አገራችን ኢትዮጵያ ከሶስት ሺህ ዘመናት ዘለግ ያለ የስልጣኔ ታሪክ ባለቤት በአገረ መንግስት ግንባታና ሉዓላዊነትን ጠብቆ በመኖርም ጥቂት ከሚባሉ አገራት ቀዳሚዋ ነች። በአንድነት፣ በቀደምት ስልጣኔና ለጠላት እጅ ባለመስጠት ብቸኛ ምስራቅ አፍሪካዊት የጥቁር ሕዝቦች ኩራት መሆኗም በልጆቿ ብቻ ሳይሆን ከሌላኛው የዓለም ክፍል በመጡ የውጭ አገር አሳሾችና የታሪክ ፀሐፊያን የተመሰከረ ጥሬ ሃቅ ነው።
ይህ መልካም ታሪካችን ሳይበረዝና ሳይከለስ ታሪክ ይመዝግበው እንጂ በሌላኛው ጎን ግን መልካም ጎናችንን ለማጠልሸት የሚገዳደሩ፣ ጥንካሬያችንን የሚፈትኑ የቀደመ ኃያልነታችን ላይ ጥቁር ጥላ የጋረዱ ክፍተቶች አሉብን። ከእነዚህ ጉዳዮች መካከል በዘመናት ጊዜ ውስጥ የሚከሰት ድርቅና ረሃብ አንዱ ነው።
በኢትዮጵያም ሆነ በዓለም ላይ የድርቅ መከሰት ተፈጥሯዊና የሚጠበቅ ቢሆንም ፤ በተፈጥሮም ሆነ በሰው ሰራሽ ችግር የሚከሰትን ድርቅ መቋቋም የሚችል ጠንካራ ኢኮኖሚ መገንባት ግን ወሳኝ ጉዳይ ነው። ይህ ደግሞ እንደኛ ባሉ ሀገራት የግብርናውን ዘርፍ ከማዘመን ጀምሮ ሀገራዊ የሰው ኃይልን እና የተፈጥሮ ሀብትን ውጤታማ በሆነ መልኩ አቀናጅቶ መጓዝን የሚጠይቅ ነው።
ጠንካራ የስራ ባህል ማዳበር፣ ዜጎችን ለአንድ አላማ በማስተባበር አፋጣኝ ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም መፍጠር ድርቅንና ከድርቅ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ችግሮች ለዘለቄታው በመቋቋም ሊያስከትል የሚችለውን ሰብዓዊ ሆነ ምጣኔ ሀብታዊ ጥፋት መቋቋም ይቻላል። ይህን ማድረግ ካልተቻለ ድርቅ ወደ ከፋ ረሃብ ተሸጋግሮ በሰው፣ በቤት በዱር እንስሳት ላይ ሊያስከትል የሚችለው እልቂት የከፋ ነው። እንደ ሀገርም በየወቅቱ መሰል ጥቁር ጠባሳዎችን ያስተናገድን እንደመሆናችን ለክስተቱ አዲስ አይደለንም።
ዋናው አሳሳቢው ጉዳይ ግን ተደጋግሞ የሚከሰትን ድርቅ በሕዝባችን ላይ የከፋ ጉዳት ሳያስከትል እንዴት መቋቋም እንችላለን የሚለውን ጥያቄ እስካሁን ድረስ መመለስ አለመቻላችን ነው። በዚህ ምክንያት በየጊዜው በርካታ ሚሊዮን ዜጎች የሚሰሩ እጆች ይዘው የተፈጥሮን ቁጣ መቋቋም አቅቷቸው እጃቸውን ለምፅዋት ሲዘረጉ እናያለን።
አሁንም ድረስ ይነስ ይብዛ ሰፋፊ መሬትና ጉልበት ይዘው ከሰማይ የሚወርድ ዝናብና ከምእራባውያን የሚዘረጋ ምፅዋት የሚጠብቁ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ቁጥራቸው ጥቂት የሚባል አይደለም።
ተፈጥሮ ስትጨክንብን፣ የሰማይ ማማዎች ሲነጥፉ ወትሮውንም ለድርቅ ተጋላጭ የሆኑ አካባቢዎች ለእርሻ ተግባር ሳይሆን ለጉሮሯቸው ማርጠቢያ ጠብታ ውሃ የማጣታቸው እውነታ እንግዳ ክስተት አይደለም። በዚህም የሚያጋጥሙ ችግሮች መልካቸው ብዙ ነው። የሚበላ እና የሚጠጣ ማጣት፤ ነገዎች ላይ ተስፋ መቁረጥና በሌሎች ምጽዋት ዛሬን መግፋት ከብዙ ጥቂቶቹ ናቸው።
ከሰሞኑ በሀገራችን በኦሮሚያ በደቡብና በሶማሌ ክልሎች ያጋጠመውም ይሄው ነው። ችግሩ ተከታታይ የዝናብ ወቅቶች ዝናብ ባለመስጠታቸው የተከሰተ ቢሆንም፤ ችግሩ ከጅምሩ ትኩረት ተሰጥቶት መፍትሄ እየተቀመጠለት ባለመምጣቱ ዛሬ አስቸኳይ መፍትሄ በማ ፈላለግ ተጠምደናል።
መንግስት የሀገርን ሉዓላዊነትና ጥቅም፣ ሰላምና ፀጥታ ከማስከበር ባሻገር የምጣኔ ሀብት ምሰሶ የሆነውን የግብርናውን ዘርፍ ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ ማሳደግ የሚያስችሉ ፖሊሲዎችንና፣ ስትራቴጂ ነድፎ መንቀሳቀስ እንደሚኖርበት ይታመናል። በተለይ 85 በመቶ የሚሆኑት ዜጎች ኑሯቸው በግብርና ላይ በተመሰረተበት ሀገር ይህ እውነታ ከፍ ያለ ትርጉም ያለው ነው።
በሀገሪቱ ጠንካራ ውጤታማ የሆነ ዘመኑን የዋጀ የግብርና ስርዓት መዘርጋት እና ለተፈፃሚነቱ መስራት ከመንግስት የሚጠበቅ ዋና ጉዳይ ነው። ከዚህ አንጻር በግልፅ እየተሰሩ ያሉ ግብርናውን የማዘመን፣ የአስተራረስ ዘዴን የመቀየርና ምርትን ማሳደግን የተመለከቱ ተግባራት የሚበረታቱና ተስፋ ሰጭ ናቸው።
መንግስት የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን በተፈጥሮና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የሚከሰት ድርቅ የከፋ አደጋ ሳያስከትል አስቀድሞ ለመከላከል የሚያደርገው ጥረት ብዙ ተግዳሮቶች እያጋጠሙት እንደሆነ አይካድም። ከነዚህም ውስጥ የመንግስት ስትራቴጂክ ፖሊሲዎች በተቀናጀና በተጠናቀረ መልኩ የማስፈፀም የአመራር ክፍተት፤ ደካማ የስራ ባህል፣ ለዘመናት ሲንከባለል በመጣው ኋላቀር የአስተራረስ ዘዴ መታመን፤ ለልምድ እንጂ ለእውቀት ቅድሚያ ያለመስጠት በዋነኝነት ተጠቃሽ ናቸው።
የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ከዘመናት በፊትም ይሆን በቅርብ ጊዜ ውስጥ ድርቅን ተከትሎ በሚከሰት ርሃብ፣ የዜጎች ሞት፣ እንግልትና ስደት ዋንኛ ምክንያት የዝናብ ወቅትን ብቻ መሰረት ያደረገው የአስተራረስ (ግብርና) ዘዴ እንደሆነ ያምናል።
በልዩ ልዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ከክረምት ወቅት ውጭ በመስኖ ግብርና አመርቂ ውጤቶች የምንመለከት ቢሆንም በጥቅሉ ግን 85 በመቶ እንደሆነ የሚገመተውን አርሶ አደር በዚህ ስርዓት ውስጥ በወጥነት ማስቀጠል አልተቻለም። ይህ ደግሞ ከእጅ ወደ አፍ ከሆነው ገቢ ባሻገር በየጊዜው ዜጎችን ለከፋ ድርቅና ረሃብ እንዲጋለጡ አድርጓል።
ከድርቅ ጋር በተያያዘ የሚፈጠሩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ለድርቅ የማይበገር የግብርና ስርዓትን መገንባት ላይ ማተኮር ያስፈልጋል። ይህ ማለት የግብርና ዘርፉ የተትረፈረፈ ምርት ባለቤት የሚሆንበትን አቅም በጠንካራ የስራ ባህልና በዘመናዊ ቴክኖሎጂ መፍጠር ይገባል። ለዚህ ደግሞ መነሻ ይሆን ዘንድ የሚከተሉትን ምክረ ሃሳቦች ለማስቀመጥ እሞክራለሁ።
ዝናብን ከመጠበቅ መላቀቅ
ከላይ በዝርዝር ለማንሳት እንደሞከርነው የኢትዮጵያ የግብርና ስርዓት በዝናብ ውሃ ላይ የተመሰረተ /ጥገኝ የሆነ/ ነው። አሃዙ ለመለየት ተጨማሪ ጥናት ቢፈልግም 90 በመቶው አርሶ አደር ከሰማይ በሚጠብቀው ዝናብ ላይ ተመስርቶ ሞፈሩን ከመሬቱ ጋር የሚያገናኝ ነው። ይህ ደግሞ ዝናብ ሲያጥር እና ድርቅ ሲከሰት እጆቹን አጣጥፎ እንዲቀመጥ ያደርገዋል። ከራሱ ፍላጎት ያለፈ ምርት ማምረት የሚያስችል አስቻይ ሁኔታ ባለመኖሩም የምግብ ዋስትናውን አረጋግጦ ነገን በተስፋ የሚጠብቅበት እድል የለውም።
ችግሩ እየከፋ ሲሄድ በሀገር ላይ የከፋ ምጣኔ ሀብታዊ ችግር ሊያስከትል የሚችል ሲሆን ፤ ቀድሞውኑ ከእጅ ወደ አፍ የሆነውን የአርሶ አደር ሕይወት ወደ ከፋ የርሃብ አደጋ በማሸጋገር ከፍ ላለ ሰብዓዊና ምጣኔ ሀብታዊ አደጋ ማጋለጡ የማይቀር ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ድርቅ በተደጋጋሚ የሚያጠቃቸው ሰቆጣና ዋግ፣ ቦረና እንዲሁም የደቡብና የምስራቁ ኢትዮጵያ አካባቢዎች የምናስተውለው ችግር መነሻው ይሄው ነው። ከችግሩ ለዘለቄታው ለመላቀቅ ተፈጥሮ ጊዜ ጠብቃ ከምትለግሰን የዝናብ ውሃ ግብርናችንን ማለቀቅ ይኖርብናል።
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ ኢትዮጵያ በከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውሃ ሃብት የበለፀገች ነች። በ12 ተፋሰሶች ከ122 ሚሊዮን ኪዩቢክ በላይ የገፀ ምድርና እና ከ6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኪዩቢክ በላይ የከርሰ ምድር ውሃ ያላት ናት። ይህንን ሀብታችንን በመጠቀም አኳያ ሲታይ ያለው እውነታ ከ3 በመቶ የማይበልጥ ነው።
እንደ ሀገር ያለንን የውሀ ሀብት ወደ ልማት ብንቀይረው /በግብርናው ዘርፍ/ በድርቅ ምክንያት ከሚፈጠር የምግብ እህል እጥረት መገላገል የሚያስችለንን አቅም መገንባት እንችላለን። የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈም ለሀገሪቱ ምጣኔ ሀብት መነቃቃት ትልቅ አቅም መፍጠር እንደሚያስችለን አፍ ሞልቶ መናገር ይቻላል።
ለዚህ ደግሞ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ መንግስት ስንዴን በበጋ ወቅት በክላስተር በማምረት፣ የመስኖ እርሻን በማስፋፋት እንዲሁም የከተማ ግብርናን ጨምሮ የአገሪቱን አጠቃላይ የግብርና ዘዴ በቴክኖሎጂና መካናይዜሽን ለማዘመን የሚያደረገው ጥረት እና እየተመዘገበ ያለው አበረታች ውጤት ለዚህ ተጨባጭ ማሳያ ነው።
ይህም ሆኖ ግን ኋላቀር የሆነውን የሀገሪቱን ግብርና ዘርፍ ለማዘመንና ወደሚፈለገው ደረጃ ለማድረስ ሳይሰለቹና ሳይታክቱ መስራት፤ ለዚህ የሚሆን የአመራር ቁርጠኝነትን መፍጠር ያስፈልጋል። የአርሶ አደር ለውጥ የሚያመጡ አዳዲስ አሰራሮችን ከባህሉና ከኢትዮጵያዊ ማንነቱ ጋር ለማስታረቅ እራሱን በስነ ልቦና ማዘጋጀት ይጠበቅበታል።
የግብርናውን ዘርፍ በቴክኖሎጂ ማዘመን
በ21ኛው ክፍለ ዘመን የግብርናውን ዘርፍ በበላይነት እየመራ ያለው ቴክኖሎጂ ነው። ዘመናዊ የአስተራረስ ዘዴ በሳይንሳዊ መንገድ ተቀምሮ ጥቂት መሬት እልፍ ምርት ይሰጣል። አንድ አርሶ አደር አንድ ቀበሌን የሚመግብበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። በአደጉት አገራት 3 ወይም 2 በመቶ የማይበልጠው አርሶ አደር ቀሪውን ዜጋ ይመግባል።
ለዚህ ታምራዊ ለሚመስል እመርታ ዋንኛ ተጠቃሹ ዓለም አሁን ላይ የደረሰችበት ቴክኖሎጂ ነው። ቴክኖሎጂው የዝናብ ወቅትን ከመጠበቅ ይልቅ የተገኘውን የውሃ አማራጭ ሁሉ መጠቀም ዓመቱን ሙሉ ምርት የሚታፈስበትን እድል ፈጥሯል።
ኢትዮጵያም የዚህ እውነታ አካል መሆን አለባት። በተለይ እያደገ ያለውን ሕዝብ ቁጥር ያለስጋት ለመመገብ ያላት ትልቁ አማራጭ ይሄው ነው። ይህንን እውን ለማድረግ የሚደረጉ ጥረቶች ቢኖርም ከቀሪው ዓለም ጋር ሲነፃፀር ግን እያስገኘልን ያለው ውጤት የሚፈለገውን ያህል አይደለም።
በዘርፉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ሆነ ዘመናዊ የግብርና ስርአትን የሚደግፍ እና የሚያበረታታ ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ቢኖረንም ወደ መሬት በማውረድ ሂደት ላይ ግን አሁንም ብዙ ችግሮች /ተግዳሮቶች/ አሉብን። ችግሮቹን ለመፍታት ከችግሮች ጋር መላመድ ሳይሆን በመፍትሄዎች ላይ ጠንክሮ መስራት ይጠበቅብናል።
እንደ ሀገር በዘርፉ ካለብን ችግር ለመውጣት አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን የግዴታ መፍጠር ወይም ያልተለመዱ ሳይንሳዊ ዘዴዎችን መከተል አይጠበቅብንም። ዓለም አሁን የደረሰበትን ተሞክሮ ውጤታማ የሆኑ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ማላመድ ብቻ በቂ ነው። ለዚህም ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ባለሙያዎች፣ ምሁራን እና የፈጠራ ባለሙያዎች ለግብርና ዘርፉ መሻሻል ባላቸው አቅም መስራት ይጠበቅባቸዋል።
የአረንጓዴ አሻራን በስፋትና በጥራት ማስቀጠል
ሌላው ተገቢው ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው የአረንጓዴ አሻራን በስፋትና በጥራት ማስቀጠል ነው። ይህ ሀገራዊ ንቅናቄ የተመናመኑ ደኖችን መመለስና የደን ሽፋኑን መጨመር የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል የድርቅ ተጋላጭነትን ይቀንሳል።
በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎች እንደሚገልጹት፤ የደን ሽፋንን መጨመር የከርሰ ምድር ውሃን ለማብዛት፣ የአፈር መሸርሸርና ድርቅን ለመከላከል ያግዛል። ዛፍን መትከል ሆነ ደኖችን መንከባከብ ለግብርና ዘርፍ ከሚኖረው ጠቀሜታ አንጻር እውነታውን በአግባቡ ተገንዝቦ መንቀሳቀስ ተገቢ ነው።
በአጠቃላይ የግብርናውን ዘርፍ ውጤታማ ለማድረግ ከዝናብ ውሃ ጥገኝነት ከመላቀቅ ጀምሮ ዘርፉን በቴክኖሎጂ ማዘመን፤ ወሳኝ ነው። ይህን ለመድረግ ደግሞ ከሁሉም በላይ በዘርፉ የሰለጠኑ ምሁራን፤ መንግስት፤ ባለድርሻ አካላትና ከራሱ ከአርሶ አደሩ ብዙ ይጠበቃል።
እስከ ዛሬ በወረቀት ላይ አስፍረን ብዙ ስንልባቸው የቆየናቸውን እነዚህን እውነታዎች መሬት አውርደን መተግበር ከቻልን፤ ለግብርናው ዘርፍ ችግር ዘላቂ መፍትሄ ከመስጠታችን ባሻገር ከኋላቀርነት መርገምት እንደምንላቀቅ አንዳች እንኳን ጥርጣሬ ሊገባን አያሻም ለማለት እወዳለሁ። ሰላም!!
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን መጋቢት 15/2015