቦታዎች ግን ነበሩ፡፡ እኔም የዋዛ አልሆንኩለትም ክፍት ቦታውን እያሳየሁት ገፍቼው ገባሁ፡፡ እየተወናጨፈና እየዛተ 20ብር እንደምከፍል ነግሮኝ ዕቃ የያዙ መንገደኞችን መፈለጉን ቀጠለ፡፡ ብዙ ዕቃ ለያዘና ከፍ ያለ ክፍያ ለሚጠየቀው የፊትለፊት መቀመጫ (ጋቢና) ተይዟል፡፡ ገና ተፈልጎ ለሚመጣ ተሳፋሪ ነው እንግዲህ ቀድሞ የተያዘው፡፡
እንደእኔ ብቸኛ ተሳፋሪ መጥቶ የጋቢናውን በር ለመክፈት ይታገላል፡፡ የታክሲው ሾፌር እያሾፈ ‹‹ይሄ ቪ አይ ፒ ነው፡፡ዋይፋይም አለው›› ይላል፡፡ ስለሌላው መብት ለመናገር ቀርቶ የራስንም ማስከበር እየተቻለ ባለመሆኑ ሰው ዝምታውን መርጧል፡፡ የሚበሳጭም ካለ ብስጭቱን ከመቻል ውጪ አማራጭ የለውም፡፡ ምክንያቱም ሾፌሩ፣ ረዳቱ፣ ተራ አስጠባቂውም ቋንቋቸው ተመሳሳይ በመሆኑ ተሳፋሪው ላይ ይተባበራሉ፡፡ በጉልበት ዝም ስላሰኙት ትራንስፖርት ላይ መብቴ ነው ቀርቷል፡፡
ታስታውሱ ከሆነ አንድ ወቅት ላይ ታክሲ ውስጥ የተለያዩ ጥቅሶች ይለጠፉ ነበር፡፡ ከነዚህ ውስጥ ‹‹መብትህን ታክሲ ውስጥ ነው የምትጠይቀው›› የሚል ጥቅስ ተጠቃሽ ነው፡፡ አሁን በጉልበት ጭጭ እንዲሉ ማድረግ እየተቻለ ለጥቅስ ለምን ወጪ ይወጣል፡፡ ያሳፈረኝ ታክሲ ላይ ጉልበተኛ ሆኜ እርሱ ያዘዘኝን 20 ብር ሳይሆን፣ ሦስት ብር ትርፍ ጨምሬ 10 ብር ከፈልኩት። ብሩን ሲቀበለኝ ግን ከስድብና ከዱላ ባልተናነሰ እየተርጎመጎመ ከእጄ መንጭቆ ነበር የተቀበለኝ፡፡ እኔ ለእርሱ በምከፍለው እንደሚኖር ማስተዋል እንኳን ቢሳነው በዕድሜም ሊያከብረኝ ይገባ ነበር፡፡
ከአገር አቋራጭ ገጠመኜ ደግሞ አንዱን ላካፍላችሁ። ከአዲስ አበባ ከተማ ወደ ቢሾፍቱ ነው ጉዞዬ፤ በመናኸሪያው ግቢ ውስጥ በእያንዳንዱ የጉዞ መሥመር የታሪፍ ዝርዝር በደረጃ በግልጽ ቦታ ላይ በሰሌዳ ላይ ተለጥፏል፡፡ ግን ብዙዎች በዚህ መሠረት መብታቸውን እየተጠቀሙ አይደለም፡፡ ሾፌሩ መንገድ ሲጀምር የሚጠይቃቸውን ዋጋ በመልመዳቸው ያንን ነው የሚፈጽሙት፡፡ የሚገርመው ደግሞ በቅጥር ግቢው ውስጥ የተለጠፈውን ታሪፍ አለማየታቸው አይደለም። ከከተማ ከወጡ በኋላ አንዳንዴ ትራፊኮች ደረሰኝ ስለሚጠይቁ አሽከርካሪዎቹ ጠበቅ ያለ ቁጥጥር መኖሩን ሲሰሙና ጠንቃቃ ለመሆን ሲሉ ታሪፍ የያዘ ደረሰኝ ለተሳፋሪው ያድላሉ፡፡
ደረሰኙ ጉዞ ካለቀ በኋላ የሚመለስ በመሆኑ በጥንቃቄ እንዲያዝ ይጠየቃል፡፡ ደረሰኙ ላይ ያለው ታሪፍና የሚጠየቁት ክፍያ ልዩነት እያለው እንኳን ተሳፋሪው ለምን ብሎ አይጠይቅም፡፡ ታዲያ እኔ ደረሰኙ ላይ በተቀመጠው ታሪፍ መሠረት ክፍያውን ሰጠሁ፡፡ ክፍያውን የሚሰበስበው ተሳፋሪ ነበር፡፡ በትርፍ ክፍያው መሠረት ባለመክፈሌ ሂሳቡን አልቀበልም አለኝ፡፡
እኔም አልተቀበልኩትም በመጨረሻ ግን ልዩነቱን ከፍሎልኝ ነው ሂሳቡን ሰብስቦ የሰጠው፡፡ ተሳፋሪው ይህን ያደረገው መብቷ ነው በሚል እሳቤ ሳይሆን፣ ገንዘብ የላትም፡፡ ወይንም ጨቅጫቃ ናት በሚል ነው፡፡ እንዲህ ያለው ገጠመኝም የተለመደ ነው፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ምን ያህል በሰው አእምሮ ላይ ጫና እንደፈጠሩ ካለው ሁኔታ መገንዘብ ይቻላል፡፡
በአገርአቋራጭ የትራንስፖርት አገልግሎት በበዓላት ወቅት ደግሞ የባሰ ነው፡፡ በአዘቦቱ ከሚደረገው ጭማሪ በላይ እንዲማረሩ ነው የሚያደርግዎት፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎቹ አብዛኞቹ ከመናኸሪያ ግቢ ውጪ ነው የሚሆኑት፡፡ደላላዎች በውጭ በር ላይ ሆነው ከቃሊቲ መናኸሪያ በመደበኛ የትራንስፖርት አገልግሎት በደረጃ ከ25 እስከ 31 ብር ከፍለው የሚጓዙበትን መንገድ እስከ ሁለት መቶ ብር በመጠየቅ ያሳፍራሉ፡፡
ደላሎቹ ያኔ የግል መኪና ሁሉ በሕገወጥ ትራንስፖርት ስምሪት ውስጥ እንዲገባ ያደርጉታል፡፡ በመደበኛ ትራንስፖርት ለመሄድ ሰልፍ ይዞ ሲጠባበቅ የነበረው ሁሉ ተስፋ ቆርጦ ከግቢ እየወጣ ለሕገወጦች ሲሳይ ይሆናል፡፡ ይሄ የሚሆነው መሽቶ ወይንም አማራጭ ጠፍቶ አይደለም፡፡ ዘርፉን የሚመራውም አካል ተባባሪ በመሆኑ ነው በጠራራ ሰዓት እንዲህ አይን ያወጣ ድርጊት የሚፈፀመው፡፡ በመናኸሪያ ግቢ ውስጥ በበዓል ወቅት ያለው ይብሳል ለማለት እንጂ ከሳምንት እስከ ሳምንት ሰልፍ የተለመደ ሆኗል፡፡
ከሰሞኑ ፖለቲካዊ ይዘት አለው ተብሎ የተነገረለት የባጃጅ ትራንስፖርት አገልግሎትን በመንግሥት በኩል ለጊዜው ተወስዶ የነበረው የማቆም እርምጃ እውነትነት ያለው ነገርም እንዳለው መዘንጋት የለበትም፡፡ የአጭር ጉዞ መነሻ ታሪፍ ከአምስት ብር ወደ አስር ብር ያሳደጉት በራሳቸው ነው፡፡ የጠየቃቸው አካል ባለመኖሩ ታሪፉ ፀድቆ ሲሠራበት ነበር፡፡
የዚህ አገልግሎት ክፍያም በዋና አስፓልት ላይ ለሚጠቀም ነው፡፡ የባጃጅ የትራንስፖርት አገልግሎት ሲጀመር ግን ውስጥ ለውስጥ አገልግሎት እንዲሰጡ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ተከታትሎ ያስፈፀመው አካል ባለመኖሩ የባጃጅ ባለቤቶች እራሳቸውን በራሳቸው ነው የመሩት ማለት ይቻላል፡፡
በአጠቃላይ ከትራንስፖርት ዘርፉ ጋር በተያያዘ ከተደራሽነት ጋር በተያያዘ የተገልጋዩ ቁጥርና አገልግሎቱ አለመጣጣም እንደምክንያት ሊነሳ ይችላል፡፡ የሥነምግባር ጉድለቱና ያለውንም በአግባቡ አገልግሎት እንዲሰጥ በቁጥጥርና ክትትል የሚያስተካክል አካል አለወይ ሲባል የለም፡፡ ምክንያቱም ችግሮቹ እየተባባሱ እንጂ መሻሻል ስለማይታይ ነው፡፡
ለመሆኑ መንግሥት ለትራንስፖርት ዘርፉ ያደረገውን የነዳጅ ድጎማ ስንቶቻችን አስተውለናል፡፡ አገልግሎት ሰጪውም እንዳይጎዳ፣ ተገልጋዩም ክፍያው ከአቅሙ በላይ እንዳይሆንበት የነዳጅ ታሪፍ ድጎማ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ ‹‹የውሾን ልጅ ያነሳ ውሾ ይሁን›› እንደሚባለው ስለዚህ ጉዳይ የሚያነሳ አካል የለም፡፡
የትራፊክ ሕግ የሚተላለፉ አሽከርካሪዎችን ለመቆጣጠር በተጨማሪ የሰው ኃይል በመንገድ ትራንስፖርት እየተሠራ ያለው ሥራ በአገልግሎቱ ላይም በተመሳሳይ መሠራት ይኖርበታል፡፡ በየትራንስፖርት ዓይነቱ ያለውን ፀባይ ለይቶና ፈትሾ በቁጥጥርና ክትትል የማጠናከሩ ሥራ ከመንግሥት ይጠበቃል፡፡
ለምለም መንግሥቱ
አዲስ ዘመን መጋቢት 23/2015