ሀገራችን ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት በሽግግር ሁኔታ ውስጥ ብታልፍም በተሟላ መልኩ የሽግግር ፍትህ አላባዎች ተተግብረው አያውቁም፡፡ በነዚህ የሽግግር ሂደቶች ያለፉ ጉልህ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች፣ በደሎች እና ጭቆናዎችን መንስኤ፣ ምንነት፣ አይነት እና የጉዳት መጠን በበቂ መንገድ በማጣራት፣ እውነትን በማውጣት እና እውቅና በመስጠት በተጠያቂነት፣ በይቅርታ እና በእርቅ ላይ የተመሰረተ የተሟላ ሂደት አልተከናወነም።
የደርግ መንግሥት የአፄ ኃይለስላሴን መንግሥት ከሥልጣን ካስወገደ በኋላ በንጉሱ ሥርዓት ዘመን መጠነ ሰፊ በደል ፈፅመዋል፣ አለአግባብ በልጽገዋል እና ለወሎው ረሃብ እልቂት ተጠያቂ ናቸው ያላቸውን መኳንንቶች፣ መሳፍንቶች፣ ሚኒስትሮች እና ሌሎች ባለሥልጣናትን አስሯል። የነዚህን ባልሥጣናት ጉዳይ እያጣራ ለፍርድ የሚያቀርብ አጣሪ ኮሚሽንም ተቋቁሞ ነበር፡፡ አጣሪ ኮሚሽኑ ምርመራውን ማካሄድ ጀምሮ የነበረ ቢሆንም – ምርመራውን ከማጠናቀቁ በፊት ደርግ ከ50 በላይ በሚሆኑት ባለሥልጣናት ላይ የሞት ፍርድ ውሳኔ በማስተላለፍ እርምጃ እንዲወሰድ አድርጓል፡፡
በ1983 ዓ.ም. ኢህአዴግ በትረ-መንግሥቱን በመቆጣጠር የኢትዮጵያ የሽግግር መንግሥት የመሰረተ ሲሆን፤ በደርግ አስተዳደር ዘመን ለተፈጸሙ ጥሰቶች ምላሽ ለመስጠት የወንጀል ክስ መመስረትን እንደ ዋነኛ መንገድ ተጠቅሟል፡፡ በአዋጅ ቁጥር 22/1985 መሰረት ተጠሪነቱ በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሆነ ልዩ የዓቃቤ ሕግ ጽህፈት ቤት የተቋቋመ ሲሆን፣ በስሩም ከ400 በላይ ሰራተኞች ነበሩት፡፡ የጽህፈት ቤቱ ዋና ስራም የደርግ ባለሥልጣናት የፈጸሟቸውን ወንጀሎች መመርመር፣ ክስ መመስረት እና ማስቀጣት ነበር፡፡
በዚህም መሰረት በተለያዩ ሰዎች ላይ ምርመራዎችን በማጣራት፣ በመደበኛው ፍርድ ቤት ክስ በመመስረት እና በመከራከር ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን ጨምሮ በበርካታ ተጠርጣሪዎች ላይ የቅጣት ውሳኔ እንዲሰጥ አድርጓል፡፡ በዚህ ሂደት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ምስክሮች እና የሰነድ ማስረጃዎችን የማደራጀት እና ክስ የመመስረት ስራው ራሱን በቻለ ተቋም እንዲሰራ መደረጉ በጥንካሬ ሊወሰድ የሚገባው ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪም በቀጣይ ዓመታት አዲስ ሕገ-መንግሥት የማውጣት፣ ዴሞክራሲያ ተቋማትን – ማለትም የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን እና የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋምን – የማቋቋም ስራ ተሰርቷል። በዚህ ወቅት የነበረውን የፍትህ ሂደት ከሽግግር ፍትህ ሂደት አላባዎች አንፃር ስንመለከተው የሚከተሉት ጉድለቶች እንደነበሩበት መረዳት ይቻላል፡-
– የፍትህ ሂደቱ መጠነ-ሰፊ የሆነ የወንጀል ክስ በማቅረብ ላይ ብቻ ትኩረት ማድረጉ እና በደርግ ጊዜ የተፈጸመውን ግፍና በደል በበቂ ሁኔታ ለመሸፈንና ለመፍታት የሚያስችሉ እንደ ይቅርታ፣ እርቅ እና እውነትን ማፈላለግ ያሉ ስልቶችን አለመጠቀሙ፤
– በደርግ መንግሥት የሥልጣን ዘመን በሌሎች አካላት የተፈፀሙ በደሎች እንደነበሩ ቢታወቅም ፤ የክስ ሂደቱ በደርግ ባለሥልጣናት ላይ ብቻ ማተኮሩ ፣ በተለይም በሌሎች ሲቪል እና ታጣቂ ቡድኖች ተፈጽመዋል የተባሉ ወንጀሎችን አለማየቱ፤ የፍትህ ሂደቱን የአሸናፊዎች ፍትህ ተምሳሌት እንዲሆን ማድረጉ፤
– በፍትህ ሂደቱ የነበረው የተጎጂዎች ተሳትፎ ማስረጃ በማቅረብ ላይ ብቻ መገደቡ፣ እንዲሁም የክሱ ሂደትም ቢሆን ከፍትሐ ብሄር ክስ ጋር ያልተጣመረ እና ማካካሻ የማግኘት መብትን ያስከበረ አለመሆኑ፤
– የድርጊቱ ሰለባዎች እና ተጎጂዎች በቂ ማካካሻ እንዲያገኙ አለማድረጉ ከሚጠቀሱ ክፍተቶች ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
በ2010 ዓ.ም. በሀገራችን የተፈጠረውን የፖለቲካ ለውጥ ተከትሎ ፣መንግሥት ያለፉ ጉልህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች፣ ቁርሾዎች እና በደሎች በእውነት በእርቅ እና በፍትህ ላይ ተመሰርቶ ለመፍታት እና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መንገዱን ለማመቻችት – በርካታ የሽግግር ፍትህ እርምጃዎችን ወስዷል። ለደረሱ በደሎች እንደመንግሥት በይፋ ይቅርታ የመጠየቅ፣ የእርቀ-ሰላም ኮሚሽን የማቋቋም፣ ክስ፣ ምህረት እና ለሽግግር ፍትህ ሂደት አስተዋፅኦ የሚያደርጉ የሕግ እና የተቋማት ማሻሻያ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡
ይሁንና የሽግግር ፍትህ አላባዎችን በተሟላ እና ወጥ በሆነ መልኩ ተቀናጅተው የሚተገበሩበት የፖሊሲ አቅጣጫ ባለመኖሩ፣ አንዱ ከሌላው ጋር ያለው መስተጋብርም በግልፅ ባለመደንገጉ፣ እንዲሁም የተወሰዱት እርምጃዎች የየራሳቸው ጉድለቶች ስለነበሩባቸው የሽግግር ፍትህ ሂደት ዓላማን ማሳካት አልተቻለም፡፡ ከተደረጉት ጥረቶች እና ከነበሩ ጉድለቶች መካከል የሚከተሉትን በማሳያነት ማንሳት ይቻላል፡-
የወንጀል ክሶችን በሚመለከት፤
ጉልህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና ከባድ ሙስና እና/ወይም ሌሎች ከፍተኛ የሕዝብ ንብረት ምዝበራ ድርጊቶችን በተመለከተ በመንግሥት ባለሥልጣናት ላይ ክስ ቀርቦ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት የታየ /በመታየት ላይ ያለ ቢሆንም ይህ ሂደት ከሽግግር ፍትህ ሂደት ዘዴዎች እና አላባዎች አንፃር የሚከተሉት ዋና ዋና ጉድለቶች ያሉት መሆኑ ተለይቷል፡፡
– ክሶቹ በኢህአዴግ ዘመነ-መንግሥት በደረሱ ጠቅላላ ጉልህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ላይ ያተኮሩ አለመሆናቸው፣ ክስ ሊቀርብባቸው የሚገቡት ጉዳዮችን በሙሉ ያላካተተና በእጅጉ አናሳ የበዳይ ወሰን ያለው መሆኑ፤
– በአመዛኙ ክሶች የቀረቡት ሊከሰሱ ከሚገባቸው መካከል ማማረጥ በሚመስል መልኩ መሆኑ፤
– ረዥም የፍርድ ሂደት መኖሩ፤ አብዛኛዎቹ ጉዳዮች አሁንም ድረስ ውሳኔ አለማግኘታቸው፤
– የጉዳት ሰለባዎች እና የተጎጂዎች ማካካሻ የማግኘት መብትን ባስከበረ መልኩ የሚካሔድ የክስ ሥርዓት አለመሆኑ፣ ይህም በተጎጂዎችና በህብረተሰቡ የፍትህ መጓደል ስሜት ከመፍጠሩም ባሻገር ፤ለእርቅ አስተዋፅኦ አድርጓል ለማለት የማያስችል ሂደት መሆኑ፤
– የዜጎችን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን አክብሮ በማስከበር፣ እንዲሁም ያለፉ ጥፋቶች እንዳይደገሙ በማድረግ ረገድ ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ የሚችሉ እንደ ፖሊስ፤ ዐቃቤ ሕግ፤ ፍርድ ቤቶች እና በሌሎች የፍትህና ዴሞክራሲ ተቋማት ላይ ከተወሰነ የአመራር ለውጥ በስተቀር – ይህ ነው የሚባል በማጣራት እና በልየታ ላይ የተመሰረተ የሽግግር ስልትን (vetting) የተገበረ ለውጥ አለመከናወኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
ምህረትን በሚመለከት፤
የምህረት አሰጣጥና አፈፃጸም ሥርዓት ወጥነት ስላልነበረው ይህን ለማስተካከል የምህረት አሰጣጥ እና አፈጻጸም ሥነሥርዓት አዋጅ ቁጥር 1089/2010 እንዲወጣ ተደርጓል፡፡ ይህን አዋጅ መሰረት አድርጎ በተለያዩ የወንጀል ድርጊቶች ውስጥ ለተሳተፉ ሰዎች ምህረት ለመስጠት የሚያስችል አዋጅ ቁጥር 1096/2010 ወጥቷል።
ዓላማውም በነበረው ፖለቲካዊ አለመረጋጋት ምክንያት በወንጀል የተሳተፉ ሰዎችን ምህረት በመስጠት ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን፣ ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር እና ይቅር መባባልን ለማበረታታት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ፣ በተለይም ፖለቲካዊ መብታቸውን ተግባራዊ ለማድረግ በመንቀሳቀሳቸው የወንጀል ተጠያቂነት ስጋት ላደረባቸው ኢትዮጵያውያንና
ትውልደ-ኢትዮጵያውያን ምህረት በመስጠት ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ሁኔታዎችን ማመቻቸት በማስፈለጉ እንደሆነ በአዋጁ ላይ ተገልጿል። ይሁንና ይህ ሂደት ከሽግግር ፍትህ ሂደት ዘዴዎች እና አላባዎች አንፃር የሚከተሉት ጉድለቶች ነበሩት፡፡
– የምህረት አሰጣጥ ሂደቱ ወንጀል ፈፃሚ ተብለው በተጠረጠሩ ሰዎች ላይ በ6 ወር ጊዜ ውስጥ ጥያቄ እንዲያቀርቡ ከመጠየቅ ውጪ ምንም አይነት ቅድመ- ሁኔታ ያላስቀመጠ መሆኑ፣ ይህም በሽግግር ፍትህ ሂደት የማይመከረውን አይነት ጠቅላላ ምህረት (blanket amnesty) የሰጠ መሆኑ፤
– የምህረት ሂደቱ ተጎጂዎችን ያላሳተፈ መሆኑ፣ በውስጡም ተጎጂዎችን የመካስ እና ይቅርታ የመጠየቅ ሥርዓቶች ያልተካተቱበት መሆኑ፤
– ሰላምና መረጋጋት ከማምጣት አንጻር ከታየ በአዋጁ ተጠቃሚ ሆነው ከእስር የተለቀቁ ሰዎች ባለፉት አራት ዓመታት በተከሰቱ ግጭቶች ውስጥ ተመልሰው መሳተፋቸው እና በቁጥጥር ስር መዋላቸው ሲታይ ከመፀፀት ጋር በተያያዘ የታለመውን ግብ ያላሳካ መሆኑ፤
– በምህረት ተጠቃሚ መሆን የሚገባቸው ሰዎች በፌዴራል እና በክልል መዋቅሮች በተዘጋጁ ቢሮዎች በመቅረብ እና በማመልከት የምህረት ምስክር ወረቀት የሚወስዱበት ሥርዓት የተዘረጋ ቢሆንም ፣አፈፃፀሙ ላይ ጠንከር ያለ ክትትል ባለመደረጉ – የምህረት አሰጣጥ እና አፈፃፀም ሥርዓቱ በአግባቡ አለመከናወኑ፤የምስክር ወረቀት ያልያዙ ሰዎችም በማናለብኝነት ወደ ማህበረሰቡ መቀላቀላቸው፣ ይህም የመንግሥትን ሕግ የማስከበር ብቃት ጥያቄ ውስጥ ያስገባው መሆኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
ተቋማዊ አደረጃጀትን በተመለከተ
ለሀገራችን የመጀመሪያ የሆነው የእርቀ-ሰላም ኮሚሽን በአዋጅ ቁጥር 1102/2011 ተቋቁሞ የነበረ ሲሆን፤ ኮሚሽኑም በኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት እና በተደጋጋሚ የተፈጸሙ ጉልህ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን፣ በደሎችን፣ ቁርሾዎችን እና ዝንፈቶችን በበቂ ደረጃ ለይቶና አጣርቶ እውቅና በመስጠት በእውነት፣ እርቅ እና ፍትህ ላይ የተመሰረተ ዘላቂ ሰላም እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለመገንባት አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ሥልጣን እና ሃላፊነት ተሰጥቶታል።
ይሁንና ተቋሙ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ የዝግጅት ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቶ ዋና ተግባሩን መፈፀም ሳይጀምር እና ተጨባጭ ውጤት ሳያስገኝ የተሰጠው የሶስት ዓመት የስራ ዘመን የካቲት 2014 ዓ.ም በማብቃቱ እንዲፈርስ ተደርጓል። ኮሚሽኑ ከሽግግር ፍትህ አንፃር የተጣለበትን ዓላማ ማሳካት ላለመቻሉ የሚከተሉትን ምክንያቶች በማሳያነት መጥቀስ ይቻላል፡፡
– የኮሚሽኑ የምስረታ ሂደት ትርጉም ያለው እና ሀገር- አቀፍ የሕዝብ ምክክር ያልተደረገበት መሆኑ፣ በረቂቁ ላይ ከሚመለከታቸው አካላትና ባለሙያዎች ጋር ምክክር አለመደረጉና ግብዓት አለመወሰዱ፣
– ለኮሚሽኑ የተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት ግልፅነት የጎደለውና ተግባራዊ ለማድረግ አስቸጋሪ መሆኑ፣ ተግባርና ኃላፊነቱ ከሌሎች የሽግግር ፍትህ ሂደቶች ጋር የነበረው መስተጋብር እና የመመጋገብ ግንኙነት በግልፅ አለመቀመጡ፣ ኮሚሽኑ ይቅርታ እና ምህረት እንዲሰጥ ሥልጣን ያልተሰጠው መሆኑ፤
– የኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች ሲመረጡ እና ሲሾሙ ቀጥተኛ የሕዝብ ጥቆማ፣ ውይይት እና ተሳትፎ ያልነበረ መሆኑ፤ ይህም በኮሚሽኑ ቅቡልነት ላይ አሉታዊ አስተዋጽኦ ማድረጉ፤
– በፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ የነበሩ እንዲሁም ገለልተኝነታቸው ጥያቄ ውስጥ የሚገባ – በዳይ ወይም ተበዳይ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ ግለሰቦች ኮሚሽነር ሆነው መሾማቸው፤
– ለዚህ ከፍተኛ ሃላፊነት የሚሰየሙ ኮሚሽነሮች የሙሉ ሰአት ሰራተኞች አለመሆናቸው፣ ቁጥራቸውም ከተለመደው እጅግ የበዛ (41 የሚጠጋ) መሆኑ፣
– ኮሚሽኑ የሚያጣራቸው ያለፉ ጉልህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ከየትኛው ጊዜ እንደሚጀመር አለመቀመጡ፣
– ተቋሙ ከሚችለው በላይ ሃላፊነት የተሰጠው መሆኑ (ለምሳሌ አሁናዊ ግጭት መፍታት ላይ የሚሰሩ እና እንዲሰሩ ሃላፊነት የተሰጣቸው መንግሥታዊ ተቋማት እያሉ ፣ይህንን ተግባር ጊዜያዊ ለሆነው የእርቀ-ሰላም ኮሚሽን ተጨማሪ ተግባር እንዲሆን መደረጉ፣ ሀገራዊ ምክክር የማድረግ ተጨማሪ ተግባር የተሰጠው መሆኑ፣
– እንደ እርቀ-ሰላም ያሉ ኮሚሽኖች ግጭት መፍታት እና ሀገራዊ ምክክርን ማካሄድ ዋና ተግባራቸው እንዲያደርጉ በማይመከርበት ሁኔታ ይህ መፈፀሙ።
በአጠቃላይ ሀገራችን በነበሩት የሽግግር አጋጣሚዎች- የሽግግር ፍትህ ሂደት አላባዎችን ለማሳካትም ሆነ ፍትህን ለማረጋገጥ ውስን ሙከራዎች እንደነበሩና በዚህም የተገኙ ልምዶችና ውጤቶች እንዳሉ መመልከት ይቻላል። ይሁንና ከ2010 ዓ.ም በኋላ የተከናወኑትን ጨምሮ በኢትዮጵያ የተደረጉ የሽግግር ፍትህ ሙከራዎች ያልተሟሉ እና በቂ ባልሆኑ ሂደቶች የተተገበሩ እንደነበሩ ተስተውሏል።
በተሟላ መልኩ – የሽግግር ፍትህ ሂደት አላባዎችን እና ዘዴዎችን አካትተው፣ በተቀናጀ ሁኔታ ባለመተግበራቸውም – ስኬታማ መሆን አልቻሉም፡፡
በመሆኑም ካለፈው አስከፊ ሁኔታ በመማር ወደ ፊት ለመራመድ – የሽግግር ፍትህ ሂደቶች የሚፈጥሯቸውን አጋጣሚዎች እንዳንጠቀም ምክንያት ሆነዋል። ይህም በራሱ እስካሁን ድረስ ለቀጠለው ግጭት፣ የእርስ በእርስ ጦርነት እና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች መንስኤ የሆኑ በርካታ ጉዳዮች ሳይፈቱ እንዲቀጥሉ አስተዋፅኦ አድርጓል።
በኢትዮጵያ የሽግግር ፍትህ አስፈላጊነት
ከላይ ለማሳየት እንደተሞከረው በ2010 ዓ.ም የመጣውን ለውጥ ጨምሮ – በኢትዮጵያ የተሞከሩት የሽግግር ፍትህ አላባዎች የታለመላቸውን ዓላማ ማሳካት አልቻሉም፡፡ ስለሆነም በተሟላ እና በተቀናጀ መልኩ የሚዘረጋ፣ አሳታፊ የሆነ፣ ተጎጂዎችን ማእከል ያደረገ፣ የዓለም -አቀፍ የሰብአዊ መብት መርሆችንና ድንጋጌዎችን ያከበረ፣ በሌሎች ሀገራት እና በሀገራችን ከነበሩ ልምዶች ትምህርት የሚወስድ፣ የሀገራችንን ፖለቲካዊ እና ማህበራዊ አውድ ግንዛቤ ውስጥ የሚያስገባ የሽግግር ፍትህ ሂደት በመቀመር እና በግልፅ የፖሊሲ ማዕቀፍ እንዲመራ በማስቻል ተግባራዊ ማድረግ እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ለዚህም የሚከተሉትን ምክንያቶች በማሳያነት ማንሳት ይቻላል፡-
ሀ) የሀገራዊ አውዱ ሁኔታ የተሟላ የሽግግር ፍትህ ሥርዓት ሂደትን መተግበር አስፈላጊ እንደሆነ የሚያመላክት መሆኑ፤
በኢትዮጵያ ጉልህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ስልታዊና መጠነ-ሰፊ በሆነ ሁኔታ ሲፈጸሙ የነበረ ስለመሆኑ በርካታ ሪፖርቶች ያመለክታሉ፡፡ ከ 2010 ዓ.ም ጀምሮ በርካታ የፍትህ ማሻሻያ ስራዎች ቢሰሩም የሰብአዊ መብት ጥሰቶች፣ አለመረጋጋት፣ ግጭቶች እና የእርስ- በርስ ጦርነት በመቀጠሉ አሁንም ዜጎች ለሞት፣ ለስደትና ለንብረት ውድመት እየተጋለጡ ይገኛሉ።
ከዚህ የጥፋት አዙሪት እንዳንወጣ ካደረጉ ምክንያቶች መካከል – በሀገራችን የነበሩ የተደራረቡ በደሎች፣ የመብት ጥሰቶች፣ የተዛነፉ የታሪክ አረዳዶች፣ ለእነዚህ ጥሰቶች የተሰጡ ምላሾች ምሉዕ አለመሆን፣ በዜጎች ላይ ለተፈፀሙ ጥሰቶች ፍትህ አለማግኘት፣ ተጎጂዎች አለመካሳቸው፣ እና ሀገራዊ እርቅ አለመከናወኑ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
የአጥፊዎች እና የተጎጂዎች ብዛት፣ የበደሎች መደራረብ፣ እና የጥፋቶች ማህበረሰባዊ ቅርፅ መያዝ ሕዝቡ ለፍትህ ተቋማት ካለው ያነሰ ቅቡልነት ጋር ተዳምሮ
– በመደበኛው የፍትህ ሥርዓት እና አካሄድ ለሁኔታዎች ፍትህ መስጠትም ሆነ ይቅርታና እርቅ ማከናወን እንዳይቻል አድርጎታል፡፡
ስለሆነም የሀገሪቱን አሁናዊ ሁኔታ ግንዛቤ ውስጥ ያስገባ፣ ያለፈውን በአግባቡ የሚያስተናግድ፣ ለነገም መሰረት ለመጣል የሚያስችል፣ በዓለም-አቀፍ እና ሀገራዊ ልምዶች የተቀመረ፣ እንዲሁም በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የተለያዩ አጀንዳዎችን ይዘውና ነፍጥ አንግበው የሚታገሉ ቡድኖችን ትጥቅ አስፈትቶ ከማህበረሰቡ ጋር እንዲቀላቀሉ የሚያደርግ – የተሟላ የሽግግር ፍትህ ሂደት መተግበር የግድ ይላል። ይህ አይነቱ አካሄድ ሀገሪቱ ካሉባት ውስብስብ ችግሮች አዙሪት እንድትወጣ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደርጋል፡፡
ለ) የተሳካ የሽግግር ፍትህ ሂደት ለሀገረ-መንግሥቱ ግንባታ እና ቀጣይነት የሚኖረው ሚና ከፍ ያለ መሆኑ፣ በሀገራችን ከነበረው የጥፋት አዙሪት ለመውጣት እና ለተፈጠሩ ጥሰቶች አግባብ ያለው ምላሽ ለመስጠት በእውነት፣ በፍትህ፣ በሰላም እና በእርቅ ላይ በመመስረት ማህበራዊ ግንኙነቶችን ማደስ እጅግ አስፈላጊ ነው። በታሪክ ኢትዮጵያ እውነተኛ የእርቅ ሂደትን አድርጋ የምታውቅበት ወቅት ወይም አጋጣሚ የለም፡፡
ይልቁንም በአንዳንድ ዘመናት ሥልጣን ላይ የነበሩ መንግሥታት የያዙት አቋም “የተጣላ የለም፤ እርቅ አያስፈልገንም” የሚል ይዘት የነበረው እንደሆነ ይታወቃል። በዚህም ምክንያት – በሀገሪቱ በተለያዩ ጊዜያት የተፈጸሙ ጉልህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እና ቁርሾዎች አግባብነት ባለው መልኩ ሳይፈቱ እየተንከባለሉ እዚህ ዘመን ላይ ደርሰዋል፡፡
ስለሆነም ያለፉ በደሎችን አንስቶ መወያየት ፈታኝ ቢሆንም -ይቅር መባባልና እርቅ እንዲኖር ማድረግ ለሀገረመንግሥቱ ግንባታ መሰረታዊ ጉዳይ ነው። በሀገሪቱ የነበሩና የቀጠሉ ውስብስብ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ ካልተበጀላቸው ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነትን የሚያሳዩ ተፃራሪ ትረካዎች ሕብረተሰቡን በተለያየ መንገድ ማቁሰላቸውን እንዲቀጥሉ ያደርጋል። በመሆኑም ሀገሪቱ የተከፋፈለውን ሕዝብ ለማቀራረብ፣ የሻከረውን ግንኙነት ለመጠገን፣ ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እና እርቅ ለመፍጠር የሽግግር ፍትህ ዘዴዎችን መጠቀም እንደ አማራጭ መውሰድ ይኖርባታል፡፡ በዚህ ሂደት ላለፈው ቁስል እውቅና ለመስጠት፣ የሰውን ክብር ለመመለስ፣ ለጋራ ዳግም ውህደት እና ለሀገር ግንባታ የሽግግር ፍትህ የሚኖረው ሚና እጅግ ወሳኝ ነው፡፡
ሐ) የተሳካ የሽግግር ፍትህ ሂደት ሳይተገበር የዴሞክራሲ ሽግግርም ሆነ ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ የማይቻል መሆኑ፡፡
በተለያዩ ሀገሮች እንደታየው ያለፉ በደሎችን እና ጉልህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በአግባቡ ሳይፈቱ፣ ሙሉ እውነትን ሳያወጡ፣ ተጠያቂነትን ሳያሰፍኑ፣ እና እውቅና ሳይሰጡ በእርቅ፣ በሰላም እና በፍትህ ላይ የተመሰረተ የተሳካ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ማድረግ አዳጋች ነው።
በዚህም ምክንያት በሀገራችን በተለያዩ ጊዜያት የተፈጸሙ ጉልህ የመብት ጥሰቶች እና ቁርሾዎች አግባብነት ባለው መልኩ ሳይፈቱ ሲንከባለሉ የመጡ እንደመሆኑ መጠን በደሎቹ እንዲሽሩ፣ ቁርሾዎች እንዲጠገኑ፣ ወደ ዴሞክራሲ የሚደረገው ሽግግር እንዲሳካ፣ እንዲሁም ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ እንዲቻል – የተሟላ የሽግግር ፍትህ ሂደት መተግበር ጠቃሚ ብቻ ሳይሆን እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡
መ) የሽግግር ፍትህ ሥርዓት መተግበር ለሰብአዊ መብት መከበር እና ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ የሚኖረው አስተዋጽኦ የማይተካ መሆኑ፤
በሀገራችን ሰፊ የሰብአዊ መብት ጥሰት የተፈፀመ ቢሆንም- ሁሉንም አጥፊዎች እንደየጥፋታቸው ያለምንም ወጣ ገባነት ተጠያቂ የሚያደርግ ሥርዓት አለመኖሩ ጥሰቶቹ ተደጋግመው ለመከሰታቸው አንዱ ምክንያት ሆኗል፡፡ እነዚህ ጥሰቶች በአብዛኛው የተፈፀሙት ምንም አይነት የፖለቲካ ተሳትፎ በሌላቸው፣ ስለነገሩም ምንም ግንዛቤ ባልያዙ ኢትዮጵያውያን ላይ ነው። ድርጊቶቹ እንዳይፈፀሙ የመቆጣጠር ወይም የመከላከል ኃላፊነት ያለባቸው የመንግሥት ሃላፊዎች እና የማህበረሰብ ልሂቃኖችም ነገሮች እንዲባባሱ ጉልህ አስተዋፅኦ ሲያደርጉ ታይተዋል፡፡
እነዚህ ድርጊቶች ተደጋግመው ስለሚፈፀሙ እና ከተፈፀሙ በኋላም ምርመራው ይሁን የክስ ሂደቱ ተጎጂዎችን ያላማከለ እና በህብረተሰቡም እምነት የተጣለበት ባለመሆኑ – በሂደት ሕዝቡ በፍትህ ሥርዓቱ ላይ ያለው እምነት አናሳ እንዲሆን አድርጎታል፡፡
ስለሆነም ሁሉን-አቀፍ የሽግግር ፍትህ ሥርዓትን ተግባራዊ ማድረግ – ተቀባይነት ያለው የክስ ሂደትን እንዲኖር፣ ለሰብአዊ መብት ጥሰቶች ተገቢ ትኩረት እንዲሰጥ፣ የተጠያቂነት ሥርዓት እንዲጠናከር፣ ተጎጂዎችን ማእከል ያደረገ የይቅርታ፣ እርቅ እና ማካካሻ ሥርዓት እንዲኖር በማድረግ – ለሰብአዊ መብቶች ባህል መዳበር እና ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ መሰረት ይጥላል።
ምንጭ /ኢትዮጵያ የሽግግር ፍትህ የፖሊሲ አቅጣጫ አማራጮች በሚል ጥር 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከባለድርሻ አካላት ግብዓት ለመሰብሰብ በተዘጋጀ መድረክ ለውይይት ከቀረበ ጥናታዊ ጽሁፍ የተወሰደ /
አዲስ ዘመን መጋቢት 22 ቀን 2015 ኣ.ም